Monday, August 20, 2012

የተወጋ ሲረሳ (ክፍል አንድ)



       የወደደንን መውደድ፣ የጠላንን መጥላት፣ ለዋለልን መስጠት፣ ለነፈገን መንሣት፣ ላሰበልን መራራት፣ ለዘነጋን መክፋት የብዙኃኑ የሰው ልጅ የአኗኗር መመሪያ ነው፡፡ ምንም እንኳን በጸጋ ዘመን ላይ ብንገኝም ዓለም ገና ዓይን ስለ ዓይን፣ ጥርስ ስለ ጥርስ፣ እጅ ስለ እጅ ከሚለው ምላሽ አልጸዳችም፡፡ እንዲያውም በዚህ ሕግ ግልጽ ሆኖ ከሚስተዋለው ለጠሉኝ እሬት አይነት አካሄድ በበለጠና በረቀቀ መንገድ ሰዎች የልባቸውን ፈቃድ እያረኩ ነው፡፡ ለብዙ ክርስቲያኖች እንዲህ ያለውን እሾህን በእሾህ፣ ደምን በደም የመመለስ ኑሮ ከእምነት ጋር አቻችሎ ማስኬድ አልከበዳቸውም፡፡ ክፉውም ጋር ደጉም ጋር ቋሚ ተሰላፊ የሆኑ ጥቂት ሆድ ሲብሳቸው “ያስቀመጥኩትን ቆንጨራ እንዳላመጣው?” በማለት የሚዝቱ ሁሉን ትተው ሳይሆን ሁሉን ለክፉ ቀን አስቀምጠው የተከተሉት አይናችን ስር ናቸው፡፡
         አብዛኞቻችን ሰው በሚለውና ክርስቲያን በሚለው መጠሪያ መካከል ያለውን ልዩነት ልብ አንለውም፡፡ ሰው ከምድራዊው ጥሪ ተካፋይ የሆንበት መንገድ ሲሆን፤ ክርስቲያን የሚለው ደግሞ ከሰማያዊው ጥሪ ተካፋይ የሆንበት መንገድ ነው፡፡ ሰው በመሆን ውስጥ በምድራዊ ስፍራና በሥጋዊ በረከት መርካት ሲስተዋልበት፡፡ (ማለትም በዚህ ምድር የምንሰበስበው ሁሉ ከፀሐይ በታች ሲሆን) ክርስቲያን በመሆን ውስጥ ደግሞ በሰማያዊ ስፍራና በመንፈሳዊ በረከት መባረክን እናስተውላለን (ኤፌ. 1÷3)፡፡
         ሰው በመሆን ልደት ይህንን ዓለም በሥጋና በደም አቋም ሆነን እንቀላቀላለን፡፡ ክርስቲያን በመሆን (ዳግም በመወለድ) ደግሞ የዘላለም ሕይወትን መቀላቀል ደግሞም የተዋረደው ሥጋችን የጌታን ክቡር ሰውነት መስሎ በሰማይ ከእርሱ ጋር እንነግሳለን፡፡ ስለዚህ ክርስቲያን ሁሉ ሰው መሆንን ቢጋራም ሰው ሁሉ ግን ክርስቲያን አይደለም፡፡ በዚህም ክርስቲያን መሆን ሰው ከመሆን በእጅጉ ከፍ ያለ እንደሆነ እንገነዘባለን፡፡
         “ቀኝ ጉንጭህን በጥፊ ለሚመታህ ሁሉ ሁለተኛውን ደግሞ አዙርለት፣ እንዲከስህም እጀ ጠባብህን እንዲወስድ ለሚወድ መጎናጸፊያህን ደግሞ ተውለት፣ ማንም ሰው አንድ ምእራፍ ትሄድ ዘንድ ቢያስገድድህ ሁለተኛውን ከእርሱ ጋር ሂድ” (ማቴ. 5÷38-42)፡፡ ጌታ በዚህ ክፍል  ላይ ያስተማረው ትምህርት ሰው በሚለውና ክርስቲያን በሚለው ስያሜ መካከል ያለውን ተግባራዊ ልዩነት ግልጽ ያደርግልናል፡፡ በመጀመሪያ እግዚአብሔር ለሚያዘን ነገር ሁሉ የምንፈጽምበትን ኃይል እንደሚሰጠን መተማመን በዚህ ክፍል የተገለጸውን ትምህርት በቅንነት ለመረዳት ወሳኝ ነገር ነው፡፡ ቀኝ ጉንጭን በጥፊ መመታት ውስጥ ያለው ክርስትና ሳይሆን ሰው መሆን ነው፡፡
