Thursday, March 29, 2012

ቅድሚያ ለሚበልጠው



           ጠባይንና ግብረገብነትን፣ ወንድማማችነትንና አብሮ መኖርን የሚያጠቃልል ኃይል ሥነ ምግባር ነው፡፡ ሰው አካባቢውን እንደመምሰሉ አብሮ ከሚውለውና አብሮ ከሚኖረው ጋር መመሳሱሉ አይቀሬ ነው፡፡ አበው “ከበቅሎ ጋር የዋለች ጊደር እርግጫ ተምራ ወደ ጋጧ ገባች” እንደሚሉት ክፉ ባልንጀራ መልካሙን አመል ያጠፋል፡፡ በውጪው ዓለም “የምታነበውን ንገረኝና ማንነትህን እነግርሃለው” እንደሚባለው እኛም ጋር “ጓደኛህን ንገረኝና ማን መሆንህን እነግርሃለው” ይባላል፡፡ በዚህም ሰዎች በእኛ ኑሮ ላይ ያላቸው ተጽእኖ ምን ያህል እንደሆነ መረዳት ያስችለናል፡፡ ከሰዎች ጋር ሊኖረን የሚችለውን ግንኙነት መመዘን ያለንንም መተባበር መፈተሽ የዘወትር ተግባራችን ሊሆን ያስፈልጋል፡፡ መልካም ጠባይ በውጭ ሰውነታችን ብቻ የምናሳየው ሳይሆን በውስጥ ሰውነታችን መለወጥም የሚታይ ነው፡፡ ተኩላ በግን “ምናለ ቤታችንን መጥታችሁ ብታዩልን?” ባላት ጊዜ በግ “ግብዣው መልካም ነው ዳሩ ግን ቤታችሁ ሆዳችሁ ውስጥ ሆነና እንዴት እንምጣ” በማለት እንዳሳፈረችው ለክፉ ባልንጀርነት እኛም ክፍተት መስጠት የለብንም፡፡

         ወላጆች ጥሩ ለብሰው፣  የላመ የጣመ ጎርሰው ስላላደጉ ልጆቻቸው ሲቆጩ እናያለን፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሔር ቃልና በሥነ ምግባር ስላላደጉ ልጆቻቸው ግድ የላቸውም፡፡ የተሻሉ የምንላቸውም በሌላው ልጅ ሥርዓት አልበኝነት፣ የተንጋደደ እድገት ይከፋሉ እንጂ በራሳቸው ልጅ አይቆጩም፡፡ በአገራችን ላይ የምናየው ስልጣኔን ትኩረት ያደረገው ጉዞ ከሰዎች ለውጥና ሥነ ምግባር ይልቅ ቁሳዊ ለሆኑ እንዲሁም ግንባታን መሰረት ያደረጉ እንቅስቃሴዎች ላይ የተደገፈ ነው፡፡ ነገር ግን ትውልድን ለማትረፍ ሥነ ምግባር ላይ መሰራት አለበት፡፡ እኛ ለፍተን ደክመን በሠራነው የተንጣለለ ቤት ውስጥ ባዶ (ኢ ግብረገባዊ) ሰው ቢገባበት ምን የሚሆን ይመስላችኋል? ባዶ ቤት ውስጥ በእግዚአብሔር የአሳብ  ሙላት ስር ያለ አንድ ሰው ቢገባ ደግሞ ቤቱን ምን ያህል በመልካም ይለውጠዋል? ሁለቱንም ለሕሊናችን ሚዛን እንተወው፡፡

         ሥነ ምግባር ከማስመሰል ያለፈ፣ ከግብዝነት የፀዳ ሲሆን ያምራል፡፡ የውጭ አቋማችን የውስጥ ሰብእናችንን የሚያብራራ በመሆኑ እውነትን መሰረት ያደረገ ሊሆን ያስፈልጋል፡፡ ዓለም በበኩሉ የራሱ ለውጥና ተሐድሶ አለው፡፡ ይህም የሰዎችን ጠባይና ባህሪ ሲለውጥ እናየዋለን፡፡ አንዳንዶቹን መንፈሳዊነትን ጠልተው ለሥጋ ኃይል ሲያንበረክካቸው፣ ሌሎቹን ደግሞ በክፉ አሳብ ተጠምደው እኔነታቸውን እንዲያከብሩ ይገዛቸዋል፡፡ ይህም ዓለም የሚሰጠው ለውጥ መለያ ጠባይ ነው፡፡ ጌታ ወደዚህ ዓለም የመጣው ሊገለገል ሳይሆን ሰዎችን ሊያገለግል ነው፡፡ (ማቴ. 20÷28) አገልግሎቱም ነፍሱን ለብዙዎች ቤዛ አድርጎ እስከመስጠት ይደርሳል፡፡ እኛም በነገር ሁሉ እርሱን ልንመስል የእርሱንም  ልንከተል ተጠርተናል፡፡

           አንድ የግሪክ ፈላስፋ ተማሪዎቹን “እኔን ምሰሉ ይህም ልጅ ወላጆቹን በመልክ፣  በቀለም፣  በቁመት መስሎ እንደሚወለደው አይደለም፡፡ ይህ ከዘርና ከደም የሚወረስ የተፈጥሮ ግዴታ በመሆኑ አያስደንቅም፡፡ እኔ ግን ያልኳችሁ ባገኛችሁት ትምህርት እንደ እኔ መምህር፣  አስተዳዳሪ፣  ሐኪም እንድትሆኑም ብቻ አይደለም፡፡ ይህንንም በጥናትና በጥረት ብዛት ማንም ሊያገኘው ይችላል፡፡ እኔን ምሰሉ ያልኳችሁ ግን በቃል፣  በሥራና በእምነት ነው፡፡ እግዚአብሔር ሰውን እንደ መልካችን እንደ ምሳሌያችን እንፍጠረው ያለው በአፍንጫችን፣ በአይናችን፣ በፀጉራችን እንድንመስለው ሳይሆን በእውቀት፣ በቅድስናና በጽድቅ እንድንተባበር፣  ከእምነት በሆነ ሥነ ምግባር እንድንገልጠውና እንድናገለግለው ነው” አላቸው፡፡ ይህ አገላለጽ በውስጡ ሰውነታችን አምላካችንን እንድንመስል ያብራራል፡፡ ስለዚህ ብዙው ኃጢአትም ሆነ በጎ ተግባር፣ ክፉም ይሁን ቅድስና ማንኛውም ክንዋኔ መነሻው የውስጥ ሕይወታችን ነው፡፡         

            በቀደመው አሳብ የውጭ ሕይወታችን የሚያንጸባርቀው የውስጥ ሕይወታችንን አቋም እንደሆነ ተነጋግረናል፡፡ ምንም እንኳን አንዳንድ ጊዜ ሰዎች እውነተኛ ውስጣዊ ጠባያቸውን አፍአዊ በሆነ ማስመሰል ለመሸፋፈን ቢሞክሩም እውነትና ንጋት እያደር . . . እንደሚባለው መሆኑ አይቀሬ ነው፡፡ ወደፊት “የክርስትናው ዓለም ጭንብሎች” በሚል በሰፊው ለማየት እንሞክራለን፡፡ በክርስትና ያለው ስነ ምግባራዊ ሕይወት እንደ ወርቅ የተፈተነ ማስመሰል የሌለበት ሊሆን ያስፈልጋል፡፡ ምክንያቱም ክርስቲያን ጽድቁ ከጸሐፎችና ከፈሪሳዊያን ጽድቅ ካልበለጠ በእግዚአብሔር መንግስት እድል ፈንታ የለውም፡፡  ስለዚህ የቃል ምስክርነት በኑሮ መገለጥና መደገፍ አለበት፡፡  ለሚታየው ሳይሆን ለማይታየው፣ ለውጪው ሳይሆን ለውስጡ፣ ለጊዜያዊው ሳይሆን ለዘላለማዊው፣ ለምድሩ ሳይሆን ለሰማያዊው፣ ለሥጋ ሳይሆን ለመንፈስ ማድላት ለሚበልጠው ማስቀደም ነው፡፡ ማስተዋል ይብዛላችሁ!!


