Friday, December 25, 2015

መልእክት ኀበ ፊልሞና፡፡(2)

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!


አርብ ታኅሣሥ 15 ቀን 2008 የምሕረት ዓመት

(መልእክት ወደ ፊልሞና)

‹‹እምጳውሎስ ሙቁሐ ለኢየሱስ ክርስቶስ፡ (ኤፌ. 3፡1)››!

           መጽሐፍ ቅዱሳችሁን ከመክፈታችሁ፤ እንዲሁም የመልእክቱን ክፍል ከመግለጣችሁ አስቀድሞ አብ፤ ወልድ፤ መንፈስ ቅዱስ፤ አንድ አምላክ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ማስተዋልን እንዲሰጣችሁ፤ እንዲሁም ከመልእክቱ ልትረዱ የሚገባችሁን ሁሉ መቀበል እንድትችሉ በቅዱስ መንፈሱ በኩል እንዲረዳችሁ በመንፈስና በእውነት በመገዛት ጸልዩ፡፡ ተወዳጆች ሆይ፤ ከዚህ በኋላ መልእክቱን ቃል በቃል በጥንቃቄና በእርጋታ አንብቡት፤ ይህንንም በመደጋገም አድርጉት፡፡

የመልእክቱ ዳሰሳ፡-

o   ‹‹ተቀብለህ ለዘላለም እንድትይዘው . . ›› /ቁ. 15/ የመልእክቱ ዋና አሳብ ሲሆን፤ ለመልእክቱ ‹‹የዘላለም መያያዝ›› ብለን ርእስ ልንሰጠው እንችላለን፡፡ ሐዋርያው ለፊልሞና ‹‹እንደ ባልንጀራ ብትቆጥረኝ እንደ እኔ አድርገህ ተቀበለው›› /ቁ. 17/ በማለት ይጠይቃል፡፡

o   መልእክቱ ከሐዋርያው ከጳውሎስ መልእክታት በጣም አጭሩ መልእክት ሲሆን፤ ሐዋርያው በእስር ቤት ሆኖ ከጻፋቸው ከፊልጵስዩስ፤ ከቆላስይስ እና ከኤፌሶን መልእክታት መካከል አንዱ ሲሆን፤ ይዘቱ ግን የተለየ ነው፡፡


o   ሐዋርያው ከጻፋቸው መልእክታት መካከል ለሦስት ሰዎች (ግለሰቦች) የጻፋቸው አራት መልእክታት ተጠቃሽ ናቸው፡፡ እነዚህም፡- አንደኛ ጢሞቴዎስ፤ ሁለተኛ ጢሞቴዎስ፤ ቲቶ እና አሁን እያጠናነው ያለነው የፊልሞና መልእክት ናቸው፡፡ መልእክቱን ወደራሳችሁ አቅርባችሁ፤ ለእናንተ እንደተላከ በመቁጠር ብታነቡት በእጅጉ ትጠቀማላችሁ፡፡

o   በመልእክቱ አሳብ ውስጥ ቁልፍ የሆኑ (ትኩረት የሚሰጣቸው) ቃላትን እናገኛለን፡፡ እነዚህም፡- ክብር፤ ቸርነት፤ ጥንቃቄ፤ ወዳጅ፤ ፍቅር፤ ትህትና፤ ጥበብ፤ ግልጽ የሆነ ንጽህና (ቅድስና)፤ ከዚህ በመነሣት የመልእክቱን ይዘት ‹‹ትህትናን የተላበሰ መልእክት›› እንደሆነ እናስተውላለን፡፡ ተወዳጆች ሆይ፤ በዚህ መልእክት ውስጥ ችግር ፈቺ የሆነውን ክርስትና ለመመልከት ሞክሩ፡፡

