Thursday, September 27, 2012

የገላትያ አዚም



          የእግዚአብሔርን ሕልውና የተቀበልንበት መንገድ እምነት ነው፡፡ እርሱን ያየውና የዳሰሰው የለም፡፡ ስለ እርሱ ከሰማነው ቃል የተነሣ ግን ወደ ማመን ከፍታ መምጣ ሆኖልናል፡፡ በእርሱና በእኛ መካከል ያለው መግባባት የተመሰረተው በእምነት ላይ እንደሆነ ለልባችን ማስረገጥ እንችላለን፡፡ እግዚአብሔርን ብቻ ሳይሆን የእግዚአብሔር የሆነውን ሁሉ በረከት የምንቀበለው የእግዚአብሔርን ሕልውና በተቀበልንበት መንገድ ነው፡፡ ራሱን በማመን ሰጥቶን የእርሱ የሆነውን እንደ ትጋታችን መጠን ሊሰጠን አይችልም፡፡ ምክንያቱም ስጦታው ጸጋ (የማይገባ) ነው!
          ሐዋርያው ለገላትያ ሰዎች በፃፈው መልእክት “የማታስተውሉ የገላትያ ሰዎች  ሆይ በአይናችሁ ፊት ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ተሰቀለ ሆኖ ተሥሎ ነበር ለእውነት እንዳትታዘዙ አዚም ያደረገባችሁ ማን ነው? (ገላ. 3÷1)” በማለት መጠይቃዊ ተግሳጽ ሲያስተላልፍ እናስተውላለን፡፡ የገላትያ ሰዎች ከሚያስመካው የእግዚአብሔር ጽድቅ ይልቅ በራሳቸው ጥረት የተመኩ ነበሩ፡፡ በሕግና በነቢያት የተመሰከረለትን ነገር ግን ያለ ሕግ የተገለጠውን የመለኮት ጽድቅ በሥጋቸው ውስጥ ካለው ትምክህት የተነሣ ገፍተውት ነበር፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ እንግዲያማ ክርስቶስ በከንቱ ሞቶአል? እስኪል ድረስ የሕዝቡ ድንዛዜ የክርስቶስን ሞትና ትንሣኤ ዋጋ ያሳጣ ነበር፡፡ ከዚህም የተነሣ ለእውነት እንዳይታዘዙ ልባቸው ደነደነ፡፡
          ለእነርሱም የእግዚአብሔር ምሳሌ የሆነ የክርስቶስ የክብሩ ወንጌል ብርሃን እንዳያበራላቸው የዚህ ዓለም አምላክ የማያምኑትን አሳብ አሳወረ (2 ቆሮ. 4÷4) ተብሎ እንደተፃፈ የዲያብሎስ ውጊያ ከአሳባችን ጋር ነው፡፡ አሳባችንን ማሳወር! ሰው ደግሞ ልቡ (አሳብ) ካላየ አይኑ አያስተውልም፡፡ በተለይ በእምነት ውስጥ ስንኖር የዚህ እውነት ተግባራዊነት ግልጽ ይሆናል፡፡ በአንድ ሰው ውስጥ ያለው ትልቁ ሐብት አሳቡ ነው፡፡ ለዚህም ነው በጉብዝናህ ወራት ፈጣሪህን አስብ የተባለው፡፡ ጉብዝናችንን እግዚአብሔርን ካላሰብንበት ሽምግልናችን የጸጸት ይሆናል፡፡ የምድሪቱ ጩኸት ምንድነው ካልን መልሱ “የአስተሳሰብ ለውጥ” የሚል ነው፡፡ ሐዋርያው የማታስተውሉ የገላትያ ሰዎች ሲል አእምሮ የሌላችሁ ማለቱ አይደለም፡፡ እየሰማችሁ የማትረዱ፣ እያያችሁ የማትቀበሉ፣ በተገለጠው እውነት የማታምኑ ማለቱ ነው፡፡
