Sunday, May 25, 2014

ቀላል ነው (ካለፈው የቀጠለ)

                   Please Read in PDF: Kelal new (yeketele)
                        እሁድ ግንቦት 17 ቀን 2006 የምሕረት ዓመት

     ‹‹ታላላቆችም ብላቴኖቻቸውን ወደ ውኃ ሰደዱ፤ ወደ ጕድጓድ መጡ፤ ውኃም አላገኙም፥ ዕቃቸውንም ባዶውን ይዘው ተመለሱ፡፡ አፈሩም ተዋረዱም ራሳቸውንም ተከናነቡ።›› (ኤር. 14÷3)፡፡

        አቤት ምድረ በዳ፤ አቤት ቃጠሎ፤ አቤት የውኃ ጥም፤ አቤት አቅም ማጣት፤ አቤት ሥጋት፤ አቤት መጨካከን፤ አቤት መጣደፍ፤ አቤት መተራመስ፤ አቤት አዙሪት፤ አቤት መዛል፤ አቤት እፍረት፤ አቤት መዋረድ፤ አቤት መደበቅ፤ አቤት አለመፈናፈን፤ አቤት ማለክለክ፤ አቤት የዕንባ ጅረት፤ አቤት የዓይን መጠውለግ፤ አቤት የማይቆጠር በድን፤ አቤት የተማሱ ጉድጓዶች፤ አቤት አፉን የከፈተ መቃብር፤ አቤት የሕፃናት ጩኸት፤ የአዛውንቶች ሲቃ፤ አቤት ሰይፍ፤ አቤት ቸነፈር፤ አቤት መበተን፤ አቤት ክሳት፤ አቤት መከራና ሰቆቃ!

        የተነሣንበት የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ወደ ኤርምያስ ስለ ድርቅ የመጣው የእግዚአብሔር ቃል ነው፡፡ አፈሩ . . . ተዋረዱ . . . ራሳቸውንም ተከናነቡ፤ የሚሉትን ቃላት ስናነብ፤ ልክ በዚያ ዘመን እንደ ነበረ ትኩስ ሀዘንተኛ የከበዱብን ነገሮች ወደ ፊታችን ይመጣሉ፡፡ ማንም ሰው በሕይወቱ እንዲህ ያሉ ውርደቶች ባይሆኑ ጽኑ መሻቱ ነው፡፡ ይሁዳ ያለቀሰችበት፤ ደጆችዋም ባዶ የሆኑበት፤ ብርሃኗን የተነጠቀችበት፤ ጩኸቷን አብዝታ ያሰማችበት የጭንቅ ጊዜ፤ የኑሮ በረሃዎቻችንን ግልጥልጥ አድርጎ ያሳየናል፡፡

       እግዚአብሔር የከለከለንን ማንም እንደማይሰጠን፤ የዘላለም አምላክ ያላሰበንን ማንም እንደማያስበን፤ የአማልክት አምላክ ያልራራልንን ማንም እንደማይራራልን፤ የጌቶች ጌታ ያልሰበሰበንን ማንም እንደማይሰበስበን፤ የነገሥታት ንጉሥ ያልሞላውን ጉድለት ማንም እንደማይሞላው፤ እርሱ ከጨከነብን የማንም ፊት እንደማይበራልን የምንረዳበት ክፍል ነው፡፡ አብዛኛውን ጊዜ የእግዚአብሔርን ቁጣ በአንድ መንገድ ብቻ እንደምናየው ይሰማኛል፡፡ ከቅጣትና ከጥፋት መልእክቱ አንፃር! ዳሩ ግን እንደዚያ ብቻ መልእክት እንዳለው እንዳናስብ የሚረዱን የእግዚአብሔር ትምህርቶች በቃሉ ውስጥ አሉልን፡፡ በዚሁ በነቢዩ በኤርምያስ የተግሣጽ ክፍል ውስጥ ውሸተኛ ነቢያት በእግዚአብሔር ስም ያልተላኩትን፤ ያላዘዛቸውን፤ ያልተናገራቸውን ግን የልባቸውን ሽንገላ ለሕዝቡ ሲናገሩ እናያለን፡፡ ሰላምን ለሕዝቡ ቢናገሩም፤ በረከትን ለሕዝቡ ቢተነብዩም እንደዚያ ግን አልሆነም፡፡

Tuesday, May 13, 2014

ቀላል ነው!

