Monday, December 30, 2013

ለልደቴ

                      Please Read in PDF: Lelidete

‹‹ለሰብእ ሰብእ ዘየዐብዮ በምንት፤
አምጣነ ኩሉ ዕሩይ በጊዜ ልደት ወሞት፡፡››
ትርጉም፡ -
‹‹ሰው ከሰው በምን ይበልጣል፤
ልደትና ሞት አንድ ያደርገዋል፡፡››  

                           (አለቃ ጥበቡ ገሜ)

       ወደዚህ ምድር መምጣት ቀላል እንዳልሆነ የነገረችኝ እናቴ ናት፡፡ ያማጠ ያውራ፡፡ የወለደ ይናገር፡፡ መወለድ ጸጋ ነው፡፡ ወላጅ፣ ስፍራ፣ ሕዝብ፣ ሁኔታ መርጠን አልተወለድንም፡፡ ዳሩ ግን ወደ ማስተዋል ስንመጣ ራሳችንን እዚህ አግኝተነዋል፡፡ ተመስገን! እንደ አሳቡ ሁሉን የሚፈጽም፣ ለአድራጎቱ ከልካይ የሌለበት አምላክ ስሙ ብሩክ ይሁን፡፡ የአርያም ደጆች ተከፈቱ፡፡ ያበጃጀኝን መዳፍ አየሁት፡፡ ከምድር አፈር የሠራኝን፣ የሕይወት እስትንፋስ እፍ ያለብኝን፣ ለእኔ ተጠቦ ገነትን ስፍራ የሰጠኝን፣ መልክና ምሳሌው ያደረገኝን፣ ቢስት እመልሰዋለሁ፣ ቢጠም አቀናዋለሁ፣ ልጅነቱን አሳድጋለሁ፣ አለማወቁን አስተምራለሁ ብሎ ኑር ያለኝን ልብ አልኩት፡፡

        መጪውን እያየ፣ መዳረሻዬን እያወቀ የፈጠረኝን የአባቶች አባት፣ የወላጅ ጥግ፣ የመውደድ ዳርቻ ኤሎሂም ወሰን መስፈሪያ በሌለው ክብር በዙፋኑ ሆኖ አስተዋልኩት፡፡ የልቤን ዓይኖች ወደ ጸጋው ዙፋን ዘረጋሁ፡፡ አባባ እንዲህ አለኝ ‹‹አሳብ ሳለህ ያሰብኩህ፣ ጽንስ ሳለህ ሰው ያልኩህ እኔ ነኝ›› ገጹ በማይቆጠር እጥፍ ያበራል፡፡ ሁሉን የሚችል ብርታቱ፣ ደከመኝ ሳይል የሚሸከም ፍቅሩ፣ ያለመጥፋት ዋስትና ምህረቱ፣ የማይናድ የማይፈርስ ኪዳኑ፣ አመጽን የማያውቅ ጽድቁ በግልጥ ይነበባል፡፡

Wednesday, December 11, 2013

የንጉሡ ኢትዮጵያ

                                           Please Read in PDF: Yengusu etyopia

                             
                                    እሮብ ታህሳስ 2/2006 የምሕረት ዓመት

      ለመጀመሪያ ጊዜ የቅዱስ ጳውሎስን ሆስፒታል የረገጥኩበት ዕለት ነው፡፡ የሕዳር ወር መጨረሻ! እንደነዚህ ያሉ ስፍራዎችን በዋናነት ሦስት ሰዎች ማለትም ሕሙማን፣ አስታማሚ (ጠያቂ) እና የሕክምና ባለሙያዎች እንደሚገኙበት አስባለሁ፡፡ ታዲያ ከቀትሩ ለመሸሽ ማለዳውን እየተሽቀዳደምኩ ነበር ወደምጠይቀው ሰው ያቀናሁት፡፡ እኔ የምፈልገው ሰው ወደሚገኝበት ክፍል ስደርስ ጽዳት ላይ የነበሩ ሠራተኞች እንድታገስ ነገሩኝ፡፡ ከመቆም ብዬ ዘወር ዘወር ለማለት ወደ ታችኛው የቅጽሩ አካባቢ ወረድኩ፡፡ በግራና በቀኝ፣ በፊትና በኋላ ዙሪያዬ መፍትሔ ሽተው በዚያ የተገኙ ሕሙማንን ልማዳዊ ከሆነው ‹‹ይማራችሁ›› ባለፈ ስለ እነርሱ በልቤ እየጸለይኩ በእርጋታ በጥጋ ጥጉ ሳይቀር ተራመድኩ፡፡ ድንገት ዓይኔ አንድ ነገር አስተዋለና ይበልጥ ተጠግቼ ተመለከትኩት፡፡ ከዚህ ጽሑፍ በላይ የምታዩትን የንጉሡ የኃይለ ሥላሴን ስዕል ነበር ያየሁት፡፡ የመጣሁበትን ዓላማ የዘነጋሁ እስኪመስለኝ ድረስ ደጋግሜ በአግራሞት አስተዋልኩት፡፡ አሁንም ይበልጥ አስተዋልኩት፡፡

Tuesday, December 3, 2013

ለፍቅር የተከፈለ(ካለፈው የቀጠለ)


           
                            እሮብ ህዳር 25/2006 የምሕረት ዓመት
    ሚስቱን በሞት ያጣ አንድ ወጣት ከብዙ መፍትሔ ፍለጋ በኋላ ወደ አንድ የስነ ልቦና አጥኚ ዘንድ ሄዶ በሕይወት ላይ ተስፋ እንደቆረጠ፣ የሚስቱ ሀዘን ለመኖር ምክንያት እንዳሳጣው በእንባ ጭምር ይነግረዋል፡፡ የስነ ልቦና አማካሪውም ወደ ወጣቱ እየተመለከተ “ሚስትህ በሕይወት ብትኖርና አንተ ብትሞት ኖሮ ሚስትህ ምን የምትሆን ይመስልሃል?” ሲል ጠየቀው፡፡ ወጣቱ ፍም የመሰለ ፊቱን በእጁ እያሻሸ “በቁሟ ጨርቋን ጥላ፣ ሚዛኗን ትስታለች እንጂ በጤና የምትሆን አይመስለኝም” በማለት ጥርሱን ነክሶ መለሰለት፡፡