Monday, November 30, 2015

እድል ፈንታችን



ሰኞ ሕዳር 20 ቀን 2008 የምሕረት ዓመት
ከወንድም እሸቱ

      ጥያቄ፡ - ‹‹ለብዙ  ጊዜ ነገሮች  ላይ እድለኛ  እንደሆንኩ ይሠማኝ ነበረ አሁን ነገሮች በተቃራኒዉ ሆኑብኝ ቀላል ሙከራየ ሁሉ ይከሽፋሉ ምን ይሻለኛል››፡፡

        ወንድም እሸቱ በሙሉ ፈቃደኝነት ችግርህን በጋራ መፍትሔ እንድንፈልግበት ልታካፍለን ስለወደድክ አስቀድሜ ላመሰግንህ እወዳለሁ፡፡ በማስከተል ችግርን በፍጹም ግልጽነት መናገር መቻል የመፍትሔው ትልቅ አካል እንደሆነ እያስታወስኩህ፤ መፍትሔ ልናገኝባቸው እንችላለን ወደምላቸው አሳቦች ከመሄዴ አስቀድሞ ጥቂት ጥያቄዎችን ልጠይቅህ (ለእሸቱ)፡፡

Wednesday, November 25, 2015

የኔታ፡ ኢየሱስ



    እሮብ ህዳር 15 ቀን 2008 የምሕረት ዓመት

ሀ ሁ አቡጊዳ ፊደልን ሊቆጥሩ
ከምምሩ የኔታ ፊት ተኮለኮሉ፤
ትንሽ ምላሶች ይንጫጫሉ
ከወረኛ ዓለም እንዲቀላቀሉ፤
እኒያኛው የሥጋ የኔታ
ዘርግተው የፊደል ገበታ፤
ሲያሻቸው ሲተኙ ሲያንቀላፉ
ሲሻቸው ሕጻናት ሲያስለፈልፉ፤
 ብላቴኖቹ ፊደል ቆጥረው ሲጨርሱ
የምምሩም እግሮች አብረው ተነሡ፤
. . . ሌላኛው የኔታ የጠልጣላ ነፍሴ
ቢያሳስባቸው መዳን መቀደሴ፤
የተግባር ትምህርት ሲጀምሩ
እጆቻቸው በምስማር ተቸነከሩ፡፡

                                       /ከቤተ ፍቅር ቤተሰብ የተላከ/
                      ‹‹ . . . ስለ እኛ ደግሞ ጸልዩ፤›› /ቆላ. 4፡3/!

Friday, November 20, 2015

ድልና ምክር (1)

                                                                      

‹‹ድልም ብዙ ምክር ባለበት ዘንድ ነው›› /ምሳ. 24፡6/፤ ‹‹እርስ በርሳችን እንመካከል›› /ዕብ. 10፡25/!
                            
   አርብ ህዳር 10 ቀን 2008 የምሕረት ዓመት

         ምክክር ወደ መፍትሔ የሚያደርስ የጋራ ችግር ፈቺ ሂደት ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱሳችን በጽድቅ ላለው ምክር እንደሚጠቅም ተጽፎአል (2 ጢሞ. 3፡16-17)፡፡ በክርስትናው መሰረት ላይ ሆኖ በእለት ከእለት ችግሮቻችን ላይ በጋራ ዝርዝር መፍትሔዎችን ማስቀመጥ፤ መመካከር፤ መጠያየቅ፤ መረዳዳት በእጅጉ አስፈላጊ ነው፡፡ ተወዳጆች ሆይ፤ የመፍትሔ ሰዎች መሆን ይብዛላችሁ! 

·        በረከቶቻችሁን ቁጠሩ፡ አስቸጋሪ ሁኔታዎች ውስጥ ስትሆኑ በኑሮአችሁ ያገኛችኋቸውን በጎ ነገሮች መመልከትን አትዘንጉ፡፡ የፈተና አንዱ መልክ ያላችሁን ሳይሆን የሌላችሁን እንድታስቡ መፈተኑ ነው፡፡ ብዙ ሰዎች በዚህ መንገድ ይቸገራሉ፡፡ እግዚአብሔር ያደረገላችሁ ይታያችሁ፡፡ በትንሹ እየተቸገራችሁያላችሁት እንኳ በመኖራችሁ እንደሆነ ይታወሳችሁ፡፡ የመኖርን ሌላኛውን ገጽታ መመልከት የምንችለው በሕይወት ስላለን ነው፡፡

