Wednesday, May 29, 2013

እየሆነ ያለው . . . (ክፍል ሁለት)


                                            እሮብ ግንቦት 22/2005 የምሕረት ዓመት

       ተወዳጆች ሆይ እንደምን ለዛሬ ደረሳችሁ? ዛሬ ብዙ ናት፡፡ በእጃችን እንዳሉ ከምናስባቸውና በብዙ ዋጋ ከማይተመኑ ነገሮች ሁሉ በላይ ናት፡፡ ለዛሬ ክብር ያልሰጡ በትላንት እየተጸጸቱ፣ በነገ ደግሞ እየሠጉ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ቃል መዳንን የሚያህል ስጦታ ያኖረው “ዛሬ” ላይ ነው (2 ቆሮ. 6÷2)፡፡ ዛሬ ለምትወዷቸው ፍቅራችሁን፣ ለበደሏችሁ ይቅርታችሁን፣ ለዕለቱ ትጋታችሁን፣ ለሚፈልጓችሁ ቸርነታችሁን የምታሳዩበት ዕድል ነው፡፡ ጌታን ለማመስገን ይህ ምንኛ የላቀ ምክንያታችን ይሆን?

      በፍቅር የምወዳችሁ ሆይ ስለ ዘላለም የሚያወራን እግዚአብሔር ነው፡፡ የዘላለም ወሬም ተግባርም የእርሱ ብቻ ነው፡፡ ሰው እንኳ ተግባሩ ንግግሩም አይጸናም፡፡ ዘመናችን ሰው በሰው ከመቼውም ይልቅ ያዘነበት፣ የተዛዘበበትና ለክፉ የተሰጣጠበት ነው፡፡ ጊዜያዊው ነገር የዘላለም ያህል ተስሎብናል፡፡ ለሚያልፈው እየተጣላን ለቋሚው መሽቶብናል፡፡ እንደ ልባችን የሆኑ ነገሮች የማያፈናፍኑ እሾህና አሜኬላ ሆነውብናል፡፡ እርሱ ጌታ ግን የዘላለም መሠወሪያ ነው፡፡ ስለ ዘላለማዊው መኖሪያ የነገረን የዘላለም መጠጊያችን ነው፡፡ ብዙ ሰው እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ያለው ግንኙነት በሚታየውና በሚያልፈው ነገር ላይ እንደተመሠረተ በተግባር ያስባሉ፡፡ እግዚአብሔር ግን የዘላለም አምላክ ነው፡፡ ምክርና ተግባሩም እንደዚሁ ነው፡፡ እርሱ ለእኛ ያለው አሳብ ጊዜያዊ ቢሆን ሰውን እንደ ሆነ ባሰብነው ነበር፡፡ ዳሩ ግን ለእኛ ያለው አሳብ ዘላለም ነው፡፡ የእርሱ ነገሮች ሁሉ ይህንን ያህል ዋጋ የተሸከሙ ናቸው፡፡

       በጌታ የተወደዳችሁ ሆይ ከሚናፍቃችሁ ልብ ሰላም ይብዛላችሁ፡፡ ዛሬ ዋጋዋ የዘላለምን ያህል እንደ ሆነ ተረድታችሁልኛል ብዬ በጌታ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ዛሬ ጀርባ ላይ ከዘላለም ሞት ወደ ዘላለም ሕይወት ሰዎች ሁሉ የሚሻገሩበት እድል መኖሩ ነው፡፡ እስቲ ደግሞ እግዚአብሔር ከበትሩ ጋር በበጎች መሐል ዱር ያገኘውን ብላቴና ከኑሮአችን ጋር አያይዘን እንማርበት፡፡ ስለ ነቢዩ ዳዊት መጠራትና ለእግዚአብሔር ዓላማ በተግባር ወደ መለየት የመጣበትን መንገድ ብዙዎቻችሁ ወይ ተሰብካችሁ አልያም አንብባችሁ እንደማትስቱት ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ እግዚአብሔር ይህንን ብላቴና በአባቱ መረሳትና በወንድሞቹ ቸል መባል (በሚጠሉት) መሐል ራሱን እንዴት ባለ ሁኔታ በዘይት እንደቀባ ለእናንተ መንገር ለቀባሪው እንደማርዳት ነው፡፡ በመሐል የሚገርመኝ አንድ ነገር አሳቤን ወደ ፊት አላራምድ አለውና ላካፍላችሁ ታዘዝኩት፡፡ ምን መሰላችሁ! ብዙ ጊዜ በየምሕረት አደባባዩ ሰዎችን እልል ስለሚያሰኛቸው አገልግሎት ሳስብ ዳዊትና ጎልያድ፣ ጠጠርና ሰይፍ ይታወሱኛል፡፡

