Wednesday, July 31, 2013

ካፈርኩ አይመልሰኝ (ካለፈው የቀጠለ)


                                እሮብ ሐምሌ 24/2005 የምሕረት ዓመት

“ቃየንም ወንድሙን አቤልን፡- ና ወደ ሜዳ እንሂድ አለው። በሜዳም ሳሉ ቃየን በወንድሙ በአቤል ላይ ተነሣበት፥ ገደለውም” (ዘፍ. 4÷8)፡፡

        ግንኙነትን አስመልክቶ የሚያሻክሩ ምክንያቶችን ከአንድ እስከ አምስት ነጥቦች ባለፈው ንባባችን ለማየት የሞከርን ሲሆን በዚህ ክፍል ደግሞ ቀሪ ምክንያቶችን የምንዘረዝርና ርእሳችንን በደንብ የምናብራራ ይሆናል፡፡

6. ሁሉም ጥሩ ወይም ሁሉም መጥፎ፡- እንደዚህ ያሉ ሰዎች ማንኛውንም ነገር ነጭ ነው አልያም ጥቁር ነው፣ መልካም ነው አልያም መጥፎ ነው ከማለት ውጪ ነገሮችን በሚዛናዊነት ለመዳኘትና ከተለያየ አቅጣጫ ለማየት ጥረት አያደርጉም፡፡ ሁሉም ነገር ለእነርሱ ከሁለት አንዱ ነው፡፡ እንዲህ ያለው አመለካከት ግንኙነትን ሚዛን ያሳጣል፡፡ ሁሉም መጥፎ እንደ ሆነ በምናስብበት ሁኔታ ውስጥ ስንሆን ደጉን ነገር ለመመልከት ጭፍኖች እንሆናለን፡፡ ሁሉም ጥሩ እንደ ሆነ በምናስብበት ሁኔታ ደግሞ ኑሮአችን ጥንቃቄ የጎደለው “በሬ ከአራጁ ጋር ይውላል” አይነት ይሆንብናል፡፡ ተወዳጆች ሆይ ሚዛናዊ ሁኑ!

7. ለፍርድ መቸኮል፡- በሰው የመፍረድ ዝንባሌ ግንኙነትን ጉዳት ላይ ይጥለዋል፡፡ አብዛኛውን ጊዜ በዚህ መንገድ የመተያየት ልማዳዊ አለማስተዋል ይስተዋላል፡፡ ነገር ግን በዚህ መንገድ ሰዎችን ማስተካከል አይቻልም፡፡ ደግሞ አብዝተን በምንፈርድባቸው ነገሮች ዘግይቶም ቢሆን ራሳችንን እናገኘዋለን፡፡ ታዲያ እውነተኛነት እኛ በደከምን ጊዜ ለድካማችን የምናሳየውን ርኅራኄ ለሌሎችም ውድቀት እንዲሁ ማሳየት ማለት ነው፡፡ ለመፍረድ አለመቸኮል ያበላሸ እንዲያስተካክል እድል መስጠት ነው፡፡ አለመፍረድ የወደቀ እንዲቆም መደገፍ ነው፡፡ እስቲ በዛላችሁባቸው ወራቶች በቁስላችሁ ላይ እንጨት የሰደዱባችሁን አስቡ፡፡ ምን ያህል ከባድ ነበር? እናንተ ግን ፈጽማችሁ እንዲህ አታድርጉ፡፡ ፍርድን ለጌታ ስጡ!     

8. አሳብ ማንበብ፡- ብዙ ሰዎች የሌሎችን አሳብ ማንበብ እንደሚችሉ ይሰማቸዋል፡፡ ነገር ግን እንዲህ ያለው ሁኔታ በእለት ከእለት ግንኙነቶቻችን ላይ ተጽእኖው ከፍተኛ ነው፡፡ ልትል የፈለከው ገብቶኛል . . . ገና ሳትናገር ሁኔታህ ይነግረኛል . . . ብዙ አትድከም አሳብህን መቼ አጣሁት . . . የሚሉት ቃላቶች ባይሰሙንም ግንኙነቶቻችንን እንደ ብል በልተው ለጉዳት የሚዳርጉ ልማዶች ናቸው፡፡ ማንም ሰው የሌላውን አእምሮ (አሳብ) የማንበብ አቅም የለውም፡፡ ባልተገለጠ አሳብ ውስጥ ያለው መብት የአሳቢው ብቻ ነው፡፡ በቃል አልያም በአካል እንቅስቃሴ (በተግባር) መገለጥ ያልቻለ አመለካከት ምስጢር ነው፡፡ አፍ ሲከፈት ጭንቅላት ይታያል እንዲሉ የሰዎች አሳብ ሲገለጥ ብቻ የምናየው ነገር ይኖራል፡፡ ከዚህ ባለፈ ግን ያውም አቅማችን ባልሆነ ነገር ግንኙነቶቻችንን መጉዳት አይኖርብንም፡፡

Wednesday, July 24, 2013

ካፈርኩ አይመልሰኝ!