Wednesday, November 18, 2015

የፍቅር ዘመቻዎች


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

                                     እሮብ ህዳር 8 ቀን 2008 የምሕረት ዓመት

1. ሁሉንም ሰው አክብር - ክርስቶስ በሁሉም ሰው ውስጥ ይኖራል፡፡ የሌሎች ሰዎችን ስሜት አክብር - እነርሱ የአንተ ወንድሞችና እኅቶች ናቸውና፡፡

2. ስለ እያንዳንዱ ጥሩ አስብ - በማንም ላይ መጥፎ ነገርን አታስብ፡፡ በመጥፎ ሁኔታዎች ውስጥ እንኳን ቢሆን ጥሩ ነገሮችን ለማግኘት ሞክር፡፡

3. ሁልጊዜም ስለ ሌሎች ጥሩ ተናገር - በማንም ላይ ዘለፋን አታድርግ፡፡ በንግግር ካልተገለፀ ቃል የሚመነጨውን ማንኛቸውም ጉዳት አርም፡፡ በሰዎች መካከል ውዝግብና አታካራ እንዲፈጠር ምክንያት አትሁን፡፡

Monday, November 16, 2015

የሕይወት አቅርቦት

(ካለፈው የቀጠለ)

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!


                                              ሰኞ ህዳር 6 ቀን 2008 የምሕረት ዓመት

       ስለ ሕይወት ስናስብ መለኮታዊነት እና ዘላለማዊነት የብቻው የሆነውን እግዚአብሔርን ልብ እንላለን፡፡ ሕይወት እግዚአብሔር ብቻና ከእርሱ ብቻ ነው፡፡ ሰዎች ስለ እግዚአብሔር የገባቸውን፤ በተረዱት መጠን ቢናገሩ እርሱ እግዚአብሔር ግን ከዚህ ያነሰ አይደለም፡፡ እግዚአብሔርን ልዩ የሚያደርገው ነገር ራሱ እግዚአብሔር ብቻ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ሕይወት አስገኝ የለበትም፡፡ ስለ እርሱ ሕልውና ስናወራ እርሱ ራሱ ብቻ መሰረትና ፍጻሜ ነው፡፡

       ዘላለማዊነት ከእግዚአብሔር አንጻር የነገሮች ረጅም ጊዜ መቆየት አይደለም፡፡ መለኮታዊነትም በበላይነት እያስተዳደሩ መዝለቅ አይደለም፡፡ እርሱ ብቻ ዳርቻ በሌለው፤ ስፍራም በማይወሰንለት ልዩነት ከ እና እስከ መቼም ሕያው ሆኖ ይኖራል፡፡ ‹‹ፊተኛ እና ኋለኛው›› (ኢሳ. 44፡6) የእርሱ በቂ ማብራሪያ አይደለም፡፡

       ይህ ከእውቀት ከፍለን እንድናውቅ የተገለጠልን እውነት ነው (1 ቆሮ. 13፡9)፡፡ ይህ አርነት እንድንወጣ በቂ ቢሆንም የምናጣጥመው መንፈሳዊ ነጻነት የመጨረሻ ማብራሪያ ግን አይደለም፡፡ ራሱን እግዚአብሔርን ለምንወርስ (ሮሜ 8፡16) ለእኛ ከመታወቅ የሚያልፍ ነገር ከእርሱ እንደተደረገልን ማመን የሐሴታችን ጥግ ነው፡፡ ገና ከዚህ ሕይወት ጋር ለማይቆጠር ጊዜ፤ በማይወሰን ስፍራ እንኖራለን፡፡ እግዚአብሔር ብቻ ያልተፈጠረ ሕይወት ነው!

