Friday, April 27, 2012

ድል የመንሣት መርኅ


         

         ሕይወት ብርቱ ሠልፍ በሆነችባት ዓለም ውስጥ በኑሮ ላይ ድል የማንግኘት ፍላጎት የሁሉም ነው፡፡ ከክርስቲያን ማብራሪያዎች አንዱም ወታደር የሚለው ነው፡፡ (2 ጢሞ. 2÷3) ወታደርን ስናስብ ለመንግስቱ ሕግ መከበር የቆመ በማንኛውም ውጊያ ውስጥ ቆርጦ የሚሠለፍ ድሉንም ሽንፈቱንም በጋራ የሚያጣጥም፣ በአጠቃላይ ፈቃዱ ሁሉ ወደ መንግስቱ የሆነ ታማኝ አገልጋይ ነው፡፡ በክርስትና ውስጥ ውጊያው እንደ ሰው ልማድ አይደለም፡፡ መጋደላችንም ከሥጋና ከደም ጋር ሳይሆን ከዚህም ከጨለማ ዓለም ገዦች ጋር በሰማያዊም ስፍራ ካለ ከክፋት መንፈሳውያን ሠራዊት ጋር ነው፡፡ (ኤፌ. 6÷12) ስለዚህ በማንኛውም ሠልፍ ውስጥ ባለ ድል ለመሆን የምንከተላቸው መርሆዎች ሽንፈታችንንም ድላችንንም የመወሰን አቅም አላቸው፡፡

        ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የፊልጵስዩስን መልእክት ሲጽፍ የነበረበት ሁኔታና በመልእክቱ ውስጥ የተላለፈው የእግዚአብሔር አሳብ ለአንድ ክርስቲያን ድል መንሣት “መርኅ” የሚሆን ትምህርትን የሚያስተላልፍ ነው፡፡ መልእክቱ የተፃፈው በሮም እስር ቤት ውስጥ ሲሆን የመልእክቱ ጥቅል አሳብ “በጌታ ደስ ይበላችሁ” የሚል ነው፡፡ (ፊል. 4÷4) ከአዲስ ኪዳን መጻሕፍት መካከል ስለ ደስታ አብዝቶ የሚናገር ክፍል ሲሆን ኑሮ የምሬት አደባባይ ለሆነባቸው፣ ዛሬን በሥጋት ለሚያሳልፉ ነገንም በፍርሃት ለሚጠባበቁ ተግባራዊ ሊደረግ የሚችል መፍትሔን የያዘ ነው፡፡ መልእክቱ አራት ምእራፎችና አንድ መቶ አራት ቁጥሮች ሲኖሩት በዋናነት የመዓዛ ሽታና የተወደደ መሥዋዕት ለእግዚአብሔርም ደስ የሚያሰኘውን ስጦታ ከአፍሮዲጡ ስለመቀበሉ የፊልጵስዩስን ቤተ ክርስቲያን ለማመስገን የተፃፈ ነው፡፡


         ሐዋርያው ያሳየውን ጥንካሬ ስንዳስሰው ሊታሰብለት በሚገባ ቦታ ላይ ሆኖ ለሌሎች ያስባል፣ ሊጠየቅ በሚገባ ቦታ ላይ ሆኖ ስለ ሌሎች ደኅንነት ይጠይቃል፣ እርሱ መጽናናት በሚገባው ስፍራ ላይ ሆኖ ሌሎችን ያጽናና ነበር፡፡ እኛ ለተወሰኑ ደቂቃዎች በወኅኒ እንደተጣልን እናስብና ምን አይነት መልእክት ልንጽፍ እንደምንችል ገምቱ? መኝታው ይቆረቁራል፣ ምግቡ አይመችም፣ እገሌን የእኔ ቀን ደግሞ ሲመጣ ያገናኘን በሉልኝ፣ የምወጣበት ቀን ናፍቆኛል፣ የመሳሰሉትን ከዚህ ዓለም ፈቀቅ ያላሉ አሳቦች ልንጽፍ እንችል ይሆናል፡፡ መሄድ ከክርስቶስ ጋር ለመኖር መናፈቅ፣ እርሱንና የትንሣኤውን ኃይል ለማወቅ መጓጓት፣ ኑሮዬ ይበቃኛል ማለትን መማር፣ ሁሉን ከሁሉ ስለሚበልጥ ጌታ እንደ ጉዳት መቁጠር፣ ወደ ሙታን ትንሣኤ ለመድረስ መመኘት፣ አገሬ በሰማይ ነው ብሎ መመካት፣ እውነተኛ የሆነውን ነገር ሁሉ ጭምትነት ያለበትን ነገር ሁሉ ጽድቅ የሆነውን ነገር ሁሉ ፍቅር ያለበትን ነገር ሁሉ ማሰብ፣ በተቃዋሚዎች አገልግሎት ደስ መሰኘት እነዚህ ሁሉ ከሥጋ እስራት ውስጥ የተፃፉ የመንፈስ አርነቶች ናቸው፡፡ ብዙ የእግዚአብሔር ሰዎች ከመከራቸው ለሌሎች ትመምህርትና መጽናናት የሚሆን ነገርን ትተዋል፡፡ ስለ እግዚአብሔር ልጅም“ምንም ልጅ ቢሆን ከተቀበለው መከራ መታዘዝን ተማረ” (ዕብ. 5÷8) ተብሎለታል፡፡ እኛስ ከፈተናዎቻችንና ከችግሮቻችን የተማርነው ምንድነው?

         በጉድለት ውስጥ ስለ እግዚአብሔር ሙላትነት፣ በሕመም ውስጥ ስለ ጌታ መድኃኒትነት፣ በርሀብ ውስጥ ስለ እርሱ እንጀራነት፣ በሀዘን ውስጥ ስለ ጌታ ደስታነት ማውራት በጉዳት ውስጥም በሁሉ ማመስገን እንዴት ያለ ዕረፍት ነው፡፡ በአንበሳ ጉድጓድ፣ በወኅኒ ሠንሰለት፣ ሰባት እጥፍ በሚነድ እሳት፣ ፍጥሞ ደሴት ላይ በግዞት፣ ከእግር እስከ ራስ በሚደርስ ቁስል፣ ቀኑን ሁሉ በመገደል ያለፉ የእግዚአብሔር ሰዎች ለጌታ ስንፍናን አልሰጡም፡፡ ይልቁንም በእውነትና በመንፈስ ለሚመለከው ተንበረከኩ፣ እጃቸውን ከልባቸው ጋር አንስተው አመሰገኑ፡፡ ታዲያ ድል የመንሣታቸው ምስጢር ምን ነበር? እስር ቤት ስለ ነፃነታቸው እንዲያወሩ፣ በሚነድ እሳት መሐል ለሕይወት ውኃ ምንጭ እንዲንበረከኩ፣ በአናብስት ጉድጓድ ውስጥ የይሁዳውን አንበሳ እንዲያመልኩ፣ በወጋሪዎች መሐል የእግዚአብሔርን ክብር እንዲያስተውሉ፣ በታላቋ ሮም ከተማ ውስጥ ሆነው አገራቸው ሰማይን ተቤዢአቸው ክርስቶስን እንዲካፍቁ የሆነበት የሕይወት መመሪያቸው ምን ቢሆን ነው? በችግር፣ በሕመም፣ በስደት፣ በብቸኝነት፣ በሀዘን፣ በመከዳት ሸለቆ ውስጥ ላለን ሁሉ የፊልጵስዩስ መልእክት ድል መንሣትን በመከራ ውስጥ መጽናትን የሚያስተምር ነው፡፡ ከዚህ በታች በአራቱም ምእራፍ ውስጥ የየምእራፉን ዋና ሐሳብ በማንሳት አራት ድል የመንሣት መርሆዎችን እናያለን፡፡

ውሳኔ፡-

ትንንሽ ከምንለው ጀምሮ ትልልቅ እስከምንለው ድረስ በየዕለቱ የምናሳልፈው ውሳኔ በነገዎቻችን ላይ ተጽእኖው ቀላል የሚባል አይደለም፡፡ ትክክለኛ ኑሮ የሚጀመረውም በውሳኔ ነው፡፡ መወሰን እንዳለመቻል ኑሮን ዝብርቅርቅ የሚያደርግ ነገር እንደሌለ በዚህ ውስጥ ያለፍን ሁሉ ዘወትር የምናየው ጠባሳ ነው፡፡ የፊልጵስዩስ ምእራፍ አንድ ዋና አሳብ “ለእኔ ሕይወት ክርስቶስ ሞትም ጥቅም ነውና” (ቁ. 21) የሚለው ነው፡፡ ክርስትና እንኳን ኑሮው ሞቱም ጥቅም አለው፡፡ ሰዎች በመኖራችን ውስጥ ከሚያዩት የበለጠ በሞታችን ውስጥ የሚጠብቀን ጥቅም የበለጠ ነው፡፡

           በመጀመሪያው መቶ ክ/ዘመን ክርስትናን ላላመኑ መመስከር እጅግ ዋጋ የሚያስከፍልበት ዘመን ነበር፡፡ ክርስቲያን መሆን የሚያስወነጅልበት ጊዜም ነበር፡፡ አንድ ክርስቲያን በወታደር ተይዞ ንጉሡ ፊት ሲቀርብ ሁለት ምርጫ ይቀርብለታል “ቄሳር ጌታ ነው” ወይንም “”ኢየሱስ ጌታ ነው” ማለት ከዚህም የተነሣ ክርስቲያኖች ለልዩ ልዩ መከራና ሞት ይሰጡ ነበር፡፡ ክርስቲያኖችም ከሞት በኋላ የሚጠብቃቸው ወዳጅ የተዘጋጀላቸው ስፍራ የዘላለም ቀጠሮ እንዳለ በአስጨናቂዎቻቸው ፊት ከእምነት በሆነ ድፍረት ይመሰክሩ ነበር፡፡ ታዲያ ሰሚዎቻቸው ክርስቲያኖቹ በሚሉት ባያምኑበትም እንኳን አይጠራጠሩትም ነበር፡፡ ስለዚህ ሞታቸውን አውቀው በሥቃይ ያዘገዩት ደግሞም በእንግልታቸው ይዝናኑበት ነበር፡፡ በክርስቶስ መኖር ያለውን ሕይወት በሞቱም መካፈል የሚያስገኘውን ጥቅም እኛ ባንረዳው አንኳን ጠላት አይጠራጠረውም፡፡ ጌታ እኛን ከምን እንዳወጣንና እንዴት ወዳለ ክብር እንዳሸጋገረን ከእኛ በላይ ጠላት ያውቀዋል፡፡ እግዚአብሔር ራሱን ለእኛ ብቻ ሳይሆን ለጠላትም ያብራራል፡፡ ሞታችንን ጥቅም ያደረገው የሁሉ ቤዛ መድኃኔዓለም ስሙ ብሩክ ይሁን፡፡

          በዚህ ምድር በምናልፍበት ማንኛውም ሁኔታ ድል መንሣትን የምናገኝበት ትልቅ ውሳኔ ሕይወት ክርስቶስ ሞትም ጥቅም እንደሆነ ማመን ነው፡፡ ከእርሱ ጋር መኖራችን ትርጉም የሚሰጠውን ያህል በእርሱ መሞታችንም ትጉሙ ከፍ ያለ ነው፡፡ ይህም ሕይወታችን ክርስቶስንና የትንሣኤውን ኃይል መረዳት ነው፡፡ የሕየወትን ያሕል አስፈላጊ እንደሆነ ያሰብነው ነገር ምንድነው? ለእርሱስ መሸነፍና ራስን መስጠት ሊያስገኝ የሚችለው ጥቅም ምን ሊሆን ይችላል? ለእኛ ሕይወት ሀብት ቢሆን ጥቅሙ ኪሳራ፣ ሕይወት ዝና ቢሆን ትርፉ በሚበልጥ ዝነኛ መረሳት፣ ሕይወት ሥልጣን ቢሆን ትርፉ መሻር አይደለምን?

           ተወዳጆች ሆይ ሁኔታን ድል የምንነሣበት መመሪያ ክርስቶስን ሕይወት ማድረግና ሞትም ጥቅም እንደሆነ መረዳት ነው፡፡ አንድ ክርስቲያን በጌታ መሞት ጥቅም እንዳለው ከተረዳና በዚህም ላይ እምነቱን ከጣለ ሀዘኑ፣ ጭንቀቱ፣ ሕመሙና ፈተናው ውስጥ እንዴት ለጥቅሙ የሚሆን ነገር አይኖርም? እግዚአብሔር በኑሮአችን ድልን የሚሰጠን እርሱን ለሕይወታችን በተብራራው መጠን ነው፡፡ ጌታ ማንንም ለሽንፈት ወደ ምድር አላመጣም፡፡ እርሱ ለእኛ ያለው ነገር የማያቋርጥ ድል ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ በነፍስ በሥጋና በመንፈሱ ላይ ድልን እንዲቀዳጅ ያስቻለው ኑሮውንም ሞቱንም ለጌታ ክብር ለማድረግ መወሰኑ ነው፡፡ ሁሉን ለእርሱ ክብር ማድረግ ቁርጥ ውሳኔና ዓላማችን ሊሆን ይገባል፡፡

አሳብ፡-

የውሳኔዎቻችን መጠበቂያ አሳብ ነው፡፡ በጎ ውሳኔዎቻችንን በክፉ አሳብ ክፉ ውሳኔዎቻችንንም በበጎ አሳብ ለመጠበቅ ብንሞክር ከንቱ ድካም ነው፡፡ መልካም የሆነውን አሳብ የምንጠብቀው በመልካም ልምምድ ነው፡፡ በእግዚአህሔር ፊት እንዳለን በስሙም እንደተሰበሰብን በእውነትና በመንፈስ እንደምናመልክ በሕይወታችንም ሙሉ አዛዥ መንፈስ ቅዱስ እንደሆነ በተሰማን ጊዜ የሥጋን አሳብ የሚቃወሙ ለመንፈሳዊው ነገር ዋጋ የሚሰጡ የምድሩን አናንቀው የሰማዩን የሚያከብሩ ውሳኔዎችን እንወስናለን፡፡ ሕይወቴ ክርስቶስ ሞቴም ጥቅም ነው እንላለን፡፡ ዳሩ ግን ምድረ በዳውን ስንቀላቀል ከፀሐይ በታች ወዳለው ኑሮአችን ስንመለስ የሚጠብቀን አሳብ ለእግዚአብሔር ነገር ክብር የማይሰጥ ከቀመስነው ፍቅር ከተረዳነው እውነት ወደኋላ የሚጎትት ይሆናል፡፡ ስለዚህም ውሳኔያችንን የዓለም አሳብ እየገዘገዘው በአለህበት ሂድ አይነት ይሆንብናል፡፡ በአንድ ሰው ውስጥ ያለው ትልቁ ነገር አሳቡ ነው፡፡ ድርጊቶቻችን የአሳብ ማሳያዎች ናቸው፡፡ መልካም ማሰብ መልካም ለማድረግ አቅም ነው፡፡ መለወጥም በአእምሮ መታደስ ነው፡፡