                                   Please Read in PDF: Kelal New                                                   
                            ማክሰኞ ግንቦት 5 ቀን 2006 የምሕረት ዓመት  

    ‹‹እግዚአብሔርም እንዲህ ይላል፡- ነፋስ አታዩም፤ ዝናብም አታዩም፡፡ ይህ ሸለቆ ግን ውኃ ይሞላል፤ እናንተም ከብቶቻችሁም እንስሶቻችሁም ትጠጣላችሁ፡፡ ይህም በእግዚአብሔር ዓይን ቀላል ነገር ነው››  (2 ነገ. 3÷17)፡፡

        እግዚአብሔር ከልምምዶቻችን በላይ ነው፡፡ እኛን የሚያጽናናው ራሱን እያጣቀሰ ነው፡፡ እርሱ ብቻ ‹‹እኔ›› ሊል ይቻለዋል፡፡ እኔነት ከእኛ አንፃር ችግር ሲሆን፤ ከእግዚአብሔር አንፃር ግን መፍትሔ ነው፡፡ እኔነት ከእኛ አንፃር ኃጢአት ሲሆን ከእርሱ አንፃር ግን ጽድቅ ነው፡፡ እኔነት ከሥጋ ለባሽ አንፃር ሞት ሲሆን ከጌታ አንፃር ግን ሕይወት ነው፡፡ እኛ ማብራሪያችን ድካምና ብርታት፤ አቀበትና ቁልቁለት ሲሆን እግዚአብሔር ግን ያውና ሕያው ነው፡፡ ያለ፤ የነበረ፤ የሚኖር እንደ እግዚአብሔር ማን ነው? በዓለም ስሌት፤ በሰዎች የአስተሳሰብ ደረጃ፤ በስልጣኔ ክንድ የማይተገበሩ ነገሮችን የእኛ አምላክ ግን ሊያደርግና ሊሠራ ይችላል፡፡ የችግሮቻችን ልዕልና በእኛ ዓይኖች ፊት ብቻ ነው፡፡ በትልቁ እግዚአብሔር ዘንድ የማይቻል የለም፡፡ እግዚአብሔር ‹‹ቀላል ነው›› የሚላችሁ ገምቶ አይደለም፡፡ እርሱ የነገሮችን ጅማሬና ፍፃሜ ጠንቅቆ የሚያውቅ አዋቂ ነውና፡፡ /የሰውን ድካሙን አንተ ታውቃለህ እንዲል ቅዳሴው/

       እኛ ካልገባን፤ ገና ካልተረዳነው ማንነታችን ጋር የምንኖር ምስኪኖች ነን፡፡ ትንሽ ተጉዘን የረጅም የምንፈነጭ፤ ጥቂት ጨብጠን የብዙ የምንፎክር፤ እየተንገዳገድን የቆምን ይመስል፤ እየሸሸን የቅርብ ያህል የሚሰማን፤ እንኳን ከመንፈሳችን ከስሜታችን ጋር የተሸዋወድን፤ ‹‹ያፋልጉኝ›› የተለጠፈበት ሰሌዳ ቢኖር የእኛ እኔነት ነው፡፡ የእግዚአብሔር እጆች እንዲህ ያለውን ሕመምተኛ ማገላበጥ፣ ማጉረስና ቀና ማድረግ፤ ማውጣትና ማግባት ሰልችተው አያውቁም፡፡ ሰው በእግዚአብሔር ቋሚ እንክብካቤ ስር ነው፡፡ የነገሮች ክብደት በእኛ እንደምንኖር ለእኛ የመለፈፋችን ውጤቶች ናቸው፡፡

Saturday, May 10, 2014

አታላምዱን

                                           
                                   Please Read in PDF: Atalamdun

                ቅዳሜ ግንቦት 2 ቀን 2006 የምሕረት ዓመት

       በአንድ አጋጣሚ በአንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ላይ ከሌላ ሁለት ወንድሞች ጋር እየተነጋገርን አሳብ እንለዋወጣለን፡፡ ታዲያ አንደኛው ወንድም አውደ ንባቡ ሊያስተላልፍ ከፈለገው ጠንካራ አሳብና ተግሣጽ ሸሽቶ ያነሠ ነገር ለማንጸባረቅ ሞከረ፡፡ ታዲያ በጊዜው ችላ ብዬ ያለፍኩት ዘግይቶ ግን ያስተዋልኩት ነገር ቢኖር፤ ሰው እግዚአብሔር ካልረዳው በቀር የማይላመደው ነገር አለመኖሩን ነው፡፡ የመጽሐፍ ቅዱሱ ክፍል ክፉ ልምዶችን የሚቃወም ሆኖ ሳለ፤ በጊዜው ግን ወጣቱ እየተላለፈ ያለውን የመለኮት ቃል ቢያውቅም እንኳ ከእግዚአብሔር አሳብ ጋር ለመቆም ፍላጎት አላሳየም፡፡

       እኛ ያልታዘዝነውን ሌሎች እንዳይታዘዙት፤ እኛ ያልደረስንበትን ሌሎች እንዳይደርሱበት፤ እኛ የፈዘዝንበትን ሌሎች እንዳይነቁበት ዝቅታውን ማላመድ ከበደልም በደል ነው፡፡ በየዘመናቱ የእግዚአብሔር ቃል በብዙ ወጀብና አውሎ ውስጥ አልፏል፡፡ ነገር ግን ጎልቶ የማይታይና ቶሎ የማይታወቅ ቢሆንም እንኳ ቃሉን በሚመሰክሩ አገልጋዮች በኩል የሚዘረጋው የጠላት ወጥመድ፤ በተለይ በዘመናችን ለእውነት ተግዳሮት ነው፡፡ ለብዙ ነውሮችና ሃይማኖት ለበስ አመፆች የእግዚአብሔር ቃል እንደ ድጋፍና ሽፋን ሲጠቀስ ማስተዋል እየቀለለ መጥቷል፡፡

Friday, May 2, 2014

ተቤዢዬ ሕያው ነው!