       ቅዱሱ መጽሐፍ ሕይወት መገኛዋ ሕይወት የሆነው እግዚአብሔር እንደሆነ ያስረዳናል፤ ‹‹በአደባባይዋም መካከል ከእግዚአብሔርና ከበጉ ዙፋን የሚወጣውን እንደ ብርሌ የሚያንጸባርቀውን የሕይወትን ውኃ ወንዝ አሳየኝ።›› (ራእ. 22፡1)፡፡ የእግዚአብሔር ሕይወት ራሱ እግዚአብሔር ነው፤ የእኛም ሕይወት እርሱ ሕይወት የሆነው እግዚአብሔር ነው፡፡ ብቻውን ጸንቶ የሚኖር ሕይወት፤ ባህርዩ ሊቀየር የማይችል ሕይወት እግዚአብሔር አምላካችንና አባታችን ነው፡፡

       ተወዳጆች ሆይ፤ የእግዚአብሔር ሕይወት ለሞት የሚገዛ ሕይወት አይደለም፡፡ ከሕልውና በቀር መጥፋት አያብራራውም፡፡ ሽንፈት ድካም፤ መለወጥ መናወጥ አይገልጸውም፡፡ ይህ ሕይወት ከራሱ ከእግዚአብሔር ካልሆነ በቀር መልአክ ቢሆን አይሰጠንም፡፡ የሥጋ ለባሽ የጥረቱ ውጤት ሊሆንም አይችልም፡፡ በምንኖርበት ዓለም እንኳ ሕይወት ከእግዚአብሔር ብቻ ነው፡፡

Monday, November 9, 2015

የሕይወት አቅርቦት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!


ጥቅምት 29 ቀን 2008 የምሕረት ዓመት
 /ፊል. 2፡14-15/

         በምጣኔ ሀብት ባለ ሙያዎች ዘንድ የፍላጎትና የአቅርቦት መጣጣም ጉዳይ የሁል ጊዜ ርዕስ ነው፡፡ የሰዎች ፍላጎት ሰፊ በሆነበት ሁኔታ ለዚያ አሳማኝ መሻት በቂ የሆነ ምላሽ መስጠት የሚጠበቅ እንደ መሆኑ የምድር መንግሥታት ለዜጎቻቸው ይሠራሉ፡፡ እግዚአብሔር የሰማያትና የምድር ገዥ ነው፡፡ የሁሉ ዓይን ተስፋ የሚያደርገው እርሱ (መዝ. 144፡15) በተለየ ሁኔታ በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ ልጁ ለሆኑት (ዮሐ. 1፡12) በሚያስፈልጋቸው ነገር ሁሉ ያስባል፤ ያደርጋልም (ፊል. 4፡19)፡፡

         የእግዚአብሔርን የዘላለም አሳብና የልብ ምክር በመስማትና በማስተዋል፤ ደግሞም በመታዘዝ ወደ እምነት የመጡትን (ሮሜ 10፡17) በሰማይና በምድር ያለ አባትነት ሁሉ የሚሰየምበት (ኤፌ. 3፡14) እግዚአብሔር እንደ አባት ይመግባል፤ ይንከባከባል፤ ያሳድጋል (1 ቆሮ. 3፡6)፡፡ እርሱ ጌታ ሕይወትን የሚሰጥ ብቻ ሳይሆን የሚያበዛም ነው (ዮሐ. 10፡10)፡፡ የዘላለምን ሕይወት ከእግዚአብሔር ጸጋ በክርስቶስ ኢየሱስ ያገኙ ሁሉ (ሮሜ 6፡23) ለዚህ ሕይወት አስፈላጊ የሆነውን ወደ ጸጋው ዙፋን በእምነት በመቅረብ ያገኛሉ (ዕብ. 4፡16)፡፡     

        ተወዳጆች ሆይ፤ እግዚአብሔር ሰውን ከመፍጠሩ አስቀድሞ ለሚፈጥረው ሰው አስፈላጊው የሆኑትን ነገሮች ሁሉ እንዳዘጋጀ (ዘፍ. 1)፤ በክርስቶስ አዲስ ፍጥረት መሆናችንን (2 ቆሮ. 5፡17) ተከትሎ ያለን ኑሮም እግዚአብሔር አስቀድሞ ያዘጋጀውን መልካሙን ሥራ ማድረግ ነው (ኤፌ. 2፡10)፡፡ እግዚአብሔር ታላቅና ድንቅ አምላክ ነው (መዝ. 85፡10)፡፡ የእርሱ እጅ ሥራ የሆነው ሰው ለቀጣዩ አሁን የሚያቅድ፤ ያውም ይድረስ አይድረስ በማያውቀው ጊዜ ላይ አስቀድሞ የሚዘጋጅ ሆኖ ሳለ እጅግ ኃያል የሆነው እግዚአብሔር እርሱ እንዴታ?