                                  እሮብ ሐምሌ 17/2005 የምሕረት ዓመት

“ቃየንም ወንድሙን አቤልን፦ ና ወደ ሜዳ እንሂድ አለው። በሜዳም ሳሉ ቃየን በወንድሙ በአቤል ላይ ተነሣበት፥ ገደለውም” (ዘፍ. 4÷8)፡፡

       በሰው ልጆች የእለት ከእለት ኑሮ ውስጥ ትልቁም ከባዱም ነገር ግንኙነት ነው፡፡ ብዙ ወገኖች በዚህ መንገድ ይፈተናሉ፡፡ በአንድ የጦር ሜዳ ውስጥ ከጠላት ትልልቅ ዒላማዎች መካከል የግንኙነት መስመሩን ማቋረጥ ቀዳሚ አጀንዳው ነው፡፡ እግዚአብሔር እንኳ ምድርም ሁሉ በአንድ ቋንቋና በአንድ ንግግር ነበረች (ዘፍ. 11) በተባለበት ዘመን በሰናዖር ሜዳ በእግዚአብሔር አሳብ ላይ በጠላትነት በተነሡት ሕዝቦች ፊት የሰማይና የምድር ጌታ የወሰደው እርምጃ ቋንቋቸውን መደባለቅ ነበር፡፡ በሌላ አነጋገር የግንኙነት መስመራቸውን አቋረጠው ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ና የተባለው እየሄደ፣ ሂድ የተባለው እየመጣ፣ ውጣ የተባለው እየገባ፣ ቁም የተባለው እየተቀመጠ ጤናማ ግንኙነት ጠፋ፡፡ እናም መጨረሻቸው ጥፋት ነበረ፡፡

       የነገሮች ሁሉ መፍረስ ጅማሬን አስተውላችሁ እንደ ሆነ “ግንኙነት” ተጠቃሽ ነው፡፡ ውጣ ውረድ በበዛበት፣ መውጣትና መግባታችን በብዙ እንቅፋቶች በተሞላበት ዓለም ሰው በሰላም ለመገናኘቱ ዋጋ ቢሰጥ ሲያንስ ነው፡፡ ምክንያቱም መገናኘት ቀላል አይደለምና፡፡ እኛ ስንተያይ ሌሎች ጋር መለያየት፣ እኛ ሰላምታ ስንለዋወጥ ሌሎች ጋር መነካከስ፣ እኛ ጤና ይስጥልኝ ስንባባል ሌሎች ቀብር ላይ መሆናቸውን መዘንጋት የለብንም፡፡ አዘውትሬ ከእንቅልፍ ስነሣ መንጋቱን እንደተመለከትኩ በአእምሮዬ የሚመላለስ ነገር ቢኖር “መንጋት ቀላል አይደለም” የሚለው ቃል ነው፡፡ በእርግጥም እውነቱ ይህ ነው፡፡ ሌሊት ስንት አንቡላንስ ጮኋል፣ ሌሊት ስንቶች በጥይት እሩምታ ያለ በደላቸው ሞተዋል፣ ሌሊት ስንቶች ከጨለማና ከሰው ጅብ ጋር ሲታገሉ አድረዋል፣ ሌሊት ለስንቶች ሲለቀስ ታድሯል፣ ሌሊት ስንት ሰው መርዶ ሰምቷል፣ ሌሊት . . . . አዎ መንጋት ቀላል አይደለም፡፡ እያንዳንዱ ሌሊት ልክ እንደ እናት ምጥ ነው፡፡ ቀኑን የምንቀበለውም ልክ እንደ አዲስ በመወለድ ነው፡፡ ሰው በቀን ላይ የመቅጠር አቅም የለውም፡፡ እግዚአብሔር ግን በቀጠረው ቀን ሁሉን ያደርግ ዘንድ ቻይ ነው፡፡ አሁን አብራችሁ ያላችሁ እንኳን ደስ አላችሁ፡፡ ይህም ስለኖራችሁ ነው፡፡

Wednesday, July 17, 2013

የንጉሥ እልልታ (ካለፈው የቀጠለ)


               
                                እሮብ ሐምሌ 10/2005 የምሕረት ዓመት

“በያዕቆብ ላይ ክፋትን አልተመለከተም፡፡ በእስራኤልም ጠማምነትን አላየም፡፡ አምላኩ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ነው፡፡ የንጉሥም እልልታ በመካከላቸው አለ (ዘኁ. 23÷21)”