         የፊልጵስዩስ ምእራፍ ሁለት ዋና አሳብ “በክርስቶስ ኢየሱስ የነበረ ይህ አሳብ በእናንተ ዘንድ ደግሞ ይሁን፡፡” (ቁ. 5) የሚል ነው፡፡ ይህ አሳብ መዋረድንም አውቃላሁ መጉደልንም ተምሬአለሁ ወደምንልበት ደረጃ የሚያሸጋግረ አሳብ ነው፡፡ በእግዚአብሔር መልክ ሲኖር ሳለ የባሪያን መልክ የያዘውን፣ በምስሉ እንደ ሰው ተገኝቶ ራሱን ያዋረደውን፣ እስከ መስቀል ሞትም የታዘዘውን ጌታ የምንመስልበት አሳብ ነው፡፡ ለወገኔ ይጠቅማል በማለት አልያም በከንቱ ውዳሴ ሳይሆን ባልንጀራችን ከእኛ ይልቅ እንዲሻል የምንቆጥርበት አሳብ ነው፡፡ “በእምነታችሁ መሥዋዕትና አገልግሎት ተጨምሬ ሕይወቴ እንኳ ቢፈስ ደስ ብሎኛል” የምንልበት ራሳችንን እንደ እንጀራ ለመቆረስ እንደ ውኃም ለመፍሰስ የምናዘጋጅበት አሳብ ነው፡፡ አሳብን ማከም አካልን እንደማከም ቀላል አይሆንም፡፡ ለጌታ ግን ሁሉ ይቻለዋል፡፡ ዛሬ የምናያቸው ትልልቅ ሕንፃዎች በፊት በመሐንዲሱ አእምሮ ውስጥ የነበሩ አሳቦች ናቸው፡፡ እንደውም አንድ ክ/አገር በመሐንዲሱ ስሕተት ፊትና ጀርባው ተቀያይሮ የቆመ ሕንፃ አይቻለሁ፡፡ ሰው አሳቡ ካልተስተካከለ ምድሪቱ ላይ የሚቆመው ሁሉ የተበላሸ ነው፡፡

            በክርስቶስ ኢየሱስ የነበረው አሳብ ትሕትና ነው፡፡ ትሕትና በመጥፎና በጠማማ ትውልድ መካከል ያለ ነቀፋ የዋሆች፣ ያለ ነውር የእግዚአብሔር ልጆች፣ ያለ ማንጎራጎርና ክፋት እንደ ብርሃን የምንታይበት አሳብ ነው፡፡ እርሱን የምንመስለውም በዚህ ነው፡፡ ቅናት፣ ትዕቢት፣ ክርክርና ዓመፀኝነት የሚወገዱት ትሕትና ሲተካቸው ነው፡፡ በእንግድነት ኑሮአችን ትሕትና በማንኛውም ሁኔታ ላይ ድልን እንድናገኝ ያስችለናል፡፡ የእግዚአብሔር ልጅ በሸላቾቹ ፊት እንደሚታረድ በግ ዝም ባይል፣ እስከ መስቀል ሞት በትሕትና ባይታዘዝ ስለ ትንሣኤው ልናወራ እንዴት ይቻለን ነበር? ስለ ክብር ለማውራት ውርደትን በትሕትና መቀበል ያስፈልጋል፡፡

          ተወዳጆች ሆይ በክርስቶስ ኢየሱስ የነበረው አሳብ ዛሬ እኛ አለን ወይ? በቅናት ወንድምን ማሳደድ፣ ለራስ ጥቅም ሌላውም መግፋት፣ የባልንጀራን ኃጢአት በአደባባይ መግለጥ፣ እውነትን ረግጦ ለራስ ክብር መኖር ይህ በጌታችን የነበረ አሳብ ነውን? ዘረኝነት፣ መለያየት፣ በሐሰት መወነጃጀል ከማን ተማርነው? ለክፋት ትውፊት የለውም፡፡ በክርስቶስ ኢየሱስ የነበረው አሳብ ከቁራሹ ላይ የሚቆርስ፣ ደካማውን ጥሎ ሳይሆን ተሸክሞ የሚያልፍ፣ እጀ ጠባብ ለሚጠይቅ መጎናጸፊያ የሚጨምር፣ ለአሳዳጅን የሚጸልይ ተሳዳቢን የሚመርቅ ነው፡፡ “ሁለት አሳብ ላለው በመንገዱም ለሚወላውል ለዚያ ሰው ከጌታ ዘንድ አንዳች እንዲያገኝ አይምሰለው” (ያዕ. 1÷8) ማስተዋል የድል ምስጢር ነውና እናንተ የምታስቡትን ናችሁ፡፡ ስለዚህ የጌታ አሳብ ይኑርባችሁ፡፡

ግብ፡-

ግብ የምንኖርበት ትልቅ ምክንያት ነው፡፡ አንድ መንገደኛ መንገድ የሚጀምርበት በቂ ምክንያቱ መድረስ የሚፈልግበት ቦታ አልያም ነገር ነው፡፡ መርካት የለጠውን እንድንፈልግ ካላደረገን እንቅፋትነቱ ይጎላል፡፡ ባለን ነገር የምንረካው ከማማረር ኑሮ እንድንድን እንጂ እንዳንተጋ አይደለም፡፡ ከፊቱ ግብ ያለው ሰው የጥረቱ ሁሉ ማብቂያ ያ ነው፡፡ የፊልጵስዩስ ምእራፍ ሦስት ዋና አሳብ “በኋላዬ ያለውን እየረሳሁ በፊቴ ያለውን ለመያዝ እዘረጋለሁ በክርስቶስ ኢየሱስ ከፍ ከፍ ያለውን የእግዚአብሔርን መጥራት ዋጋ እንዳገኝ ምልክትን እፈጥናለሁ” (ቁ. 13) የሚል ነው፡፡

        ክርስትና የዓላማ ኑሮ እንደመሆኑ ማንኛውም እውነተኛ አማኝ የሚፈጥንለት ግብ አለው፡፡ ስለዚህ እግዚአብሔር ለእኛ ወደወሰነው ግብ የመድረስ ኃላፊነት አለብን፡፡ ትጋታችን እንዴት ዓይነት መሆን እንደሚገባውም በሩጫ ተብራርቷል፡፡ እግዚአብሔር ባቀደልን መንገድ ወደ ግቡ የምንደርስ ከሆነ ሽልማትን እናገኛለን፡፡ ብድራታችንን ትኩር ብለን ማየት ግን የእድሜ ዘመን ተግባራችን ሊሆን ይገባል፡፡ (ዕብ. 11÷25) ቅዱስ አውግስጢኖስ “ጌታ ሆይ ነፍሴ አንተን አግኝታ እስካላረፈች አላርፍም” እንዳለ ወደ ምልክቱ መፍጠን ያስፈልጋል፡፡ (ሉቃ. 11÷30) በዚህም ላይ የእግዚአብሔርን መጥራት ዋጋ ልብ ልንል ይገባል፡፡ በውሳኔአችን ስንጨክን ውሳኔአችንን የምንጠብቅበት አሳብ ይኖረናል፡፡ ከፊታችን ደግሞ የምንሮጥለት ግብ ይኖረናል፡፡ ነገር ግን በዚህ ሁሉ ውስጥ የሰው አቅም ምን ያህል ነው? ማለት እንችላለን፡፡ በውሳኔአችን በአሳባችንና በግባችን መሐል ለተግባራዊነቱ የሚረዳን ኃይል ከየት እናገኛለን? “የእምነታችንንም ራስና ፈጻሚውን ኢየሱስን ተመልክተን በፊታችን ያለውን ሩጫ በትዕግሥት እንሩጥ” (ዕብ. 12÷1)፡፡

መቻል፡-

ውሳኔ መወሰናችንውሳኔያችንን የምናስጠብቅበት አሳብ መኖሩ ከፊት ለፊታችን የቆመ ግብ ማስቀመጣችን እነዚህ ሁሉ በራሳቸው ውጤት ሊሆኑ አይችሉም፡፡ እነዚህን ወደ ተግባር የምንለውጠው በመቻል (ተግባራዊ በማድረግ) ነው፡፡ የፊልጵስዩስ ምእራፍ አራት ዋና አሳብ ሁሉ ስለምንችልበት ኃይልና ምንጭ ይናገራል፡፡ “ኃይልን በሚሰጠኝ በክርስቶስ ሁሉን እችላለሁ” (ቁ.13)፡፡

           ኃይል አንድን ነገር ሊያንቀሳቅስ የሚችል ጉልበት ነው፡፡ የሰው አቅም ውሱን ነው መቻሉም የፈረቃ ነው፡፡ በክርስቶስ ምንጭነትና ሰጪነት ወደ ሕይወታችን የሚዘልቀው ኃይል ግን ሁሉን የሚያስችል ነው፡፡ ሁሉ ማለት ማንኛውንም ሁኔታ ማለት ነው፡፡ ይህ ኃይል ብርታቱን በሞት ላይ ገልጧ፡፡ አሁን በሞት የሚደነቅ የለም ሞትን ታግሎ በጣለው ጌታ ግን ገና ቀሪ ዘመናችንንም እንገረማለን፡፡ መቻል በትንሣኤው ኃይል መንቀሳቀስ ነው፡፡ ስላቃታችሁ ነገር አትማረሩ ስለሚችለው ጌታ አውሩ፣ ስለተዘጋባችሁ ደጅ አትበሳጩ የተከፈተውን በር ተመልከቱ፣ ሽንፈትን አታሰላስሉ ድልን ሊሰጥ በሚችለው ጌታ እመኑ፡፡ ሁለንተናችን ሆይ እናመሰግንሃለን!!












Tuesday, April 24, 2012

የኤልያስ ሽሽት



           መጽሐፍ ቅዱስ ስለ በረቱ ሰዎች ብቻ የሚናገር መጽሐፍ አይደለም፡፡ እግዚአብሔር የተጠቀመባቸውንም ሰዎች ድካም ያለመሸሸግ የሚያስነብበን ሚዛናዊ መጽሐፍ ነው፡፡ ስለ በረቱት ጉብዝና ስናነብ መዛል መድከም አለና አንታበይም፡፡ ስለተፍገመገሙት ስለወደቁት ስናነብ ደግሞ መቆም አለና ተስፋ አንቆርጥም፡፡ የእግዚአብሔር ቃል ሀብታም ነኝና ባለ ጠጋ ሆኛለሁ አንድም ስንኳ አያስፈልገኝም ለሚሉ ነገር ግን ጎስቋላና ምስኪን፣ ደሀና እውር የተራቆቱም መሆናቸውን ለማያውቁ የሕይወት ተላሎች ብርቱ ተግሳጽ ነው፡፡ ለመከራ የተፈጠሩ፣ ለፈተና የተበጁ፣ በመጨረሻው የውርደት ስፍራ ላይ የተጣሉ ለሚመስላቸው፣ ከችግር ወደበለጠ ችግር ለሚገላበጡ፣ የመሸ እንደማይነጋ፣ የመረረ እንደማይጥም፣ የጠመመ እንደማይቀና፣ ያጣ እንደማያገኝ የገዛ ልባቸው ለሚሰብክላቸው ደግሞ ቃሉ መጽናናት ነው፡፡

(In the very same revelation that shows us God, then, we see also His dealings with us- how He loves us, desires the best for us, sets forth His plan for us.)1

         በዚህ የሕይወት መጽሐፍ ታሪካቸው በማይዋሸው መንፈስ ቅዱስ ከተፃፈላቸው የእግዚአብሔር ሰዎች መካከል ካነሣነው ርእስ ጋር ሊሄድ የሚችለውን የኤልያስ ኑሮ እንዳስሳለን፡፡ (1ነገ. 18÷1) በእስራኤል ምድር ላይ ለሦስት ዓመት ከመንፈቅ ዝናብ ከተከለከለ በኋላ የእግዚአብሔር ድምጽ ወደ ኤልያስ “ ሂድ ለአክዓብ ተገለጥ በምድር ላይም ዝናብ እሰጣለሁ” ሲል መጣ፡፡ ሁለት አሳብ ላለው በመንገዱም ሁሉ ለሚወላውል ለዚያ ሰው ከጌታ ዘንድ አንዳች እንዲያገኝ አይምሰለው እንደተባለ የእስራኤል ልጆች በሁለት አሳብ ያነክሱ ስለነበር ነቢዩ ኤልያስ ሕዝቡ ከእግዚአብሔር አምላክነትና ከበኣል አምላክነት የሚበጃቸውን አስተውለው እንዲከተሉ አማረጣቸው፡፡ የእስራኤል ልጆች በኤልዛቤል ማዕድ የሚበሉ 450 የበኣል ነቢያት፣ ንጉሡ አክዓብ፣ 400 የማምለኪያው ዐጸድ ነቢያት፣ ራሱ ኤልያስን ጨምሮ ሁሉም በቀርሜሎስ (ፍሬያማ ቦታ) ተራራ ላይ ተሰበሰቡ፡፡ ኤልያስም በእነዚያ ሁሉ የበዓል አምላኪዎችና ነቢያት መሐል ለብቻው በእግዚአብሔር ስም ተገለጠ፡፡ ከበኣል የሆኑትም ሁሉ ለጣዖታቸው ወይፈኑን አሰናድተው ከማለዳ እስከ ቀትር ድረስ በአል ሆይ ስማን እያሉ ስሙን ይጠሩ ነበር፡፡ በታላቅ ቃል እየጮኹ ትንቢት እየተናገሩ ደማቸው እስኪፈስ ድረስ ገላቸውን በካራና በቀጭኔ ይብዋጭሩ ነበር፡፡ ነገር ግን የሚመልስ፣ የሚያደምጥም አልነበረም፡፡

          ኤልያስ ከመስዋዕተ ሠርክ በኋላ ማፈርን በተሞሉት የበኣል አምላኪዎች ፊት ሕዝቡን ሰብስቦ የእግዚአብሔርን መሠዊያ አበጀ፡፡ ወይፈኑንም በብልት በብልቱ ቆርጦ በእንጨቱ ርብራብ ላይ አኖረው፡፡ ከጣዖታቸው የእሳት ምላሽ ባጡት ሁሉ ፊት እንዲህ ሲል ጸለየ “አቤቱ የአብርሃምና የይስሐቅ የእስራኤልም አምላክ ሆይ አንተ በእስራኤል ላይ አምላክ እንደ ሆንህ እኔም ባሪያህ እንደ ሆንሁ ይህንም ሁሉ በቃልህ እንዳደረግሁ ዛሬ ይገለጥ፡፡” ከዚህ በኋላ የእግዚአብሔር እሳት ወደቀች መሥዋዕቱንም በላች፡፡ ሕዝቡም ሁሉ በግንባራቸው ተደፍተው እርሱ እግዚአብሔር አምላክ ነው አሉ፡፡ ኤልያስም የበኣልን ነቢያት ሁሉ በቂሶን ወንዝ ወስዶ አሳረዳቸው፡፡ እግዚአብሔርም የሰው እጅ ከምታህል ጥቂት ደመና ብዙ ዝናብን ለምድሪቱ ሰጠ፡፡ ኤልያስም በአክዓብ ሠረገላ ፊት ወገቡን አሸንፍጦ ይሮጥ ነበረ የእግዚአብሔርም እጅ በእርሱ ላይ ነበረች፡፡