Wednesday, May 22, 2013

እየሆነ ያለው . . . (ክፍል አንድ)


                             እሮብ ግንቦት 14/2005 የምሕረት ዓመት

         የእግዚአብሔር ጸጋና ሰላም፤ ምሕረትና ፍቅር የበዛላችሁ፤ መኖራችሁ ከዚህ የተነሣ እንደ ሆነ የአፍና የልብ ምስክርነት ያላችሁ ተወዳጆች ሆይ ሕይወት እንዴት ነው? መቼም ሰው ሁሉ እንደ አንድ የሚጠላው ጥያቄ ይህ ይመስለኛል፡፡ በእርግጥ ጥያቄው ከተሸከመው ቁም ነገር የተነሣ ቢከብደን የሚገርም አይሆንም፡፡ በዚህ ምድር ከሕይወት በላይ የበለጠ ምን ርዕስ ሊኖር ይችላል፡፡ የእግዚአብሔር ልጅ ራሱን ያብራራበት ትልቁ መንገድ “ሕይወት ነኝ” የሚል ነው (ዮሐ. 14÷6)፡፡ የየትኛውም ቤተ እምነት አስተምህሮ ለሕይወት ዋጋ ይሰጣል፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ልክ እንደ መጽሐፉ “ወልድ የሌለው ሕይወት የለውም” (1 ዮሐ. 5÷2) በማለት ዕለት ዕለት ትመሰክራለች፡፡

         በእድሜያችሁ ከሰዎች ጋር በብዙ ዓይነት ርዕስ እንዳወራችሁ እገምታለሁ፡፡ ዳሩ ግን ምን ያህሉ ሕይወት ነበረበት? አልያም ምን ያህሉ የሕይወትን ያህል ዋጋ ነበረው? የእግዚአብሔር ቃል “አንተ ግን ሕይወት ለሚገኝበት ትምህርት የሚገባውን ተናገር” (ቲቶ. 2÷1) በማለት ያስጠነቅቀናል፡፡ ይህ ቃል ተናጋሪውን ብቻ እንደሚመለከት ልታስቡ ትችላላችሁ፡፡ ዳሩ ግን ለሰሚውም የዚያኑ ያህል መልእክት አለው፡፡ የስንቶች ጆሮ ስለ ሕይወት ለመስማት ወኔው አለው? ብለን ብንጠይቅ መልሱ ምላሳችን ላይ ነው፡፡ እንዲህ ያለውን ጥያቄ ለራሳችን ባቀረብንባቸው ጊዜያቶች ሁሉ ከውስጠታችን ጋር ተዛዝበናል፡፡

       አሁን በዚህ ሰዓት በሚሊዮን የሚቆጠር ሕዝብ በአንድም በሌላም ምክንያት ተገናኝቶ በብዙ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ያወራል፡፡ መረጃ ይለዋወጣል፡፡ ይከራከራል፡፡ ደግሞም ይካሰሳል፡፡ እባካችሁ በሁላችንም ሞት ይሁንባችሁና አሁን በዚህ ቅጽበት በምን ርዕሰ ጉዳይ ላይ እያወራችሁ እንደ ሆነ ቆም ብላችሁ አስተውሉ፡፡ የማታወሩ ደግሞ ካላስቸገርኳችሁ በምን ርዕሰ ጉዳይ ላይ እያሰባችሁ እንደ ሆነ አስተውሉ፡፡ በዚያ በምታስቡት አልያም በምታወሩት ውስጥ ሕይወት የሆነው ነገር ምን ያህል ይሆናል፡፡ እግዚአብሔር ሚዛን ላይ ይቅርና እናንተ ሚዛን ላይ እንኳ ክብደቱ ስንት ነው? ብዙ ዜናዎችን የምትከታተሉ ከሆነ የሰዎች ቀልብ የሚሰለብበት፣ ዓይን ፈጦ ጆሮ የሚቆምበት ምን ዓይነቱ የወሬ ርዕስ ነው? መርዶ መርዶው አይደለምን? ሰውን እንዲህ ካለው የሞት ወሬ ጋር ያያዘው ጉዳይ ምን ይሆን? ድህነት ነውን? አለመሰልጠን ነውን? ወይስ አማራጭ ማጣት ይሆን? ወይስ . . . . !