            እጀ ጠባብን ለሚወስድ ያንኑ መተው ሰው በመሆን ደረጃ የሚከናወን ተግባር እንጂ ክርስቲያን መሆንን አይጠይቅም፡፡ አንድ ምእራፍ በመሄድ ውስጥም እንዲሁ ከክርስትና ይልቅ ያለው ሰው መሆን ነው፡፡ የክርስትናው የአኗኗር ልኬት የሚጀምረው ታዲያ የቱ ጋር ነው? ካልን ሁለተኛውን ጉንጭ በመስጠት፣ መጎናጸፊያን በመጨመር፣ ሁለተኛውን ምእራፍ በመሄድ የሚል ይሆናል፡፡ ከዚህ ያነሰው ግን ማንም ሰው ከሰብአዊ ርኅራኄ በመነሣት አልያም ከሥጋ ሕግ በመነጨ ሁኔታ የሚከውነው ነው፡፡ “የሚወዱአችሁን ብትወዱ ምን ዋጋ አላችሁ? ቀራጮችስ ያንኑ ያደርጉ የለምን? ወንድሞቻችሁንም ብቻ እጅ ብትነሡ ምን ብልጫ ታደርጋላችሁ? አሕዛብስ ያንኑ ያደርጉ የለምን?” (ማቴ. 5÷46)፡፡
         የነከሰንን ማጉረስ፣ የበደለንን መካስ፣ የተጣላንን ገፍቶ መታረቅ፣ የረገመንን ከልብ መመረቅ ተወግቶ እንደ መርሳት ነው፡፡ ጉዳቱ እያለ በደልን አለመቁጠር፣ ስቃዩ እየታየ ጥፋትን መተው፣ ጉድለቱ እየተስተዋለ ኪሳራን አለማስላት መንፈሳዊ የኑሮ ልዕልናን ይጠይቃል፡፡ ክርስትና የተወጋ ሲረሳ ነው!
         ከብሉይ ኪዳን በዳዊትና በሳኦል መካከል የነበረው የገፊና ተገፊ፣ ያሳዳጅና ተሰዳጅ፣ የጠዪና ተጠይ ታሪክ ለተነሣንበት ርእስ ጥሩ ማሳያ ነው፡፡ የመጀመሪያው የእስራኤል ንጉሥ ሳኦል ወደ ንግሥና የመጣበትን መንገድ የስነ መለኮት አዋቂዎች ሲያስረዱ “እግዚአብሔር ከሕዝቡ ጋር የተስማማበት ሂደት ነው” ይላሉ፡፡ ለዚህም ምክንያቱ ሳኦል የእስራኤል ንጉስ የሆነው እንደ እግዚአብሔር ፍላጎት ሳይሆን በሕዝቡ ፍላጎት ተመርጦ በእግዚአብሔር አጽዳቂነት መሆኑ ነው፡፡
          እግዚአብሔር ሳሙኤልን “እንደጠየቁ ቀባላቸው” በማለት ከሕዝቡ አሳብ ጋር ተስማማ፡፡ ይህም በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ብቸኛው ክፍል እንደሆነ ይነገራል (1 ሳሙ. 15)፡፡ ምን ጊዜም ቢሆን እግዚአብሔር ከአሳባችን ጋር ከተስማማ ኪሳራው የሰው ነው፡፡ ወደኋላ መለስ ብለን ያለፈውን ፍላጎታችንን እና ዛሬ በዚያ ፍላጎት ላይ ያለንን አተያየት ብንመለከተው ለየቅል ነው፡፡ ያኔ እግዚአብሔር በፊቱ ካቀረብነው አሳብ ጋር ተስማምቶ ቢሆን፤ እንደጠየቅነው ሁሉን ቢሰጠን ኖሮ ዛሬ ከምናፍርበት ነገር ጋር ለመኖር  በተገደድን ነበር፡፡
          እግዚአብሔር ሲሰጥ ብቻ ሳይሆን ሲከለክል፣ ሲመልስ ብቻ ሳይሆን ዝም ሲል፣ ሲያኖር ብቻ ሳይሆን ሲገድልም አይሳሳትም፡፡ የእርሱ ጌትነት ምቾትን ብቻ ሳይሆን ጉስቁልናንም ያጠቃልላል፡፡ ክርስትና መብዛትን ብቻ ሳይሆን መዋረድን፣ መጥገብን ብቻ ሳይሆን መራብን፣ ከፍታን ብቻ ሳይሆን መጉደልንም ማወቅ ጭምር ነው (ፊል. 4÷12)፡፡ ስለዚህም አሳቡን እንስማማበት፣ መንገዱን እንጓዝበት ዘንድ እግዚአብሔር ከእኛ አሳብና መንገድ እጅግ የራቀ ነው፡፡ እርሱ ከፍላጎቶቻችን ጋር ሳይሆን እኛ ከእርሱ ፍላጎት ጋር፤ ከምርጫዎቻችን ጋር ሳይሆን እኛ ከእርሱ ፈቃድ ጋር፣ ከልባችን ጋር ሳይሆን እኛ ከልቡ ምክር ጋር  እንስማማ ዘንድ አግባብ ነው፡፡