         ከዚህ ሁሉ የእግዚአብሔር ሰው ድል በኋላ አክዓብ ወደ ቤተ መንግሥቱ ሲመለስ ለሚስቱ ለኤልዛቤል የሆነውን ሁሉ ነገራት፡፡ ኤልዛቤልም፡-ነገ በዚህ ጊዜ ነፍስህን ከእነዚህ እንደ አንዲቱ ባላደርጋት አማልክት ይህን ያድርጉብኝ ይህንም ይጨምሩብኝ ብላ ወደ ኤልያስ መልእክተኛ ላከች፡፡ ኤልያስም ነፍሱን ሊያድን አንድ ቀን የሚያህል መንገድ በምድረ በዳ ሄደ መጥቶም ከክትክታ ዛፍ በታች ተቀመጠና፡-ይበቃኛል አሁንም አቤቱ እኔ ከአባቶቼ አልበልጥምና ነፍሴን ውሰድ ብሎ እንዲሞት ለመነ (1ነገ. 19÷1-4)፡፡

         ከላይ ለማየት የሞከርነው የኤልያስ ታሪክ ለትምህርትና ለተግሳጽ ልብንም ለማቅናት የሚሆን ብዙ ቁም ነገሮችን የያዘ ነው፡፡ በዚህ ምድር ላይ የምናልፍባቸው ልዩ ልዩ ሁኔታዎች ለልባችን የሚሰጡት የተለያየ ትርጉም አለ፡፡ አንዳንዶቻችን ከመከራችን እንኳን መታዘዝን ስንማር ሌሎች ደግሞ እንኳን ከፈተናቸው ከምቾታቸውም ትርፋቸው አመጽ ይሆናል፡፡ አዳንዶች ከሕይወት ውጣ ውረድ ኑሮዬ ይበቃኛል ማለትን ሲማሩ ሌሎች ደግሞ ስለ ሥጋ በማሰብ እጣቸው ሞት ይሆናል፡፡ ከመከራችን ውስጥ ለሌሎች የሚተርፍ በረከት፣ ከሀዘናችን ውስጥ ለሌሎች የሚተርፍ ደስታ፣ ከመገፋታችን ውስጥ ለሌሎች የሚተርፍ ዕረፍት ይኖር ይሆን? በኑሮ ለሚያጋጥሙን ተግዳሮቶች የምንሰጠው ምላሽስ ምንድነው?  

        ኤልያስ በቀርሜሎስ ተራራ ላይ ከእምነት በሆነ ድፍረት ከእርሱ መንፈሳዊ አቋም ፍጹም ተቃራኒ በሆኑ ሰዎች ፊት በእግዚአብሔር ስም ቆመ ድልም ነሣ፡፡ ከኤልዛቤል ማስፈራሪያ በኋላ ግን ክትክታ (ፍሬ አልባ ጨፈቃ) ዛፍ ስር ተኝቶ ሞትን ለመነ፡፡ ነቢዩ በርሃብ ዘመን እግዚአብሔር በዮርዳኖስ ትይዩ በሚገኘው በኮራት ፈፋ ዋሻ ውስጥ ሸሽጎ ጠዋትና ማታ እንጀራና ሥጋ በቁራ እየላከ መግቦታል፣ ከማድጋ እፍኝ ዱቄት፣ ከማሰሮ ጥቂት ዘይት፣ ከመበለት ተስፋ መቁረጥ ውስጥ በልቶ መጥገብን፣ ቆርሶ ማትረፍን አሳይቶታል፡፡ በቀርሜሎስ ተራራ ላይም ለመሥዋዕቱ በእሳት በመመለስ በበቅሎና በፈረስ ለሞት በፈለጉት ንጉስና የበኣል ነቢያት ፊት አክብሮታል በዚያ ያለውንም ሕዝብ በእጁ አሳልፎ ሰጥቶአል፡፡ አሁን ግን ከሰማው የዛቻ ድምጽ የተነሣ ሞትን መፍትሔ አድርጓል፡፡ ሁላችንም ብንሆን ከዚህ የተለየን አይደለንም፡፡ ከእግዚአብሔር ብዙ ተውሎልን እንዳልተቀበልን በብዙ አውሎና ወጀብ ውስጥ መንገድ ሰጥቶ እንዳልተደረገልን ወደ ራሳችን መፍትሔና ተስፋ መቁረጥ መምጣታችን የሚያስደንቅ አይሆንም፡፡ ተስፋ መቁረጥ ሞትን መመኘት በአቋራጭ የመገላገል ፍላጎት የእኛ የግል ስሜት ብቻ አይደለም፡፡ እግዚአብሔር ኑሮአቸውንም ሞታቸውንም ለክብሩ የተጠቀመበት ብዙ የእግዚአብሔር ሰዎችም ይህንን የሸለቆና የምድረ በዳ ኑሮ ተለማምደዋል፡፡


የኤልያስ መፍትሔ፡-

1. ከሞት ወደ ሞት፡ - አስተውለነው ከሆነ ወደ ሕይወታችን ፈተና ሀዘን ጭንቀት ሲመጣ የእኛ መፍትሔ ከምንሸሸው የተሻለ አይደለም፡፡ ኤልያስ የኤልዛቤልን እገድልሃለው ሸሽቶ እግዚአብሔር ግደለኝ ወደሚል ስንፍና ነው የመጣው፡፡ እግዚአብሔር በኮራት ፈፋ ያደረገለት፣ በሲዶና አጠገብ በሰራፕታ ያዘጋጀለት፣ ቀርሜሎስ ላይ በእሳት የመለሰለት እንዲህ ባለው ፍርሃት ውስጥ ላለመውደቅ ከበቂ በላይ ነው፡፡ ነገር ግን ኤልያስ እንደ እኛው ሰው ነበር፡፡ (ያዕ. 5÷17)

        መራርነት በደጃችን ሲያደባ፣ አንደበታችንን እሮሮ ሲሞላው፣ ባላሰብነው መንገድ ባልጠበቅነው ሰዓት ችግር ደጃችንን ሲያንኳኳ ሞትን እንመኛለን፡፡ ነገር ግን እየሸሸነው ያለው ፈተና ቢበረታ ያው ራሱ ሞት ነው፡፡ ታዲያ ሰው እግዚአብሔርን ከዚህ ለተሻለ መፍትሔ ባይጋብዘው፣ ሁሉን ታደርግ ዘንድ ቻይ ነህ በሚል መንፈስ በጸሎትና በምልጃ ጉዳዩን ወደ እርሱ ባያቀርብ ምንኛ ምስኪን ነው፡፡ ጸብና ክርክርን ሸሽተው መጠጥ ውስጥ የሚደበቁ፣ ስርቆትን ሸሽቶ ነፍስ የሚያጠፉ፣ ከኪሳራ ፊት ሮጠው ዝሙት ውስጥ የሚደበቁ መፍትሄያቸው እንዴት ያስደምማል፡፡ እግዚአብሔርን የምንጠይቀው በፈተና ውስጥ ስንሆንስ እንዲያደርግልን የምንፈልገው ምንድነው? በእርግጥ የምንለምነው ነገር የእርሱን ክብርና ኃይል የሚገልጥ ነገር ነውን? አንተ ከእኔ ጋር ነህና ክፉውን አልፈራውም የሚል ነው? ወይስ ልዑልን መጠጊያው ያደረገ ሁሉን በሚችል አምላክ ጥላ ውስጥ ያድራል የሚል የዋስትና ቃል አለን? አልያም ደግሞ በአጠገቤ ሺ በቀኜም አስር ሺ ይወድቃሉ ወደ እኔ ግን አይቀርብም የሚል የእምነት አዋጅ ይኖረን ይሆን?ተወዳጆች ሆይ ችግራችሁን ሸሽታችሁ የት ነው ያላችሁት? የባሰ ችግር ውስጥ አልያስ በመጠበቂያችሁ ላይ ናችሁ? በአንዱ ፈተና ተማራችሁ ብዙ ፈተና እያመረታችሁ ይሆን? ከሞት ሸሽታችሁ የት ናችሁ?

2. ከቀርሜሎስ ወደ ክትክታ ስር፡- ሽሽት ከውድቀት በኋላ የታየ የሰው ቀዳሚ መፍትሄ ነው፡፡ አዳምና ሔዋን ባለመታዘዝ ኃጢአትን ከሠሩ በኋላ ያደረጉት ነገር መሸሽ ነው፡፡ ነገር ግን ከመንፈሱ ወዴት እንሄዳለን? ከፊቱስ ወዴት እንሸሻለን? በበረታ ቀትር (ፀሐይ) ሁላችንም ጥላ መፈለጋችን እሙን ነው፡፡ ለእኛ ግን ወደ እግዚአብሐር መቅረብ እንዲሻለን ማወቅ ግን ያስፈልገናል፡፡ ቅጠል ማገልደም፣ ከግንድ ጀርባ መሸሸግ፣ ምክንያት መደርደር እነዚህ ሁሉ የሰው መፍትሔዎች ናቸው፡፡ እግዚአብሔር ግን እንዲህ ካለው አሳብና መንገዳችን መንገዱ የተለየ አሳቡም የራቀ ነው፡፡  

         ኤልያስ ፍሬያማ ከሆነው ቀርሜሎስ ጨፈቃ ወደሆነው የክትክታ ምድረ በዳ ሸሸ፡፡ ያንን ከሚያህል ከፍታ እንዲህ ወዳለው ዝቅታ ወረደ፡፡ ኤልዛቤል፡-“ነፍስህን ከእነዚህ እንደ አንዲቱ ነፍስ ባላደርጋት”አለችው፡፡ እርሱ ደግሞ እግዚአብሔርን፡-“እኔ ከአባቶቼ አልበልጥምና ነፍሴን ውሰድ” ብሎ እንዲሞት ለመነው፡፡ የኤልያስ ልመና የእስራኤልን መጽናናት ይጠባበቅ እንደነበረው በኋላም በሰዎች ሁሉ ፊት እግዚአብሔር ያዘጋጀውን ማዳን እንዳየውና እንደቃልህ ባሪያህን አሰናብተኝ እንዳለው ስምዖን (ሉቃ.2÷29) አልያም ልሄድ ከክርስቶስ ጋርም ልኖር እናፍቃለሁ እዳለው ቅዱስ ጳውሎስ (ፊል. 1÷23) ያለ አይደለም፡፡ ይህ ዛቻ የወለደው ፍርሃት ያናገረው ነው፡፡ ተወዳጆች ሆይ የእኛስ መፍትሔ ከድጡ ወደ ማጡ አይነት ይሆን? ተራራው ላይ በብርታት ሸለቆ ላይ በዝለት ምን ያህል ጊዜ ተገኝተናል? እግዚአብሔርን ከማዳመጥ ራሳችንን ወደ ማዳመጥ ፈቀቅ ባልንበት ጊዜ ሁሉ የሚሆነው ይኼው ነው፡፡ እግዚአብሔር ግን አዋቂ ነው፡፡


የእግዚአብሔር መፍትሔ፡-

1. ከሞት ወደ ሕይወት፡- ከእድሜያችሁ ምን ያህል የቀራችሁ ይመስላችኋል? ከምንኖረው የኖርነው እንደሚበልጥ ባይካድም የፊቱን የሚያይልን ግን እግዚአብሔር ብቻ ነው፡፡ ኤልያስ ሞትን ሸሽቶ ከሞት የበለጠ ነገር ግን አለመነም፡፡ ከለመነው አብልጦ የሚሰጥ እግዚአብሔር ግን ነቢዩ ግደለኝን ሲያወራው ኑርልኝን ይነግረው ነበር፡፡ ኤልያስ ስላጠናቀቀው ስላከናወነው ነገር በእግዚአብሔር ፊት ሲያወራ እግዚአብሔር ግን ገና ስላልተጨረሰ መፈጸምም ስላለበት ሩቅ መንገድ ይነግረው ነበር፡፡

       ጌታ እንዴት ያለ ወዳጅ ነው፡፡ እስከ ሽምግልና ወደሚሸከመን እንጂ ወደ ሞት አንሸሽም፡፡ ከሸክማችን ወደሚያሳርፍ የዘላለም ሕይወት እንጂ ወደ ባዶ ተስፋ አንጠጋም፡፡ የእግዚአብሔር ልጅ (ልዑል)ሞታችንን ሞቶ መጠጊያ ሆኖናል፡፡ ከበደልና ከኃጢአታችን የተነሣ መተላለፍ ወደ ሞት ሲነዳን ቀራንዮ ላይ ሞታችንን ሞቶ ሕይወትን የሰጠን ጌታ ስሙ የተመሰገነ ይሁን፡፡ እግዚአብሔር የሞት መፍትሔ የለውም፡፡ እርሱ የሟቹን ሞት የማይፈልግ ትጉህ እረኛ ነው፡፡

2. ከሸለቆ ወደ ከፍታ፡- ወደ መቃብር እየሄድን በአብ ቀኝ ስፍራ እንደተዘጋጀልን የሰማንበት የምስራች ክርስቶስ ኢየሱስ ነው፡፡ ስለ እኛ ተዋርዶ ወደ ክብር ያሸጋገረን ወዳጅ ይህ ነው፡፡

“እርሱም ወደታች ወርውሩአት አለ ወረወሩአትም ደምዋም በግንቡና በፈረሶቹ ላይ ተረጨ ረገጡአትም” (2ነገ. 9÷33)፡፡ ዝናብ በተከለከለባቸው ዓመታት ሁሉ ኤልያስ በበቅሎና በፈረስ ለሞት ሲታሰስ ነበር፡፡ እግዚአብሔር ግን የማያስደፍር አጥር ነው፡፡ ጥቅሱ በኢዩ ትዕዛዝ ኤልዛቤል ከመስኮት ወደ መሬት ተወርውራ የሞተችበት ቃል ነው፡፡ ስለ ኤልያስ የተባለውን ደግሞ እንይ፡፡ “ሲሄዱም እያዘገሙም ሲጫወቱ እነሆ የእሳት ሠረገላና የእሳት ፈረሶች በመካከላቸው ገብተው ከፈሉአቸው ኤልያስም በአውሎ ነፋስ ወደ ሰማይ ወጣ” (2ነገ. 2÷11)::

          የእግዚአብሔር ቃል የኤልዛቤልን ውድቀት የኤልያስን ከፍታ ይነግረናል፡፡ ነቢዩ ለራሱ ያየው ሞት ነው የፊቱን የሚያውቅ እግዚአብሔር ያየለት ደግሞ ሕይወት ነው፡፡ እርሱ ክትክታ ስር ተኛ እግዚአብሔር ግን ለእርሱ ያዘጋጀው እረፍት ከፍታ ነበር፡፡ ኤልዛቤል ከከፍታው ስትንኮታኮት ኤልያስ ደግሞ ከሸለቆ ወደ ሰማይ ወጣ፡፡ ከቀርሜሎስ ተራራ እስከ ኢይዝራኤል ወገቡን አሸንፍጦ በአክዓብ ሠረገላ ፊት እንዳሮጠ አሁን በእሳት ሠረገላ ተወሰደ፡፡ እግዚአብሔር ባለ ጠጋ አይደለምን? ተወዳጆች ሆይ ጌታ ከሞት የተሻለ መፍትሔ አለው፡፡ ይህ ይታያችኋልን?ማስተዋል ይብዛልን!!

