       ከዚህ በፊት በተነጋገርንበት ክፍል ድብልቅ ሕዝብ እግዚአብሔር “የእኔ” ብሎ በለየው ሕዝብ መንፈሳዊ ሁኔታ ላይ የነበረውን ተጽእኖ በዚህ ዘመን ካለው የክርስቲያናዊ ኑሮ ፈተናዎች ጋር በማዛመድ ለማየት ሞክረናል፡፡ በዚህ ክፍል በቀጥታ ከርእሳችን ጋር ወደሚዛመደው አሳብ እንገባለን፡፡ ነህምያ ባነበበው የሕጉ ክፍል ላይ ድብልቁ ሕዝብ ወደ እግዚአብሔር ጉባኤ እንዳይገባ ትዕዛዝ የተሰጠበት አንዱ ምክንያት “ይረግማቸው ዘንድ በለዓምን ስለ ገዙባቸው ነው” የሚለው ይጠቀሳል (ከሞዓብ አንፃር)፡፡ ይህ አገላለጽ ደግሞ በቀጥታ ወደ ኦሪት ዘኁልቍ መጽሐፍ ምእራፍ 23 እና 24 አሳብ ይወስደናል፡፡ የሴፎር ልጅ ባላቅ የሞዓብ ንጉሥ በነበረበት ዘመን በለዓም የእስራኤልን ሕዝብ እንዲረግምለት የተስማማበት የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ነው፡፡

       ስለ ሞዓብ ጥቂት ለማስታወስ ብንሞክር ሞዓብ ሎጥ ከታላቅ ሴት ልጁ የወለደው የሞዓባውያን አባትና የሰዶም ፍሬ ሲሆን (ዘፍ. 19÷37)፡፡ ሞዓባውያን ለእስራኤል በመንገዳቸው ሁሉ ብርቱ ፈተናና እንቅፋት የሆኑ ሕዝቦች ነበሩ (መሳ. 11÷17)፡፡ ከተግባሮቻቸውም መካከል በለዓም ሕዝቡን እንዲረግም በጀት በጅተው የተንቀሳቀሱበት ታሪክ በብዙ የአዲስ ኪዳን መጽሐፍት ውስጥ ይታወሳል፡፡ በእግዚአብሔር አሳብ ላይ የሰይጣን ብልሃትና የሥጋ ጠላትነት በግልጥ የሚስተዋል ብርቱ ተግዳሮት ነው፡፡ እንደ ሞዓብ ያለ የአሮጌው ሰው ጠባይና እንደ በለዓም ያለ የመናፍስት ሟርታዊና ሰይጣናዊ አሠራር የተቀደሰውን ማንነት ያለማቋረጥ የሚታገሉ ፈተናዎች ናቸው፡፡

       በለዓምና ባላቅ እስራኤልን ለመርገም የተጓዙበት መንገድ በፊታችን አስደናቂ ትምህርትን ያስቀምጥልናል፡፡ “በለዓምም ባላቅን፦ ሰባት መሠዊያ በዚህ ሥራልኝ፥ ሰባትም ወይፈን ሰባትም አውራ በግ በዚህ አዘጋጅልኝ አለው” (ዘኁ. 23)፡፡ ጠላት የእግዚአብሔርን ሕዝብ ለመርገም በእግዚአብሔር ፊት መሠዊያንና መሥዋዕትን መጠቀሙ በእጅጉ አስገራሚ ነው፡፡ ብዙ ማደናገሪያዎችና አመፃዎች በሃይማኖት ሽፋንና በእግዚአብሔር ስም መደረጋቸውን ስናስብ እናዝናለን፡፡ ዛሬም እንኳ በሚያፋቅረው ክርስትና መጠላላታችን፣ በረከትን እንወርስ ዘንድ ክርስቶስ በሞተለት ክርስትና ጥላ ስር ሆነን መረጋገማችን፣ እግዚአብሔርን እየጠራን ጉድጓድ መማማሳችን የምንወቀስበት ነው፡፡

       “ባላቅም በለዓም እንደ ተናገረ አደረገ ባላቅና በለዓምም በየመሠዊያው ላይ አንድ ወይፈንና አንድ አውራ በግ አሳረጉ።” ከስጦታው ባለፈ የሰጪውን ልብ የሚመረምር እግዚአብሔር ፃድቅ ነው፡፡ እግዚአብሔር በስጦታዎቻችን የሚደለል ሕፃን አይደለም፡፡ እርሱ ለእውነቱ የጨከነ ነው፡፡ ባለ ጠጋ፣ ባለ ሥልጣን፣ ባለ እውቀት፣ ባለ ጥበብ፣ ባለ ዝና፣ ባለ ኃይል . . . እነዚህ ሁሉ የእግዚአብሔርን ተግባር ቀርቶ አሳብ የማስለወጥ አቅም የላቸውም፡፡ እርሱ ለሚሠራው ነገር አማካሪ፣ ለሠራው ነገርም አስተያየት ሰጪ አያሻውም፡፡ በለዓምና ባላቅ ግን ሁሉን በሚችል አምላክ ፊት እቃቃ የመጫወትን ያህል እግዚአብሔርን እንደ እግዚአብሔርነቱ አልቆጠሩትም፡፡ እነርሱ በዘረጉት መሠዊያና ባቀረቡት መሥዋዕት ተደልሎ ሕዝቡን ለእርግማን የሚሰጥ፣ የልባቸውን እሺ የሚል አምላክ እንዲሆን አስበዋል፡፡ እርሱ ከመረጃም ከግምታችንም ልዩ ነው፡፡ እርሱ ስለ ራሱ የተናገረው ብቻ ምን ጊዜም ልክ ነው፡፡