Wednesday, August 31, 2016

የተደረገልን /2/

              በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

 እሮብ ነሐሴ 25 ቀን 2008 የምሕረት ዓመት

           ተወዳጆች ሆይ፤ ጥበብ ለእናንተ ምንድነው? እውነተኛ ጥበብ መገኛው የት ነው? ጥበብን ስለ ማግኘት ልንከፍለው የምንችለው ዋጋ ስንት ነው? ባለፈው ክፍል ለእነዚህ ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት የሚያስችሉ በቂ አሳቦችን አይተናል፡፡ ትክክለኛውን ጥበብ ጥበባችን አድርገን እንኖር ዘንድ ጸጋው ይርዳን፡፡

           ጽድቅ

           ‹‹ሰማዮችን ቀድደህ ምነው ብትወርድ!›› (ኢሳ. 64፡1)፤ በቀደመው ኪዳን የነቢዩ የኢሳይያስ ብርቱ ጸሎትና መሻት ነበር፡፡ ይህንን ልመና ወደ እግዚአብሔር እንዲያቀርብ ምክንያት የሆነውን ነገር ስንመረምር ደግሞ ‹‹ሁላችን እንደ ርኩስ ሰው ሆነናል፤ ጽድቃችንም ሁሉ እንደ መርገም ጨርቅ ነው . . ›› (ኢሳ. 64፡6) ተብሎ ተጽፎ እናገኘዋለን፡፡ ኃጢአት በአንድ ሰው ወደ ዓለም ከገባበት (ሮሜ 5፡12) ጊዜ አንስቶ የሥጋ ለባሽ ሁሉ ብርቱ የጋራ ጩኸት ‹‹የጽድቅ ያለህ›› የሚል ነው፡፡

Wednesday, August 24, 2016

የተደረገልን

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

እሮብ ነሐሴ 18 ቀን 2008 የምሕረት ዓመት

       ማንኛውም እውነተኛ ክርስቲያን ከእግዚአብሔር ጋር ያለውን ትክክለኛ ኅብረት ከእርሱ ዘንድ የተደረገለትን በማወቅና በማመን ይጀምራል፡፡ እንዲህ የማይጀመር መንፈሳዊ ኑሮ እግዚአብሔርን ተቀባይ ራሱን ደግሞ ሰጪ አድርጎ ይሰይማል፡፡ እግዚአብሔር በፊቱ ከምናሳያቸው ትጋቶች ሁሉ በላይ ከእርሱ ለእኛ ያደረገውን ማወቃችን በእጅጉ ደስ ያሰኘዋል፤ ክብርና ምስጋናንም ያመጣለታል፡፡ ‹‹ነገር ግን፡- የሚመካ በእግዚአብሔር ይመካ፤ ተብሎ እንደ ተጻፈው ይሆን ዘንድ ከእግዚአብሔር ዘንድ ጥበብና ጽድቅ ቅድስናም ቤዛነትም በተደረገልን በክርስቶስ ኢየሱስ የሆናችሁ ከእርሱ ነው፡፡›› (1 ቆሮ. 130) ተብሎ እንደ ተጻፈ፤ እግዚአብሔር ያደረገው ሁሉ በእርሱ እንመካበት ዘንድ የተደረገ ነው፡፡

        የቆሮንቶስ መልእክት መጀመሪያይቱ በቤተ፡ ክርስቲያኒቱ (ማኅበረ ምእመናን) የነበረውን መንፈሳዊ ችግር ለመፍታት እንደ መጻፉ፤ በመልእክቱ መጀመሪያ ምእራፍ መንፈስ ቅዱስ ይህንን አሳብ ማጻፉ የቀጣይ መፍትሔ አሳቦች ትልቅ መሠረት ነው፡፡ በእግዚአብሔር ላይ የማይደገፍ ሰው፤ ቢያንስ አንድ ሌላ የሚደገፍበት አለው፡፡ ሰው ከምንም ነገር ነጻ ቢሆን እንኳ፤ ከራሱ ግን ነጻ አይደለም፡፡ ሕያው የሆነ አምላካችን እግዚአብሔር ደግሞ በሌላው ቀርቶ በራሳችንም እንድንመካ አይፈቅድልንም፡፡ ‹‹ማንም እንዳይመካ ከሥራ አይደለም›› (ኤፌ. 28) ተብሎ ተጽፎአልና፡፡

         ምእራፍ አንድ፡ - በአሁኑ ዓለም የቤተ፡ ክርስቲያን መለየትና ምስክርነት፡፡

አከፋፈል፡ -

1. በጸጋው የተደረገልን፤ እንዲሁም የተሰጠን ዋስትና (11-9)
2. ክርክርና መለያየት (110-16)
3. የክርስቶስ መስቀልና የእግዚአብሔር ኃይል (117-31)

Wednesday, August 17, 2016

ሁለቴ የኔ ነሽ፡፡ (2)

