Sunday, April 19, 2015

በዚያ አይፈልጓችሁ


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
እሁድ ሚያዝያ 11 ቀን 2007 የምሕረት ዓመት
‹‹ሕያውን ከሙታን መካከል ስለ ምን ትፈልጋላችሁ? ተነሥቶአል እንጂ በዚህ የለም።››
 /ሉቃ. 24፡5/
         የብሉይ ኪዳን መጻሕፍ የሚጀምረው የእግዚአብሔርን ሉዓላዊነት በማወጅ ነው፡፡ ‹‹በመጀመሪያ እግዚአብሔር ሰማይንና ምድርን ፈጠረ።›› /ዘፍ. 1፡1/፤ እግዚአብሔር የበላይ የሌለበት ሉዓላዊ አምላክ ነው፡፡ እርሱ እንደሚያይ የሚመለከት ሌላ፤ እርሱ እንደሚያውቅ የሚረዳ ሌላ፤ እርሱ እንደሆነው የሚገኝ ሌላ የለም፡፡
         ‹‹ብቻውን ተአምራትን የሚያደርግ የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ይባረክ›› /መዝ. 71፡18/፤ ‹‹እርሱ ብቻውን ታላቅ ተአምራትን ያደረገ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና›› /መዝ. 135፡7/፤ ‹‹እርሱ ግን ብቻውን ነው፤ እርሱንስ የሚመስለው ማን ነው? ነፍሱም የወደደችውን ያደርጋል።›› /ኢዮ. 23፡13/፤ የሚሉት መዝሙራት እግዚአብሔር ብቻውን የበላይ ገዥ አምላክ መሆኑን ያስረዱናል፡፡
         ነቢዩ በሌላ ስፍራ ‹‹እግዚአብሔር ታላቅ ነው፤ እጅግም የተመሰገነ ነው፤ ለታላቅነቱም ፍፃሜ የለውም፡፡ ትውልደ ትውልድ ሥራህን ያመሰግናሉ፤ ይልህንም ያወራሉ፡፡ የቅድስናህን ግርማ ክብር ይነጋገራሉተአምራትህንም ይነጋገራሉ፡፡ የግርማህንም ኃይል ይናገራሉታላቅነትህንም ይነጋገራሉብርታትህንም ይነጋገራሉ፡፡›› /መዝ. 144፡3-6/ ይላል፡፡ ስለ እግዚአብሔር ከተነጋገርን ብርታትና ታላቅነቱን እንነጋገራለን እንጂ እርሱ ድካም የለበትም፡፡ በዘመናት የማይቀያየር፤ በሁኔታዎች የማይዝል ግርማ የእግዚአብሔር ነው፡፡ ይታጣል ይሞታል ተብሎ ለእርሱ አይሠጋም፡፡

Saturday, April 11, 2015

ሞቶ መዋል


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
ቅዳሜ ሚያዝያ 3 ቀን 2007 የምሕረት ዓመት
‹‹ . . እትቤዝወከ በመስቀልየ ወበሞትየ››
‹‹ . . በመስቀሌና በሞቴ አድንሃለሁ።››
(ኪዳነ አዳም ፫፡፫-፮፤ ዘፍ.፫።፲፭)
     ‹‹ቀደምት የኢትዮጵያ ነገሥታት ስመ መንግሥታቸው ከመስቀል ጋር የተጣመረ ነበር፣ የቅዱስ ንጉሥ ላሊበላ (፩ሺህ፩፻፶፮ - ፩ሺህ፩፻፺፯ ዓ.ም) ስመ መንግሥቱ ገብረ መስቀል ሲሆን የእቴጌይቱ ስመ መንግሥት መስቀል ክብራ ነበር፤ የዐፄ ይስሐቅም (፩ሺህ ፬፻፲፬ - ሺህ፩፬፻፳፱ ዓ.ም) ስመ መንግሥታቸው ገብረ መስቀል ነበር። የደብዳቤያቸውም ርእስ ትእምርተ መስቀልና ኢየሱስ የሚል ነበር።
ኢ            የ
   +      
ሱ            ስ  ››             /መጋቤ ብሉይ ሠይፈ ሥላሴ ዮሐንስ/

          በኢትዮጵያ ታሪክ የክርስትና እምነት ከቤተ መንግሥት ወደ ሕዝቡ እየወረደ እንደተስፋፋ ይነገራል፡፡ ለዚህም ከመጽሐፍ ቅዱስ እንደ ዋና ማሳያ የሚጠቀሰው ኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ነው /ሐዋ. 8፡26-39/፡፡ በአገራችን ወንጌል እንዲሰበክ፤ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲገለጥ፤ ክርስቶስ ትውልዱን እንዲገዛው ሕዝባችን ሰፊ እድል እንደነበረውና እንዳለው አመላካች ታሪኮችን ከመዛግብት ልንረዳ እንችላለን፡፡ ዳሩ ግን ለእውነት የማይታዘዝ ኑሮ፤ የእግዚአብሔርን አሳብ የሚቃወም አመጽ፤ ከቃሉ በተቃራኒ የሆኑ ሥርዓቶች ሕዝቡን ያሰከሩ ጉሽ ወይን ጠጆች ሆነው በየዘመናቱ ዘልቀዋል፡፡