Tuesday, March 27, 2012

ቤት ያለ አጥር (ካለፈው የቀጠለ)



1. የእግዚአብሔር ቃል፡- የምንሰማውን የምናጠልበት፣ የምንናገረውን የምንመርጥበት፣ የምንኖረውን የምናስተውልበት ኃይል የእግዚአብሔር ቃል ነው፡፡ ሕይወት ለዚህ ስትሰጥ ለነዋሪውም ለተመልካቹም የበዛ ውበት ናት፡፡ ጠላት የሚርቀው፣ ትግል የሚቀለው፣ ዕረፍታችንን ከሚዋጋ ተግዳሮት የምናመልጠው በዚህ የሕይወት ቃል ነው፡፡ ይህንን ቃል አልፎ፣ ተስፋውንም ረግጦ ወደ እኛ የሚሻገር ኃይል የለምና ከቃሉ ጋር ያለንን ሕብረት ማጠናከር አጥራችንን መጠበቅ ነው፡፡

        ቃሉ እርሱን ለማምለክ፣ ለክብሩ ለመገዛት፣ በፈቃዱም ምሪት ስር ለመኖር የሚያስችለን ኃይል ነው፡፡ ጠዋት ስንነሣ አንዲት የአምላክ ቃል ማንበብ ከብዶብን ቀኑን ሙሉ ጆሮ ጭው የሚያደርግ ነገር እየሰማን እንመረራለን፡፡ የቀኑን ክፋት፣ የሰውን ጥመት፣ የዓለምን እንቶ ፈንቶ የምንቋቋምበት ጉልበት ያለው ከእግዚአብሔር ቃል ጋር በማሳለፍ ነው፡፡ ሕያውና የሚሠራ፣ ሁለት አፍም ካለው ሰይፍ ይልቅ የተሳለ፣ ልብና ኩላሊትን የሚመረምር ይህ ቃል ሕይወት የተስተካከለች አልያም የተንጋደደች ለመሆኗ ወሳኝ ነገር ነውና ለመስማት ጥማትን ለመፈጸም ፈቃደኝነትን ማሳየት ይገባል፡፡ ተወዳጆች ሆይ ቃሉን የኑሮአችሁ መመሪያ፣ የእንቅስቃሴአችሁ ካርታ፣ የማነንነታችሁ መስተዋት አድርጉት እናም ውጤቱን በዘመናችሁ ተመልከቱ፡፡

2. ጸሎት፡- የሰናፍጭ ቅንጣት የምታህል እምነት ተራራን ፈቀቅ ታደርጋለች፡፡ ትንሽ ጸሎት ደግሞ የእግዚአብሔርን ክንድ ለማዳን ታስነሳለች፡፡ እኛ የእግዚአብሔር ቤት ከሆንን ማንኛውም ነገር ከቤቱ ጌታ አንፃር መከወን አለበት፡፡ ለእኛ ያለውን ፈቃዱን የምንረዳው ደግሞ በጸሎት ነው፡፡ ንግግርና ተግባር በጸሎት ካልታጠረ የጠላት አሰራር የሚከናወንበት ግዛት መሆኑ እርግጥ ነው፡፡

         ጥቂት ሳንጸልይ ቀርተን ብዙ የተጎዳንበት፣ ትንሽ ደቂቃ መንበርከክ ተስኖን በብዙ የተፈተንበት ጊዜ አጥር አልባ ለሆነው ኑሮአችን እማኝ ነው፡፡ ከቅርብም ከሩቅም፣ ከውስጥም ከውጭም የሚመጣውን መከራ ለመቋቋም መጸለይ አለብን፡፡ በሕይወታችሁ እግዚአብሔር ካስተማራችሁ እንደ ጸሎት ያለ የማያስደፍር አጥር የለም፡፡ ከእግዚአብሔር ጋር በጸሎት ስንነጋገር ከእኛ ሸክም ይሄዳል ከእግዚአብሔር ደግሞ ዕረፍት ይመጣል፡፡ ችግራችንን

3. ቅድስና፡- ላመንነው መለየት ለተለየንለት መኖር ቅድስና ይባላል፡፡ ይህም እምነትና የማመን ፍሬ ነው፡፡ በክርስቶስ ስናምን የምንኖርበት ግዛት በእግዚአብሔር መንግስት ስር ይሆናል፡፡ ግዛቱም የማይደፈር ብርቱ ነው፡፡ የመቀደሳችን ዓላማ ቅዱስ የሆነውን እግዚአብሔር በሕይወት ለመግለጽ እንደመሆኑ የኑሮ ቅድስና ሌላው የማያስደፍር አጥራችን ነው፡፡ በአንድ ቤት ውስጥ መልካም አባት መኖሩ ብቻ ቤቱን የተፈራ አያደርገውም፡፡ ምክንያቱም በአመለ ክፉ ልጅ ቤቱ ሊደፈር ይችላል፡፡

        መልካሙን እረኛ ወደ ሕይወታችን ወደ ኑሮአችን የሚመጣው ሁሉን ለውጦ ለክብሩ ሊያደርገው ነው፡፡ የለዋጩም ኃይል በተለወጠው ሰው የዕለት ተዕለት ኑሮ መገለጥ አለበት፡፡ ይህም የተቀደሰ የተለየ ሰብእናችንን ያሳያል፡፡ ቅድስና ለአንድ ክርስቲያን የማያስደፍር አጥር ነው፡፡ ሰዎችን በማስረዳት ብዛት ክብርን እንዲያሳዩን ማድረግ አንችልም፡፡ የቅዱሱ እግዚአብሔር ቅድስና በሰብእናችን መንጸባረቅ ሲጀምር ጠላት ፊታችን ደፍሮ ሊቆም፣ የሥጋና የደም ምክር ሊከናወን አይቻለውም፡፡ ይህ አጥር ከፈረሰ ግን ለሁሉም ኢላማ ስለምንመቻች በቀላሉ ለሽንፈት እንጋለጣለን፡፡ ቅድስና ለእግዚአብሔር፡፡ ማስተዋል ይብዛላችሁ!!