           ዳዊት እግዚአብሔር በጠላቶቹ ፊት ለፊት በዘይት የቀባው፣ ከወንድሞቹ መካከል ለይቶ በአባቱ ንቀት ፊት ያከበረው ሰው ነው፡፡ ትልቁ እግዚአብሔር በብላቴናው ሕይወት ኃይሉንና ክብሩን ይገልጥ ዘንድ ስለወደደ ከበጎች ጥበቃ ወደ ንግሥና አመጣው፡፡ ሰው እኛን ወደተሻለ ነገር ለማምጣት ደረጃ በደረጃ ይሠራ ይሆናል፡፡ እግዚአብሔር ግን ከትቢያ አንስቶ ወደ ልዕልና ለማምጣት እርከን አያስፈልገውም፡፡ ዳዊት በሳኦል መንግሥት ዘመን ለሕዝቡ ፍርሃት፤ ለመንግስቱ ሥጋት የሆነውን ጎልያድ በእግዚአብሔር ስም በማሸነፍ ባለ ውለታ ነው፡፡ ከድሉ በኋላም ቤተ መንግሥት ውስጥ በገና በመደርደር የሳኦልን ርኩስ መንፈስ በማውጣት ለሳኦል ባለ ውለታ ነው፡፡ የሳኦል ምላሽ ግን ዳዊት ካደረገው ቅንነት ፍፁም ተቃራኒ ነበር፡፡ ሳኦልን ሊቀበል የወጣው ሕዝብ ለዳዊት በመዘመሩ (እልፍ ገደለ) እጅግ ተቆጣ፡፡ በገናምም እየደረደረ ሳለ ከግንቡ ጋር አጣብቀዋለሁ በማለት በእጁ የያዘውን ጦር ወረወረበት፡፡   
          በክፉዎችና በበጎዎች ላይ ፀሐይን የሚያወጣ እግዚአብሔር ሁሉ በፊቱ የተራቆተለት አምላክ ነው፡፡ የአመፀኛውን አመጽና የትሁቱን ትህትና የእርሱ ጽድቅ በእውነት ይዳኛል፡፡ ዳዊት እንዲህ ባለው ጌታ ፊት አንደኛ ሳኦል የሚያደርግበትን ክፉ፤ ሁለተኛ ለሳኦል የሚያደርግለትን መልካም ነገር አይቆጥርም ነበር፡፡ ለዳዊት ጤና ይህ ነበር!
       በሕይወታችን ውስጥ ከሚስተዋለው ድካም መካከል ያደረግነውን መልካም መተሳሰብና የተደረገብንን ክፉ መቁጠር በጉልህ የሚስተዋል ነው፡፡ የእግዚአብሔር ሰው ዳዊት የወንድሞቹን ጥላቻ፣ የአባቱን መናቅ፣ የሳኦልን ማሳደድ የተበቀለበት ትልቁ መንገድ መርሳት (አለመቁጠር) ነው፡፡ ሰው በቀል የተጠማ ልቡን የሚያረካበት መንገድ በደልን መቁጠር እንዲሁም ለበደሉ ተመጣጣኝ ምላሽ በመስጠት ነው፡፡ ነቢዩ ግን ሁሉን ማድረግ በሚችል እግዚአብሔር ፊት የተደረገበትን ይተወው ነበር፡፡ ሳኦል ጦርን ያህል ነገር ወርውሮበት ምድረበዳ ለምድረበዳ ሲያሳድደው የሚያደርገውን እንደማያውቅ ምስኪን ሰው ይቆጥርለት ነበር፡፡ እግዚአብሔር ከእኔ ጋር ነው! ብሎ ጉልበቱን ለማጥፋት አልተጠቀመበትም፡፡ ለሚያምኑ ሁሉ የእግዚአብሔር ኃይል ለማዳን ነው (ሮሜ. 1÷16) ተብሎ እንደተፃፈ የእግዚአብሔር የሆኑቱ ጉልበታቸውን በደልን ለመርሳት እንጂ ለመቁጠር አያውሉትም፡፡
                                                                               - ይቀጥላል -
      
     ውድ የቤተ ፍቅር ብሎግ ተከታታዮች በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስና በክቡር ጠቅላይ ሚኒስትራችን ሞት የተሰማንን ሀዘን ለመግለጽ እንወዳለን፡፡ ጌታ እግዚአብሔር ምድሪቱንና ሕዝቡን ይባርክ!!    