          ተግባራዊ ወደሆነው ሕይወታችን ስንመጣ የገላትያ አዚም በግልጥ ይስተዋላል፡፡ አዚም መፍዘዝንና መደብዘዝን የሚያመለክት ቃል ሲሆን ይህም ከድግምት ኃይል ጋር የተቆራኘ ነው፡፡ የሥራ ብዛት፣ የጤና መቃወስ፣ የእድሜ ሕፃንነት ያመጣው መንፈሳዊ ችግር ሳይሆን እግዚአብሔር በልጁ የሠራውን ማዳን ባለማስተዋል፣ ከመንፈሳዊ ጤና ማጣትና በቃሉ ካለማደግ ጨቅላነት የሚመጣ ድንዛዜ ነው፡፡ ይህም የዚህ ዓለም አምላክ በተባለው ሰይጣን አጋዥነት የሚከወን ድርጊት ነው፡፡
         ኢየሱስ ክርስቶስ እንድናስታውሰው ያዘዘን ሞቱንና ውርደቱን ነው፡፡ ምክንያቱም የእኛ ታሪክ መቀየር ያለው እርሱ በመስቀል ላይ ኃጢአታችንን ተሸክሞ የሕግ እርግማን ሆኖ በመሞቱ ነው (ዘዳ. 21÷23)፡፡ እኛ የተዋረድንበትን ቀን ሌሎች አይደሉም እኛው ራሳችን እንኳን ልናስበው አንፈልግም፡፡ ቤታችን ላይ የሚሰቀለው ፎቶ እንኳ ምቾታችንን የሚያሳየው ተመርጦ ነው፡፡ ከስተን ጠቁረን የተነሣነው የት ነው የሚቀመጠው? ጌታ ግን በእጅና በእግሮቹ ላይ ችንካር እንዳለፈ፣ ፊቱ ላይ ምራቅ እንደተተፋ፣ ራሱ ላይ የእሾህ አክሊል እንደደፋ፣ ጀርባው በጅራፍ እንደተገረፈ፣ በየሸንጎው እንደተንገላታ፣ እርጥብ እንጨት ተሸክሞ ተራራው ላይ ደፋ ቀና እንዳለ አስቡት ሲል አላፈረም፡፡
          ለጠፋው መልካችን መልክ የሆነን ባየነው ጊዜ እንወድደው ዘንድ ደምግባት የለውም ተብሎለት ነው (ኢሳ. 53÷2)፡፡ የተናቀ ከሰውም የተጠላ የሕማም ሰው ደዌንም የሚያውቅ ስለ መተላለፋችን የቆሰለ ስለ በደላችን የደቀቀ እርሱ ነው፡፡ ከመስቀሉ ጋር የተያያዘው ሕይወት ሕይወቱን ለእኛ አሳልፎ የሰጠው ጌታ ነው፡፡ የምናከብረውም እንደ ወንበዴ የተሰቀለልንን ፃድቅ ክርስቶስን ነው፡፡ በኃጢአት ምክንያት ያጣነው መልካችን ጽድቅ፣ ቅድስና እና እውቀት የተመለሰው ክርስቶስ መልክ ሆኖልን ነው፡፡ እርሱ ደምግባት የለውም ቢባልለትም መልካችን ነውና አናፍርበትም፡፡ በመልኩ የሚያፍር የለምና፡፡
          በኃጢአት ምክንያት በእኛና በእግዚአብሔር መካከል የነበረው የጥል ግድግዳ (ኤፌ. 2÷14) የፈረሰው እርሱን እግዚአብሔር በእምነት የሚገኝ በደሙም የሆነ ማስተስሪያ አድርጎ ስላቆመው ነው (ሮሜ. 3÷25)፡፡ ሁላችንም እንደሚገባን በሁለት ሰዎች መሐል ለረጅም ጊዜ ጸብ ቆሞ ከነበረ የሚፈርሰው እርቅ በመካከላቸው ሲቆም ነው፡፡ አለዚያ ቦታው ባዶ ሊሆን አይችልም፡፡ በእግዚአብሔር ፊት ተቀባይነት ያገኘነው በልጁ በክርስቶስ ክርስቲያን በሆንበት መታወቅ ነው፡፡ ሁላችንም ዳግም የእግዚአብሔር የሆነው በልጁ በክርስቶስ ቤዛነት በኩል ነው፡፡ ስለዚህም ክርስቶስ መታወቂያችን ነው፡፡ ታዲያ ልጁ የሌለው ሕይወት የለውም ቢባል ምን ይደንቃል?