Wednesday, May 15, 2013

የሰው ልጅ እንጀራ



                                 እሮብ ግንቦት 7/2005 የምሕረት ዓመት

         አገልግሎት አንድ አካል ብቻውን የሚያደርገው ነገር ሳይሆን ሁሉም ምዕመን ተገናዝቦና ተባብሮ የሚያከናውነው ተግባር ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን እንደ ክርስቶስ አካል በምትተረጎምበት ሁኔታ እኛ ሁላችን የክርስቶስ አካል ብልቶች ነን (ሮሜ. 12÷5)፡፡ ሁላችንም በአንዱ ክርስቶስ አንድ ልብ አለን (1 ቆሮ. 2÷16) አንዲሁም አንዱን ምግብ (የእግዚአብሔር ቃል) ሁላችን እየተመገብን በህብረት እናድጋለን፡፡ ነገር ግን ጤነኛ ምግብ መመገባችንን እርግጠኛ ልንሆን ይገባል፡፡ መመገብ ውድቀትን ተከትሎ የመጣ እርግማን አይደለም፡፡ ከሰው ተፈጥሮ ጋር የተያያዘ የእለት ከእለት ተግባር እንጂ፡፡ በውኑ ምንድነው የምንመገበው? ክርስቶስ በምድር  ላይ ሲመላለስ በአንድ ወቅት በሰማርያ ደክሞት አረፍ ብሎ ነበር፡፡ ያን ጊዜ ደቀ መዛሙርቱ እንጀራ ሊገዙ ሄደው ነበር መጥተውም ብላ ብለው ይለምኑት ጀመር፡፡ እርሱም የበላ መሆኑን ሲገልጽላቸው ሰው አምጥቶለት ይሆንን ተባባሉ እርሱ ግን የእኔስ መብል የላከኝን ፈቃድ አደርግ ዘንድ ሥራውንም እፈጽም ዘንድ ነው አላቸው (ዮሐ. 4÷34)፡፡

         እንግዲህ ክርስቶስ ሊያገለግል እንጂ ሊገለገል አልመጣም (ማቴ. 20÷8) እንደተባለው እርሱ በምድር በተመላለሰበት የሥጋው ወራት ሁሉ የአባቱን ፈቃድ ማድረግ ቋሚ ትጋቱ ነበረ፡፡ ወደዚህ ዓለም የመጣበትን እውነተኛ ዓላማ እስኪፈጽም ድረስም እረፍት አልነበረውም፡፡ መብሉ የአብን ፈቃድ መፈጸም ነበርና መንፈሳዊ ርሀብ አልነበረበትም፡፡ ጌታ በቃልና በኑሮ አባቱን ደስ ያሰኘ ልጅ ነበር፡፡ በሙላት የተመገበ ሰው ለአባቱ ደስታ ነው፡፡ እኛም ይሄ ነው! የተጠራንለት ዓላማ ሁሌም ፈቃዱን መፈጸም ሁሌም ቃሉን መመገብና በቃሉ መሞላት፡፡

Friday, May 10, 2013

የእንባ መባ


                  አርብ ግንቦት 2/2005 የምሕረት ዓመት



እንባ ነው መባዬ አንተን መቅረቢያዬ
እንባ ነው መባዬ ውዴን መቅረቢያዬ
ሌላማ ምን አለኝ የምከፍልህ የለኝ /2/

                                  ገና በማህፀን የምታውቀኝ
                                  ከእናቴ አስቀድመህ ያየኸኝ
                                  የዘመኔ ጌታ የእድሜዬ
                                  መከበሪያዬ ነህ ግርማዬ