Friday, March 23, 2012

ቤት ያለ አጥር



            ኑሮ ከሚጠይቃቸው ነገሮች አንዱ ስርዓት ነው፡፡ አንድ ቤት ውስጥ ያሉ ዕቃዎች በስርዓትና በአግባብ አልተቀመጡም እንበል መኝታ ቤት ውስጥ የሳሎን ዕቃ፣ እልፍኝ ውስጥ ደግሞ የማዕድ ቤት ዕቃዎች ቢቀመጡ፣ መጸዳጃው የእንግዳ ማረፊያ እንዲሆን ቢደረግ ምን የሚሆን ይመስላችኋል? ስርዓት ለአንድ ቤት ሰላም እጅግ አስፈላጊ ነገር ነው፡፡ አጥርን ስናስብ ለአንድ ቤት ሕልውና ያለውን ትልቅ ድርሻ እናስተውላለን፡፡ አበው “አጥር የሌለውን ቤት ዶሮም ትደፍረዋለች” ይላሉ፡፡

                አስተውላችሁ ከሆነ አንዳንድ ቤቶችን ለማንኳኳት ፈራ ተባ የምንልበት፣ ከኃይላችን ቆጥበን በጥቂቱ የምናኳኳበት ጊዜ አለ፡፡ ይህም የሚሆነው በስተውስጥ ያለው ሰው ሰብእና እየታወሰን ነው፡፡ ፍቅሩ፣ ደግነቱ፣ አክብሮቱ፣ ትህትናው፣ ቅንነቱ፣ ይቅርታና ትዕግስቱ . . . . እነዚህ ሁሉ ልባችንን ከመግዛት አልፈው የእጃችንንም ይቆጣጠሩታል፡፡ በሌላ መልኩ ደግሞ እጅ ይበዛበታል ተብሎ በእግር የሚንኳኳ ቤትም አለ፡፡ ይህ ደግሞ የነዋሪው ሞልቶ የተረፈ ክፋት፣ ለባልንጀራዬ የማይል ስስት፣ አይንን በጨው ያጠበ ድፍረት እየታወሰን የምናደርገው ነው፡፡ ምንም እንኳን ሁለቱም ጠባያት በውስጥ ያለውን ሰው ማንነት የሚጠቁሙ ብቻ ናቸው ማለት ባንችልም በአብዛኛው ግን ከሚያንኳኳው ይልቅ የሚከፍተውን ሰው ሁኔታ ይገልፃሉ፡፡

                 እኛ ራሳችንን የምንደፍረውን ያህል ሌሎች ሰብእናችንን አይደፍሩትም፡፡ የሰዎች እኛን ማክበር የሚመጣው እኛ ለራሳችን ከሚኖረን ከፍተኛ አክብሮት ነው፡፡ ሕይወት ስጦታ እንደሆነች ካመንን ሰጭውን የምናከብረው ስጦታው ያለውን ዋጋ በሰጭው መጠን በመረዳትና በመንከባከብ ተገቢውን አክብሮት በመስጠትም ጭምር ነው፡፡ የእግዚአብሔር ቃል በመጠን መኖር እንዳለብን ይመክራል፡፡ (1ጴጥ. 1÷13) ከኃጢአት የምንርቅበት ማስተዋል በመጠን መኖራችን ነው፡፡ የኃጢአት አንዱ ትርጉም ትርፍ ነገርን መፈለግ የሚል ነው፡፡ ያልተመጠነ ኑሮ ይቅርና ያልተመጠነ ቅመም እንኳን ያለውን ጉዳት እናውቀዋለን፡፡ ንግግር ካልተመጠነ በአፍ መበደልን፣ ተግባር ካልተመጠነ በኑሮ ኪሳራን ማስከተሉ እሙን ነው፡፡ ያልተመጠነ ግንኙነት ለዝሙት፣ ያልተመጠነ ጨዋታ ለሀዘን፣  ያልተመጠነ ጥረት ለሞት ይዳርጋል፡፡ ሰው ለአኗኗሩ ለአረማመዱ አጥር ሊበጅለት ይገባል፡፡ ዛሬ በወጣትነታችን ላይ የሚስተዋለው ገደብ የለሽ ፍላጎት ነው፡፡ ያየሁት ሁሉ አይለፈኝ፣ ከሁሉ ካልቀመስኩ አይሆንም፣ ካልሞከርኩ አልማርም የዘመናችን ተግዳሮት ነው፡፡ የሚቆምበት ቦታ ከተራመድን፣ የሚሠራበት ቦታ ከተኛን፣ ዝም ማለት ባለብን ቦታ ከለፈለፍን ኑሮ ስርዓት አልበኝነት የሰፈነበት ትንሽ ዓለም ይሆናል፡፡ እኛ የሕያው እግዚአብሔር ቤት ነን፡፡ (1ቆሮ. 3÷9) ቤት ደግሞ የማያስደፍር አጥር ያስፈልገዋል፡፡

                  አስተውለን ከሆነ ወደ ቤታችን የመጣ ሰው ወንበር ስቦ ቢቀመጥ፣ ውኃ ቀድቶ ቢጠጣ፣ ሞቆት መስኮት ቢከፍት ማንም የሚገረም ደግሞም ቅር የሚለው የለም፡፡ ነገር ግን አልጋ ላይ ሄዶ ቢቀመጥ ይህ እንደ ነውር ነው፡፡ ይህንን ያደረገው ወንድ ቢሆን ምን አስቦ ነው፡፡ ሴት ብትሆን ደግሞ ምን አስባ ነው ያስብላል፡፡ ስለዚህ በቤታችን ካሉት ዕቃዎች እንደ አልጋ ክብርና መፈራት የሚቸረው የለም፡፡ ይህ የሆነው ደግሞ በእያንዳንዳችን ሕሊና ውስጥ ከተተከለው አጥር የተነሳ ነው፡፡ በልክ መኖር እኛ ወደ ክፋት እንዳንሄድ ብቻ ሳይሆን ክፉም ወደ እኛ እንዳይመጣ አጥር ነው፡፡  ኢየሱስ ክርስቶስ የሕይወት መሰረት፣ የማዕዘን ድንጋይና ራስ ነው፡፡ ቤትን ስናስብ እነዚህ ነገሮች ወሳኝ ናቸው፡፡ ያለ መሰረት መጽናት፣ ያለ ማዕዘን መቆም፣ ያለ ራስም ፍፃሜ አይታሰብም፡፡ በቀጣይ ለአንድ ክርስቲያን የማያስደፍሩ አጥሮች ምን ምንድናቸው የሚለውን ለማየት እንሞክራለን፡፡ ጥበብ ይብዛላችሁ!!