           ዳሩ ግን ይህንን ሁሉ የእግዚአብሔር ባለ ጠግነት እንዳናስተውል ደግሞም ለእውነቱ እንዳንታዘዝ በኑሮአችን ውስጥ ልዩ ልዩ አዚም ጋርዶን ይስተዋላል፡፡ ሐዋርያው በፊታችሁ እንደተሰቀለ ሆኖ ይላል፡፡ እለት እለት በፊታችን እናስተውለው ዘንድ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ያደረገልን ውለታ በግልጥ ተስሏል፡፡ የእግዚአብሔር ውለታ ደግሞ ወቅት እየጠበቅን የምንዘክረው ሳይሆን በየጊዜው የምናከብረውና ልባችን ላይ ትልቁን ስፍራ የያዘ ሐቅ ሊሆን አግባብ ነው፡፡
            እርሱ ስለ እኛ በመስቀል ላይ እንዴት ራሱን እንዳዋረደ ስናስተውል ክብሬ ብለን አንሟገትም፡፡ እርሱ ሕማማችንን እንዴት እንደተሸከመ ስናስተውል ሕመማችንን ቆጥረን አንማረርም፡፡ እርሱ በመከራ እንዴት እንደደቀቀ ስንረዳ የሰዎች ማሳዘን፣ የኑሮ ውጣ ውረድ፣ የሕይወት ፈተናችን ሁሉ ይፈወሳል፡፡ ተወዳጆች ሆይ የተሰቀለውን እዩ! ደግሞም ስላደረገው ሁሉ ልባዊ በሆነ መንገድ ስሙን አክብሩ፡፡ በገላትያ ምእመናን ላይ የተስተዋለው አዚም ግን ለዘላለም አይግዛን!!      
            

Tuesday, September 18, 2012

የተወጋ ሲረሳ (ክፍል አራት)


                    
“ዮፍታሔም የገለዓድን ሽማግሌዎች፡- የጠላችሁኝ ከአባቴም ቤት ያሳደዳችሁኝ እናንተ አይደላችሁምን? አሁን በተጨነቃችሁ ጊዜ ለምን ወደ እኔ መጣችሁ? አላቸው” (መ. መሳ. 11÷7)፡፡
        ተስፋ መቁረጥ ማለት ከጨለማ ቀጥሎ ብርሃን፣ ከመጨነቅ ቀጥሎ ሰላም፣ ከድካም ቀጥሎ ድል፣ ከርሀብ ቀጥሎ ጥጋብ፣ ከስደት ቀጥሎ እረፍት እንደሚመጣ አለማስተዋል ነው፡፡ የጠሉን እንደጠሉን፣ ያሳደዱን እንዳሳደዱን፣ የናቁን እንደናቁን፣ ያሳዘኑን እንዳስነቡን፣ ያስቸገረን እንዳማረረን አለመቀጠሉ ለመኖር የምንናፍቅበት ጥቂቱ ምክንያታችን ነው፡፡ ያስጨነቁን አንድ ቀን ይጨነቃሉ፣ ያሳደዱን አንድ ቀን ይሰደዳሉ፣ ያስቸገሩን አንድ ቀን ይቸገራሉ፡፡ ያን ጊዜ እኛን እግዚአብሔር መፍትሔ ያደርገናል፡፡ ያስከፉን ተከፍተው ይመጣሉ፡፡ ያን ጊዜ እኛ መጽናናት ነን፡፡ ያቆሰሉን ታመው ይመጣሉ፡፡ ያን ጊዜ መፈለግንም ማድረግንም በእኛ ከሚሠራው ጌታ የተነሣ ፈውስ ነን፡፡ የነቢዩ የዳዊት ታላቅ ወንድም ኤልያብ ዳዊትን እንደ ችግር ቢቆጥረውም እግዚአብሔር ግን እርሱን ለእስራኤል መፍትሔ አድርጎት ነበር (1 ሳሙ. 17÷28)፡፡  