Wednesday, August 15, 2012

የግያዝ ዓይኖች


             
         ከሆነብን በላይ የሆነውን የምንተረጉምበት፣ ከሰማነው በላይ ያደመጥነውን የምንረዳበት፣ ከመጣው ፈተና በላይ መከራውን የምናስተናግድበት መንገድ ጽናታችንንም ሆነ መብረክረካችንን ይወስነዋል፡፡ ልጅ እያለን በጨለማ ስንሄድ አንዱ ዛፍ እንደ ብዙ ዛፍ፣ አንድ ድምጽ ልክ እንደ ብዙ ውኃዎች ድምጽ፣ አንድ ሰውም እንደ ትንሽ መንጋ ሆኖ ይታየን ነበር፡፡ በብዛት ብቻ ሳይሆን በኃይልም የምንረዳበት መንገድ ከሆነው በእጅጉ የተጋነነ ነው፡፡ የቅጠል መተሻሸት፣ የነፋስ ሽውታ፣ የሌሊት ወፍ ድምጽ ልክ እንደ አንበሳ ግሳት፣ እንደ ነብር ፍጥነት፣ እንደ ዲያብሎስ ትጋት ተቆጥሮ ልባችን ይሸነፍበታል፡፡ በሕይወታችን ድንግዝግዝ ነገር ሲበዛ አጥርቶ ማየት ከባድ ነው፡፡ በልኩም መረዳት አስቸጋሪ ነው፡፡ ከከበበን ብዙ መፍትሔ ይልቅ ጥቂት ችግራችንን እሽሩሩ ማለት ይቀናናል፡፡
         በአካል ካደግን፣ በአእምሮ ከበሰልን፣ የኑሮ ተግዳሮቶችን መጋፈጥ ከጀመርን በኋላ የምንፈተነው የሆነውን በሆነው ልክ ማየት ባለመቻል ነው፡፡ መከራ አይለመድም፡፡ የሕይወት ዘመን እንግዳ፤ የየማለዳው አዲስ ነው፡፡ ሰው ወድዶ አለመደሰት ይችላል፡፡ አለመፈተን ግን ከቶ አይችልም፡፡ በደስታ ላይ በርን መዝጋት ይቻላል፤ ችግር ግን የተዘጋውንም ጥሶ ይዘልቃል፡፡ የምስራቹን አልቀበልም ያሉ ዛሬ የበዪ ርሀብተኛ፣ የአዋቂ መሀይም፣ የብልጥ ተላላ፣ የዘናጭ ታራዥ፣ የትጉህ ብኩን ሆነዋል፡፡ ጌታ ግን በተዘጋው ደጅ የሚያልፍ መፍትሔ አለው፡፡ እርሱም “ሰላም ለእናንተ ይሁን” (ዮሐ. 20÷19) አላቸው፡፡
       በማንኛውም አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ሰይጣን የሚዘጋቸው፤ ሥጋም መጋረጃ ሆኖ የሚከልላቸው ነገሮች ይኖራሉ፡፡ እምነት ግን ከተዘጋው ባሻገር ማየት ነው፡፡ ከሚታየው አልፎ የማይታየውን መመርመር ነው፡፡ ከሥጋ ሁኔታ ወደ መንፈሳዊው ሁኔታ፤ ከዚህ ዓለም አሳብ ወደ ሰማያዊው አሳብ ከፍ ማለትም ነው፡፡ እምነት ከሥጋ አይን ልኬት፣ ከጆሮ የመስማት ደረጃ፣ ከአካልም የመስራት ኃይል በላይ ነው፡፡ ግዙፉን ጎልያድ በአንድ እዚህ ግባ በማይባል ብላቴና ፊት ያሳነሰው እምነት ነው፡፡ ለአሥሩ ሰላዮች በከነዓን የሚኖሩትን ሕዝብ ያገነነው ደግሞም ለእስራኤል ማኅበር ፍርሃትን እንዲያወሩ ያደረገው የእምነት ማነስ ነው፡፡ እነርሱም ሲናገሩ “በዓይናችን ግምት እንደ አንበጣዎች ነበርን ደግሞ እኛ በዓይናቸው ዘንድ እንዲሁ ነበርን አሉ” (ዘኁ. 13÷33)፡፡ እግዚአብሔር ደግሞ  ”“እኔ ሕያው ነኝና በጆሮዬ እንደተናገራችሁት እንዲሁ በእውነት አደርግባችኋለሁ” (ዘኁ. 14÷28) አለ፡፡ እንደ ቃሉም ሁሉን በሚችል አምላክ ፊት ያጉረመረሙት በሙሉ በምድረ በዳ ሞቱ፡፡