                                                                                  ይቀጥላል


Monday, March 19, 2012

እመጣለሁ ያለን ይመጣል


         በአንድ መንፈሳዊ የመፍትሔ ፍለጋ ውይይት ላይ  ሰፋ ያለ ርዕስ ተነስቶ ሁሉም አሳብ መስጠት ጀመረ፡፡ አንዳንዱ ጊዜያዊ ያለውን ሌላው ደግሞ ዘላቂ ያለውን ብቻ ሁሉም እንደ አስተሳሰቡ ደረጃ መፍትሔ ይሆናል ያለውን ሰነዘረ፡፡ ከታደምነው መሐል አንዱ ግን ሐሳብ ለመስጠት የመጨረሻ ሰው ስለነበር ሁላችንም የእርሱን ለመስማት ጓጓን፡፡ ምክንያቱ ደግሞ የሁላችንም አሳብ ተቀራራቢ መሆንና ልጁ በትምህርት አብሮን ባሳለፈባቸው ያለፉ ዓመታት በተለምዶ “ወጣ ያለ” የሚባል ዓይነት ተማሪ መሆኑ ነው፡፡ ታዲያ የመናገር ዕድሉ ሲሰጠው  “ላነሣነው ችግር ጊዜያዊው መፍትሔ የክርስቶስን ዳግም መምጣት መጠባበቅ ሲሆን ዘላቂው መፍትሔ ደግሞ የጠበቅነው ጌታ በክብር መገለጡ (መምጣቱ) ነው” ብሎ ንግግሩን አጠናቀቀ፡፡ በዚያ ክፍል ውስጥ ከነበርነው አወያያችንን (መምህር) ጨምሮ ያልተደመመ አልነበረም፡፡ መሰብሰባችንም በዚሁ አስተያየት ተደመደመ፡፡

       ክርስቲያን እንደመሆናችን ትልቁ ተስፋችን የክርስቶስ ዳግም መመለስ ነው፡፡ ለሕይወታችንም የተሻለው ዕረፍት ያመነውን ጌታ መገናኘት ነው፡፡ ቅዱስ አውግስጢኖስ “እምነት ማለት ያላየኸውን ማመን ሲሆን የዚህም ሽልማቱ ያመንከውን ማየት ነው” ይላል፡፡ ከዚህ የሚበልጥ ምንም የለም፡፡ ምድራችን ላይ መፍትሔ የምናገኝላቸው ጊዜያዊ ችግሮች ከፀሐይ በታች በሆኑ ጥበቦች የሚቃለሉ ተግዳሮቶች ይኖራሉ፡፡ ዳሩ ግን እነዚህም እንኳን ፋታ የመስጠትን ያህል ናቸው፡፡ ሌላው ደግሞ የባለቤቱን መምጣት የብርቱ ክንዱን መገለጥ የሚጠብቁ ከሥጋና ከደም ምክር የተላለፉ መከራዎች አሉ፡፡

       ዓለማችን ውሉን እንዳጣ ልቃቂት የተዘበራረቁ ነገሮቿ ይበዛሉ፡፡ ላመነው ለእኛ ደግሞ ናፍቆታችን በጌታ መምጣት መሰብሰብ ነው፡፡ ጌታ “በአባቴ ቤት ብዙ መኖሪያ አለ እንዲህስ ባይሆን ባልኋችሁ ነበር ስፍራ አዘጋጅላችሁ ዘንድ እሄዳለሁና ሄጄም ስፍራ ባዘጋጅላችሁ እኔ ባለሁበት እናንተ ደግሞ እንድትሆኑ ሁለተኛ እመጣለሁ ወደ እኔም እወስዳችኋለሁ (ዮሐ. 14÷2)፡፡” እንዳለ በዚህ ተስፋ መጽናት ለመሄድ ከእርሱም ጋር ለመኖር መናፈቅ በጸሎት “ጌታ ሆይ ቶሎ ና” ማለት ይገባናል፡፡

       ከክርስቶስ መምጣት ጋር የብዙዎቻችን ሕይወት ያለው ትስስር ከደስታ ይልቅ በአመዛኙ ከፍርሃት ጋር የተያያዘ ነው፡፡ እንዲህ ያለው ስሜት ለመምጣቱ እንደ ቃሉ የሆነ ዝግጅት እንድናደርግ ከረዳን ጥቅሙ የበዛ ነው፡፡ ከዚህ ውጪ ከሆነ ግን ግብዝነት ነው፡፡ የክርስቶስ መምጣት በፍቅር የምንጠብቀው በማስቸኮል የምንለምነው በደስታም የምናስበው ነው፡፡ መተላለፍና አለመታዘዝ የጽድቅን ብድራት የሚቀበልበት ወገባቸው የታጠቀ መብራታቸው የበራ ትጉህ ባሪያዎች የድል አክሊል የሚቀዳጁበት እውነት ያለ ከልካይ የሚገዛበት የዘላለም ቀጠሮ ከጌታ ጋር ስላላችሁ በዚህ ሐሴት አድርጉ፡፡

        ከማስታመም በላይ በሆነ የሕሊና ቁስል በማያቋርጥ ልባዊ ጸጸት ለምትሰቃዩ በሰው መሐል እየኖራችሁ ብቸኝነት ለሚሰማችሁ ሁለንተናችሁን ሰጥታችሁ በወዳጅ ለተከዳችሁ የፈተና ወጀብ የመከራ ማዕበል ለሚያንገላታችሁ በሀዘንና መከፋት ለቆዘማችሁ የሰው መጠቋቆሚያ የወሬ ርዕስ ለሆናችሁ እመጣለሁ ያለን ይመጣልና በዚህ ደስ ይበላችሁ፡፡ ሚዛን እንደተዛባ ደሀ እንደተበደለ ፍርድ እንደተጓደለ የጌታ የሆኑቱ እንደተገፉ ምድር ግፍን እንደተሞላች እውነት አደባባይ ላይ እንደወደቀ የዓመፀኞች ልብ እንደደነደነ የመለኮት ቃል ወደ ጎን ተትቶ የሰው ወግ እንደፋነነ አይዘልቅም፡፡ አዎ! እመጣለሁ ያለን ጌታ እንደ ቃሉ ይመጣል፡፡



 










Friday, March 16, 2012

ሠግቶ መኝታ (ካለፈው የቀጠለ)


1. እግዚአብሔር አለ፡- ለብዙዎቻችን የእግዚአብሔር መኖር የሚሰበከው ለእግዚአብሔር የለሾች ብቻ እንደሆነ እናስባለን፡፡ ዳሩ ግን እግዚአብሔር የሚኖረው ለማያምኑት ብቻ ሳይሆን ለሚያምኑትም ሕልውናውን እያብራራ ነው፡፡ ምክንያቱም በሕይወት ውጣ ውረድ ለሚፈጠሩብን ማናቸውም ዓይነት ጥያቄዎች የእርሱ ሕልውና ብርቱ መልስ ነው፡፡

      በአንድ የፍልስፍና ትምህርት ቤት ውስጥ ስለ እግዚአብሔር ሕልውና ርዕስ ተነስቶ ፕሮፌሰሩ እንዲህ በማለት የእግዚአብሔርን አለመኖር ለማስረዳት ሞከረ “ እግዚአብሔርን በዚህ ክፍል ውስጥ ካላችሁት የሰማው አንድ ሰው አለ?” በማለት ጠየቀ፡፡ ከሚሰሙት ተማሪዎች መሐል የሚመልስ ጠፋ፡፡ መምህሩ በማስከተልም “በዚህ ካላችሁት መሐል እግዚአብሔርን የነካው ሰው አለን?” ሲል ጠየቀ፡፡ አሁንም በድጋሚ መልስ ጠፋ፡፡ ፕሮፌሰሩ ለመጨረሻ ጊዜ ጠየቀ “ከእናንተ መካከል እግዚአብሔርን ያየው ሰው አለ?” አሁንም ለሦስተኛ ጊዜ ከተማሪዎቹ መልስ ጠፋ፡፡ መምህሩም “በቀላሉ ከዚህ ተነስተን በእግዚአብሔር አለመኖር መስማማት እንችላለን” በማለት ደመደመ፡፡