o   መልእክቱ ባለ ሀብት የነበረው የቆላስይስ ክርስቲያን እና የሐዋርያው የጳውሎስ ቅርብ ወዳጅ የፊልሞና ባሪያ አናሲሞስ (ጠቃሚ፤ ዋጋ ያለው ማለት ነው) ከጌታው ወደ ሮም ኮብልሎ መጥፋቱ፤ በኋላም በክርስቶስ ክርስቲያን ሆኖ ወደ አሳዳሪው መመለሱን ማእከል ያደረገ ‹‹የእርቅ›› ደብዳቤ ነው፡፡ ተወዳጆች ሆይ፤ ጥሩ የማይባለውን አጋጣሚ ጌታ አንድን ነፍስ ወደ ክብር ለማምጣት እንዴት ለበጎ እንደ ተጠቀመበት አስተውሉ፡፡

o   መልእክቱ የ‹‹እርስ በርስ መዋደድን›› /ዮሐ. 13፡34/ አዲስ ትእዛዝ መሰረት ያደረገው የክርስትና ኑሮ የፍቅር ገጽታ ምን እንደሚመስል በተግባር የሚያስረዳ ሲሆን፤ በዓለም ላይ የሰዎች ባርነት (ስቃይን ጭምር የተሞላ) ተስፋፍቶ በነበረበት የሐዋርያት ዘመን ባሪያን አስመልክቶ የተጻፈ ብቸኛው መልእክት ነው፡፡ በዚህም ክርስትና የባርነትን ችግር ለመፍታት ያለውን የላቀ መንገድ የሚያሳይ ጽሑፍ ሆኖ ጥቅም ላይ ውሏል፡፡

o   ሐዋርያው በቆላስይስ መልእክቱ ላይ ‹‹ከእናንተ ከሆነውና ከታመነው ከተወደደውም ወንድም ከአናሲሞስ . . ›› /ቆላ. 4፡9/ ብሎ እንደጻፈው፤ ፊልሞና በቆላስይስ የሚኖር ባሪያ አሳዳሪና ቤተክርስቲያኒቱም (የምእመናን ስብስብ) በቤቱ የነበረች እንደሆነ፤ እንዲሁም የፊልሞና መልእክት እና የቆላስይስ መልእክት በተመሳሳይ ጊዜ የተጻፉና የተላኩ መሆኑን እንረዳለን፡፡ በዚህ ክፍል መሰረት መልእክቱ የተላከው ‹‹በአናሲሞስና በቲኪቆስ›› እጅ ነው፡፡    

‹‹ጽኑዕ ኃያል ለምጻም››

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!


አርብ ታኅሣሥ 15 ቀን 2008 የምሕረት ዓመት

        እግዚአብሔር የሌለበት ጀግንነት፤ እርሱ ሞገስ ያልሆነለት ከፍታ፤ ቅዱሱን አምላክ የማያሳይ መክበር፤ ለእርሱም የማይገዛ ሥልጣንና ባለ ጠግነት እጅግ ከንቱ ነው (ሉቃ. 12፡21)፡፡ ጌታችን ‹‹ከእኔ ጋርም የማያከማች ይበትናል።›› (ማቴ. 12፡30) ብሎ እንደተናገረ፤ ከእግዚአብሔር ጋር ሰላም ማድረግ ከየትኛውም ብልጥግና የላቀ ነው (ኢሳ. 27፡5-6)፡፡ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢያተርፍ ነፍሱንም ቢያጎድል ምን ይጠቅመዋል?›› /ማቴ. 16፡26/ እንዳለን፤ ለሰው ወደ እግዚአብሔር እንደመድረስ ያለ ስኬት፤ ብልጥግናም የለም፡፡

         የሶሪያ ንጉሥ ሠራዊት አለቃ ንዕማን፤ በጌታው (በንጉሡ) ዘንድ ታላቅ ክቡር ሰው ነበረ፤ ደግሞም ጽኑዕ ኃያል ነበረ (2 ነገ. 5፡1-4)፤ ነገር ግን ለምጻም ነበረ፡፡ የሠራዊት አለቃ ለምጻም፤ ታላቅ ክቡር ሰው ለምጻም፤ ጽኑ ኃያል ለምጻም ነበረ፡፡ ከአህዛብ የሆነውን ይህን ሰው ከእግዚአብሔር ቃል በቀር ማን እንዲህ ሊለው ይችል ነበር? ከስሩ የሚታዘዙ ሎሌዎቹ ታሪኩን ቢጽፉት ኖሮ እንዲህ ተጽፎ አናነብም፡፡ የአለቆቻቸውን ግብር እየበሉ ታሪክ አምታተው ስለጻፉ ተወቃሾች ብዙ የሚባልባት አገር ላይ እንዳለን አንስተውም፡፡ እግዚአብሔር ብቻ ልካችሁን ይናገራል፡፡

Thursday, December 17, 2015

ድልና ምክር (2)

                          በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!



