Wednesday, June 26, 2013

የንጉሥ እልልታ


                          እሮብ ሰኔ 20/2005 የምሕረት ዓመት

“በያዕቆብ ላይ ክፋትን አልተመለከተም፡፡ በእስራኤልም ጠማምነትን አላየም፡፡ አምላኩ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ነው፡፡ የንጉሥም እልልታ በመካከላቸው አለ (ዘኁ. 23÷21)”

         በምድሪቱ ላይ መኖርን የታደሉ ሰዎች ሁሉ አንዱ ከሌላው ጋር አብሮ በመኖር ውስጥ ያለውን ጣዕምና ምሬት በአግባቡ ያውቃሉ፡፡ እንደ ሰው እንዲኖሩን ከምንፈልጋቸው ቁሳቁሶች በላይ ሰዎች በዙሪያችን መኖራቸው እጅግ አስፈላጊ ነው፡፡ አውራኝና ደስ ይበለኝ፤ አናግሪኝና እንቅልፍ ይውሰደኝ የሚሉ ሰዎችን ሳስባቸው አንዳችን በሌላችን ላይ ሊኖረን የሚችለውን አዎንታዊም ሆነ አሉታዊ ተጽእኖ አስተውላለሁ፡፡ እስቲ ለመኖር እንድትጓጉ፣ ለመሥራት እንድትተጉ፣ በፍቅር እንድትመላለሱ፣ ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም እንድትኖሩ በምክርና በምሪት የተጉላችሁን ሰዎች አስቧቸው፡፡ በምታምኑት አምላክ ስምም ባርኳቸው፡፡

         ሰዎች ከእኛ ጋር መሆናቸው፣ በሀዘንና በደስታ ዙሪያችንን መክበባቸው ምንኛ ግሩም ነው? አንዳንዴ አፋችንን ሞልተን በመተማመን የምንደገፍባቸው ሰዎች እንኳ በቁጥር ብዙ ናቸው፡፡ ታዲያ እንደማይጥሉን ተማምነን በመንገድ የተካካዱን፣ ላንለያይ በቃል ኪዳን ተሳስረናቸው በጥላቻ የተቆራረጡን፣ ብዙ ጠብቀንባቸው የውኃ ሽታ የሆኑብን የዚያኑ ያህል ናቸው፡፡ በእርግጥም ሰውን ክንድ ማድረግ እርግማን ነው (ኤር. 17÷5)፡፡ የእግዚአብሔር ኪዳን ግን የማይሻገረው የለም፡፡ ክንዱ የዘላለም ዋስትና ነው፡፡ እርሱ ከእኛ ጋር ያለው ኪዳን በደም የሆነ ነው፡፡ ሁኔታዎች ቢቀያየሩ፣ ነገሮች እንደ ነበሩ ባይቀጥሉ፣ የሰዎችን ብርታት ድካም ቢፈራረቀው፣ ጠላት ለእልልታ አፉን ቢያሰፋ፣ ከሥጋና ከደም አልቆ ቢቆረጥ ተስፋ እርሱ እግዚአብሔር ያውና ሕያው ነው፡፡ እውነቱ በሰዎች እውነተኛነት ላይ፣ ጽድቁ በሰው ጽድቅ ላይ፣ ቅድስናው በሰዎች ቅድስና ላይ የተመሰረተ አይደለም፡፡ እርሱ ሁሉን የሚቀድስ ቅዱስ፣ የሚያጸድቅ ፃድቅ፣ የምናውቅበት ሀቅ ነው፡፡

Wednesday, June 5, 2013

የሚያስመካ እኔነት


                                እሮብ ግንቦት 29/2005 የምሕረት ዓመት

         እግዚአብሔር ለሙሴ “ያለና የሚኖር እኔ ነኝ” ብሎ ያህዌ የሚለውን ስሙን በብሉይ ኪዳን እንደ ገለጠለት ከቃሉ እንረዳለን (ዘፀ. 3÷14)፡፡ ጌታ ደግሞ ለአይሁድ ሲናገር፡- “አብርሃም ሳይወለድ እኔ አለሁ (እኔ ነኝ)” (ዮሐ. 8÷58) በማለት አምላክ የሆነ የአምላክ ልጅ መሆኑን አስረዳቸው፡፡ እርሱ ጌታ፡-
1. በልቶ አለመጥገብ በሚስተዋልበት፣ ሰው ከብዙ እንጀራው ጋር ሆኖ በጠኔ በሚሰቃይበት በዚህ ዓለም ምድረ በዳ ውስጥ የማይቋረጥ እንጀራ ኢየሱስ ነው፡፡ ለርሀባችን መጥገብ ልኩ ይህ እንጀራ ነው፡፡ ለሕይወት ዋስትናን፣ ለዕድሜ ልምላሜን፣ ለትጋታችን ፍፃሜን የሚሰጥ እንዲህ ይላል፡-
Ø “የሕይወት እንጀራ እኔ ነኝ” (ዮሐ. 6÷35)!

2. ምድሪቱ ላይ ፀሐይ ስትወጣና ስትጠልቅ ማየት ልባችን በተለየ ሁኔታ የማያስተውለው ልምምድ ነው፡፡ ዳሩ ግን በብዙ ሰዎች ልብ ላይ ፀሐይ ብርሃኗ ስፍራን አላገኘም፡፡ የጭፍን አስተሳሰብና የጭፍኖች ተግባር ምድሪቱን ማስጨነቁም ከዚህ ገሀድ የተነሣ ነው፡፡ ሰው ውጫዊ አካባቢው ቢጨልም፣ የእጁ ሥራ መኖሪያ ቤቱን ጨለማ ቢሞላው ሻማ ይለኩሳል፡፡ ሰው ግን ከልቡ ጨለማ ጋር እስከ ሞት ለሞኖር መቁረጡ ምንኛ ያሳዝናል? ዙሪያ ገባው ለጨላለመባችሁ፣ የጠራ የነፃ አልታይ ላላችሁ፣ ዓይን ፈጥጦ ልብ ለታወረባችሁ ጨለማን የሚያጋልጠው፣ ከዚህ እስራት ለዘላለም የሚፈታው እንዲህ ይላል፡-

Ø “እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ” (8÷12)!

3. ለዓለም ሁሉ ኃጢአት የመሥዋዕት በግ ሆኖ ራሱን ያቀረበው ጌታ የወዳጅ ልክ ነው፡፡ ወዳጅነት ሁሉ በእርሱ ይለካል፡፡ የፍቅር ሚዛን እርሱ ነው፡፡ የመውደዱ ፍፃሜ እኛን በእርሱ መጠቅለል ነው፡፡ በእውነተኛ ፍቅር እጮኛውን የሚወድ ባል የልብ ናፍቆቱ ሴቲቱን መጠቅለል(የብቻ) ነው፡፡ እርሱ የልቡን እልፍኝ፣ የሰማይን ደጆች የከፈተልን ነው፡፡  በዚህ ምድር ላይ ብዙ የተዘጉብን ነገሮች ይኖራሉ፡፡ አንዳንዴ መኖራችንን የሚወስኑልን ነገሮች እስኪሆኑ ድረስ በተስፋ መቁረጥ እንሞላለን፡፡ ክርስቶስ ግን ለእኛ ማንም የማይዘጋው በር አለው፡፡ የማንም ጣልቃ ገብነትና ሰብቅ እርሱን አያስጨክነውም፡፡ በጎቹን የሚወድድ፣ በስስት ዓይንና በፍቅር ልብ የሚመለከተን እንዲህ ይላል፡-