        ተማሪዎቹ ግን እንዲህ ባለው ንግግር ደስተኖች አልሆኑም፡፡ ስለዚህ ሁሉም እድል እንዲሰጣቸው በመጠየቅ በአንድነት ቆመው “በዚህ ካለነው መሐል የፕሮፌሰራችንን አእምሮ (አንጎል) ያደመጠው አለ?” ክፍሉን ፀጥታ ዋጠው፡፡ አሁንም ሌላ ጥያቄ ተደመጠ “የፕሮፌሰራችንን አእምሮ የነካው ሰው አለ?” አሁንም ምላሽ ጠፋ፡፡ በማስከተልም “የፕሮፌሰራችንን አእምሮ የዳሰሰውስ በዚህ ክፍል ካለነው መሐል አለ?” ክፍሉ ከፊት ይልቅ ዝምታ ሰፈነበት፡፡ ተማሪቆቹም “በፕሮፌሰራችን ሎጂክ (ምክንያታዊነት) መሰረት በእርግጠኝነት ፕሮፌሰራችን አእምሮ የላቸውም” በማለት ሁሉም በጭብጨባ ተበተኑ፡፡  

        የሰይጣን የዘመናት ውጊያ በእግዚአብሔር ሕልውናና ፍቅር ላይ ያነጣጠረ ነው፡፡ ብዙ ነገሮች የሚከብዱብንም ልባችን ከዚህ ሀቅ ሲሸፍት ነው፡፡ በእያንዳንዱ የኑሮ ተግዳሮት ፊት የእግዚአብሔርን ሕልውና ብናብራራበት በማኅበራዊም ሆነ በግል ኑሮአችን እጅግ አትራፊ በሆን ነበር፡፡ እግዚአብሔር በፊቱ ለምናቀርበው ጸሎት ቀዳሚ ምላሹ “አለሁ” የሚል ነው፡፡ ይህ ለምናምን ለእኛ ትልቁ ዕረፍ ነው፡፡ ማግኘት ቢሆን ማጣት መክበር ቢሆን ውርደት መወደድ ቢሆን መከዳት መራብ ቢሆን መጠማት ተወዳጆች ሆይ እግዚአብሔር አለ፡፡ በዚህ ምድር ላይ ያለን ግንኙነት ከሰው ጋር ብቻ ቢሆን ሕይወት ምንኛ በመረረች ነበር፡፡ ዳሩ ግን ሁሉን ከሚችልና ከሚያስችል እግዚአብሔር ጋር ሕብረት ስላለን ሕልውናው ጉልበታችን ነው፡፡ የትምና ከማንም ጋር ትኖሩ ይሆናል፡፡ በዚያም ግን ጌታ ያለከልካይ አለ፡፡ በዚህ ሕያውና ቻይ አምላክ ታመኑ!

2. ሁሉን በልኩ እዩት፡- ኑሮን ከሚያከብዱብን ከሰዎች ጋር ያለንን ግንኙነት ከሚጎዱብን ነገሮች መሐል ሁሉን በልኩ አለማየት ተጠቃሽ ነው፡፡ እንዲህ ያለው ችግር ከራሳችን ጋር ላለን ሰላማዊ ትስስር ትልቅ እንቅፋት ነው፡፡ ማኅበራዊ ኑሮ ነገሮችን በአግባቡ ማስተዋልን ይጠይቃል፡፡

       ማንኛውም ሰው የራሱ የሆነ ውስጣዊና ውጫዊ ጊዜያዊና ዘላቂ የሕይወት ሠልፍ አለበት፡፡ ከዚህም የተነሣ ከሰውም ሆነ ከራሳችን የምንጠብቀው ልከኛ ሊሆን ይገባዋል፡፡ ሁሉን በልኩ ማየት ማለት ከሰው ትንሽ ከራስ ብዙ መጠበቅ ነው፡፡ በዚህም ከምንቀበለው ይልቅ የምንሰጠው የበዛ ይሆናል፡፡ የማንም ሰው ጉዳት ወደ እኛ ደርሶ ከመጎዳታችን በፊት የሚጎዳው ራሱ ባለቤቱ ነው፡፡ አንበሳ ሌላውን ከመጉዳቱ በፊት አስቀድሞ ራሱን ማስቆጣት አለበት፡፡ እኛ ጋር የሚደርሰው ጉዳት ከጎጂው የተረፈ ነው፡፡

3. ለዓላማችሁ ትኩረት ስጡ፡- ዓላማ የምንኖርለት ትልቁ ምክንያታችን ነው፡፡ ሰው ለመኖር የሚጓጓው ለመሥራት የሚተጋው በፊቱ የተቀመጠ ዓላማ ሲኖር ነው፡፡ በተለይ በስደት ሀገር በተለያየ ምክንያት የምትኖሩና በማኅበራዊ ኑሮ ለምትቸገሩ ከሁኔታው በላይ በዚያ ለምትኖሩበት ዓላማ ትኩረት መስጠቱ መቸገራችሁን ይቀንሰዋል፡፡ በእንቅፋቶቻችን ማንም አይደነቅም፡፡ በዚያ ውስጥ የምናገኘው ድልና የምናሳየው ስኬት ግን ለምድራችን ድንቅ ነው፡፡

4. እግዚአብሔር ያስችላል፡- ከድካም ሁሉ ትልቁ ድካም አቅምን አለማወቅ ነው፡፡ እግዚአብሔር ዘመናችንን ሁሉ የሚተጋው አቅማችንን እንድንረዳና የእርሱን ኃይል እንድናምን ነው፡፡ እግዚአብሔር ድካማችንን የሚያስንቅ ብርታት የሰውን ጥላቻ የሚሽር መውደድ ልብን የሚያሰፋ ቃል አለው፡፡ ትላንትን ያሻገረን ዛሬን ሊያሳልፈን ትላንት ያበረታን ዛሬንም ሊደግፈን የበረታች ክንዱ ተዘርግታለች፡፡ ምን ተስኖት ጌታ ነውና ስሙ ይባረክ፡፡ ፍቅር ይብዛላችሁ!