‹‹ድልም ብዙ ምክር ባለበት ዘንድ ነው›› /ምሳ. 24፡6/፤ ‹‹እርስ በርሳችን እንመካከር›› /ዕብ. 10፡25/!

                              ሐሙስ ታህሳስ 7 ቀን 2008 የምሕረት ዓመት

         ፈተና የምንኖርበት የአሁኑ ዓለም አንደኛው መልክ ነው፡፡ የኖረ ይቸገራል፤ የሚራመድን እንቅፋት ይመታዋል፡፡ መኖር ባይኖር መቸገር ከወዴት አለ? መንቀሳቀስስ ባይኖር እንቅፋት ከወዴት አለ? በዓለም ሳለን መከራ እንዳለብን ይህ አስቀድሞ የተባለ አይደለምን? (ዮሐ. 16፡33)፡፡ ተወዳጆች ሆይ፤ ችግርን ብርቱ ዓይን ሲመለከተውና ደካማ ሲያየው የተለያየ ነው፤ ፈተና በሚያስተውል ሰው ጆሮና በማያስተውል ዘንድ ሲሰማ ሁለቱም ጋር አንድ አይደለም፡፡

       ለችግሮች ጊዜያዊ መፍትሔ ስለ መፈለግ ከምትደክሙ ራሳችሁን በጥንካሬ መገንባት ላይ ጊዜ ውሰዱ፡፡ ፈተና በማንኛውም ጊዜ ሊመጣ ይችላል፡፡ ዳሩ ግን ዛሬ ያልተሠራ ማንነታችሁን በቅጽበት አልያም ውስን በሆነ ጊዜ ውስጥ አትገነቡትም፤ ሁኔታዎችን ለመቀየር ከመድከም ራስን መቀየር ላይ ትኩረት ማድረግ ይበልጣል፡፡ በዚህም ችግር የማይጠጋው ሰው ሳይሆን ችግርን በትክክለኛው መንገድ የሚፈታ ሰው ትሆናላችሁ፡፡  

መልእክት ኀበ ፊልሞና፡፡(1)


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!


ሐሙስ ታህሳስ 7 ቀን 2008 የምሕረት ዓመት

(መልእክት ወደ ፊልሞና)

‹‹እምጳውሎስ ሙቁሐ ለኢየሱስ ክርስቶስ፡ (ኤፌ. 31)››!

          የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ለመንፈሳዊ ሕይወት ትክክለኛ እድገት መሰረታዊ ነገር ነው፡፡ በስብከትና በንባብ የምናዘወትረውን የእግዚአብሔር ቃል በጥናት መልክ ለመረዳት መሞከር፤ ጊዜ መድቦ መመርመር ከክፍሉ የበለጠ እንድንጠቀም ይረዳናል፡፡ በክርስትና ኑሮአችን ቋሚ የሆነ፤ አማራጭ የማናስቀምጥበት ‹‹ቃሉን የማጥናት ጊዜ›› ቢኖረን እራሳችንን፤ እንዲሁም በዙሪያችን ያሉትን እንጠቅማለን፡፡

         ተወዳጆች ሆይ፤ ያለ እግዚአብሔር ቃል በማንሻገረው የአሁኑ ዓለም ቋሚ ውጊያ እንዲሁም  በዲያብሎስ ሽንገላ መካከል እንደምንመላለስ ላስታውሳችሁ እወዳለሁ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹ . . . የመንፈስንም ሰይፍ ያዙ፤ እርሱም የእግዚአብሔር ቃል ነው›› /ኤፌ. 6፡17/ ይለናል፡፡ በሚታየው ዓለም የማይታየውን መንፈሳዊ ውጊያ በመንፈስ ሰይፍ ካልሆነ በቀር ድል ልናገኝ አንችልም፡፡