Wednesday, May 8, 2013

የቀርሜሎሱ ጽናት



                                        እሮብ ሚያዝያ 30/2005 የምሕረት ዓመት      

    በዕብራይስጥ ቀርሜሎስ ማለት ፍሬያማ ማለት ሲሆን ኤልያስ በተገለጠ ሁኔታ ብቻውን ከእግዚአብሔር ጋር የቆመበት፣ አምላኩን እንደማያሳፍረው የተወራረደበት ተራራ ነው (1 ነገ. 18)፡፡ ታዲያ በዚህ ተራራ ላይ የኤልያስን ጽናት በግልጥ እንመለከታለን፡፡ በተለይ ከዝሙት ጋር በተያያዘ በአምላኩ ፊት ያሳየውን የእምነት ብርታት እናስተውላለን፡፡ ምክንያቱም እስራኤላውያን ለእግዚአብሔር ጀርባቸውን ሰጥተው ያመልኩት የነበረው በኣል (ጣዖት) አምልኮ ይፈጸምለት የነበረው በዝሙት፣ ራስን በማጎሳቆልና ሰውን መሥዋዕት አድርጎ በማቅረብ ነበር፡፡ ታዲያ ኤልያስ ለእግዚአብሔር እስራኤል ለጣዖታቸው የአምልኮ ሥነ ስርዓት ለመፈጸምና መሥዋዕት ለማቅረብ ተራራው ላይ በተሰበሰቡ ጊዜ የእግዚአብሔር ሰው ኤልያስ እያንዳንዱን ትዕይንት በዓይኑ ተመልክቶአል፡፡

Monday, May 6, 2013

አንተ ጎንበስ . . . . !



                         

አንተ ጎንበስ እኔ ቀና
የእሾህ አክሊል ደፋህና
የእኔን ላንተ ያንተን ለእኔ
እንዴት ላውራው በምን ቅኔ
                           ሳትበደር አንተው ከፋይ
                           ተመሳቅለህ መስቀሌ ላይ
                           ባለ ዕዳው በነፃነት
                           ተቀመጥኩኝ በሰገነት
መቼ ገብቶኝ ያንተ ነገር
ተጠቅልዬ በሞት ባህር
ፍቅር ፍቅር የሚሆነው
ለካ እንዲሁ ሲወዱ ነው

Wednesday, May 1, 2013

የአብ ቤት ማብራሪያ (ጎጆዬ)


እሮብ ሚያዝያ 23/2005 የምሕረት ዓመት

“. . . በቀን ከሙቀት ለጥላ፤ ከዐውሎ ነፋስና ከዝናብም ለመጠጊያና ለመሸሸጊያ ጎጆ ይሆናል (ኢሳ. 4÷6)”

          የእግዚአብሔር ቃል በማይቋረጥ ዋስትናና በማይታጠፍ ቃል ኪዳን የተሞላ ነው፡፡ በሰው ታሪክ ዋስትናና ቃል ኪዳን ሲከተሉን የሚኖሩ ብርቱ ፍላጎቶቻችን ናቸው፡፡ እግዚአብሔር ከሰው ጋር ያለው ግንኙነት እነዚህን ብርቱ መሻቶች ያሟላ መሆኑ እርሱን የዘላለም መጠጊያ እናደርገው ዘንድ ያስችለናል፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ምድር ሰው ሆኖ በሰው መካከል በተመላለሰበት ጊዜ ሕሙማን እንደ ተፈወሱ፣ የተራቡ እንደ ጠገቡ፣ የተናቁ ወደ ክብር እንደ መጡ፣ የተጠሉ ኃጢአተኞች ወዳጅ እንዳገኙ፣ የታወሩ ዓይኖች እንዳዩ፣ የደነቆሩ ጆሮዎች እንደ ሰሙ፣ የሰለሉ አካሎች እንደ ተዘረጉ በቅዱሱ መጽሐፍ ውስጥ በግልጥ ተጠቅሷል፡፡ ዳሩ ግን በዚህ ምድር ለማንም መኖሪያ ቤት እንደ ሠራ አልተፃፈም፡፡ ራሱ ጌታ እንኳ ከአእዋፋት ባነሰ ሁኔታ ራሱን የሚያስጠጋበት ቤት የሌለው ሆኖ ነው የተመላለሰው (ማቴ. 8÷20)፡፡