Tuesday, March 13, 2012

ሠግቶ መኝታ



      ሰው ጥርስ ስላለው ብቻ ማኘክ ምላስ ስላለው ብቻ ማላመጥ እንቅልፍ ስላለውም ብቻ መተኛት አይችልም፡፡ እያንዳንዱ የሰውነታችን ብልት እርስ በእርሱ የተያያዘ በመሆኑ የአንዱ ጉዳት በሌላው ላይ ተጽእኖ ይፈጥራል፡፡ ከፍተኛ ራስ ምታት በያዘን ጊዜ ለመሳቅ እንቸገራለን፡፡ በዚህም የያዝነው ሰብእና ምን ያህል የተባበረ እንደሆነ እንረዳለን፡፡ በማህበራዊ ኑሮም ያለው ግንኙነት ከዚህ የሸሸ አይሆንም፡፡ ከባንቱ ፍልስፍና የተገኘ አንድ ጽሑፍ እንዲህ ይላል፡- “ኑሮ የጋራ ነው፡፡ መኖርም ደስታውንም ችግሩንም አብሮ ለመካፈል ነው፡፡ በማኅበራዊ ኑሮ ውስጥ የግል የሆነ ነገር የለም፡፡ አንዱን የሚመለከተው ሌላውንም ይመለከታል፡፡ የጥቂቶች ኃይል የሁሉም ኃይል ነው፡፡ የጥቂቶችም ድካም የሁሉም ድካም ነው፡፡ ከሠራተኞችና ከታታሪዎች ጋር በኖርን ቁጥር ትጉህና ጠንካራ እንሆናለን፡፡ የእነርሱ ኃይል እኛንም ያነሣናል፡፡ ከሰነፎችና ከደካሞች ጋር ከኖርንም የእነርሱ ስንፍና ተጽእኖ ያደርግብናል፡፡ እናም ከከፍታ ይልቅ ቁልቁል ያወርደናል፡፡”

       ምድር ላይ ያለው ትልቁ ሀብት ሰው እንደመሆኑ አንዳችን ከሌላው ጋር የምንፈጥረው ሕብረት የግድ አስፈላጊ ነው፡፡ በዚህ ሂደት ውስጥ ደግሞ መጠቃቀም እንዳለ ሁሉ ማስታመም የሚከብዱ ጉዳቶችንም ማስተናገዳችን አይቀሬ ነው፡፡ የምንኖረው ምርጫችን ሁሉ ተግባራዊ በሚሆንበት ዓለም አይደለም፡፡ ሌሎችም የራሳቸው ዓላማ የሕይወት ዘይቤ የአስተሳሰብ ደረጃ የግል መረዳት አላቸው፡፡ በማኅበራዊ ሕይወት ውስጥ ለጉዳት ከሚዳርገን ነገር ውስጥ አንዱ ይህንን የተብራራ ሀቅ አለመረዳትና አለመቀበል ነው፡፡ በትዳር ውስጥ እንኳን አንዱ ለሌላው አሳብ ካልተሸነፈ በቀር አንድ ሥጋ ናቸውና በአንድ ጊዜ በአንድ ነገር ላይ ተመሳሳይ አመለካከት ይኖራቸዋል ማለት አንችልም፡፡

       በጣም አምሽቶ የሚተኛ ወዳጄ ሲያጫውተኝ “እኔ ከመተኛቴ በፊት የማስተኛቸው ብዙ ነገሮች አሉ” በማለት ለምን እንደሚያመሽ ነገረኝ፡፡ ሕሊናዬ “በላጤነት የማውቀው ይህ ባልንጀራዬ ዛሬ የሚያስተኛቸው ከየት አገኘ?” በማለት ይበልጥ ለመስማት ያለኝ ጉጉት ጨመረ፡፡ እርሱም “ሙቀጫና ዘነዘና  ቴፕና ሲኒ የአቶ እገሌ ሚስትና የወይዘሮ እገሊት ባለቤት የፊት አውራሪ ልጆች እነዚህን ሁሉ ካላስተኛሁ አልተኛም፤  ዝም ብዬ ልተኛ ብሞክር እንኳን ፈቃዴ በማይጠየቅበት መንገድ ምንም አይነት መዳፍ በላዬ ላይ ሳያርፍ እቀሰቀሳለሁ፡፡ ስለዚህ የእኔ እንቅልፍ ሠግቶ መኝታ ነው” አለኝ፡፡ እኔም “አትጸልይም እንዴ?” አልኩት፡፡ “እጸልያለሁ! የምጸልየው ግን እንቅልፍ ስጠኝ ብዬ ሳይሆን ጎረቤቶቼን እና ንብረቶቻቸውን አስተኛልኝ ብዬ ነው” አለ፡፡ ባልና ሚስት በተጣሉት እንቅልፍ አጥተው የሚያድሩ ላጤዎች ጎረቤት እስከ ስድስተኛ በሚፈላ ቡና አፍጠው የሚያመሹ ወገኖች ወዳጅነትን ጠብቆ መኖር ብዙ ዋጋ መክፈልን እንደሚጠይቅ ማስረጃዎች ናቸው፡፡

       ከሀገር ወጥተው በስደት አገር የሚኖሩ ሰዎች ከገዛ ወገናቸው ጋር በቀላሉ መግባባትና አብሮ መኖር ሲቸገሩ ይስተዋላል፡፡ ከዚህ ይልቅ በቋንቋም በዜግነትም ልዩ ከሆነ ወገን ጋር መተባበር ሲቀላቸው ይታያል፡፡ ይህም በሕሊናችን ውስጥ አንድ ጩኸት ይፈጥራል “እኛ ለእኛ የምንሆነው መቼ ነው?”፡፡ ማኅበራዊ ኑሮ እኛ ቤት ማስተኛ የሆነው ነገር ጎረቤት ጋር መቀስቀሻ ከሆነ ቢቀርስ? ማለትን ይጠይቃል፡፡ በክርስትና ውስጥ ደግሞ እንዲህ ያለው ውሳኔ ራስን ብቻ ወዳድ መሆንን መኮነን ነው፡፡ ለሌሎች እንቅልፍ ሥጋት ለኑሮአቸው ፍርሃት ለልባቸው ሁከት ላለመሆን መጠንቀቅ ማስተዋል ነው፡፡ በፍጥረት መጀመሪያ ላይ እግዚአብሔር ከጠየቃቸው ጥያቄዎች አንዱ “ወንድምህ ወዴት ነው?” የሚል ነበር፡፡ (ዘፍ. 4÷9) ለራሳችን ከምናሳየው ፍቅር ባልተናነሰ መልኩ ለሌሎች ፍቅር ማሳየት መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሰረት ያለው ነው፡፡

        በፊት በፊት መንገድ ላይ አስተውላችሁ ከሆነ ልጆች “እስካልነካሁህ ድረስ እንደፈለኩ መሆን እችላለሁ፤ ስምህንም እስካልጠራሁም ድረስ መሳደብ መብቴ ነው” ይላሉ፡፡ ትልልቆቹ ጋር ስትመጡ ደግሞ ስክር ብሎ “እኔ ብሰክርም አልረብሽም” ይላሉ፡፡ ራሳችንን የማንችልባቸው ብዙ ነገሮች አሉ፡፡ ራሳቸውን የሚያጠፉ ሰዎች እንኳን ሰው ላለማስቸገር ብለው ጉድጓዳቸውን ቆፍረው ቢሞቱ አፈር አልባሽ ድንጋይ አጋዥ ያስፈልጋል፡፡ ተወዳጆች ሆይ ከሰው ጋር ላላችሁ ወዳጅነት ዋጋ ስጡ፡፡ የእገሌ ጠቡ እንኳን ናፈቀኝ እየተቆጣኝም ቢሆን አጠገቤ በሆነ ብላችሁ አታውቁም? የያዝነውን ነገር ዋጋና ጥቅም ካጣነው በኋላ የምናስተውል ተላላ መሆን የለብንም፡፡ ሁላችንም የአንድ አካል አባሎች ነን፡፡ ተፈጥሮ በእኛ ውስጥ የእርስ በእርስ መፈቃቀርንና መፈላለግን ዘር ተክላለች፡፡ አብረን ለመኖርም የምንችል አድርጋ ቀርፃናለች፡፡ ስለዚህ ሁላችንም የተፈጠርነው ለሁላችንም የጋራ ደኅንነት መሆኑን ማመን ይገባናል፡፡