     
_________________________________________________
1. The Orthodox Study Bible New Testament and Psalms, St. Athanasius Orthodox Academy, 1993, page 823, USA.

Friday, April 20, 2012

የጠወለጉ መንገደኞች


        ከሕይወት ትርጉም አንዱ ሕይወት ጉዞ ናት የሚለው ነው፡፡ የምንኖርበትን ዓለም በማስተዋል ከተመለከትነው ሁሉም ነገር በጉዞ ላይ ነው፡፡ በዚህ ዙሪያ ጥናት እያደረጉ እንደሆነ የሚታመንባቸው ምሁራንም በዚህ አሳብ መስማማታቸው ይነገራል፡፡ የእኛንም ሕይወት ስንቃኘው እውነታው ከዚህ የተለየ አይደለም፡፡ ትውልድ ይመጣል ትውልድ ይሄዳል፡፡ በዚህ ሂደት ውስጥ ግን ሰው ጉዞውን በአግባቡ እንዲያጠናቅቅ በቂ ዝግጅት አስፈላጊ ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ ጉዞው ፈታኝ ይሆንና ስንቅ ሊያልቅመዛል ሊከሰት መጠውለግ ሊመጣ ይችላል፡፡ በክርስትና ውስጥም የሚሆነው እንዲሁ ነው፡፡
         የእግዚአብሔርን ቃል እንሰማለን በሰማነው እናምናለን በዚህም በእውነት መሰረት ላይ እንተከላለን፡፡ ዕለት ዕለት ከዚሁ የሕይወት ቃል ጋር በሚኖረን የጠበቀ ሕብረት በመለምለም ራስ ወደ ሆነው ጌታ እናድጋለን፡፡ (ኤፌ. 4÷15) ሰው ከእግዚአብሔር አሳብና ከተሰጠው ተስፋ እየራቀከማመን እየዘገየ ሲሄድ መጠውለግ ይመጣል፡፡ ዓለም የምስራች የሰማው ሞት በሞት የተዋጠውመቃብር ባዶውን የታየው፣ የኃጢአት ዋጋ የተከፈለው፣ ጽድቃችን የታወጀው፣ የሰዱቃውያን እምነት ፉርሽ የሆነው፣ የክርስትናው ትልቅ ኃይል የተገለጠው ክርስቶስ ከሙታን መካከል ተለይቶ በመነሣቱ ነው፡፡ የክርስቶስ ትንሣኤ የእምነታችን መሰረትና ብርታት ነው፡፡ ኢየሱስ ከሙታን መካከል ተለይቶ ከተነሣ በኋላ ከደቀ መዛሙርቱ ሁለቱ ከኢየሩሳሌም ወደ ኤማሁስ እየሄዱ ስለሆነው ነገር ሁሉ እርስ በእርሳቸው እየተነጋገሩና እየመረመሩ በመንገድ ሳሉ ጌታ በመካከላቸው እንደተገኘ ወንጌላዊው ሉቃስ ጽፎልን እናነባለን፡፡ (ሉቃ. 24÷13-35) ኤማሁስ በኢየሩሳሌም አቅራቢያ የሚገኝ ከተማ ሲሆን ዛሬ ከኢየሩሳሌም በስተሰሜን ርቀው የሚገኙ ሦስት ከተሞች ቀድሞ ኤማሁስ በሚል ስያሜ በአንድነት ይጠሩ እንደነበር ይታሰባል፡፡ የቀለዮጳም ቤት በዚያው እንደነበር ይታመናል፡፡
          ከሰው ብርቱ መሻት አንዱ የፊቱን ቀድሞ ማወቅ ነው፡፡ ነገዎቻችንን ከሚያበላሹብን ነገሮች ምክንያቶች መሐል ስለ ነገ ቀድመን የማወቅ ፍላጎታችን (መጨነቃችን) ተጠቃሽ ነው፡፡ ጌታ ግን “ነገ ለራሱ ይጨነቃልና ለነገ አትጨነቁ” (ማቴ. 6÷34)” ይላል፡፡ ስላመለከትነው ጉዳይ አፈፃጸም፣ ስለጠየቅነው መሻታችን ምላሽ፣ ስላሳየነው ትጋት ውጤት ቀድመን ማወቅ የሚያስችል አቅም ባይኖረንም እንገምታለን፡፡ አንዳንዴም ከግምታችን በመነሣት ወደ ተግባር እንሸጋገራለን፡፡ እግዚአብሔር ግን አይገምትም ደግሞም አይገመትም፡፡ እርሱ ነገዎቻችንን ጠንቅቆ ያውቃል፡፡ ከተናገረው የሚቀር፣ ከወሰነው የሚዛነፍ፣ ከልኬቱ የሚጎልና የሚተርፍ የለም፡፡ በተለይ በመከራ ውስጥ ስናልፍ መፈተናችን ስፋትና ርዝማኔው ምን ያህል እንደሆነ ለማወቅ እንጓጓለን፡፡ እግዚአብሔር ግን ሁሉን ያውቃል፡፡
        ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ሁላችንም ኃጢአት በመስቀል ላይ ከመሞቱ አስቀድሞ አሥራ ሁለቱንም ደቀ መዛሙርት ወደ እርሱ አቅርቦ፡-“እነሆ ወደ ኢየሩሳሌም እንወጣለን ስለ ሰው ልጅም በነቢያት የተፃፈው ሁሉ ይፈጸማል፡፡ ለአሕዛብ አሳልፈው ይሰጡታልና ይዘብቱበትማል ያንገላቱትማል ይተፉበትማል ከገረፉትም በኋላ ይገድሉታል በሦስተኛውም ቀን ይነሣል (ሉቃ. 18÷34)” አላቸው፡፡ ወደ ፊት ሊሆን ያለውን አስቀድመው ማወቅ ለማይችሉት ደቀ መዛሙርት እንዲህ ያለው የኢየሱስ ንግግር ምንኛ ፍቅርን የተሞላ ነው? አዳምን በእርሱ መልክና (እውቀት፣ ጽድቅ፣ ቅድስና) ምሳሌ (ወኪል ገዥነት) ፈጥሮ በዔደን ገነት ካስቀመጠው በኋላ ከዚህ አትብላ ብቻ አላለውም፡፡ ይልቁንም መብላቱ (አለመታዘዝ) የሚያስከትለውንም ውጤት አብሮ ነገረው፡፡(ዘፍ. 2÷17) ወላጆች ብዙ ጊዜ ልጆቻቸውን እንዳያጠፉ እንጂ ጥፋታቸው የሚያስከትለውን ለመንገር ዝንጉዎች ናቸው፡፡ ትዕዛዛቸው እንጂ ቅጣታቸው በልብ የተሰወረ ነው፡፡
        ኢየሱስ ክርስቶስ ሊሆን ያለውን እስከ መጨረሻው ለወደዳቸው ተናገረ፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ግን ከነገራቸው ምንም አላስተዋሉም ከአፉ የወጣውም ቃል ተሰውሮባቸው ነበር፡፡ ይህንን አለመረዳታቸው ደግሞ ትንሣኤውን በጽናትና ከእምነት በሆነ ድፍረት እንዳይጠባበቁና ፈጥነው እንዳይቀበሉ መሰናክል ሆኖባቸዋል፡፡ ቀለዮጳ (Whom tradition identifies as the brother of Joseph, Mary's husband, and thus Jesus' uncle) እና ሉቃስ (The unnamed follower who, according to tradition, is the evangelist Luke himself)1 እኛ ግን እስራኤልን እንዲቤዥ ያለው እርሱ እንደሆነ ተስፋ አድርገን ነበርበማለት ተስፋ መቁረጣቸውን አንጸባርቀዋል፡፡ እግዚአብሔር በብርሃን የነገረንን በጨለማ፣ በፀጥታ ውስጥ የነገረንን በመከራ፣ በደስታ የነገረንን በሀዘን ውስጥ ከተጠራጠርነው ውጤቱ እየጠወለጉ መሄድ፣ ወደ ፊት (ኢየሩሳሌም) ሳይሆን ወደ ኋላ (ኤማሁስ) መመለስ ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ዳግም እንደሚመጣ ወዳዘጋጀልንም ስፍራ እንደሚወስደን የነገረንን ተስፋ ምን ያህሎቻችን በናፍቆትና በእርግጠኝነት እንጠባበቀው ይሆን? እነ ቀለዮጳ ተስፋቸው ስለተናደ እርስ በእርሳቸው የሚነጋገሩትና የሚመረምሩት ነገር ከመጠውለግ አልታደጋቸውም፡፡
         ሰው በተስፋው ከዛለ ምንም የሚያቆመው ነገር የለም፡፡ በጴጥሮስ ፊት አውራሪነት ደቀ መዛሙርቱ ሰው በማጥመድ ፈንታ ዓሣ ወደ ማጥመድ ተግባራቸው የተመለሱት ጌታ የሰጠውን የተስፋ ቃል ባለማስተዋልና ባለመጽናታቸው ጠንቅ ነው፡፡ (ዮሐ. 21÷1-14) ነገር ግን ሌሊቱን ሙሉ በመጠውለግ (በድካምና በሀዘን)አሳልፈዋል፡፡ አዝኖ መንገድ ምን ያህል አድካሚ ነው? የኤማሁስ መንገደኞች ወደ መቃብሩ ማልደው ስለሄዱና የጌታን ሥጋ ስላጡ “ሕያው ነው” የሚል የመላእክትን ራዕይ እንዳዩ፣ ከወንድሞችም መሐል ወደ መቃብሩ ሄደው የእህቶችን ቃል እውነተኛነት እንዳረጋገጡ ቀርቦ ለጠየቃቸው ጌታ አስረድተውታል፡፡ ነገር ግን የተስፋውን መፈጸም እንዳይቀበሉ አለማስተዋል ጋርዶባቸዋል፡፡ አለማስተዋል ደግሞ ከማመን አዘግይቶአቸዋል፡፡ ከማመን መዘግየት ደግሞ አጠውልጓቸዋል (ሀዘንና ምሬት)፡፡
እናንተ የማታስተውሉ + ልባችሁ ከማመን የዘገየ = እየጠወለጋችሁ ስትሄዱ
          የእኛ ድካም እግዚአብሔርን ከመሥራት አለመከልከሉ ለልባችን የዘወትር መደመም ነው፡፡ የእነርሱ መጠውለግ ታላቁ መምህር ከሙሴና ከነቢያት ጀምሮ ከታላቁ መጽሐፍ ታላላቅ ቁም ነገሮችን እያብራራ ብዙ በረከቶችን ወደ ሰዎች ልብ እንዲያደርስና እንዲተረጉም ምክንያት ሆኗል፡፡ ተወዳጆች ሆይ የትኛውም ድካማችን እግዚአብሔርን እንዳይሠራ አያግደውም፡፡“እርሱም፡-ጸጋዬ ይበቃሃል ኃይሌ በድካም ይፈጸማልና አለኝ፡፡ እንግዲሕ የክርስቶስ ኃይል ያድርብኝ ዘንድ በብዙ ደስታ በድካሜ ልመካ እወዳለሁ” (2ቆሮ. 12÷9)፡፡ ጌታ መጠውለጋችንን አለመጸየፉ፣ በድካማችንም አለመራቁ ምንኛ ድንቅ ነው? የእርሱ መገኘት መጠውለጋችንን ያለመልመዋል፡፡ እርሱ በእግዚአብሔርና በሕዝቡ ሁሉ ፊት በሥራና በቃል ብርቱ የሆነ ጌታ ነው፡፡ ቀለዮጳና ሉቃስ ጌታ ጭንካር ባለፈበት እጁ እንጀራውን ባርኮና ቆርሶ ሲሰጣቸው ትንሣኤና ሕይወት የሆነውን መድኃኒት አስተዋሉት፡፡ በመንገድም ሳሉ ከአፉ በሚወጣው የጸጋ ቃል ልባቸው ይቃጠል (ይነካ) እንደነበር አስታወሱ፡፡ በመጠውለግ ወጥተው በመለምለም ወደ ኢየሩሳሌም ተመለሱ፡፡

ለመለምለም፡-
1. ማስተዋል፡- ሰውን ከእንስሳ ጋር የሚያተካክለው ጠባይ አለማስተዋል ነው፡፡ ማስተዋል ያለመቻል ውጤቱ ደግሞ ጥፋት ነው፡፡ (ሆሴ. 4÷6) በፊታችን የተገለጠውን እውነት ካልተረዳነው ለነፍሳችን ጥቅም የሚሆን ነገር አይኖርም፡፡ ማስተዋል ንባብ ሳይሆን ትርጓሜ ነው፡፡ ስለዚህ መንፈሳዊ ሙቀት ልምላሜ እንዳይለየን ወደ ጥልቁ ፈቀቅ ማለት አለብን፡፡
2. ለማመን መፍጠን፡- ለብዙዎቻችን ከመሥራት ይልቅ ማመን ቀላል ነው፡፡ ለትሩፋት መሰረቱ ግን ጠንካራ እምነት ነው፡፡ የሰናፍጭ ቅንጣት ታህል እምነት ተራራን ማሸሽ ከቻለች ይህ እንዲኖረን መትጋት እንዴት ቀላል ሊሆን ይችላል? በተረዳነው የእግዚአብሔር ነገር ለማመን ቀጠሮ አይያዝም፡፡ ብዙ የተደከመባቸው የከበረውንም እውነት የሰሙ ነገር ግን በልዩ ልዩ ምክንያት ከማመን የዘገዩ ዛሬ ያመነቱበት ሐቅ ነገ በዘላለም ሸንጎ ፊት የሚያቆምም እንደሆነ አለማስተዋላቸው ልብን ያቆዝማል፡፡ ከእግዚአብሔርን ቃል ይበልጥ እየተረዳን በመጣን ቁጥር ከቃሉ ባለቤት ጋር የበለጠ ሕብረት ለማድረግ ጉጉታችን ይጨምራል፡፡ እምነት ደግሞ ለዚህ መሰረቱ ነው፡፡ ከማመን መዘግየት እየሄዱ መጠውለግን ያስከትላል፡፡
3. በተስፋ መጽናት፡- ተስፋ ተስፋ ያደረግነውን ስናገኘው የሚጠናቀቅ ነው፡፡ ጌታ በተዘጋው ደጅ አልፎ በመካከል በመቆም “ሰላም ለእናንተ ይሁን” በማለት የትንሣኤውን ተስፋ ፈጽሟል (ዮሐ.20÷19)፡፡ እሰቀላለሁ ብሎ የተሰቀለልን፣ ልሙትላችሁ ብሎ የሞተልን፣ እነሣለሁ እንዳለ በዝግ መቃብር በኃይልና በሥልጣን የተነሣ ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው፡፡ በኑሮአችንም የሚሆነው እንዲሁ ነው፡፡ እግዚአብሔር ካለው የሚስቀርብን ከከለከለንም የሚያደርግልን የለም፡፡ ሰይጣን ከብርታት ወደ መዛል የሚያደርሰን የተሰጠንን የተስፋ ቃል እንድንጠራጠረው በማድረግ ነው፡፡ ተወዳጆች ሆይ ጌታ የታመነ ነውና በተስፋ ጽኑ፡፡ ማስተዋል ይብዛልን!!