          ሰው ተሰማርቶ መሰብሰብን ሲያስብ ቤትን ያስባል፡፡ ሰው ተከፍቶ ማልቀስ ሲፈልግ ቤቱ ማሳለፍን ይመርጣል፡፡ ደስታውንም ሀዘኑንም “የሚችለኝ ቤቴ ነው” ብሎ ለማሳለፍ በዚያ መሆን ይቀናዋል፡፡ ሰው ቢጥመውም ቢመረውም ዞሮ ዞሮ ቤቱ ይገባል፡፡ ቤቱ በጎም ይቆየው ክፉ ተመልሶ ይመጣል፡፡ ምክንያቱም ቤቱ ነው፡፡ አደባባይ ላይ በብዙ ወዳጅ የተከበበ ሰው፣ ባማሩ ሆቴሎች ሲጋበዝ፣ መናፈሻ ለመናፈሻ ሲዞር፣ አንቱታና ውዳሴ ሲጠግብ የዋለ ሰው ሲመሽ የሚሰበሰበው እንደ አቅሚቲ በሠራት ቤት ውስጥ ነው፡፡ ተማሪ ቤት እያለሁ የቅኔ ክፍለ ጊዜ መምህራችን “ይህ ሁሉ አደባባይ ላይ የምትመለከቱት ዘናጭ መሽቶ ቤቱ ሲገባ ተከትላችሁ ብታዩት አብዛኛው ጭቃ ቤት የሚኖር ነው፡፡ እዚህ “ጦጣ መጀመሪያ የመቀመጫዬን አለች” የሚለው አባባል ስለማይሠራ የአደባባይ ለባሽ፣ የቤት ውስጥ ቀማሽ (ጠግቦ የማያድር) የበረከተበት ነው፡፡ እናም በምታዩት አትወሰዱ ትምህርታችሁን ጠንክራችሁ ተማሩ፡፡” በማለት የመከሩንን አስታውሳለሁ፡፡ ታዲያ እርሳቸው የነገሩን ምን ያህል ትክክል ነው? በማለት አንዳንድ ጥሩ ለብሰዋል ያልናቸውን ሰዎች ሲመሽ ተከትለን ለማረጋገጥ በሞከርንባቸው ጊዜዎች መምህሩ የነገሩን እውነት እንደ ሆነ አመሳክረናል፡፡ በእርግጥም ሰው አደባባይ ላይ ቢያጌጥ ቢደምቅ፣ ቢከበር ቢወደድ መጨረሻው መጠለያው ናት፡፡ ብታዘምም ብትቆምም ቻዩ ያችው ቤቱ ናት፡፡    

          ጌታ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ብዙ ነገር አውርቶአል፡፡ እነርሱም የሕይወት ቃል ባለው በእርሱ ነፍሳቸው ሐሴትን አድርጋለች፡፡ ሥጋቸውም በሚፈፀም ተስፋ አድራለች፡፡ አንድ ጊዜ ግን ልባቸውን የሚያውክ ነገር ገጠማቸው (ዮሐ. 14÷1-7)፡፡ እርሱም ጌታ እንደሚሄድ ሲነግራቸው ነው፡፡ ለሰው ልጅ ከባድ ከሆኑ ነገሮች አንዱ ስንብት ነው፡፡ በተለይ ቁርጥ ሲሆን መለያየት ይከብዳል፡፡ መለያየትን ሊቃውንቱ በሦስት መንገድ ይከፍሉታል፡፡ የመጀመሪያው በቦታ መለያየት ሲሆን በዚህ ውስጥ የመንፈስ አንድነት አለ፡፡ ሁለተኛው መካካድ ሲሆን በዚህ ውስጥ ጠንካራ ቅራኔ አለ፡፡ ሦስተኛው ቀብሮ መመለስ ሲሆን በዚህ ውስጥ ደግሞ ብርቱ ሀዘን አለ፡፡ ጌታ ግን ደቀ መዛሙርቱን “ልባችሁ አይታወክ” በማለት አጽናናቸው፡፡ እርሱ ብቻ ስለ ሰው ልብ ይዞታ ሊናገር ድፍረት አለው፡፡ ሰው ከፊታችንና ከሁኔታችን ነገሮችን ለመፈረጅ ይቸኩላል፡፡ ጌታ ግን የልብ ነው፡፡ እርሱ ሲናገር ከልብ ይጀምራል፡፡  እርሱ ከጥርሳችን ፈገግታ ባለፈ፣ ከልብሳችን ንጽሕና በዘለቀ የተሰወረውን መታወክ ያውቃል፡፡ እርሱ ለአፋችን ቅርብ ሰሚ ሳይሆን ለልባችን የቀረበ አዳማጭ ነው፡፡ ለልባችን መታወክ ቅርብ መጽናኛ ኢየሱስ ነው!