                            Please Read in PDF: Tebeziye Heyaw New
 
                          አርብ ሚያዝያ 24 ቀን 2006 የምሕረት ዓመት
 
           ‹‹ምነው አሁን ቃሌ ቢጻፍ! ምነው በመጽሐፍ ውስጥ ቢታተም! ምነው በብረት ብዕርና በእርሳስ በዓለቱ ላይ ለዘላለም ቢቀረጽ! እኔን ግን የሚቤዠኝ ሕያው እንደ ሆነ፥ በመጨረሻም ዘመን በምድር ላይ እንዲቆም፥ ይህ ቁርበቴም ከጠፋ በኋላ፥ በዚያን ጊዜ ከሥጋዬ ተለይቼ እግዚአብሔርን እንዳይ አውቃለሁ። እኔ ራሴ አየዋለሁ፥ ዓይኖቼም ይመለከቱታል፥ ከእኔም ሌላ አይደለም። ልቤ በመናፈቅ ዝሎአል።››
(ኢዮ. 19÷23-27)፡፡

           ስለ ቃል ብርታት፤ የሚናገርና የሚሰማ ሁሉ ልብ ይለዋል፡፡ በቃል የቀኑ፤ በቃል የወደቁ፤ በቃል የተጽናኑ፤ በቃል የተሰበሩ፤ በቃል የተሰበሰቡ፤ በቃል የተበተኑ፤ በቃል የጸኑ፤ ቃል ኪዳን ያፈረሱ፤ በቃል ያመለጡ፤ በቃል የተያዙ ምድሪቱ ላይ እንደ ትቢያ ናቸው፡፡ የመጽሐፉ ኢዮብ መልካምንና ክፉን፣ ደስታና ሀዘንን፣ ማግኘትና ማጣትን፣ መክበርና ውርደትን ያየ፤ ሁለቱንም የኑሮ ጽንፍ የነካ ነው፡፡ እንዲህ ያለው ኢዮብ በአሥራ ዘጠነኛው ምዕራፍ ላይ አንዳች እንዲፃፍለት የፈለገውን ቃል በተማጽኖ ጭምር ይነግረናል፡፡ ብዙ ሰው የግል ማስታወሻ ወይም ዲያሪ እንዳለው ልብ እንላለን፡፡ እንደዚህ ያሉ የግል ማስታወሻዎች ዕንባና ፈገግታ፤ መከፋትና ቡርቅታ፤ ተስፋና ሥጋት የሰፈረባቸው ዥንጉርጉር ናቸው፡፡ ለዚህ ጽሑፍ ዝግጅት የተጠና ነገር ለማቅረብ ጊዜው ባይኖረኝም አብዛኛው የጽሑፍ ይዘት መከፋትንና ቅዝቃዜን ማዕከል ያደረገ እንደ ሆነ ይሰማኛል፡፡ በተለይ ለመፃፍ እንደ ሰበብ የሚሆነው ነገር፤ ከሌላው ወደ እኛ የሚመጡ ስብራትና ተስፋ አስቆራጭ ነገሮች ናቸው፡፡

         ኢዮብ ወደዚህ ምድር መምጣቱን የኮነነ፤ የመቃብር ሙቀትን የተመኘ፤ ሥጋውን በጥርሱ ነክሶ ያዘነ፤ በገዛ ወዳጆቹ ግብዝነት የተከበበ፤ ከአምላኩ ጋር ሙግት የገጠመ የመከራ ሰው ነው፡፡ በሕይወቱ ከገጠመው ብርቱ ፈተና የተነሣ የሚናገራቸው እያዳንዱ ቃል በስቃይና ሮሮ የተለወሱ ናቸው፡፡ በመጽሐፉ የተለያዩ ምእራፎች ውስጥ ጠንካራ ጩኸቱንና ያልተቋረጠ ክርክሩን እናነባለን፡፡ እንደዚያ ባለ ስቃይ ውስጥ፤ የወዳጆቹ ፍርደ ገምድልነት፤ የሚስቱ ስንፍና ተጨምሮ ኑዛዜ በሚመስለው ቃሉ ውስጥ ለሥጋ ለባሽ ሁሉ መፍትሔ የሆነ ነገርን ሲናገር ልብ እንላለን፡፡