       

       











          1. St. Athanasius Orthodox Academy, The Orthodox Study Bible New Testament and Psalms,1993, Page 201, USA.

Wednesday, April 18, 2012

ፍቅር ጲላጦሳዊ



       አንዳንድ ሰዎች ፍቅር ልክ እንደ እቅፍ አበባ ለሌላው የሚሰጥ ነገር እንደሆነ ሲያስቡ ሌሎች ደግሞ በላይህ ላይ የተጣለ የማይረባ ግን ደግሞ የጠነከረ ኃይል ነው በማለት ይስማማሉ፡፡ ፍቅር ግን ልንሰጠው የምንችለው ማንኛውም ነገር አይደለም፡፡ ፍቅር ራሱ ሌሎች ነገሮችን እንድንሰጥ የሚያስችለን ከፍተኛ ግፊት ነው፡፡ ጥንካሬን፣ ኃይልን፣ ነፃነትንና ሰላምን ለሌሎች እንድንሰጥ የሚረዳን ጉልበት ነው፡፡ ከዚህ መንፈስ በመነሣት ፍቅር ውጤት ሳይሆን መንስኤ፣ ወራጅ ሳይሆን ምንጭ ነው ማለት ይቻላል፡፡ ስለዚህ በፍቅር የተነሣ የማንሰጥ ከሆነ፣ በፍቅር የተነሣ ይቅር የማንል ከሆነ፣ በፍቅር የተነሣ የማንራራ ከሆነ፣ በፍቅር የተነሣ ለእውነት የማንኖር ከሆነ በእኛ ያለው የፍቅር ኃይል ዋጋ የለውም አሊያም ሞቷል ማለት ነው፡፡

           የሰው ፍቅር ልዩ ልዩ ቢሆንም የእግዚአብሔር ፍቅር አንድ መሆኑ ዘመን የማይሽረው መጽናኛችን ነው፡፡ እግዚአብሔር እኛን እንዴት እንደወደደን መጽሐፍ ቅዱስ ሲናገር “እንዲሁም ዓለም አንተ እንደላከኝ በወደድከኝም መጠን እነርሱን እንደወደድካቸው ያውቃሉ” (ዮሐ. 17÷23) ይላል፡፡ እግዚአብሔር እኛን የወደደን ፃድቅ፣ የዋህና ትሁት የሆነውን እስከ መስቀል ሞትም የታዘዘውን አንድ ልጁን በወደደበት ፍቅር ነው፡፡ ለዚህም ነው እግዚአብሔር ሲወድ የሰውን ማንነት ታሳቢ አድርጎ አይደለም የምንለው፡፡ መልክና ቁመና ሀብትና ስነ ምግባርን ግምት ውስጥ በማስገባት አልያም ቅድመ ሁኔታ በማስቀመጥ ሰውን መውደድ የሰው ፍቅር ነው፡፡ አይነቱም ልዩ ልዩና ብዙ ነው፡፡ በዚህ ጽሑፍ ፍቅር ጲላጦሳዊን በመጠኑም ቢሆን ለማየት እንሞክራለን፡፡ ክርስቶስ በሥጋ ተገልጦ ወደ መስቀል በሚያደርገው ጉዞ ውስጥ ከምናስተውላቸው ሰዎች መሐል እንዱ ጲላጦስ ነው፡፡

         ጲላጦስ የጴንጤን አገር ሰው ሲሆን ከ26-36 ዓ.ም የነበረ የይሁዳ ገዥ ነው፡፡ በጭቆና የገዛና ብዙ ሰዎችን ያስገደለ እንደነበር እንዲሁም ከገሊላ ገዥ ከሄሮድስ ጋር እንደተጣላ እናውቃለን፡፡ (ሉቃ. 23÷12) ጲላጦስ በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ እንዲፈርድ አይሁድ በፊቱ ባቀረቡለት ጊዜ በቅንዓት እንደፈረዱበት ተረድቶ ነበር፡፡ ከዚህም በላይ የገዛ ሚስቱ በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ፍርድ እንዳያዛባ ውሳኔውንም እንዲያጤነው አስጠንቅቃዋለች፡፡ (ማቴ. 27÷18-19) ራሱ ጲላጦስ ስለ ክርስቶስ ንጽሕና ሦስት ጊዜ መስክሯል፡፡ (ሉቃ. 23÷4፡15፡22)

         ጲላጦስ የኢየሱስን መንፈሳዊ ሥልጣን ይፈራ ነበር፡፡ በመግረፍም ሊለቀው ሞክሮ ነበር፡፡ ኢየሱስ አንዳች ለሞት የሚያበቃ ወንጀል እንደሌለበትም ተገንዝቧል፡፡ ነገር ግን እጁን ታጥቦ ለሞት አሳልፎ ሰጠው፡፡ ጲላጦስ ላመነበት መጨከን ያቃተው ምስኪን፣  የቄሳር ወዳጅ ለመባል የሰማይና የምድር ንጉስ የሆነውን ጌታ ለነጣቂዎች የተወ ገዥ ነበር፡፡ ፍቅር ጲላጦሳዊ መልኩ እንዲህ ነው፡፡ ይታጠባል ግን የቆሸሸ ተግባር ይፈጽማል፡፡ በአፍ ስለ መልካምነታችሁ ያወራል ግን በወንበዴ መሐል ያሰቅላል፡፡ በአፍ ፍትሐዊ በተግባር ግን ፍትህ አጉዳይ ነው፡፡ ፍትሕ የሰው ልጆች ሁሉ ቋሚ ጥማት ነው፡፡ ለድህነት እንደ መንስኤ ከሚጠቀሱ ምክንያቶች አንዱ የፍትህ መጓደል ነው፡፡ ፍትሐዊ ያልሆነ የሐብት ክፍፍል፣ አድሎአዊ የሆነ የጥቅም ማጋራት ሂደት እነዚህን የመሳሰሉት ሁሉ ድህነትን የፍትህ መዛባት ውጤት ያደርጉታል፡፡ የፍቅር ትልቁ ጠባይ ፍትህ ነው፡፡ ፍቅር ጲላጦሳዊ፡-

1. ፍትህን ያዛባ ነው፡- ሕሊና ስውር ፍትሃዊ ዳኛ ነው፡፡ እግዚአብሔርን የምንመስልበት ትልቁ ጠባይ ደግሞ ማስተዋላችን ነው፡፡ ነገር ግን የሰውን ሕሊና ሐሰት ሲጠመዝዘው ፍትህ ይዛባል፣ ፍርድም ይጓደላል፡፡ ገጣሚው፡-
እውነት ቤት ሥትሠራ
ውሸት ላግዝ ካለች
ጭቃ ከለሰነች
ሚስማር ካቀበለች
ቤቱም አልተሠራ
እውነትም አልኖረች፡፡

        ፍቅር ለፍትህ የሚኖርና ለእውነት የሚሞት ነው፡፡ ጲላጦስ ለእውነት ቢፈርድ ወንበሩን ያጣ፣ የቄሳር ወዳጅነት ይቀር፣ የሕዝቡን ጥላቻ ይጋፈጥ ይሆናል፡፡ ነገር ግን ሕሊናውንና ትልቅ ወዳጅ እግዚአብሔርን ያተርፍ ነበር፡፡ ሰው ኖሮ ኖሮ እግዚአብሔርን ካላተረፈ ሁሉስ ምን ይረባዋል? ተወዳጆች ሆይ ፍትሃዊነት እግዚአብሔርን የምንመስልበት መንገድ ስለሆነ ፍቅራችን ለፍትህ የቆመ ደግሞም የቆረጠ ሊሆን ይገባል፡፡ ጲላጦስ ንጹሁን ጌታ ለሞት አሳልፎ ሰጥቶ ወንጀለኛና ኃጢአተኛውን በርባንን የለቀቀ ነው፡፡ ፍቅራችን ፍትህን ያልበደለ፣ እውነትን ያልደለለ ይሁን፡፡

2. ግብዝ ነው፡- ጲላጦስ አደባባይ ላይ እጁን ታጥቦ ከደሙ ንጹሕ ነኝ አለ፡፡ የእግዚአብሔርን ልጅ ግን ለመስቀል ሞት አሳልፎ ሰጥቶታል፡፡ ይህ ምንኛ የሚገርም ግብዝነት ነው፡፡ እጁን ቢታጠብም ልቡ ከአመጽ አልጸዳም ነበር፡፡ ቃሉ፡-“ፍቅራችሁ ያለ ግብዝነት ይሁን” (ሮሜ. 12÷9) ይላል፡፡ ግብዝነት የምናወራውን አለመኖር ነው፡፡ ከደሙ ንጹህ መሆኑን አፍአዊ በሆነ መንገድ ቢናገርም በተግባር የገለጠበት ሁኔታ ግን የሰነፍ ብልሃት ነበር፡፡ በአፍ መርቆ በልብ እንደ መሸርደድ ያለ ነው፡፡

           ለብዙዎቻችን ማስመሰል የመሆን ማካካሻ አልያም ለድካማችን ዋሻ ነው፡፡እግዚአብሔር ግን ካስመሰልነው ብዙ በሆነው ጥቂት ይከብራል፡፡ ሚስቱ ላይ ወንበር ሰባብሮባት፣  ልጁንም እኩለ ሌሊት ከቤት አስወጥቶ ሸምጋይ ፊት ሲቆም “ይህንን ያደረኩት ሚስቴንና ልጄን ስለምወድ ነው” ብሎ ቢናገር አትደነቁምን? ፍቅራችን ያለ ግብዝነት ይሁን፡፡

3. ዋጋ አይከፍልም፡- ለእውነት ዋጋ ሳይከፍሉ እውነተኛ፣ ለፍቅር ዋጋ ሳይከፍሉ አፍቃሪ፣ ለፍትህ ዋጋ ሳይከፍሉ ፍትሃዊ፣ ለወንጌል ዋጋ ሳይከፍሉ አገልጋይ የመባል ፍላጎት በእጁጉ የሚስተዋልበት ዘመን ላይ ደርሰናል፡፡ ፍቅር ጲላጦሳዊ የተጠናወታቸው ለእውነት ሳይሆን ለአብላጫ ጩኸት የተሸነፉ ናቸው፡፡ ሞት ባይገባችሁም ለሞት አሳልፈው ይሰጥዋችኋል፡፡ ጲላጦስ ክርስቶስ አንዳች በደል እንደሌለበት እየመሰከረ ክርስቶስን ደግሞ ልሰቅልህ ወይንም ልፈታህ ሥልጣን እንዳለኝ አታውቅምን? ይለው ነበር፡፡

      ሁሉም ሰው ዋጋ የማያስከፍል ኑሮ፣ ወዳጅነት፣ ትዳር፣ አገልግሎት፣ ትምህርት ይፈልጋል፡፡ ሕይወት ደግሞ በዚህ መንገድ ወደ ከፍታን ስኬት፣ ወደ በረከትና ድል መድረስ አታስችልም፡፡ ፍቅር ላይ የጨከኑ፣  እውነት ላይ የቆረጡ እነርሱ አሸናፊዎች ናቸው፡፡ ዛሬ ላለንበት ሁኔታ ባለፈው ጊዜ፣ ትውልድ፣ ቤተሰብ ምን ያህል ዋጋ ተከፍሏል? ከበደል በኋላ የሰው ሕይወት ዋጋ በመክፈል (በመስዋዕትነት) ላይ የተመሰረተ ነው፡፡ ጲላጦስ ለተረዳው እውነት ያልጨከነ ነበር፡፡ እኛም በክርስቶስ ነገር በወንጌል ጉዳይ ልባችን እንዲጨክን ጌታ ይርዳን፡፡ ክርስቶስ ተነሥቷል መቃብሩም ባዶ ነው!!!
                                                           





Friday, April 13, 2012

ታርዶልሃል



ታርዶልሃልና በጉ
ተሰጥቶሃል የመግቢያ ካርዱ
ወደ ትልቅ ግብዣ ወደ ሠርጉ
ቤዛ ከኃጢአት መዋጃ
ምትክ ለበደላችን ካሳ
የተትረፈረፈ መከር
የማይጎድል ጥጋብ
ሆኗልና በጉ
በሐሴት በእልልታ ግባ ወደ ሠርጉ
ሸክም ጭነት ተራግፎልህ
የሞት መውጊያው ተሰብሮልህ
ተዘልለህ እንደ ዘሩባቤል
መኖሪያህ እንዲደላደል
ኪዳንህን አጽና በደሙ
ሞት ተደምስሷል በስሙ፡፡
                              - ካንባቢ -

