Monday, June 29, 2015

ስፍራችሁን ያዙ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!



ሰኞ ሰኔ 22 ቀን 2007 የምሕረት ዓመት

በዚህ ምድር ላይ እጅግ አስፈሪው ሰው ክርስቶስ የሌለውን ማንነት የያዘ ነው፡፡ ለምድሪቱ እግዚአብሔር እንደሌለው ሰው ያለ ሥጋትና ሽብር፤ የሁከት ርዕስና የክፋት ሥር የለም፡፡ ለአመፃ ጉልበት በሚሆኑ፤ ለከንቱ ኑሮ አቅም በሚፈጥሩ፤ ሰውን ከባህርዩ ውጪ ነውርን በሚያለማምዱ ብዙ ነገሮች መሐል በምንመላለስበት የዚህ ዓለም ስርአት፤ ማምለጥ የደኅንነት አምላክ በሆነው በእግዚአብሔር ነው፡፡
‹‹አምላካችንስ የደኅንነት አምላክ ነው፤ ከሞት መውጣትም ከእግዚአብሔር ነው።›› /መዝ. 67፡20/ እንደተባለ፤ ደኅንነት ከእግዚአብሔር፤ ከሞት ማምለጥም ሁሉን ከሚችል አምላክ ነው፡፡ ነቢዩ በሌላ ስፍራ ‹‹እግዚአብሔር ከመቅደሱ ከፍታ ሆኖ ተመልክቶአልና፥ ከሰማይ ሆኖ ምድርን አይቶአልና የእስረኞችን ጩኸት ይሰማ ዘንድ፥ ሊገደሉ የተፈረደባቸውን ያድን ዘንድ›› /መዝ. 101፡19-20/ እንዳለ፤ መዳን በእርሱና ከእርሱ ካልሆነ በቀር ሥጋ ለባሽ ሁሉ ከዘላለም ፍርድና ኩነኔ ሊያመልጥ አይችልም፡፡