       በመጽሐፈ ነገሥት ካልዕ ምእራፍ 6 ላይ የሶርያ ንጉሥ ከእስራኤል ጋር ሊዋጋ ወደ ሕዝቡ እንደመጣ እናነባለን፡፡ ንጉሡም ፈረሶችንና ሰረገሎችን እጅግም ጭፍራ ሰደደ በሌሊትም መጥተው ከተማይቱን ከበቡ፡፡ የእግዚአብሔር ሰው ኤልሳዕ ሎሌ የሆነው ግያዝም “ጌታዬ ሆይ ወዮ ምን እናደርጋለን?” አለው፡፡ ግያዝ እንዲህ ሊናገር የቻለው ኤልሳዕ እንደሚያይ ማየት ባለመቻሉ ነው፡፡ የኤልሳዕ ዓይኖች ግን ከተማይቱን በከበቡት የሶርያ ንጉሥ ጭፍሮችና ድቅድቅ በሆነው ጨለማ ላይ ሳይሆን ያረፉት ከከበባቸው ሠራዊት በላይ በሆነው እግዚአብሔር ላይ ነበር፡፡ “ክርስቶስን ተመልከቱ” (ዕብ. 3÷2)!
       በኑሮ ውስጥ ብዙ የሚከቡን ነገሮች አሉ፡፡ የዚህ ዓለም ከንቱ አሳብ፣ የሰይጣን ውጊያ፣ የሕይወት ውጣውረድ፣ ድካምና ኃጢአት እነዚህ ሁሉ በዙሪያችን ያሉ የዕለት ከዕለት ፈተናዎች ናቸው፡፡ እምነት ግን ከሁኔታ ባላይ መኖር የምንችልበት ኃይል ነው፡፡ በእምነት ዓይን ፊት የማይቀልና የማያንስ ነገር የለም፡፡  ተወዳጆች ሆይ እኛ በኑሮ ሠልፍ ላይ ያለን ዓይን የግያዝ አይነት ነው ወይስ የኤልሳዕ? በዙሪያችን ያለው ችግር ወይስ ከእኛ ጋር ያለው እግዚአብሔር ነው የሚበልጥብን? ችግር ተኮፍሶ መፍትሔው ካነሰ ውጤቱ እንደ ሎሌው መፍራት ነው፡፡ ነቢዩ ዳዊት “መክበቡንስ ከበቡኝ በእግዚአብሔርም ስም አሸነፍኋቸው” (መዝ. 117÷11) ይላል፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞን ደግሞ  “የእግዚአብሔር ስም የጸና ግንብ ነው ጻድቅ ወደ እርሱ ሮጦ ከፍ ከፍ ይላል” (ምሳ. 18÷10) ይለናል፡፡ ከዚህ ዓለም ጥበብ የእግዚአብሔር ሞኝነት እጅግ እንደሚበልጥ ስናስተውል በአባትና ልጅ የተናገሩት እነዚህ ቃላት ለልባችን ይጠጋሉ፡፡
         የእግዚአብሔር መቻል የማይቻለውንም ይጠቀልላል፡፡ እርሱ እንዲያደርግልን የምንፈልገውን ሁሉ ቢያደርግልን እንኳ መቻሉ እዚያ ጋር አይቆምም፡፡ ከዚያም በብዙ ያልፋል፡፡ ኢዮብ ስለ እግዚአብሔር መቻል “ሰሜንን በባዶ ስፍራ ላይ ይዘረጋል ምድሪቱንም በታችዋ አንዳች አልባ ያንጠለጥላል ውኆችን በደመናዎቹ ውስጥ ያስራል ደመናይቱም ከታች አልተቀደደችም፡፡ . . . . ይህም የሰማነው ነገር ምንኛ ጥቂት ነው!” (ኢዮ. 26÷7) በማለት ይናገራል፡፡ በእርግጥም ሰማያት በመንፈሱ ውበት ያገኙበት፣ ምድር ከተግሣጹ የተነሣ የምትደነግጥለት፣ ስሙን ሰምቶ ሞት የሚብረከረክለት፣ ክብሩን አይተው ቀላያት የሚሰነጣጠቁለት ጌታ ሁሉን ያደርግ ዘንድ እንዴት አይችልም? አባቱን እንደሚገባ ያልተረዳው ልጅ የአባቱን አቅም በሁኔታ፣ በሰውና በቦታ መገደቡ የሚደንቅ ሊሆን አይችልም፡፡ እግዚአብሔርን የምናርፍበት በእምነት የተረዳነውን ያህል ነው፡፡  