የጌልገላው ባልጩት



            የእስራኤል ልጆች ዮርዳኖስን ከተሻገሩ በኋላ እግዚአብሔር ኢያሱን አንድ ነገር አዘዘው፡፡ ይኸውም የእስራኤልን ልጆች ሁለተኛ ጊዜ በባልጩት እንዲገርዛቸው ነው፡፡ (ኢያ. 5÷2-10) እስራኤላውያን ከግብጽ ከወጡ በኋላ እንደተገረዙ ነገር ግን በምድረ በዳው ጉዞ ባለመታዘዛቸው ጠንቅ እንደተቀሰፉ እንረዳለን፡፡ በዚህም እግዚአብሔር ጉዳዩ ከሥጋቸው ሸለፈት ጋር ሳይሆን ከልብ መገረዝና ስነ ምግባራዊ ከሆነው ነገር ጋር እንደሆነ መረዳት እንችላለን፡፡ ምክንያቱም ያ ሕዝብ ግብጽን ጥሎ ቢወጣም መገረዝን ቢፈጽሙም የግብፅ ነውርና እርም ግን ከልባቸው አልወጣም ነበር፡፡ ስፍራውን ለቀው ነበር የግብጽ ጠባይ ግን ከልባቸው ላይ ስፍራ አለቀቀም ነበር፡፡ ስለዚህ ሕዝቡ ከሕጉ አንፃር ይዳኝ ስለነበር ደግሞም እግዚአብሔር መንግስት በመሆኑና ኃጢአትን መቅጣት ስላለበት ሕዝቡ ምድረ በዳ ቀርተዋል፡፡ አሁን ግን እንደምናየው እግዚአብሔር ልጆቻቸው በጌልገላ ተራራ ላይ በባልጩት እንዲገርኣቸው ኢያሱን ያዛል፡፡ ጌልገላ በኢያሪኮና በዮርዳኖስ መካከል ያለ ስፍራ ሲሆን የስያሜው ትርጉም ማንከባለያ ማለት ነው፡፡ የእስራኤል ልጆች በመንገድ ሳሉ ሸለፈታሞች ስለነበሩ ፈጽመው መገረዝ ነበረባቸው፡፡ ስለዚህ ኢያሱ የተባለውን ሁሉ አደረገ፡፡ እግዚአብሔርም ኢያሱን፡-ዛሬ የግብፅን ነውር ከእናንተ ላይ አንከባልያለሁ አለው፡፡
            የእስራኤል ልጆች በጌልገላ የግብፅን ሸለፈት በመገረዝ ኮረብታ በባልጩት (ስለታም ድንጋይ ሲሆን በአገራችን የሰማይ ድንጋይ ይባላል) ካሶገዱ በኋላ በኢያሪኮ ሜዳ ላይ ፋሲካ አደረጉ፡፡ የእስራኤል ልጆች አባቶቻቸው ከግብፅ ሲወጡ በቤታቸው መቃንና ጉበን ላይ የበጉን ደም ከመቀባታቸው የተነሣ ሞት በደጃቸው አለፈ፡፡ ከእያንዳንዱ ግብፃዊ ቤት ሬሣ ሲጎተት የእስራኤል ቤቶች ግን በሕይወት ነበሩ፡፡ ለጠላቶቻቸው ሲጨልም ለእነርሱ ግን ብርሃን ነበር፡፡ በጠላቶቻቸው ደጅ እንባ እንደ ጅረት ሲፈስ በእነርሱ ቤት ግን ሰላምና ደስታ ነበር፡፡ የእስራኤል ልጆች እንዲህ ያለውን በዋጋ የማይተመን የሕያው እግዚአብሔር ውለታ የዘከሩት የግብፅን ነውርና ሸለፈት በማስወገድ ነው፡፡ ወላጆቻቸው ከግብፅ ሲወጡ ተገርዘው ነበር፡፡ ነገር ግን የእግዚአብሔርን ቃል ባለመስማታቸው ለአባቶቻቸው የማለላቸውን ምድር እንዳያሳያቸው እግዚአብሔር ማለ፡፡ አሁን ግን እግዚአብሔር በጌልገላው ባልጩት የልጆቻቸውን ሸለፈት ጣለ ከግብፅ ተጽእኖና ነውር አሳረፋቸው፡፡ በዚህም ሸክም መቅለልና ዕረፍት ውስጥ ሆነው ፋሲካውን አከበሩ፡፡
           በአዲስ ኪዳን የእግዚአብሔር ቃል “ፋሲካችን ክርስቶስ ታርዷልና እንግዲህ ያለ እርሾ እንዳላችሁ አዲሱን ሊጥ ትሆኑ ዘንድ አሮጌውን እርሾ አስወግዱ” ይላል፡፡ ከላይ ለማየት ከሞከርነው የብሉይ ኪዳን ታሪክ አንፃር እኛስ ፋሲካችን ክርስቶስን እንዴት ነው የምናከብረው? የማለፍን በዓል፣ ከድቅድቅ ጨለማ ወደሚደነቅ ብርሃን የመምጣትን በዓል፣ ከሰማያዊው ጥሪ ተካፋይ የመሆንን በዓል፣ የመንግስት ልጆች የመባልን በዓል እንዴት ነው የምናስበው? ቃሉ ግን “እንግዲህ በምድር ያሉ ብልቶቻችሁን ግደሉ÷ እነዚህም ዝሙትና ርኩሰት ፍትወትም ክፉ ምኞትም ጣዖትንም ማምለክ የሆነ መጎምጀት ነው” (ቆላ. 3÷5-11) ይላል፡፡
           ከፋሲካው በፊት በአንድ እውነተኛ ክርስቲያን ሕይወት ውስጥ ሊታሰብበትና ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባ ጉዳይ ይህ ነው፡፡ የመድኃኒዓለም ፈቃድና ደስታም በዚህ ይፈፀማል፡፡ በምድራዊ ብልቶቻችን ላይ የሰለጠነውን የግብፅን ነውርና ሸለፈት በቃሉ ባልጩትነት (የመንፈስ ሰይፍ) ቆርጠን ፋሲካውን ውስጣዊ በሆነ እርካታና ዕረፍት ብናከብረው ለነፍሳችን ትርጉም ይኖረዋል፡፡ ጎሎጎታ ኃጢአታችንን የምንጥልበት፣ ሸክም የሚቀልበት ነው፡፡ እርሱ ደዌያችንን ስለ ተቀበለ፣ ስለ መተላለፋችን ስለ ቆሰለ፣ ስለ በደላችን ስለደቀቀ በእርሱ መቁሰል ተፈውሰናል፡፡ ተወዳጆች ሆይ በምድር ያሉ ብልቶቻችንን ማለትም ዝሙትና ፍትወት፣ ክፉ ምኞትና ርኩሰት እነዚህን የመሳሰሉትን ለማሶገድ ምን ያህል ቆራጦች ነን? ምክንያቱም ሸለፈት ላይ ባልጩት ማሳረፍ መጨከንን ይጠይቃል፡፡ የክርስቶስ መከራና መስቀል ለዚህ ብርቱ ኃይል ነው፡፡ ኃጢአት የእግዚአብሔርን አንድያ ልጅ ለሞት ተላልፎ እንዲሰጥ ያደረገ መሆኑን ከተረዳን በእኛ አመለካከት ጥቂት የምንላት በደል እንኳን ክርስቶስን መስቀል ላይ እንዲቸነከር እንዳደረገው ከገባን በእርግጥም ፋሲካችን ነውርን በማከባለል ይሆናል፡፡ “አጥፊው የበኩሮችን ልጆች እንዳይነካ ፋሲካንና ደምን መርጨትን በእምነት አደረገ” (ዕብ. 11÷28)፡፡ ጌታ ሆይ ሞት ከደምህ የተነሣ አልፎናልና መንግስትህ ይባረክ!!

Thursday, April 12, 2012

የኃጢአተኞች ወዳጅ




          እግዚአብሔር ስሙን እንዲቀድስ ክብሩን እንዲወርስ በጽድቅ የፈጠረው ሰው ፈቅዶ ኃጢአተኛ ቢሆንበት እውነትና ምሕረቱን ጽድቅና ሰላሙን አስማምቶ በማዳን ዳግመኛ የራሱ ሊያደርገን ወደደ፡፡ እግዚአብሔር ሰውን በአርአያውና በምሳሌው ፈጠረው አዳም ከውድቀት በኋላ በመልኩና በምሳሌው ልጅ ወለደ ኃጢአተኝነትም በዚህ መንገድ ለሰው ሁሉ ደረሰ፡፡ (ዘፍ. 5÷3) እግዚአብሔር አብ ለበደለ ሰው የሚወደውን አንድያ ልጁን ወደ ዓለም ሰደደ፡፡ እርሱም በሰው መካከል በመገለጥ በሞት ላይ ስልጣን ያለውን ዲያቢሎስ በሞት እንዲሽር በሕይወታቸውም ሁሉ ስለ ሞት ፍርሃት በባርነት ይታሰሩ የነበሩትን ሁሉ ነፃ እንዲያወጣ በሥጋና በደም እንዲሁ ተካፈለ፡፡ (ዕብ. 2÷14) መዳን የሚጠይቀውን ሁሉ ዋጋ ለመክፈል አንዱ ስለ ሁሉ ሊሞት ሞትን ዓላማ እኛን አድራሻ አድርጎ መጣ፡፡     
“የሰው ልጅ እየበላና እየጠጣ መጥቶአልና፡- እነሆ በላተኛና የወይን ጠጅ ጠጭ ÷ የቀራጮችና የኃጢአተኞች ወዳጅ አላችሁት፡፡ (ሉቃ. 7÷34)”

          የጉንዳን መንጋ ላይ ቆሞ የሰፈሩበትን ጉንዳኖች እንደሚያራግፍ ምስኪን ሰው ኃጢአትን በልቡ ሞትንም በጀርባው ተሸክሞ ለዘመናት ከኩነኔ በታች ለተንከራተተው ጽድቁ እንኳ እንደ መርገም ጨርቅ ለተቆጠረቅ የሰው ዘር በክርስቶስ በምጣት ታላቅ የምስራች ሆነ፡፡ ተገለጠ፡፡ በአንዱ በእግዚአብሔር ልጅ ለሚያምኑ ሁሉ በእርሱ በማመን የሚገኘው በሕግና በነቢያት የተመሰከረለት የእግዚአብሔር ጽድቅ ያለ ሕግ ተገልጧል፡፡ በነፍስ በሥጋ በመንፈስም ለታሰሩት መፈታት፣ ለዕውሮች ማየት፣ ለተጠቁት ነፃ መውጣት፣ ለድሆችም የወንጌል መሰበክ በክርስቶስ ሰው መሆን የሆነ ነው፡፡ በገነት ሰውን የተሸሸገበት ድረስ ሄዶ ወዴት ነህ? በማለት የሕይወትን ጥሪ ያሰማ አምላክ (የሸሸነው ጽድቅ) ያለንበት ድረስ መጣ፡፡ በበደልና በኃጢአታችን ሙታን የሆንነውን በማይለካ ፍቅሩ ወደደን፡፡

         በመዳፍህ የያዝከው ዕንቁ ከእጅህ ወጥቶ ጭቃ ውስጥ ወደቀ፡፡ ጭቃውን ብትጠላውም ለዕንቁው ያለህ ፍቅር ግን አይቀንስም፡፡ ስለዚህ አንጽተህ ዳግም የራስህ ልታደርገው ንጹሕ ለመሆን የሚጠይቀውን ሁሉ ዋጋ ትከፍላለህ፡፡ ካሉት መቶ በጎች የባዘነውን አንዱ ፍለጋ ዘጠና ዘጠኙን ትቶ እንደተሰማራ ባገኘውም ጊዜ ካልባዘኑት ይልቅ በአንዱ መገኘት ደስ እንደሚሰኝ መልካም እረኛ ክርስቶስ በቃል ከሚሰማው ነቀፋ በተግባር እስከሚታየው መከራ ሁሉን ስለ እኛ ሲል ተቀበለ፣ ለመዳንም የሚያስፈልገውን ሁሉ ዋጋ መስቀል ላይ ከፈለ፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋና በደም አቋም በዚህ ምድር በተመላለሰበት ወራት የሞት ቀንበር ለከበደበት፣ የኃጢአት ሸክም ለሚያንገዳግደው የሰው ዘር ባሳየው ርኅራኄ፣ በለገሰው የማይነጥፍ ፍቅር የኃጢአተኞች ወዳጅ ተብሏል፡፡ ሕሙማን (ኃጢአተኛ) እንደሆኑ ለሚያምኑ ሁሉ ክርስቶስ መድኃኒት ነው፡፡ አይሁድና ፈሪሳውያን ግን ከዘላለም ሞት ሊያድን የመጣውን ጌታ የኃጢአተኖች ወዳጅ፣ የግፉአን ባልንጀራ እያሉ ያሙት ነበር፡፡ መልካም መሆናችን ላለመታማት ዋስትና የለውም፡፡ በጎነታቸው በክፋት እየተመዘነ፣ መውደዳቸው የጥላቻን ያህል ዋጋ እየጠነፈገ፣ እንደ ማር የጣፈጠ ንግግራቸው ሕይወት የሆነ ምክራቸው እንደ ሬት እየተቆጠረ ኖረው ያለፉ እውነተኞችን ታሪክ ያስታውሰናል፡፡ ጌታም የጥላቻ ጉልበት ያደቀቃቸውን፣ የገዛ ነውራቸው ያሳፈራቸውን፣ የሰው ፊት የገፋቸውን በልቡ ተቀብሎ በቤታቸው ስለተስተናገደ ክፉዎች በጎውን ያሙት ነበር፡፡

            ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ሰዎች በጻፈው መልዕክቱ “አሳቾች ስንባል እውነተኞች ነን ያልታወቁ ስንባል የታወቅን ነን የምንሞት ስንመስል እነሆ ሕያዋን ነን” (2ቆሮ. 6÷9) ይላል፡፡ የብዙዎቻችን ጥረት ክፉ ላለመሆን ሳይሆን ክፉ ላለመባል ነው፡፡ ስለዚህ ሌሎች ስላሉን እንጂ ስለሆነው፣ ስለሚወራብን እንጂ ልባችን ስለሚያወራልን ግድ አይለንም፡፡ በመባልና በመሆን መካከል ግን ሰፊ ልዩነት አለ፡፡ ሰዎች እኛን በሚያሙበት ክፉ ነገር ውስጥ አለመገኘት በመልካም መታማት ነው፡፡ መርቆ መረገም፣ ወድዶ መጠላት፣ አቅፎ መገፋት፣ አጉርሶ መነከስ፣ በጎ ውሎ መሰደድ የክርስቲያን ክብሩ ነው፡፡ ክርስቶስም በመልካምነቱ ታምቶአል፡፡ ሐዋርያው በጊዜው ሰዎች ስለሚሉትና እርሱ ስለሚኖረው ኑሮ ሲያስረዳ አሳቾች ይሉናል እውነተኞች ነን፣ ያልታወቁ ይሉናል የታወቅን ነን በማለት ኑሮውንና ሐሜታውን ለይቶ ያሳየናል፡፡ ተወዳጆች ሆይ እኛ ስንባል ስንታማ ምን ዓይነት ሰዎች ነን? ንፉግ ስንባል ለጋስ፣ ክፉ ስንባል ደግ፣ ጠላት ስንባል ወዳጅ ነን ወይ? ሰዎች እኛን በሚያሙበት ነገር ውስጥ ከተገኘን ችግሩ ያለው እነርሱ ጋር ሳይሆን እኛ ጋር ነውና አካሄዳችንን ማስተካከል አለብን፡፡ ከዚህ ውጪ ከሰው ለሚመጣው ማንኛውም ሀሜትና ወቀሳ ይልቅ እግዚአብሔር ስለ እኛ በሚለው ነገር ላይ ማረፍ አለብን፡፡ በሕይወት ትልቁ ቁም ነገር ሌሎች ስለ እኛ የሚሉት ሳይሆን እግዚአብሔር የሚለው ነው፡፡

          ኃጢአተኛ እንደሆናችሁ ለሚሰማችሁ ሁሉ ጌታን የሚያህል ወዳጅ አላችሁና ከሞት ጋር የጀመራችሁትን ግብግብ አቁሙ፡፡ በደጃችሁ ቆሞ ለሚያንኳኳውም በመክፈት ምላሽ ስጡ፡፡ ሕሙማንን ሊፈውስ የእግዚአብሔር ልጅ በውርደት ተገልጧል፡፡ ከተለያየ ክፉ ልማድና ዓለማዊ አሠራር መላቀቅ ያቃታችሁ እናንተን ከዚህ የሚታደግ መድኃኒት ተገልጧልና በዚህ ደስ ይበላችሁ፡፡ የኑሮ ቀንበር የነውር ሸክም የከበደባችሁ ልባችሁን መሰላቸት የሞላው ሁሉ ነገር የማይታኘክ መራራ የሆነባችሁ እናንተን ሊያሳርፍ የኃጢአተኞች ወዳጅ የሆነ ጽድቅ ተገኝቷልና በእምነት ቅረቡ፡፡ ጌታ ሆይ ለፍቅርህ ተመን ልኬት የለውምና አንተ በምታውቀው መጠን ተመስገን!!!         

