Tuesday, February 16, 2016

መልእክት ኀበ ፊልሞና፡፡(4)

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!


ማክሰኞ የካቲት 8 ቀን 2008 የምሕረት ዓመት

(መልእክት ወደ ፊልሞና)

‹‹እምጳውሎስ ሙቁሐ ለኢየሱስ ክርስቶስ፡ (ኤፌ. 3፡1)!››

‹‹ሐዋርያው ጳውሎስ በተገኘበት ቦታ ሁሉ በጥልቅ ትህትና የተመላለሰ፤ ባሮችን ነጻ የሚያወጣውን እና ከጌቶቻቸው ጋር የሚያስተካክላቸውን፤ እንዲሁም የእግዚአብሔር ልጆች የሚያደርገውን የወንጌል ኃይል የገለጠ ነው›› /ከቀደሙት፡ - ቲዎዶሬት/

‹‹የእምነት ኅብረት›› /ቁ. 6/

          ከሞት በኋላ የሚቀጥል አብሮነት ከእምነታችን ኅብረት የሚመጣ ነው (1 ዮሐ. 1፡3)፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹እምነት ከመስማት ነው፤ መስማትም በእግዚአብሔር ቃል ነው›› (ሮሜ 10፡17) እንዲል፤ እውነተኛ እምነት በእግዚአብሔር ቃል መሠረት ላይ የቆመ ነው፡፡ ፊልሞናን በተመለከተ ‹‹የእምነትህም ኅብረት›› ተብሎአል፡፡

         በቀደመው ጥናታችን በፊልሞና ቤት ውስጥ ክርስቲያኖች በኅብረት ይሰባሰቡ እንደነበር አይተናል፡፡ ይህም ኅብረት ‹‹ሁለት ወይም ሦስት በስሜ›› (ማቴ. 18፡20) የሚለውን እውነት ማእከል ያደረገ ነው፡፡ ‹‹ለተወደደውና አብሮን ለሚሠራ›› በተባለለት በፊልሞና አገልግሎትም የክርስቲያኖቹ (ቅዱሳን) ልብ አርፎአል፡፡