        የዮፍታሔ ሕይወት ተወግቶ መርሳትን፣ ተበድሎ መማርን፣ ተንቆ ማክበርን የምንማርበት ነው፡፡ የልዩ ሴት ልጅ መሆኑ በአባቱ ቤት ካለው ሀብት እንዳይካፈል አደረገው፡፡ ከዚህም በላይ ከአካባቢው እንዲሰደድ ሆነ፡፡ ይህ የሆነው ደግሞ ከአንድ አባት በተወለዱ ወንድሞቹ ነው፡፡ እንዲህ ያለው መወጋት ሕመሙ ምን ያህል እንደሆነ በዚህ ያለፉ ሁሉ አይስቱትም፡፡ የሰው ፊት ለጠቆረብን፣ ጥላቻቸው እንደ ሳማ ቅጠል ለሚለበልበን፣ ወድደን መከዳት፣ ፈልገን መገፋት፣ ተጠንቅቀን መረሳት ለገጠመን ይህም ዘመን አልፎ የመወደድ ጊዜ ይመጣልና በዚህ ቃል ተጽናኑ፡፡
        የመጣል ዘመን አልፎ የመፈለግ ጊዜ ይመጣል፡፡ ገፍተው ያባረሩን ለምነው ይገናኙናል፡፡ አዋርደው የሰደዱን አክብረው ይቀበሉናል፡፡ በዮፍታሔ የሆነው ልክ እንደዚህ ነው! ከአባቱ ቤት ያሳደዱት፣ ከጋለሞታ ሴት በመወለዱ የናቁት፣ በእግዚአብሔር ዘንድ ያለውን ሞገስ ሳያስተውሉ ቁሳዊውን ነገር የከለከሉት ሰዎች የዮፍታሔን ጽናትና ኃይል የሚፈልጉበትና የሚያስተውሉበት ሁኔታ ተፈጠረ፡፡ እግዚአብሔር ሲገልጠን የትኛውም የሰው አሳብ ሊሸፍነን አይችልም፡፡ ጸጋው በድካማችን ይገለጣልና በዚህ እንመካለን፡፡
        ለሰው ከባዱ ነገር መጠበቅ ነው፡፡ በተለይ በጭንቀትና በብዙ ውጣ ውረድ ውስጥ እያለፍን የእግዚአብሔርን ምላሽ በእምነት መታገስ ጭንቅ ይሆንብናል፡፡ በማርቆስ ወንጌል ምእራፍ አምስት ላይ ኢያኢሮስ የተባለ የምኩራብ አለቃ ልጁ ታማበት ጌታ እንዲፈውስለት ተማጸነው በመንገድም ሳሉ አሥራ ሁለት ዓመት ደም የሚፈስሳት ሴት ጌታን አዘገየችው፡፡ ኢየሱስም ቆመ! የነካውም ማን እንደሆነ ጠየቀ፡፡ እንዲህ ያለው ሁኔታ የአለቃውን እምነት ምን ያህል እንደሚፈትነው አስቡ፡፡ በቤቱ ውስጥ በሞትና በሕይወት መካከል ያለች ልጁን እያሰበ በተመሳሳይ ሁኔታ ደግሞ ጌታን ቆሞ መጠበቅ ነበረበት፡፡ ይህ ምንኛ የሚያስደንቅ እምነት ነው?