Wednesday, April 11, 2012

ሰነፍ እርቅ




         ሐይቅ እስጢፋኖስ (ኢየሱስ ሞዓ) አካባቢ ከገዳሙ ትንሽ ራቅ ብሎ ለመጀመሪያ ጊዜ የሰማሁት ነው፡፡ ለብዙዎቻችሁም አዲስ ሊሆን እንደሚችል እገምታለሁ፡፡ አገራችን የመፈቃቀር፣ አብሮ የመብላት፣ እንግዳ የመቀበል ታሪክ ብቻ ያላት አይደለችም፡፡ ደም የመቃባት፣ የገዛ ወገንን ገሎ የመሸለል፣ አቂሞ ለበቀል ዱር የመሸፈትም ታሪክ የተሸከመች ናት፡፡ ስለ ፍቅር አብዝቶ በሚነገርበት፣ አብሮ መኖርና መደጋገፍ እንደ ስልጣኔ በሚቆጠርበት ዓለም ዛሬም ድረስ በሞት የሚፈላለ፣ጉ ለጥፋት የተሰማሩ መኖራቸውን ማስተዋል እጅጉን ለልብ ሀዘን ነው፡፡

       
  አካባቢው ላይ በተገኘንበት ወቅት አንድ ሰው ተገድሎ ፀጥታ አስከባሪዎች ስፍራውን በብርቱ ይጠብቃሉ፡፡ ከመጠየቅ እንደተረዳነው ምክንያቱ የሟች ቤተሰቦች የገዳይን ወገን እንዳይገሉ ለመጠበቅ መሆኑን ተረዳን፡፡ በአንድ ሰው ስህተት ሙሉ ቤተሰብ መጨነቁ፣ ነፃነት አጥቶ የቤት ውስጥ እስረኛ መሆኑ፣ በሞትኩ አልሞትኩ ሥጋት መሸበሩ እንኳን ለባለቤቶቹ ለታዛቢውም የሚጨንቅ ነበር፡፡ ማኅበረሰቡ ግን አብሮት እንዳደገ የቤት እንስሳ በጉዳዩ አለመገረሙ ያስገርም ነበር፡፡ እኛም ያለበደሉ ሞት በደጁ የሚያደባበትን ቤተሰብ ሊታደግ የሚችለው መፍትሔ ምንድነው? በማለት ጠየቅን፡፡ የተሰጠን መልስ ግን ለሌላ ጥያቄ የሚጋብዝ ነበር “የሰነፍ እርቅ”፡፡ እንደተነገረን ከሆነ የሰነፍ እርቅ ማለት ገዳይ በሕግ ጥላ ስር ከሆነ በኋላ ጉዳዩ በፍርድ ቤት እየታየ በዚህ መሐል የገዳይ ቤተሰቦች በሟች ወገን ጥቃት (ግድያ) እንዳይደርስባቸው ለጊዜው የሚደረግ መገላገያ ነው፡፡ ስለ ዋስትናው የጠየቅናቸው አባት እንደነገሩን “በሰነፍ እርቅ አስገደለኝ” የሚባል አባባል እንዳለ ጠቅሰው የሟች ቤተሰብ እርቁን ሊያፈርስ፣ የገዳይን ቤተሰብ ሊገድል እንደሚችልና በብዛት እንዲህ ያለው ነገር ሲከሰት እንደሚስተዋል አስረድተውናል፡፡ በማከልም የሟች ቤተሰብ ውሉን አፍርሶ ቢገኝ በሕብረተሰቡ ዘንድ ነውር እንደሆነ ነግረውናል፡፡ ከዚህም ጋር አያይዘው ልብን የሚነካ ታሪክ ማለትም የሰነፍ እርቅ ከተደረገ በኋላ ስለሞተ ሰው አጫውተውናል፡፡ ብዙ ጊዜ የሰነፍ እርቅ ሲከናወን ካሳ ስለማይካስና ሽምግልናው ገዳይ ተገኝቶ መጸጸቱን የማያሳይበት በመሆኑ ዘላቂነቱ አጠራጣሪ እንደሆነም መረዳት ችለናል፡፡

          ደም በደም፣ ወንጀል በበለጠ ወንጀል፣ ቅያሜ በከፋ በቀል የሚመለስበት አገር ላይ እየኖርን መሆኑን ማወቃችን ምን ያህል በጸሎት መትጋት እንዳለብን የሚጠቁም ይመስለኛል፡፡ አንዱ በዘራው ሌላው እያጨደ፣ አንዱ በበደለ ሌላው እየካሰ፣ አንዱ ባጠፋ በጅምላ እየተላለቅን መኖራችን እውነት በልባችን ላይ ስፍራ እንደተነፈገ የሚያስረዳ ነው፡፡ እንዲህ ያለውን ነገር ለመቀየር የተለያዩ ቤተ እምነቶች በጋራ መሥራት ይኖርባቸዋል፡፡ በግለሰብ ደረጃ ደግሞ ለይቅርታ ያለንን አመለካከት ማስተካከልና ማሳደግ አለብን፡፡ የእግዚአብሔር ቃል “ክርስቶስ ይቅር እንዳላችሁ እናንተ ደግሞ እንዲሁ አድርጉ” (ቆላ. 3÷13) ይላል፡፡ የይቅርታችን መሠረት እግዚአብሔር በልጁ በኩል ለእኛ ያሳየን (የሚወደውን አንድያ ልጁን በመስጠት) ይቅርታ ሲሆን እኛ ለሌሎች ይቅርታ እንድናደርግ የሚያስችለን ኃይል (ገና ኃጢአተኞች ሳለን ክርስቶስ ስለ እኛ ሞቷልና) ደግሞ በመስቀል ላይ ሆኖ ለወጉት ምሕረትን የለመነው ጌታ ነው፡፡ ያንን የመስቀል ላይ ምሕረት በደም የሆነ ይቅርታና ስርየት ዕለት ዕለት የሚያስታውሰን ደግሞ ቅዱሱ የእግዚአብሔር መንፈስ ነው፡፡

          ክርስቶስ እኛን ይቅር ያለን በበደላችንና በኃጢአታችን ሙታን፣ ከፍጥረታችንም የቁጣ ልጆች ሳለን ነው፡፡ የኃጢአት ደመወዝ ሞት እንደመሆኑ የዘራነውን ማጨድ ፍትሃዊነት ሆኖ ሳለ ክርስቶስ ግን የማይገባንን ሕይወት ሰጥቶ የሚገባንን ሞት እርሱ ሞተልን፡፡ (ኤፌ. 2÷1-6) ዛሬ በእኛ ላይ የሚሆንብን ነገር እኛ በእግዚአብሔር ላይ ከሠራነው በደል አይበልጥም፡፡ ብዙው ተትቶልን ጥቂቱን ይቅር ማለት ካልቻልን ግን እጀ ነካሽ፣ ወጪት ሰባሪዎች ነን፡፡ እግዚአብሔር ሰነፍ እርቅ የለውም ይቅርታና ምሕረቱ ለዘላለም ነው፡፡ በዚህም ይጸጸት ዘንድ እግዚአብሔር ሰውን አይደለም፡፡

         ይህንን ርዕስ ያነሣሁበት ምክንያት ለምክርና ለተግሳጽ የሚሆን ጥቂት ቁም ነገር ስላገኘሁበት ነው፡፡ በእኛስ ሕይወት ሰነፍ እርቅ አይስተዋል ይሆንን? ፆም እስኪፈታ የይምሰል ታርቀን በነገር የምንፈስክ ስንቶቻችን ነን? ካንጀት ሳይሆን ካንገት፣ የልብ ሳይሆን የአፍ እርቅም ሰነፍ እርቅ ነው፡፡ ከፊል ቂም ከፊል ይቅርታ፣ ከፊል ኩርፊያ ከፊል ሰላምታ፣ ከፊል መንፈግ ከፊል መቸር ባጠቃላይ ይግደልሽ እያሉ ይማርሽ እንደሚባለው ያለ አይነት ነው፡፡ እግዚአብሔር የእርሱ የሆኑትን፣ በእውነትና በመንፈስ የሚያመልኩትን እንዲህ ይላል “እንግዲህ መባህን በመሠዊያው ላይ ብታቀርብ በዚያም ወንድምህ አንዳች በአንተ ላይ እንዳለው ብታስብ በዚያ በመሠዊያው ፊት መባህን ትተህ ሂድ አስቀድመህም ከወንድምህ ጋር ታረቅ በኋላም መጥተህ መባህን አቅርብ፡፡ (ማቴ. 5÷23-24)  ክርስቶስ ለእኛ ያሳየውን ይቅርታ ስንረዳ እኛም ሌሎችን ይቅር የማለት ጉልበት እናገኛለን፡፡ ይቅር ማለት ይብዛላችሁ!!

Monday, April 9, 2012

ሰው ለቤቱ



         የመጽሐፍ ቅዱሳችን የመክፈቻ ክፍል በሆነው የዘፍጥረት መጽሐፍ ውስጥ ብዙ ከመለኮት ለሰው የተላለፉ ለትምህርትና ለተግፃጽ ልብንም ለማቅናት የሚያገለግሉ መንፈሳዊ መልእክቶች እንዳሉ እናውቃለን፡፡ ከዚህ ርዕስ ጋር በተያያዘ የምናነሣው ከያዕቆብ ታሪክ የተወሰነውን ክፍል ይሆናል፡፡ ይስሐቅና ርብቃ ያዕቆብና ዔሳው የሚባሉ ልጆች እንደነበሯቸው እነርሱም ገና በማህፀን ሳሉ ይጋፉ እንደነበር ያም መገፋፋት ወደ ማስተዋል ከመጡ በኋላም በኑሮአቸው እንደተገለጠ ዜና መዋዕላቸው ያስረዳናል፡፡

       ይስሐቅ በእድሜው ምሽት፣ በዘመኑ መጨረሻ፣ አይንን በሚይዝ እርጅና ውስጥ ሆኖ በኩሩንና የሚወደውን ልጁን ዔሳውን በመጥራው “ከመሞቴ በፊት እንድመርቅህ ወደ ዱር ሂድ አድነህም ጣዕም ያለውን ምግብ አዘጋጅተህ አብላኝ” አለው፡፡ ርብቃ ይህንን ትሰማ ስለነበር እርሷም በተራዋ የዔሳውን እግር ጠብቃ ለምትወደው ልጇ ለያዕቆብ በወንድሙ ምትክ በረከትን መቀበል እንደሚችል ለዚህም አደን መውጣት እንደማያስፈልገው ይልቁንም በቤት ካሉት ጠቦቶች መካከል የሰቡና የጣሙትን ሁለት እዲያመጣ አዘዘችው፡፡ ያዕቆብ የእናቱ ብልሀት የተቃኘ ማታለል አልዋጥ ቢለው “ወንድሜ ሰውነቱ ጠጉራም ነው የእኔ ገላ ደግሞ ለስላሳ ነው ታዲያ አባቴ ይህንን ባረጋገጠ ጊዜ በበረከት ፈንታ መርገምን አተርፋለሁ” አላት፡፡ ርብቃ ግን መርገሙ በእኔ ላይ ይሁን በማለት ያዘዘችውን እንዲፈጽም ነገረችው፡፡

        በዚህ ቤተሰብ ውስጥ ከምናስተውለው ነገር አንዱ መለያየትን ነው፡፡ በያዕቆብና በዔሳው መካከል ግፊያ የጀመረው ገና በማኅፀን ሳሉ ቢሆንም ያ ባለማስተዋል የነበረ ነው፡፡ ወደ ማስተዋል ከመጡ በኋላ ግን የምናየው መለያየት የቤተሰብ ተጽእኖ ውጤት ነው፡፡ እናትና አባት ለልጆቻቸው እኩል ፍቅር ባለማሳየታቸው በወንድማማቾቹ መካከል ዛሬ ድረስ ያልጠፋ መለያየትና ጠላትነትን አትርፏል፡፡ በእኛም አገር እንዲህ ያለው የቤተሰብ መሐል መለያየት ጎልቶ የሚስተዋል ችግር ነው፡፡ አንድ ሰው የአካባቢውና የቤተሰቡ ውጤት እንደመሆኑ ችግሩ ተሸጋጋሪ፣ ጉዳቱ ሁለንተናዊ ነው፡፡ እየሰማን ካደግነው ይትባህል መሐል “ሴት ልጅ አባቷን ወንድ ልጅ እናቱን ይወዳል” የሚለው ተጠቃሽ ነው፡፡ ከዚህም ስር ሰደድ ብሒል የተነሣ በአንድ ቤት ውስጥ ሁለት ዓይነት ጽንፍ፣ በተለይ በእናትና በአባት አለመግባባት ወቅት ይስተዋላል፡፡ ቤተሰብ አርአያነቱ መጀመሪያ ለቤቱ ሰዎች እንደመሆኑ በመልካም ምሳሌ መሆን እንዲሁም  ሚዛናዊነቱን የጠበቀ ፍቅር ለልጆች ማሳየት አግባብ ነው፡፡

          ያዕቆብ የእናቱን ምክር ሰምቶ በድምጽ ራሱን በሰውነቱ ደግሞ ወንድሙ ዔሳውን መስሎ ቆመ፡፡ ይስሐቅ የያዕቆብን ዔሳው አለመሆን ቢጠራጠረውም ከዚህ ያለፈ አቅም አልነበረውም፡፡  ልብንና ኩላሊትን በሚመረምረው እግዚአብሔር ፊት ግን ሰው በሁለት ማንነት ሊቆም  ከመታወቅስ ሊያመልጥ እንዴት ይችላል? ያዕቆብ ሁሉን በእናቱ ምክር ቢያደርገውም አጨዳውን ግን ከእናቱ ጋር አላጨደውም፡፡ እንደውም ያዕቆብ የወንድሙ ቁጣ እስኪበርድ ድረስ ወደ አጎቱ ላባ ዘንድ ከሸሸ በኋላ እናቱ የሞተችው ዳግመኛ ሳይተያዩ ነው፡፡ ያዕቆብ አባቱ ቤት የዘራውን ማታለል አጎቱ ቤት ዐሥራ አራት ዓመት በመታለል እንዲሁም የገዛ ልጆቹ ዮሴፍን ለምድያም ሰዎች ወደ ግብጽ ሸጠውት ልብሱን በደም ነክረው በማምጣት ልጅህ ሞቷል በማለት በእርጅናው አታለሉት፡፡ “ሰው የሚዘራውን ሁሉ ያንኑ ደግሞ ያጭዳል” (ገላ. 6÷7) ተብሎ እንደተፃፈ ያዕቆብ የዘራውን አጨደ፡፡