/ካለፈው የቀጠለ/      
   

እሮብ ነሐሴ 11 ቀን 2008 የምሕረት ዓመት

       ኤሎሂም የእርሱ ሥራ በሆነው ፍጥረት በኩል የጥበቡ ኃይል ብርታት ይገለጣል፡፡ ስለ ፍጥረት በተጻፈበት ክፍል ‹‹አቤቱ ሥራህ እጅግ ብዙ ነው፤ ሁሉን በጥበብ አደረግህ፤ ምድርም ከፍጥረትህ ተሞላች፡፡›› (መዝ. 103፡24) ተብሏል፡፡ ተወዳጆች ሆይ፤ እጁ ሠርታናለችና (ዘፍ. 2፡7) ስለ እኛ ሕያው እግዚአብሔር እጅግ የተመሰገነ ይሁን፡፡

       ዓለም ከተፈጠረበት ይልቅ፤ የበደለው ዓለም የዳነበት የእግዚአብሔር ጥበብ እንደሚበልጥ ሲነገር ሰምታችሁ እንደ ሆነ አስባለሁ፡፡ የእግዚአብሔር የኃይሉ ታላቅነትና የብርታቱ ጉልበት የሚታይበትን ሁለተኛውን ታላቅ ጥበብ ስናነብ ‹‹እኛ ፍጥረቱ ነንና፤ እንመላለስበት ዘንድ እግዚአብሔር አስቀድሞ ያዘጋጀውን መልካሙን ሥራ ለማድረግ በክርስቶስ ኢየሱስ ተፈጠርን፡፡›› (ኤፌ. 2፡10) ተብሎ እናነባለን፡፡ ልብ በሉ! በዚህ ክፍል ላይ ያለው መፈጠር አስቀድሞ ካየነው የተለየና አዲስ ነው፡፡ መፍጠር የሚለውን ቃል በተመለከተ ግን በግሪኩ ተመሳሳይ ግስ የምናገኘው በሮሜው ባየነውና በዚህ በኤፌሶኑ ክፍል ብቻ ይሆናል፡፡

Thursday, August 11, 2016

ሁለቴ የኔ ነሽ፡፡

                         
            
             በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

ሐሙስ ነሐሴ 5 ቀን 2008 የምሕረት ዓመት

         ‹‹አንድ ትንሽ ልጅ በእጁ የሠራት ጀልባ ከዕለታት በአንዱ ቀን ተሰረቀችበት፡፡ እንዲህ ከሆነ ከብዙ ቀናት በኋላ፤ ዕቃ እያስያዘ ገንዘብ በሚያበድር ሰው ሱቅ በኩል ሲያልፍ ጀልባውን አያት፡፡ በደስታ ወደ ሰውየው ሮጦ ‹‹ያቺ የእኔ ትንሽ ጀልባ ናት›› አለው፡፡ ዕቃ አስይዞ አበዳሪውም ‹‹የለም፤ እኔ ስለገዛኋት የእኔ ናት›› ብሎ መለሰለት፡፡ ‹‹አዎ፤›› አለ ትንሹ ልጅ፤ ‹‹ግን የእጄ ሥራ ስለሆነች የእኔ ናት›› በማለት አስረዳው፡፡ ‹‹እንግዲያውስ›› አለ ዕቃ አስይዞ አበዳሪው፤ ‹‹ሁለት ዲናር ከሰጠኸኝ ልትወስዳት ትችላለህ›› አለው፤ ጀልባውን ዳግም የራሱ ለማድረግ በብርቱ የፈለገው ልጅ የተጠየቀውን ለመክፈል የጉልበት ሥራዎችን በመሥራት ገንዘቡን አገኘ፡፡

          ከዚያም ወደ ሱቁ በመሔድ ገንዘቡን ከፍሎ ጀልባውን አስመለሰ፡፡ በመጨረሻም ጀልባውን በእጆቹ አቅፎ እየሳመ ‹‹አንቺ ውድ ትንሽ ጀልባ፤ እወድሻለሁ፡፡ አንቺ ሁለቴ የእኔ ነሽ፡፡ በፊት ሠራሁሽ፤ አሁን ደግሞ ገዛሁሽ›› አለ፡፡ /William Moses Tidwell, Pointed Illustrations (Kansas City, Mo.; Beacon Hill Press, 1951) P. 97/.

        ከላይ ያነበብነው ታሪክ የወጣ ሲመለስ፤ የጠፋ ሲገኝ፤ የወደቀ ሲነሣ . . ያለውን ደስታና እርካታ ቆም ብለን እንድናስብ ይጋብዘናል፡፡ ሁሉም ነገር ላይ ‹‹የማይዘልቅ›› የሚል በተለጠፈባት የአሁኗ ዓለም የኑሮ ሥርዓት ውስጥ ባትጠፉ እንኳ የጠፋ ፈልጋችሁ እንደምታውቁ ግልጥ ነው፡፡ የተወደደው ባለ መድኃኒቱ ሉቃስ (ቆላ. 414) በጻፈው የወንጌል ክፍል፤ ከዘኬዎስ መጎብኘት ጋር በተያያዘ ‹‹ኢየሱስም፡- . . የሰው ልጅ የጠፋውን ሊፈልግና ሊያድን መጥቶአልና›› /ሉቃ. 199/ ተብሎ ተጽፎ እናነባለን፡፡ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ፈላጊም አዳኝም›› ነው፡፡