            ግያዝ በእግዚአብሔር ፊት እንደ አገልጋይ ቢኖርም እግዚአብሔርን ግን እንደሚያገለግል ባሪያ አልተረዳውም፡፡ እግዚአብሔርን እንደሚያገለግል ተገልጋዩን መረዳት በሚያጸድቅና በሚኮንን በእርሱ ፊት ለመቆም ቀዳሚው ነገር ነው፡፡ ግያዝ እግዚአብሔር ለሶርያው ንጉሥ አለቃ ንዕማን የሰጠውን ደኅንነትና የገለጠውን ኃይል ተመልክቶአል፡፡ ዳሩ ግን በሶርያ ወታደሮች ፊት በእምነት እንዲቆም አላስቻለውም፡፡ አልዓዛር ከመሞቱ በፊት ማርያም በጌታ እግር ስር ቁጭ ብላ እንደተማረች ቃሉ ይነግረናል (ሉቃ. 10÷38)፡፡ ነገር ግን አልዓዛር ከሞተ በኋላ ማርያም በጌታ እግር ስር እንደተማረ ስትመልስ አናያትም፡፡ በሀዘን ሠልፍ ፊት አይኖችዋ ልክ እንደ ግያዝ ያሉ ነበሩ፡፡ ጌታ ግን አላት ትንሣኤና ሕይወት እኔ ነኝ በእኔ የሚያምን ቢሞት እንኳን ሕያው ነው፡፡ (ዮሐ. 11÷25)
       ችግር ወደ ሕይወታችን ሲመጣ “በኤልሳዕ ዙሪያ ያሉት የእሳት ፈረሶችና ሰረገሎች ተራራውን ሞልተውት ነበር” የሚለውን ማስተዋል ያቅተናል፡፡ ከሶርያ ጭፍሮች መክበብ በላይ በኤልሳዕና በሎሌው ዙሪያ ያሉት ይበልጡ ነበር፡፡ በግልጥ የምናየው በሥጋና በመንፈስ ሠራዊት መካከል ያለ ልዩነት ነው፡፡ በሰማያዊ ኃይልና በምድራዊ አቅም መካከል የነበረ ፍጥጫ ነው፡፡ በእምነትና በራስ ትምክህት መካከል በግልጥ የሚስተዋል ልዩነትም ነበር፡፡ ግያዝ በመንፈስ ከማስተዋል ይልቅ በሥጋ ለመዳኘት የቀረበ ነበር፡፡ ከሰማዩም ይልቅ የምድሩ የቀረበው ነበር፡፡ እግዚአብሔር ግን የብላቴኖችን ዓይን ይከፍታል፡፡ “የቃልህ ፍቺ ያበራል ሕፃናትንም አስተዋዮች ያደርጋል” (መዝ. 119÷130)፡፡
        ተወዳጆች ሆይ በዙሪያችሁ ካሉት ጠላቶች ይልቅ ወዳጆቻችሁ ብዙ ናቸው፡፡ ከከበባችሁ ችግር የከበባችሁ መፍትሔ ይበልጣል፡፡ ከሚወረወረው ቀስት ከሚበረው ፍላፃ ይልቅ እንደ ጋሻ የከበበን እውነት ኃያል ነው፡፡ የምትኖሩበት አገርና መንደር ላልተመቻችሁ እግዚአብሔር በተኩላና በእባብ ላይ ያጫማል፡፡ ባርነት ላንገሸገሻችሁ፣ የሰው ፊት ለጠቆረባችሁ፣ ነፃነት ብርቱ ናፍቆት ለሆነባችሁ እግዚአብሔር አንበሳውንና ዘንዶውን ያስረግጣል፡፡ ጌታ ያለማመንን ቅርፊት ከልባችን ላይ ያንሣ፣ በዓይናችን ላይ ያለውን የኃጢአት ሞራ ይግፈፍ፡፡ ሁሉም የሚያየው ገደል በሆነበት ዘመን ተራራው ላይ ያለውን ከፍታ፣ ከትንሽ እስከ ትልቅ በራደበት በዚህ ጊዜ በዙሪያችን ያለውን የእሳት ሠራዊትና መንፈሳዊ ኃይል በእምነት እንድናስተውል ጸጋ ይብዛልን፡፡                               

Friday, August 3, 2012

ለአፍንጫ ጥላ



       አንድ አባት ለሕፃናት በሚገባቸው መንገድ ለማስተማር የተጠቀሙበት ምሳሌ ነው፡፡ አብዛኛውን ጊዜ በአገልግሎት ውጤታማ ላለመሆን እንደ ምክንያት ከሚጠቀሱ ነገሮች መካከል በእድሜ ከፋፍሎ አለማስተማር ዋንኛው ነው፡፡ በእርግጥም ይህንን አስተያየት መሮንም ቢሆን ልንቀበለው ግድ ይሆንብናል፡፡ የእግዚአብሔር ቃል በወተትና በአጥንት ደረጃ ለሰዎች እንደሚቀርብ ስናስብ ሕፃናትና አዋቂዎች በአንድነት በተቀመጡበት ጉባኤ ላይ የትኛውን ዓይነት መልእክት ማስተላለፍ እንዳለብን ግራ ያጋባል፡፡ ምክንያቱም ወተት ብናቀርብ አዋቂዎቹን ወደኋላ እንጎትታቸዋለን፤ አጥንት ብናቀርብ ደግሞ ልጆቹን እንገድላቸዋለን፡፡ በዓለም የትምህርት ስርዓት እንኳን ያለውን የማስተማር ሂደት ስንመለከት በእድሜና በተቀራራቢ የማገናዘብ ደረጃ የተከፋፈለ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ተፈጥሮአዊውን ምክንያት የተከተለ ነው፡፡
