Showing posts with label የሥነ ልቦና ምክክር. Show all posts
Showing posts with label የሥነ ልቦና ምክክር. Show all posts

Thursday, December 17, 2015

ድልና ምክር (2)

                          በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!



‹‹ድልም ብዙ ምክር ባለበት ዘንድ ነው›› /ምሳ. 24፡6/፤ ‹‹እርስ በርሳችን እንመካከር›› /ዕብ. 10፡25/!

                              ሐሙስ ታህሳስ 7 ቀን 2008 የምሕረት ዓመት

         ፈተና የምንኖርበት የአሁኑ ዓለም አንደኛው መልክ ነው፡፡ የኖረ ይቸገራል፤ የሚራመድን እንቅፋት ይመታዋል፡፡ መኖር ባይኖር መቸገር ከወዴት አለ? መንቀሳቀስስ ባይኖር እንቅፋት ከወዴት አለ? በዓለም ሳለን መከራ እንዳለብን ይህ አስቀድሞ የተባለ አይደለምን? (ዮሐ. 16፡33)፡፡ ተወዳጆች ሆይ፤ ችግርን ብርቱ ዓይን ሲመለከተውና ደካማ ሲያየው የተለያየ ነው፤ ፈተና በሚያስተውል ሰው ጆሮና በማያስተውል ዘንድ ሲሰማ ሁለቱም ጋር አንድ አይደለም፡፡

       ለችግሮች ጊዜያዊ መፍትሔ ስለ መፈለግ ከምትደክሙ ራሳችሁን በጥንካሬ መገንባት ላይ ጊዜ ውሰዱ፡፡ ፈተና በማንኛውም ጊዜ ሊመጣ ይችላል፡፡ ዳሩ ግን ዛሬ ያልተሠራ ማንነታችሁን በቅጽበት አልያም ውስን በሆነ ጊዜ ውስጥ አትገነቡትም፤ ሁኔታዎችን ለመቀየር ከመድከም ራስን መቀየር ላይ ትኩረት ማድረግ ይበልጣል፡፡ በዚህም ችግር የማይጠጋው ሰው ሳይሆን ችግርን በትክክለኛው መንገድ የሚፈታ ሰው ትሆናላችሁ፡፡  

Monday, November 30, 2015

እድል ፈንታችን



ሰኞ ሕዳር 20 ቀን 2008 የምሕረት ዓመት
ከወንድም እሸቱ

      ጥያቄ፡ - ‹‹ለብዙ  ጊዜ ነገሮች  ላይ እድለኛ  እንደሆንኩ ይሠማኝ ነበረ አሁን ነገሮች በተቃራኒዉ ሆኑብኝ ቀላል ሙከራየ ሁሉ ይከሽፋሉ ምን ይሻለኛል››፡፡

        ወንድም እሸቱ በሙሉ ፈቃደኝነት ችግርህን በጋራ መፍትሔ እንድንፈልግበት ልታካፍለን ስለወደድክ አስቀድሜ ላመሰግንህ እወዳለሁ፡፡ በማስከተል ችግርን በፍጹም ግልጽነት መናገር መቻል የመፍትሔው ትልቅ አካል እንደሆነ እያስታወስኩህ፤ መፍትሔ ልናገኝባቸው እንችላለን ወደምላቸው አሳቦች ከመሄዴ አስቀድሞ ጥቂት ጥያቄዎችን ልጠይቅህ (ለእሸቱ)፡፡

Friday, November 20, 2015

ድልና ምክር (1)

                                                                      

‹‹ድልም ብዙ ምክር ባለበት ዘንድ ነው›› /ምሳ. 24፡6/፤ ‹‹እርስ በርሳችን እንመካከል›› /ዕብ. 10፡25/!
                            
   አርብ ህዳር 10 ቀን 2008 የምሕረት ዓመት

         ምክክር ወደ መፍትሔ የሚያደርስ የጋራ ችግር ፈቺ ሂደት ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱሳችን በጽድቅ ላለው ምክር እንደሚጠቅም ተጽፎአል (2 ጢሞ. 3፡16-17)፡፡ በክርስትናው መሰረት ላይ ሆኖ በእለት ከእለት ችግሮቻችን ላይ በጋራ ዝርዝር መፍትሔዎችን ማስቀመጥ፤ መመካከር፤ መጠያየቅ፤ መረዳዳት በእጅጉ አስፈላጊ ነው፡፡ ተወዳጆች ሆይ፤ የመፍትሔ ሰዎች መሆን ይብዛላችሁ! 