            ኦሪት ዘፍጥረት ምዕራፍ ሠላሳ ቁጥር ሠላሳን ስናነብ ግን ያዕቆብ ወደ ልቡ እንደተመለሰና “እኔ ደግሞ ለቤቴ የምሠራው መቼ ነው?” በማለት የአጎቱን ቤት ጥሎ እንደሄደ እናስተውላለን፡፡ እግዚአብሔር የቃል ብቻ ሳይሆን የሕይወትም መምህር ነው፡፡ ስለዚህ ሁኔታን መንገር ብቻ ሳይሆን በሁኔታ ውስጥም ያሳልፈናል፡፡ ያዕቆብ ባለፈባቸው የኑሮ ብርቱ ሰልፎች ውስጥ ምን ያህል እንዳጣ አስተውሎ የአጎቱን የተመለስ ልመናና የአደርግልሃለው ማባበያ እንቢ አለ፡፡ ያዕቆብ ዕድሜውን ለራሱ ለመሰብሰብ ቢተጋበትም እኔነቱ ያስገኘለት ነገር ግን የለም፡፡ በዚህም የእግዚአብሔር ጸጋ ምን ያህል ሰፊ እንደሆነ እናገናዝባለን፡፡

          የእግዚአብሔር ቃል በግልጥ እኛ የመለኮት ቤት እንደሆንን ይናገራል፡፡ (2ቆሮ. 6÷16) ቤትን ስናስብ ደግሞ ብዙ ነገሮች ወደ ሕሊናችን ይመጣሉ፡፡ ዞረን ዞረን የምንሰበሰብበት፣ ክፉውንም ደጉንም የምናሳልፍበት፣ ከፀሐይ ንዳድ ከበረታ ብርድ የምንሸሸግበት፣ ቢከፋን ማኩረፊያ፣ ቢመቸን ማረፊያችን ነው፡፡ ነገር ግን ቤትን ቤት ሊያሰኙ፣ መኖርም ሊያስችሉ፣ መንፈስና ቀልብን ሊስቡ የሚያስችሉ አስፈላጊ ነገሮች አሉ፡፡ የመጀመሪያው ንጽሕና ነው፡፡ ሰው የቤት ዕቃ ስለማሟላት ለማሰብ የቤቱን ንጽሕና በቅድሚያ ሊያስተውል ግድ ነው፡፡ ንጹሕ ባልሆነ ቤት ስለተሟላ የቤት ዕቃ ማውራት ግብዝነት ነው፡፡ በቁሙ ቤትን ያለ ንጽሕና ማሰብ አለኝ እያሉ ለመኖር ካልሆነ በቀር ከቤቱ ተጠቃሚ መሆን አይቻልም፡፡

           እኛ የሕያው እግዚአብሔር ቤት መሆናችንን ከተረዳን የቤቱ ንጽሕና እንዲጠበቅ መትጋት አለብን፡፡ ልብሳችን ላይ ቁሻሻ ማየት የሚያስቆጣን ከሆነ ልባች ላይ የሚገላበጠው የኃጢአት ብዛት ምነው አያስከፋንም? መልካምነት የሚጀምረው ከቤት ነው፡፡ ለቤታችን ንጽሕና ሳንቆረቆር ለመንደር ንጽሕና ዘብ መቆም የራስን እያሳረሩ የሰው ማማሰል ነው፡፡ ኃጢአት የለብንም ብንል ራሳችንን እናስታለን እውነትም በእኛ ዘንድ አይኖርም፡፡ (1 ዮሐ. 1÷8) ኃጢአት ደግሞ ለእግዚአብሔር ጽድቅ ጠላት ነው፡፡ ኃጢአትም ከዘላለም ሞት ፍርድ በታች ማብቂያ ለሌለው ኩነኔ ተላልፎ ተሰጥቷል፡፡ ሰው ከዚህ ኃጢአት የሚነፃበት ከፍርድም ነፃ የሚሆንበት ኃይል ያስፈልገዋል፡፡ የልጁም የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ከኃጢአት ሁሉ እንደሚያነፃ መረዳት ደግሞ እንደቆሸሹ ለሚያምኑ ሁሉ የሚያጠራ ውሃ ነው፡፡ (1ዮሐ. 1÷7) በሰማይና በምድር ፊት እግዚአብሔርን እንደበደልነው ሲሰማን ወደ ምሕረቱ የምንቀርበው በንስሐ ሲሆን እግዚአብሔር ለእኛ ይቅርታን የሚሰጠን ደግሞ አንድ ጊዜ ከፈሰሰው የልጁ ደም የተነሣ ነው፡፡ ስለዚህ የምንነፃበት እያለ ቆሽሸን የምንቀደስበት እያለ ረክሰን የምንድንበት እያለ ተኮንነን የሚቀበለን የምሕረት እጅ እያለ ተቅበዝብዘን መኖር የለብንም፡፡ ኃጢአትን በመሰወር ውስጥ ልማት የለም በመናዘዝና በመተው ግን በረከት አለና ተወዳጆች ሆይ ንጽሕና ይጠበቅ!!

           ሁለተኛው ፀጥታ ነው፡፡ ዛሬ ዓለም ላይ ጮኸው የሚሰሙት በፀጥታ ውስጥ የተከናወኑ ተግባራት ናቸው፡፡ እንደዚህ ዘመን መደማመጥ የጠፋበት አሳብ የተደበላለቀበት የሚመስለውን ከሆነው መለየት ያስቸገረበት ጊዜ የለም፡፡ ሕይወትን ለኪሳራ የሚዳርጋት ትልቁ ነገር ጽሞና የለሽ ትጋት ነው፡፡ ሰው ያገኘውን ካጣው የያዘውን ከበተነው ያተረፈውን ካጎደለው በፀጥታ ካልመረመረና ካለየ እድገት እንዴት ሊኖር ይችላል? ፀጥታ በተሳሳተ መንገድ ሮጦ የተሳሳተ ነገር ከማጨድ ይጠብቃል፡፡ እግዚአብሔር ለሕይወታችን ያለውን አሳብ ልንሰማውና ልንረዳው የምንችለው ፀጥታን መለማመድ ስንችል ነው፡፡ አለዚያ እየሮጡ መታጠቅ እየሮጡ መፈታት ይሆናል፡፡

          ከኃጢአት ቀጥሎ ለሕይወታችን መታወክ ምክንያት የሚሆነው ለኑሮ መጨነቅ ነው፡፡ እግዚአብሔር እኛን ወደዚህ ምድር ያመጣን አስቀድሞ የሚያስፈልገንን በመፍጠር ነው፡፡ ዛሬ ጭንቀት ስናመርት የምንውለውም ከእኛ ቀድመው ለተፈጠሩት ነገሮች ነው፡፡ የሠራን እግዚአብሔር ነው ለኑሮአችንም ከእርሱ በላይ ሊያስብ የሚችል የለም፡፡ መጨነቅ የማያስረዝሙትን ፀጉር ሲጎትቱ መኖር ነው ይህ ደግሞ ለውጥ በማይመጣበት መልኩ ራስን መጉዳት ነው፡፡ ክርስቲያን ወደ መኖር ባመጣው በአንድ ልጁ በክርስቶስ ኢየሱስ ባዳነው አምላክ ያረፈ አሳቡም በዘላለም ሕይወት የተሞላ ነው፡፡ ቃሉ “እርሱ ስለ እናንተ ያስባልና የሚያስጨንቃችሁን ሁሉ በእርሱ ላይ ጣሉ” ይላል፡፡ ግን ጥለናል ወይ?

        የሕይወት ፀጥታ የመጣንበትን ያለንበትንና መዳረሻችንን አጥርተን እንድናይ ይዳናል፡፡ እግዚአብሔር የሰላም አምላክ እንጂ የሁከት አምላክ ስላይደለ ከእርሱ ጋር ለመገናኘት ፀጥታ ብርቱ ነው፡፡ ስለዚህ በነገር ሁሉ በጸሎትና በምልጃ ከምስጋና ጋር በእግዚአብሔር ዘንድ ልመናችሁን አስታውቁ እንጂ በአንዳች አትጨነቁ፡፡ አእምሮንም ሁሉ የሚያልፍ የእግዚአብሔር ሰላም ልባችሁንና አሳባችሁን በክርስቶስ ኢየሱስ ይጠብቃል፡፡ (ፊል. 4÷6) ተወዳጆች ሆይ በልባችሁ ግድግዳ ላይ የተሰቀለውን ማስጠንቀቂያ አንብባችሁታልን? እንዲህ ይላል “ፀጥታ ይከበር”፡፡ ለበረከት ሁኑ!!

Thursday, April 5, 2012

መጽናናት




     በአዲሱ እለት አጥቢያ ላይ ከእንቅልፌ ስነቃ ልክ የመከራ ወጀብ ወደ እኔ እንደሚመጣ መስሎ ተሰማኝ፡፡ ማየት የቻልኩት ሁሉ ከችግር ቀጥሎ የሚመጣ ሌላ ተግባር ነው፡፡ እናም ጮኼ ማልቀስ ጀመርኩ አቤት ጌታዬ ከእኔ የምትፈልገው ምንድን ነው?” ከከፍታው የመጣው ምላሽ ምንም ሳይሆን በጣም ቀላል ምላሽ ነበር፡፡ አንድ ያልተጠበቀ ነገር ግን እውነተኛ ምላሽ፡፡ ከእኔም ሆነ ከእናንተ የሆነ የሚፈልገው ነገር አለ፡፡ ሁሉንም ነገርሲል መለሰልኝ፡፡ እንደ አዳኝህና እንደ መሪህ ሁልጊዜም በመንገድህ ሁሉ አብሬህ እንዳለሁ የአንዲቷ ፀጉርህ ዘለላ እንኳን ወዳጅ፤ እኔ እንደሆንኩ እንድታውቅ እፈልጋለሁ፡፡

     በመልካም ጊዜያትም ሆነ በክፉዎቹ በእውነትና በመንፈስ እንድታገለግለኝ፣ ተደሰትክም ተከፋህም በምስጋና መሥዋዕት እንድታከብረኝ እፈልጋለሁ፡ በእያንዳንዷ እለት እምነትህ እየጠነከረ እንዲያድግ ለምንለሚሉት ጥያቄዎችህ መልስ ባይኖርህም እንኳን በእኔ እንድታምን እፈልጋለሁ፡፡ ያጋጠመህን አስቸጋሪ ነገር እንድትኖርበት ስትጠራ፤ የእኔን ፍቅር እንድትማርና እቅፌም እንዲሰማህ እፈልጋለሁ፡፡ ማንም ሆነ ምንም በልብህ ያለኝን ቦታ እንዲወስድ አልፈልግም፡፡ ልታደርገው በሚገባህ በማንኛውም ነገር ውስጥ ቀዳሚና ትልቅ ድርሻ እንዲኖረኝ እፈልጋለሁ፡፡ ምንም ነገር አያናውጽህ በቃል ኪዳኔም ጽና በስተመጨረሻም ሁሉ ነገር ተከናውኖልህ ታያለህ፡፡ እስኪ አስብ?

W ሕመም የማይሰማህ ቢሆን ፈዋሽ መሆኔን እንዴት ታውቃለህ?

W በመከራ ውስጥ ካላለፍክ ነፃ አውጪ መሆኔን እንዴት ልታውቅ ትችላለህ

W ብስጭት ካልተሰማህ እንዴት ሆሃ ምቹ እንደሆንክ ታውቃለህ

W ፈተናዎች ከሌሉብህ እንዴት አድርገህ ራስህን ጽኑ እኔን አሸናፊ ብለህ ልትጠራ ትችላለህ?

W ስህተቶችን ጭራሽ ካልሠራህ ይቅር ባይ መሆኔን እንዴት ማወቅ ይቻልሃል?

W ሁሉን የምታወቅ ከሆነ ጥያቄዎችህን ሁሉ እንደምመልስልህ በምን ታውቃለህ?

W ጭራሽ ያልተሰበርክ ብትሆን ኖሮ ሙሉ ላደርግህ እንደሚቻለኝ ከወዴት ታውቃለህ?

W የማልቀጣህ ቢሆን እኔ እንደምወድህ፣ አንተም ልጄ እንደሆንክ እንዴት ትረዳለህ?

W ኃይል ሁሉ ቢኖርህ በእኔ ላይ መደገፍን እንዴት ልትማር ትችላለህ?

W ሕይወትህ ፍጹም ቢሆን ኖሮ ከእኔ የምትፈልገው ምን ይኖር ነበር?

        አየህ ውድ ልጄ በሁሉም ነገር ውስጥ ሁሉ ነገርህ እንድሆን እና ወደቅህም ጸናህም በእኔ መኖር ላይ እንድትደገፍ እፈልጋለሁ፡፡ ከእኔ የምትፈልገው ምንድነው? ለሚለው ጥያቄህ መልሴ ሁሉንም ነገርየሚል ነው፡፡ ልክ አንተ ለእኔ ሁሉ ነገር እንደሆንክ ሁሉ፡፡ ከግርግርና ከፈተና የጸዳ ቀለል ያለ ሕይወትን መፈለግ ለብዙዎቻችን አዲስ ነገር አይደለም፡፡ ይልቁንስ የማንረዳው ነገር ቢኖር ያለ ውጣ ውረድ የምንኖርባት ሕይወት ያን ያህል የሻትነውን ነገር ከግቡ ለማድረስ እንደማታስኬደን ነው፡፡

     ደስታን ለማድነቅ ሐዘን ያስፈልጋል በትንሽ ስጦታ ውስጥ እርካታን ለማግኘት መሰላቸት ይኖራል፡፡ ይህም እያንዳንዱን አስፈላጊ ሥራ የምናደርግበትን፣ አዳዲስ አሳቦችን የምናፈልቅበትን እና አስቀድመን የያዝነውን ጸጋ የምንናፍቅበት እድል የሚፈጥርልን ነው፡፡ ቢሆንም ግን ልብ ልንለው የሚገባን ነገር ሕይወት የተመሠረተችው እኛ በከፊል በምናደርገው ነገር ላይ ብቻ ሳይሆን እግዚአብሔር ለሰው በሚያደርገው ሙሉ ነገር ላይ መሆኑን ነው፡፡ ሙሉ እኛነታችን ይህንን ታላቅ እውነት እስካልተቀበለውና እስካልኖርንበት ድረስ መልካምነትና ሰላም በሙላት በእኛ ውስጥ ሊኖር አይችልም፡፡ እርሱ ብቻውን እውነተኛ አዳኝ ነው፡፡ ስለዚህ በዋናነት በራሳችን ላይ የምንደገፍ ከሆነ ሕይወት የማይገፋ እየሆነብን ይመጣል፡፡ የእግዚአብሔር ጸጋ ሕልውናችን ነው፡፡ በእርሱ ላይ እንሄዳለን፡፡ እርሱንም እንተነፍሳለን፡፡ በእርሱም ውስጥ ኖረን በእርሱም ውስጥ እንሞታለን፡፡