        ምሳሌያቸው ለዚህ ጽሑፍ መነሻ የሆነንም አባት ከሁሉም አይነት እድሜ የተውጣጡ ሰዎች (ሕፃን፣ ወጣት፣ ሽማግሌ) ባሉበት ጉባኤ ላይ ተገኝተው በትምህርት ሰዓት ሕፃናቱ ከጨዋታና ከረብሻ ውጪ ምንም ተሳትፎ እንዳልነበራቸው አስተውለው ለልጆቹ ብቻ መልእክት አስተላለፉ፡፡ መልካም አስተማሪ የሚያሰኘው ትምህርትን ማክበድ ሳይሆን በተቻለ መጠን አሳቡ በሰሚው ልብ ውስጥ በግልጽ መቅረት እንዲችል ማስቻል ነው፡፡ ይህ ማለት ግን ቋንቋና የአቀራረብ ዘዴን ማስተካከል እንጂ የእግዚአብሔርን አሳብ ማስተካከል ማለት አይደለም፡፡ አብዛኛውን ጊዜ የምንመለከተው ግን የእግዚአብሔርን አሳብ እንደግል አሳብ አቅልሎ የማቅረብ ሂደት ነው፡፡ እንዲህ ያለው መንገድ እግዚአብሔር የሚለውን ሳይሆን እኛ መናገርና ሕዝቡ መስማት የሚፈልገውን ነገር በአቅርቦት ማርካት ነው፡፡ ይህ ተናጋሪውንና ሰሚውን ደስ ቢያሰኝም በእግዚአብሔር ዓይኖች ፊት ግን ከፍርድ አያመልጥም፡፡
         ታዲያ እኚህ አባት መንጋትና መምሸትን የሚያዘው ማነው? መፍጠርና ማኖርስ ሥልጣኑ የማን ነው? በሚል ጀምረው ክረምትንም የሚሰጥ፣ ዝናምንም የሚያዘንብ እግዚአብሔር እንደሆነ ተናገሩ፡፡ በልጆቹ ፊት ላይ ይነበብ የነበረው ደስታና የ“ተረድተናል” ምላሽ አስገራሚ ነበር፡፡ በማስከተልም ከዝናብ ጋር አያይዘው ስለ ተፈጥሮአችን ለልጆቹ ማውጋት ቀጠሉ፡፡ “እግዚአብሔር አፍንጫችንን ወደ ላይ አድርጎ ቢሠራው ኖሮ ዝናብ ሲዘንብ ትንንሽ የአፍንጫ ጥላ እንገዛ ነበር፡፡ ታዲያ ድሀ ከየት ያመጣ ነበር?” ሲሉ ሕፃናቱን ጨምሮ ሁላችንም ሳቅን፡፡ መልእክቱ ለሕፃናቱ ተብሎ የተነገረ ቢሆንም እንኳን አዋቂዎችንም የመስበር (የመንካት) አቅም ነበረው፡፡ ከዚህ ምን ተረዳችሁ? እግዚአብሔርን ለማመስገን ከበቂ በላይ ምክንያት አልታያችሁም? ትንንሽ የሚመስሉን ነገሮች ለእግዚአብሔር ትልልቅ ምስጋና የያዙ ስውር ምክንያቶች ናቸው፡፡
        የመገብከኝ እግዚአብሔር ተመስገን ስንል ስለጎረስኩበት እጅና ስለጎረሰው አፌ ተመስገን የምንል ስንቶቻችን ነን? ስለሰማነው የምስራች በእግዚአብሔር ደስ ስንሰኝ ስለሰማንበት ጆሮ የምናመሰግን ምን ያህሎቻችን ነን? ለሚያስተውል ሰው መራመድ፣ ማላመጥ፣ መናገር፣ ማየት ቀላል ሊሆን አይችልም? እኛ ምግቡ ብቻ፣ መሬቱ ብቻ ነው የእግዚአብሔር የሚመስለን፡፡ በእርግጥ እንደ ተባለው አፍንጫ ወደ ላይ ቢሆን ኖሮ ለዚህም መፍትሔ አፈላላጊ ይቋቋም ነበር፡፡ ድሀ ደግሞ በጥላ ካልተሸሸገ አፍንጫን በመኪና ማስጠለል ከየት ይመጣል? እግዚአብሔር በማንኛውም ነገር ላይ አዋቂ ነው!