          ደቀ መዛሙርቱ ስለ ልባቸው መታወክ ጌታን አላስረዱትም፡፡ ሊያስረዱትም አይጠበቅባቸውም፡፡ እርሱ ሁሉን የሚያውቅ ነው፡፡ ከእርሱ ማወቅ የተሰወረ ነገር የለም፡፡ የፀጉራችሁ ቁጥር በእርሱ ዘንድ የታወቀ ነው፡፡ ከዓይኑ እይታ ውጪ ሊሆን ማን አቅም አለው? ከማወቁስ ሊሰወር ማን ይቻለዋል? ሁሉን በሚችል በእርሱ ፊት ማን በኃይሉ ይበረታል? ልቦችን ሁሉ እርሱ ያውቃል፡፡ ይህንን እያነበባችሁ በዚህ ሰዓት በልዩ ልዩ ጉዳይ የምትታወኩ ወገኖቼ ሁሉ ጌታ የልባችሁን መታወክ ያርቅላችሁ፡፡ ሰሜን ከምስራቅ እንደሚርቅ ጌታ ጭንቀታችሁን ያርቅ፡፡ ሌላም ትኩረት  ልንሰጠው የሚያስፈልገንን ትምህርት በዚሁ ክፍል ላይ እናገኛለን፡፡ የአብዛኛው ሰው መታወክ ምክንያቱ ምን ሊሆን ይችላል? ለሚለው ጥያቄ ጌታ “በእግዚአብሔር እመኑ፤ በእኔም ደግሞ እመኑ” በማለት ለሁከት የምንጋለጥበትን ትልቅ ምክንያት “የአለማመን ጠንቅ” ይነግረናል፡፡ “እነርሱ በእምነት መንግሥታትን ድል ነሡ፣ ጽድቅን አደረጉ፣ የተሰጠውን የተስፋ ቃል አገኙ፣ የአንበሶችን አፍ ዘጉ፣ የእሳትን ኃይል አጠፉ፣ ከሰይፍ ስለት አመለጡ፣ ከድካማቸው በረቱ፣ በጦርነት ኃይለኞች ሆኑ፣ የባዕድ ጭፍሮችን አባረሩ (ዕብ. 11÷33)” ተብሎ እንደ ተፃፈ ዓለምን የምናሸንፍበት ኃይል ያለው እምነት (ከእግዚአብሔር ለተወለዱ ብቻ) ውስጥ ነው፡፡ 

1. በእግዚአብሔር እመኑ፡- በእግዚአብሔር ማመን ማለት በአንድነቱና በሦስትነቱ ማመን ነው፡፡ በአካል ሦስትነት በግብር አንድነት የተገለጠ አምላክ እግዚአብሔር እርሱ ብቻ ፈጣሪ እንደ ሆነ በልብ መቀበልና ማመን ነው፡፡ ሁሉን አዋቂነት፣ በሁሉ መገኘትና ሁሉን መቻል የእርሱ ብቻ እንደ ሆነ መረዳትና ማመንም ይገባል፡፡ ልባችን ለዚህ እውነት በተሸነፈበት ዘመን ሁሉ እውነተኛ አማኞች ነን፡፡