        በማኅበራዊ ኑሮ ለምትቸገሩ ሁሉ በሥጋ ለባሹ ሰው አልጎዳም ሊል የሚችል ማንም የለምና በዚህ አትደነቁ፡፡ ቁም ነገሩም ይህ አይደለም፡፡ ዋናው ነገር በዚህ ውስጥ ምን ተማርን? ምን አተረፍን? ለሌሎች የሚረባ ምን ነገር ያዝን? የሚለው ነው፡፡ ከዚህ ባለፈ ሰዎች ከሚያደርሱብን ጉዳት ከሚዘረጋብን ወጥመድ ለማምለጥ በእግዚአብሔር ላይ መደገፍ የሚረዳንንም ኃይል ለማግኘት ወደ ጸጋው ዙፋን በእምነት መቅረብ ይኖርብናል፡፡ ሠግቶ ላለማንቀላፋት ከማኅበራዊ ኑሮ አንፃር ጥቂት መፍትሔ በቀጣይ እንመለከታለን፡፡ ፍቅር ይብዛላችሁ!

                                                                   ይቀጥላል

Thursday, March 8, 2012

የግልግል ኑሮ



      ለአገልግሎት ወደ አንድ ከተማ ሄደን የተመለከትኩትና የሰማሁት ነገር ብዕሬን እንዳነሣ ምክንያት ሆኖኛል፡፡ ነገሩ እንዲህ ነው! የታመመ ሰው ልንጠይቅ የገባንበት ክፍል ውስጥ ሰው ከብቦት፣ ፊቱ ተለጣጥፎ በሰመመን ያለ አንድ ሕመምተኛ አስተዋልን፡፡ እኛም የሄድንበት ዓላማ እንዳለ ሆኖ ይህም ወገን ነውና "ምን ሆኖ ነው?" በማለት ጠየቅን፡፡ ከታዛቢዎች መሐል አንዱ "ሚስቱ ደብድባው እስከ አሁን አልነቃም" አለን፡፡ እንደ እኛ ሕመምተኛ ሊጠይቅ የመጣ አንድ ሌላ ሰው ቀበል አደረገና "ማርች ኤይትን አስመልክቶ ነው?" በማለት ለመቀለድ ሞከረ፡፡ አንዳንዶቹ ሴቶች ደግሞ "ምነው እንደ አንቺ ሺ በተወለደ" በሚል መንፈስ በሌለችበት ሙገሳ ቸሯት፡፡ እኛም ጥቂት አይተን ልባችን ግን ብዙ ታዝቦ ተመለስን፡፡

       ዘመናችን የምናየው የምንሰማው ሁሉ ጉድ የሆነበት፤ ሰው ተፋቅሮ ቀርቶ ተቻችሎ፣ ተቀራርቦ ቀርቶ ተራርቆ ለመኖር አቅመቢስ የሆነበት ነው፡፡ ስለ ፍቅር የሚጻፉ መጻሕፍት፣ ስለ ይቅርታ የሚሰበኩ ስብከቶች፣ ስለመቻቻል የሚለፈፉ ንግግሮች፣ ስለ መብት የሚበተኑ ማስገንዘቢያዎች እነዚህ ሁሉ መደለያዎችና ማባበያዎች አልፎም ማስፈራሪያዎች ለምናየው ችግር የማገላገልን ያህል እንኳን መፍትሔ መስጠት ተስኗቸዋል፡፡ እጮኛው ላይ አሲድ ስለደፋ ፍቅረኛ፣ ባሏን ገላው ሬሳው ላይ ምጣድ ስለጣደች ሚስት፣ የባለቤቱን ዓይን ስላወጣ አባወራ፣ የባሏ ሰውነት ላይ የፈላ ውኃ ስለደፋች ሚስት ወዘተ እነዚህ ሁሉ ሰውን የሚያስብ አራዊት፣ አንድ ቤት የሚኖር ጣውንት አስመስለውታል፡፡ ጭካኔ ማስተዋልን፣ ክፋት ትምህርትን፣ ዓመጽም ችሎታን አይጠይቅም፡፡ 

      ወዳጅነትን በመልካም መጠበቅ፣ ከባልንጀራ ጋር በፍቅር መዝለቅ ግን አይቶ እንዳላየ ሰምቶ እንዳልሰማ ማለፍን፤ ተጎድቶ እንዳልተጎዳ አዝኖ እንዳላዘነ መታገስን፣ የሚበልጥ አሳብ ይዞ የተሻለ ራዕይ ኖሮ ግን ላነሰው መሸነፍን ይጠይቃል፡፡ አልፎም ተርፎ የራስን ለሌሎች ጥቅም አሳልፎ በመስጠት መገለጥን ይጠይቃል፡፡ በፍቅራቸውና በኑሮአቸው የምንቀናባቸው ደግሞም ለሌላው አርዓያ መሆን የቻሉ ሰዎች ቤታቸው ችግር ስለሌለ አለመግባባት ስለማይከሰት አይደለም፤  ለሚበልጠው ስለሚሸነፉ ብቻ ነው፡፡ መብቴ ከማለት ፍቅሬ ማለት የሰውን ከማሰብ የእግዚአብሔርን መመልከት አማራጮችን ከመቁጠር የመረጡትን መንከባከብ ይልቃል፡፡  

      ብዙ ትዳሮች እንዳልሆነ እየሆኑ፣ ብዙ ልጆች ያለ በደላቸው እየተበተኑ፣ በዙሪያችን ያሉ ከልብ እያዘኑ ነው፡፡ ትዳር በፍቅር እንጂ በመብት አይቆምም፡፡  ወዳጅነት ከልብ በሆነ ሕብረት እንጂ በሕግ ወሰን አይጸናም፣ ማኅበራዊ ኑሮም በወንድማማችነት መንፈስ እንጂ በመጠባበቅ አይቆምም፡፡ አሁን አሁን ስናይማ  ያለ ገላጋይ የማይሆኑ ጥምረቶች (ማንኛውም) እየበረከቱ መጥተዋል፡፡ በእናትና በልጅ መካከል ያለው ግንኙነት እንኳን ገላጋይ አስፈልጎታል፡፡ ገላጋይ ካለ ለድብድብ የሚጋበዙ ሰዎችን አስተውላችሁ፤ አልያም ገላጋይ የሌለበት ቦታ ሄደን ይዋጣልን! ያሉ ልጆችን ተመልክታችሁ ይሆናል፡፡ ገላጋይ ካለ ሁሉም የአቅሙን ይሞክራል፤ ካልሆነለት ደግሞ በገላጋዩ ተተግኖ ይወራጫል፡፡ ስለዚህ ኑሮን ውጥረት የነገሰበት ያደርገዋል፡፡ መቼም ቢሆን በማስፈራሪያዎች መሐል እውነተኛ ፍቅር፤ ልብ የሚያርፍበት ሰላም አይኖርም፡፡  እንደ እኔ የሴቶች ቀን የወንዶች ቀንም ነው! ከሴት ያልተወለደ ብሎም ያልወለደ የለም፡፡ በትዳር ውስጥ ያሉ ደግሞ "አንድ ሥጋ ናቸው" ተብሏል፡፡ ተወዳጆች ሆይ መፍትሔው አንድነትና ፍቅር  ነው፡፡ ስለጭቆና ማውራት ጭቆናን አያስቀረውም፤ መብት አለኝ ማለትም ገፍቶ ከመጣ ሞት አያድንም፡፡ ፍቅር ግን ከሁሉም ይበልጣል፡፡