          ከቤቱ ሰዎች መርዶ ይዘው ሲመጡ እርሱ ያመነ እንጂ የፈራ አልነበረም፡፡ ክርስቶስ እስኪመጣ ድረስ ታሪካችን በበደልና በኃጢአት ምክንያት የዘላለም ሙታን የሚል ነበር፡፡ በየትኛውም አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የምናልፈው እርሱ በአስቸጋሪ ሁኔታዎቻችን ላይ በኃይልና በብርታት እስኪገለጥ ድረስ ነው፡፡ የሚያምኑ ሁሉ የሚያስመካውን ጌታ ታምነው ይጠብቁታል፡፡ ጨለማ ቢያስፈራችሁ እርሱ የማይጠፋ ብርሃን ነው፡፡ የእንጀራ ዋስትና ቢያሻችሁ እርሱ የሕይወት እንጀራ ነው፡፡ መከዳት ቢሰብራችሁ እርሱ የእስከ መጨረሻ ወዳጅ ነው፡፡ የጠላት ፍላፃ ቢከብባችሁ እርሱ የማይደፈር የበጎች በር ነው፡፡ የሞት ጣር ቢያስጨንቃችሁ እርሱ ትንሣኤና ሕይወት ነው፡፡ በእርግጥም ጌታ ለሚጠብቁት ከግምት በላይ ይሠራል፡፡ በእኛም ሕይወት ጌታ ከዚህ በላይ ይሠራል፡፡ በየትኛውም ሁኔታ ውስጥ የእርሱን አሠራርና ጊዜ በጽናት መጠበቅን መለማመድ ይኖርብናል፡፡ ቢዘገይም የእግዚአብሔር ይበልጣል፡፡
          ተወዳጆች ሆይ ከፍርሃቶቻችሁ ጋር ሳይሆን ከተስፋዎቻችሁ ጋር ተወያዩ፡፡ ስለ ሰዎች ማሳደድ ሳይሆን ተቀባይ ስለሆነው የእግዚአብሔር ብርቱ ክንድ አስቡ፡፡ በአጣችሁት ነገር መብሰልሰሉን ትታችሁ በምሕረቱ ባለ ጠጋ የሆነውን ጌታ ታመኑት፡፡ አስተዋይ ሰው በፊቱ ያለውን መከራ ሳይሆን በልቡ ያለውን ራዕይ እየተከተለ በትዕግስት ይጓዛል፡፡ ተስፋ የሕይወት ዘመናችን ብቸኛው ወዳጅ ነው፡፡ የሚበልጠው ተስፋችን ደግሞ ክርስቶስ ኢየሱስ ነው!
          በፈተና ውስጥ ስትሆኑ ከሁሉም ነገር በላይ የልባችሁን ሰላም ጠብቁ፡፡ ከማንኛውም ሀብት ይልቅ የከበረ ነውና፡፡ ዛሬ ያጣነው ነገር ነገ በተሻለ ይኖረን ይሆናል፡፡ ዛሬ ራሳችንን ከከሰርን ግን ነገ ባዶአችንን ነን፡፡ ስለዚህ ራሳችሁን ለእግዚአብሔር ስጡ፡፡ ሰዎች ከሚበድሉን በላይ እኛ በደሉን በማሰላሰል የምንከፍለው ዋጋ ይከፋል፡፡ ለራሳችንና ለሌሎች ምሕረት ስናደርግ ግን ተወግቶ የመርሳትን በረከት እንለማመዳለን፡፡
          ዮፍታሔ የጠሉት ሰዎች በጠላት እጅ ሲወድቁ “የዘሩትን ይጨዱ” በማለት በተማጽኗቸው ላይ አልጨከነም፡፡ የገዛ ወገኖቹ ወግተውት ቢረሱም እርሱ ግን ተወግቶ አላስታወሰውም፡፡ የእርሱ ወደ ሆነው መጣ÷ የገዛ ወገኖቹም አልተቀበሉትም (ዮሐ. 1÷11) ተብሎ እንደተፃፈ ክርስቶስ በገዛ ወገኖቹ ተቀባይነትን አጥቶአል፡፡ እስከ መስቀል ሞትም አሳድደውታል፡፡ እርሱ የናዝሬቱ ኢየሱስ ቢሆንም በዚያው ልክ ደግሞ የነገሥታት ንጉስ የጌቶችም ጌታ ነው፡፡ መልካም ነገር አይወጣብሽም ከተባለችው ከተማ የመልካምነት ልክ፣ የደግነት ዳርቻ፣ የሕግ ሁሉ ፍፃሜ የሆነው ክርስቶስ ተገኝቶአል፡፡ ከዚህ ጌታ ጽናትና ኃይል መካፈል የሚፈልጉ ሁሉ ነቀፋውን ተሸክመው ዮፍታሔን እንደተከተሉት ምናምንቴ ሰዎች ከሰፈር ውጪ (ከሥጋ አሳብ) እርሱን መከተል አለባቸው፡፡ ተወግቶ መርሳት ቀላል አይደለም፡፡ ግን ደግሞ በዚህ ውስጥ ያለው ትርፍም ቀላል አይደለም፡፡ ለዚህ ያለ ልክ ከፍ ከፍ ያለው፣ ከአለቅነትና ከሥልጣንም ከኃይልም ከጌትነትም ሁሉ በላይ ከዚህና ከሚመጣው ዓለም የሚልቅን ስም የያዘው ጌታ ሕያው ትምህርት ነው፡፡   
                                                              - ይቀጥላል -


Tuesday, September 11, 2012

እቅድ በአረቄ


  
         ዘመን የማይቆጠርለት እግዚአብሔር የዘመኖቻችንን ርዝማኔ ወስኖ ለእድሜያችን ዳርቻ አበጅቶ ሁሉን በሚችለው ኃይሉ ፍጥረትን ያኖራል፡፡ ታዲያ ከዘመን ለውጥ ጋር ተያይዞ ሰዎች ኑሮአቸውን ሲፈትሹ የጎደለውን ለመሙላት፣ ያረጀውን ለማደስ፣ የጠመመውን ለማቅናት፣ የሚናፍቁትን ለመያዝ ያለፈውን ገምግመው ለወደፊቱ እቅድ ያወጣሉ፣ ያንንና ይህንን ለመሥራት ይወጥናሉ፡፡ ሰው እንስሳ ስላልሆነ በዘፈቀደ ሊኖር አይችልም፡፡ መብላት መጠጣት፣ መንቃት ማንቀላፋት፣ መውለድ ማሳደግ እግረ መንገድ እንጂ የተፈጠርንበት ብቸኛ ምክንያት አይደለም፡፡ ስለዚህ በእቅድና በዓላማ መኖር እንደ አማኝ መኖር ሳይሆን አንደ ሰው የመኖር ጥበብ ነው፡፡  
         ዘመን ስጦታ ነው፡፡ የምንፎክርበት ሳይሆን የምንሠራበት፣ የምንዝናናበት ሳይሆን የምንዘጋጅበት፣ የምንበድልበት ሳይሆን በንስሐ የምንታጠብበት ነው፡፡ እግዚአብሔር በእድሜ በረከት የሚጎበኘን የሥጋን አሳብ ወደ ፍፃሜ እንድናደርስ ሳይሆን ሥጋን ከነመሻቱ ሰቅለን ስለ በደላችን የሞተውን ደግሞም እኛን ስለማጽደቅ የተነሣውን የእግዚአብሔር ልጅ በማመን የዘላለም ሕይወት እንዲሆንልን ነው፡፡ ዘመንን እግዚአብሔር በእኛ ላይ ካለው ዓላማ አንፃር ማየት መቻል በብዙ ማትረፍ ነው፡፡ ዘመንን እንደ ስጦታ ካሰብነው በየትኛውም ጊዜ ሊወሰድ ይችላል ማለት ነው፡፡ ሙሉ ሥልጣኑም በሰጪው ዘንድ ነው፡፡ ስለዚህ የተሰጠንን ዕድሜ በእግዚአብሔር አሳብ፣ በፍቅር፣ በጤና፣ በይቅርታ፣ በለጋስነት . . . . ልንከባከበው ይገባል፡፡ በእድሜአችን ምሽት ላይ የማናፍርበትን ነገር ለማየት ቀን ሳለ እንደሚገባ ልንሠራና እንደ ታማኝ ሎሌ ልንተጋ ያስፈልገናል፡፡