·        በረከቶቻችሁን ቁጠሩ፡ አስቸጋሪ ሁኔታዎች ውስጥ ስትሆኑ በኑሮአችሁ ያገኛችኋቸውን በጎ ነገሮች መመልከትን አትዘንጉ፡፡ የፈተና አንዱ መልክ ያላችሁን ሳይሆን የሌላችሁን እንድታስቡ መፈተኑ ነው፡፡ ብዙ ሰዎች በዚህ መንገድ ይቸገራሉ፡፡ እግዚአብሔር ያደረገላችሁ ይታያችሁ፡፡ በትንሹ እየተቸገራችሁያላችሁት እንኳ በመኖራችሁ እንደሆነ ይታወሳችሁ፡፡ የመኖርን ሌላኛውን ገጽታ መመልከት የምንችለው በሕይወት ስላለን ነው፡፡

Friday, February 21, 2014

ምክር፡

                               
                           አርብ የካቲት 14 ቀን 2006 የምሕረት ዓመት

          ልጄ ሆይ፤ ዋዘኛና ቀልደኛ አትሁን፡፡ በመከራ ለሚኖሩ ሰዎች ሁሉ የምታዝንና የምትራራ ሁን፤ በድኃ ላይ አትጨክን፤ ርስቱንና ቤቱንም በምክንያት አትውሰድበት፤ ለመጨረስም የማትችለውን ነገር አትጀምር፡፡ እሳትና የሞላ ውኃ አትድፈር፡፡ በማናቸውም ነገር ከሚበልጥህ ሰው ጋር ባልንጀርነት አትያዝ፡፡ ከዳኛ ጋር ወዳጅ ሁን፡፡ በፊቱ በቆምህ ጊዜ እውነቱን እንዲፈርድልህ፡፡ ከሀኪምም ጋር ወዳጅ ሁን፡፡ በታመምህ ጊዜ ፈጥኖ እንዲመጣልህ፡፡

          ልጄ ሆይ፤ በልተህ ስትጠግብ ረኃብን፤ ስትበለጥግ ድኅነትን፤ ስትሾም ሽረትን፤ ሌላውንም ይህን የመሰለውን ሁሉ አትርሳ፡፡

         ልጄ ሆይ፤ ለሞተው ወዳጅህ ከማልቀስ ይልቅ በሕይወቱ ሳለ የክፋት ሥራ ለሚሠራ ወዳጅህ አልቅስለት፡፡

         ልጄ ሆይ፤ ባለ ጠጋ ሲወድቅ ሰው ሁሉ ይደግፈዋል፤ ድኃ ሲወድቅ ግን ሰው ሁሉ ወዲያው ይገፋዋል፡፡ ባለ ጠጋ ሲከሰስ በሸንጎ የተቀመጠው ሁሉ ይሟገትለታል፤ ድሀ ሲከሰስ ግን በሸንጎ የተቀመጠው ሁሉ ይፈርድበታል፡፡ መልካም ዳኛ በመካከላቸው የተቀመጠ እንደ ሆነ ግን ፍርዱ እንደ ፀሐይ ያበራለታል፡፡ ስለዚህ በምትኖርበት ሀገር መልካም ዳኛ አያጥፋብህ፡፡

Tuesday, February 18, 2014

ምክር፡

                                    Please Read in PDF: Miker 4

                                       
                    ማክሰኞ የካቲት 11 ቀን 2006 የምሕረት ዓመት

        ልጄ ሆይ፤ ክፉ ሕልም አለምሁ ብለህ አትደንግጥ፡፡ ደግ ሕልምም አየሁ ብለህ ደስ አይበልህ፡፡ ሕልም ማለት የሰው አሳብ እንደ ሆነ እወቅ፡፡ እንኳን ሌሊት በሕልም ቀንም ባይን የታየ ነገር ሳይደረግ ይቀራል፡፡ ደግሞ ሌሊት በሕልም፤ ቀንም ባይን ያልታየ ነገር እንዲያው በድንገት ይደረጋል፡፡ እግዚአብሔር ይሁን ያለው ነገር ጊዜውን ይጠብቃል እንጂ ምንም ቢሆን ሳይሆን አይቀርም፡፡

         ልጄ ሆይ፤ አካልህና ልብስህ ዘወትር ንጹሕ ይሁን፡፡ እጅህን ለሥራ፤ ዓይንህን ለማየት፤ ጆሮህን ለመስማት ፈጣኖች አድርግ፡፡ አፍህን ግን በጠንካራ ልጓም ለጉመህ ያዝ፡፡ አረጋገጥህ በዝግታ፤ አነጋገርህ በለዘብታ ይሁን፡፡ ያልነገሩህን አትስማ፤ ያልሰጡህን አትቀበል፡፡ ያልጠየቁህን አትመልስ፡፡ ሽቅርቅር አትሁን፤ ንብረትህ ጠቅላላ ይሁን፤ ምግብህና መጠጥህ በልክ ሆኖ ያው የጠዳና የጣፈጠ ይሁን፡፡ ምግብህና መጠጥህም የሚቀርብበት ዕቃ ሁሉ ንጹሕ ይሁን፡፡ የምትተኛበት አልጋና የምትቀመጥበት ስፍራ ከእድፍና ከጉድፍ ንጹሕ ይሁን፡፡ በእውነትና በሚገባ ነገር ሁሉ ይሉኝታ አትፍራ፡፡ የምትሠራው ሥራ ሁሉ የመንግሥት ሥራ ካልሆነ በቀር ፖለቲከኛ አትሁን፡፡

Tuesday, February 11, 2014

ምክር፡



                         ማክሰኞ የካቲት 4 ቀን 2006 የምሕረት ዓመት

       ልጄ ሆይ፤ በነገርህ ሁሉ የታመንህ ሁሉ፡፡ በአነጋገርህም ደማም ሁን፡፡ ሰውን የሚያስፈራና የሚያሳዝን ነገር ለመናገር አትድፈር፡፡ በልዝብ ምላስ ሰውን አታታል፡፡ ሰውንም ከሚያሙ ሰዎች ጋር አትደባለቅ፡፡ ልጄ ሆይ፤ ንብረትህ በልክ ይሁን፡፡ ቤተ ሰዎችም አታብዛ የቀንድ ከብትና የጋማ ከብትም በብዙ አታርባ፡፡ ላንተ የማይገባውን ነገር ከማንም ቢሆን አትቀበል፡፡ አንተም ለማንም ቢሆን የማይገባውን ነገር አትስጥ፡፡ የማታገኘውንም ነገር አትመኝ፡፡ በዓይንህ ካላየህና እርግጥ መሆኑን ካልተረዳኸው በቀር በማንም ሰው ላይ የሚወራውን ወሬ እውነት ነው ብለህ አትቀበል፡፡ ለሰውነትህ የሚያስፈልገውን ነገር ለማግኘት አስብ እንጂ ሰው የሚጠፋበትን ሰው የሚጨነቅበትን ነገር አታስብ፡፡

       ልጄ ሆይ፤ ሮጠህ ለማታመልጠው ነገር አትሽሽ፡፡ እርሱም ሞት ነው፡፡ ደጋ ብትወጣ፤ ቆላ ብትወርድ፤ ወንዝ ተሻግረህ ብትሔድ፤ በዋሻ ብትደበቅ፤ ጠመንጃና መድፍ ይዘህ ብትሰለፍ ምንም ቢሆን ከሞት ለማምለጥ አትችልም፡፡ እግዚአብሔርንም ፍራ በሥጋና በነፍስ ላይ ሥልጣን አለውና፡፡ ንጉሥንም አክብር እግዚአብሔር ሠይፍን አስታጥቆታልና፡፡ በአንተም ላይ የሹመት ሥልጣን ያላቸውን አገረ ገዢዎችን ሁሉ አክብራቸው፤ ታዘዝላቸው፡፡ አባትና እናትህን፤ የእግዚአብሔርን ቃል የሚያስተምሩህን መምህሮችህን፤ የሀገር ሽማግሌዎችንና ባልቴቶችን ሁሉ በሚቻልህ ነገር እርዳቸው፡፡

       ልጄ ሆይ፤ ካረጀህ በኋላ እንደ ገና ተመልሼ ምነው ልጅ በሆንኩ ብለህ አትመኝ፡፡ ምንም ቢሆን አታገኘውምና፡፡ ወደፊትም ምነው በሞትኩ ብለህ አትመኝ፤ ምንም ቢሆን አይቀርልህምና፡፡
        ልጄ ሆይ፤ እገሌ ቸር ነው ይበሉኝ ብለህ ገንዘብህን ለማንም አትስጥ፡፡ ለወዳጅ ከመስጠት ለዘመድ መስጠት ይሻላል፡፡ ለጠላት ከመስጠት ለወዳጅ መስጠት ይሻላል፡፡ ከሁሉ ይልቅ ለተቸገሩ ድሆች መስጠት ይበልጣል፡፡ ለድሆች የሰጠ ሰው ብድሩን በሰማይ ያገኛል፡፡

       ልጄ ሆይ፤ ማናቸውንም ነገር ቢሆን ለመስማት እንጂ ለመናገር አትቸኩል፡፡ ከወዳጅህም ጋር በተጣላህ ጊዜ ቀድሞ በወዳጅነታችሁ ጊዜ የነገረህን ምስጢር አታውጣበት፡፡ ከወዳጅህም ጋራ አንድ ጊዜ ጠብ ከጀመርክ በኋላ፤ ምንም ብትታረቅ ሁለተኛ ምስጢርህን ለእርሱ ለመናገር አትድፈር፡፡ ቂምህንም አትርሳ፡፡ ቂምህን አትርሳ ማለቴ ከታረቅህ በኋላ ክፉ አድርግበት ማለቴ አይደለም፡፡ ነገር ግን እርሱ ሞትንና ኩነኔን የማያስብ ክፉ ሰው የሆነ እንደ ሆነ እርቅ አፍርሶ እንዳያጠፋህ ሳትዘናጋ ተጠንቅቀህ ተቀመጥ ማለቴ ነው፡፡