Monday, March 5, 2012

ቅን



       ኑሮ ሕሊና ውስጥ ነው፡፡ በእዚህ ውስጥ ያለውም ትልቁ የማሸነፍ ኃይል ቅንነት (አዎንታዊ አመለካከት) ነው፡፡ የሕይወትን ሠልፍ በማሸነፍ ሒደት ውስጥ አዎንታዊ አስተሳሰብ ያለው ድርሻ የጎላ ነው፡፡ ካለን ጥበብ ይልቅ ብልሀታችንን የሚመራው አመለካከት በእጅጉ አስፈላጊ ነው፡፡ ሁሉም ነገር ኖሮን ነገር ግን እውነተኛ አስተሳሰብ ከሌለን ሕይወትን በግርድፉ የምንኖር ምስኪኖች እንሆናለን፡፡ አስተሳሰባችን ለማንኛውም ሁኔታ ምላሽ የምንሰጥበት መንገድ ነው፡፡ ስለዚህ ልዩነት የሚፈጥረው አንድ ሰው በሕይወት ውስጥ ያገኘው ነገር ሳይሆን ሕይወትን የተቀበለበት መንገድ ነው፡፡

      ጌታ በመስቀል ላይ ሳለ ሁለት ወንበዴዎች አብረው ተሰቅለው እንደነበረ ቅዱሳት መጻሕፍት ይመሰክራሉ፡፡ ለዘመናት ያስተሳሰራቸው ተመሳሳይ አሳብ አንድ ዓይነት ዓላማ ክርስቶስ በመካከላቸው ሲሆን እንደነበረ ሊቀጥል አልቻለም፡፡ ጌታ ለአንዱ ቀይ ለሌላው ጥቁር፣ ለአንዱ ቸር ለሁለተኛው ንፉግ፣ ለአንደኛው ወዳጅ ለሌላው ጠላት፣ ለአንዱ ቅርብ ለሁለተኛው ሩቅ አልነበረም፡፡ ነገር ግን ለሁለቱም አንድ የሆነው ጌታ በሁለቱ አእምሮ ውስጥ ግን ሁለት ነበረ፡፡ ይህም የሆነው ከአመለካከታቸው የተነሣ ነበር፡፡ አንዱ በሥጋ የተገለጠ የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ ሲያስተውል አንዱ ግን ምንም አይነት መለኮታዊ መቻል የሌለው ሰው ብቻ (ሩቅ ብእሲ) እንደሆነ አሰበ፡፡ ሁለቱም ግን የአሳባቸውን አጨዱ፡፡  

       ሕይወት ወደ እኛ ቢለዋ ብትወረውር ቢለዋውን ማቆሚያ ሁለት መንገዶች አሉ፡፡ አንደኛው በስለቱ በኩል ሲሆን ሌላኛው ደግሞ በእጀታው በኩል መያዝ ነው፡፡ እናንተ የትኛውን ትመርጣላችሁ? ያለምንም ጥርጥር የሚያጋጥሙን ነገሮች በሕይወት ላይ ተጽእኖ ማምጣታቸው አይቀሬ ነው፡፡ ሆኖም ግን ከምንም በላይ በሕይወታችን ውስጥ ተጽእኖ መፍጠር የሚችለው ባጋጠሙን ነገሮች ላይ እኛ የሚኖረን አመለካከትና ተግባራዊ የምናደርገው ልምምድ ነው፡፡ ሕይወትህን ለመቀየር እጅግ ጠቃሚው መንገድ ስለ ሕይወት ያለህን አስተሳሰብ መቀየር ነው፡፡ አስታውሱ! በምድርና በገነት መካከል ያለው ርቀት የከፍታ ጉዳይ ሳይሆን የአመለካከት ጉዳይ ነው፡፡ ተወዳጆች ሆይ በአእምሮአችሁ መታደስ ተለወጡ፡፡ ቅንነት ይብዛላችሁ!

Friday, March 2, 2012

ጠባይ ሲመሽ



   ወድዶ አለመዝለቅ፣ የያዙትን አለማጥበቅ፣ ጨበጥ ለቀቅ፣ ኮስተር ሞልቀቅ፣ ከዋሉበት በጎ ጋር አለማንቀላፋት ሰሞነኛው የሰው ጠባይ ነው፡፡ ቀኑን እንደ ዐሥር ሰው ጠባይ ተስተናግደንበት የምንሸኘው፤ ለአንዱ ውኃ ለሌላው እሳት፣ ለአንዱ ማር ለሌላው እሬት፣ ለአንዱ ምንጣፍ ለሌላው እሾህ ጠዋት ትሁት ከሰዓት በኋላ ቁጡ በሆነ ጠባይ ከሁሉም ዓይነት ሆነው የሚያሳልፉ ብዙ ናቸው፡፡

   እንደ ማለዳ ጮራ፣ እንደ ቀትር ፀሐይ ለሁሉም የሚታይና የሚያበራው መልካምነት ከጀንበሯ ጋር አብሮ እየጠለቀ፣ የወዳጅ ጠባይ እየጨለመ፣ ከሁኔታ መክፋት ጋር አብሮ እየከፋ፣ ከሰው ሽሽት ጋር አብሮ እየጠፋ ከልብ ያዘንን ሁሉ ጨለማን የሚገስጽ ብርሃን፣ ሁከት የማይደፍረው ሰላም፣ ሀዘን የማይጋርደው ደስታ፣ ስደት የማያደክመው ዕረፍት፣ ዓመጽ ታግሎ የማይጥለው ብርታት የሁሉም አይን ብቸኛ ተስፋ፣ በየትኛውም ጨለማ ውስጥ መቅረዝ በማንኛውም ብርቱ ሠልፍ መሐል ጽኑ ግንብ ክርስቶስ ኢየሱስ አለላችሁ!

   ሰው ቀን ቢመሽበት ሻማ ለኩሶ ያድራል፡፡ ጠባይ ቢመሽ ግን እንዴት ያንቀላፋል? በተዋበ ሕንፃ ባማረ መንደር በሚስቡ ዕቃዎች ተከብበን ጨለምተኛ አመልን ማስተናገድ አንችልም፡፡ ሰው ጠጉሩን አበጥሮ አለባበሱን አሳምሮ የሕሊናው ጀንበር ካዘቀዘቀች ውጫዊ ምቾት ምን ይረባዋል? የቀንና ሌሊት መፈራረቅ ተፈጥሮአዊ ነው፡፡ የሰው ጠባይ ግን የዝንባሌው ውጤት ነው፡፡ መልካሙን አመል ያዝልቅልን!

      "
ማለዳ ማለዳ አዲስ ነው ታማኝነትህ ብዙ ነው፡፡ ሰቆ.ኤር. 3÷23"