በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
ሰኞ መስከረም 16 ቀን 2009 የጸጋ ዓመት
‹‹ፍቅርም እውነትም ማን ነው?››
ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የመስቀል አደባባዩ ትልቁ ደመራ፤ ትንንሽ
ደመራ ልጆች በየአካባቢው መታየታቸው እየተለመደ መጥቶአል፡፡ ይህ ሊሆን የቻለበትን ብንመረምር ደግሞ ብዙ ምክንያቶችን ልናገኝ እንችላለን፡፡
ነገር ግን ሁሉም ሰው በቀላሉ የሚያስተውለውን ለማየት ብንሞክር ሃይማኖታዊ መልክና ዓለማዊ መልክ ብለን በሁለት ልንከፍለው እንችላለን፡፡
ከእምነት ጋር በተያያዘ መጽሐፍ ቅዱሳዊ የመስቀሉን ቃል ይዞ
ታሪካዊ የሆነውን ተዛምዶ በማስከተል በዓል የሚያደርጉትን ልብ ስንል፤ ከዚህ ውጪ የሆነው ደግሞ መጠጥ ማሻሻጫ፤ የሥጋን ጥያቄ በመንፈሳዊ
ሽፋን ማርኪያ፤ ከአላፊ አግዳሚው ገንዘብ መሰብሰቢያ፤ መዝፈን መጨፈሪያ፤ ይህንንም የሚመስል ሁሉ ነው፡፡
ለዚህ ጽሑፍ የመጻፍ ግፊት ኃይል የሆነኝ ዛሬ ማለዳ በተንቀሳቀስኩበት
አካባቢ ዓይኖቼ የተመለከቱት ጽሑፍ ነው፡፡ ምሽት ሊለኮስ አንድ መጠት ቤት ፊት ለፊት የተደመረ ደመራ ጉልላት ላያ፤ የተመሳቀለውን
እንጨትና ጉንጉን አበባ ታኮ በነጭ ወረቀት በጥቁር እስክርቢቶ የተጻፈ ‹‹ፍቅርም እውነትም ማን ነው?›› የሚል ትልቅ ጥያቄ ላይ ዓይኖቼ አረፉ፡፡ አሥር ደቂቃ ቆሜ ብዙ አሰብኩ፡፡
ነገር ግን ቀለል አድርጌ ላየው በሞከርኩ ቁጥር ዙር እየከረረ፤ ነገሩ እየከበደ መጣብኝ፡፡ እናም ውስጤ ‹‹መልሱ ላይ ጥያቄ›› የሚል ርዕስ ተፈጠረ፡፡
ፍቅር እና እውነት በክርስትና ውስጥ እጅግ መሰረታዊ ነገሮች ናቸው፡፡
መንፈስ ቅዱስ በሐዋርያው ጳውሎስ በኩል ‹‹ . . በተጠራችሁበት መጠራታችሁ እንደሚገባ ትመላለሱ ዘንድ እለምናችኋለሁ›› ባለበት ክፍል ‹‹ . . እውነትን በፍቅር እየያዝን በነገር ሁሉ
ወደ እርሱ ራስ ወደሚሆን ወደ ክርስቶስ እንደግ›› (ኤፌ. 4፡15) ይለናል፡፡ እውነት ያመንበት መሰረት ሲሆን፤ ፍቅር ደግሞ ያመነውን
በተግባር የምንገልጥበት መንገድ ነው፡፡ እውነት ኖሯቸው ፍቅር የሌላቸው እውነቱን የብቻቸው ከማድረግ ጀምሮ ሌላውን ለመጉዳት ጭምር
ሊያውሉት ይችላሉ፡፡ ፍቅር ኖሯቸው እውነቱ የሌላቸው ደግሞ ሚዛን በሌለው ፍቅር እውነትን እየረገጡ ይበድላሉ፡፡