        አስባችሁት ከሆነ እኛ መቃብር እስክንገባ እንኳን በአግባቡ የማናውቀው የሰውነት ክፍሎች ያሉን ሰዎች ነን፡፡ ምግብ መመገብ የጀመርነው ጨጓራ እንደሚፈጭ በማናውቅበት ሰዓት ነው፡፡ ከመተንፈስ ጋር የተዋወቅነው ስለ ልብ ምት የሰናፍጭ ቅንጣት የምታህል እውቀት ሳይኖረን በፊት ነው፡፡ እግዚአብሔር ምን ለምን እንዳደረገ በሙላት ያውቃል፡፡ አንዳንዴ አንዱ የአካል ክፍላችን ከሌላው ጋር ቦታ ቢቀያየር ምን ዓይነት ገጽታ እንደሚኖረን ስናስበው እንደመማለን፡፡ ሰይጣን የእግዚአብሔርን ምስጋና የሚሰርቅበት መንገድ ያለንን አሳንሶ የሌለንን በማብዛት፣ የያዝነውን አደብዝዞ የሌለንን በማጉላት ነው፡፡ ከዚህ ሁሉ ትበላላችሁ የሚለው ካላረካን ከዚህች አትብሉ ላይ መውደቃችን የተፈተነ እውነት ነው፡፡
        አንድ ትጉህ አመስጋኝና ዋዘኛ ተገናኙ፡፡ ታዲያ ትጉሁ እግዚአብሔር እስራኤልን በኤርትራ ባህር ያሻገረበትን ታሪክ እያሰበ ሁሉን ቻይነቱን ያመሰግናል፡፡ ይህንን የሰማው ዋዘኛ እርሱ አመስጋኙ እንደሚለው ባህር እንዳልነበረና አነስተኛ ጉድጓድ እንደነበረ በመሆኑም ለዚህ ምንም ማመስገን እንደማይገባ ተናገረ፡፡ ትጉሁም አመስጋኝ ከልብ በሆነ ፈገግታ ውስጥ ሆኖ “አሁን ደግሞ የደነቀኝ እግዚአብሔር ፈርዖንና ሠራዊቱን በጠባብ ጉድጓድ ውስጥ ማስጠሙ ነው” በማለት የዋዘኛውን ተቃውሞ ለበለጠ ምስጋና ተጠቀመበት፡፡ እኛ አጥተን የምናማርረውን ምሬት ተርፎአቸው የሚያማርሩ አሉ፡፡ ክርስትናውን ልዩ የሚያደርገው ግን በመብዛት ብቻ ሳይሆን በመጉደልም ውስጥ ለጌታ የምስጋናን ነዶ ማቅረብ መቻሉ ነው፡፡ እኛ አጠገባችን ላለ ነገር ሩቅ፣ ለጨበጥነውም ነገር ስውር ነን፡፡ ስለዚህ ኑሮዬ ይበቃኛልን መለማመድ ለእኛ ከባድ ነው፡፡
         ለዝናም እንጂ ለብርድ፤ ለፀሐይ እንጂ ለሙቀት፣ ለአካል እንጂ ለነፍስ ገበያ ጥላ የለውም፡፡ ልዑል ግን መጠጊያችን ነው፡፡ ሁሉን የሚችል አምላክ ጥላም ማደሪያችን ነው፡፡ ላባዎቹ ይጋርዱናል፡፡ በክንፎቹም በታች ለዘላለም እንተማመናለን፡፡ ምስጋና ይብዛላችሁ!