         በሌላ ጎን የአዲስ አመት መምጣትን ለሞት ከፊት ይልቅ መቅረብ እንደሆነ ልናስተውል ይገባናል፡፡ ሃምሳ ዓመት የሚኖር አንድ ሰው አርባኛ አዲስ አመቱን ቢያከብር የቀረው አሥር ዓመት ይሆናል፡፡ ይህ ሰው በሕይወት ዘመኑ ሊሠራው የሚገባውን በቀልድ ቢያሳልፍ አሥሩ ዓመት ቀልዱን ለማረም እንኳን አይበቃውም ማለት ነው፡፡ ለዚህ ጽሑፍ መነሻ የሆኑኝ ሰው እቅድን ከአረቄ ጋር ያያዙ ሰው ናቸው፡፡ ለዚህም ቅዱስ ጳውሎስ ለጢሞቴዎስ የተናገረውን ምክር ይጠቅሳሉ፡፡
          ብዙ ጊዜ የሚስተዋለው ችግር ከራስ አሳብና ፈቃድ ተነሥቶ ወደ እግዚአብሔር ቃል የሚደረግ ጉዞ ላይ ነው፡፡ ምክንያቱም የምናጣቅሰው ሁሉ የራሳችንን አሳብ እንዲደግፍልን በመሻት ስሜት ውስጥ ሆነን ነው፡፡ ይህ ቃሉን ከልባችን ምክር ጋር እንዲስማማ በግድ መጠምዘዝ ነው፡፡ ነገር ግን ከቃሉ ተነሥተን ወደ ራሳችን ሕይወት ብንመለከት እንደ ቃሉ ራሳችንን ማስተካከልና መታዘዝን እናሳያለን፡፡ ለእነዚህ ሰው አረቄ ከሌለ እቅድ የለም፡፡ አዲስ አመት ያለ አረቄ እርሳቸው ጋር ትርጉም የለውም፡፡ ሲጠጡ የማያፈርሱት ጎጂ ነገር፣ የማይገነቡት በጎ ነገር የለም፡፡ ከጠጡ ሰፈራቸው ኒዮርክ፣ መዝናኛቸው ባንኮክ ነው፡፡
         የማይሰጡት ተስፋ፣ ቃል የማይገቡት ነገር የለም፡፡ የድህነት ወሬአቸው እንኳን የሀብትን ያህል ያስፈነድቃል፤ ልክ እንደ አመት በዓል ሆያ ሆዬ ለአንዱ መኪና ለሌላው መርከብ፣ አንዱን ዘፋኝ ሌላውን መሪ፣ አንዱን ዶክተር ሌላውን መሃንዲስ ብቻ የሚሰጡት እንደ ቸርነታቸው ነው፡፡ መመረቅ ከፈለጋችሁ መለኪያ አረቄ በተኮማተሩት እጆቻው ማስያዝ ነው፡፡ ለአሜንታ እንኳን ክፍተት ለምናችሁ ካልሆነ በቀር ፍንክች የለም፡፡ አንዳንዴ እንዲህ ያለውን እቅድ ሳይሰክሩ ቢያቅዱት ኖሮ ብዬ እቆጫለው፡፡ ሲጠጡ ባለ ብዙ ራዕይ ባለ ብዙ ዓላማ፤ ከመለኪያው ሲርቁ ከስካር ሲነቁ ደግሞ ቀልደኛ ነዋሪ ናቸው፡፡ (አንድምታው ቁጭ ሲል ይነፋዋል ሲቆም ይጠፋዋል እንዲል) የአረቄ ዕቅድ ይሏችኋል እንግዲህ ይህ ነው!
         ለብዙ ሰው አዲስ ዓመት ከእቅድ አንፃር ብቻ ሳይሆን ከመጠጣት፣ ከመልበስ፣ ከዝሙት እንዲሁም ከብዙ ምድራዊ ክፉ ነገሮች ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ለመኖር ብቻ ሳይሆን ለማጥፋትም ይታቀዳል፡፡ አዲስ ዓመትን ሕሊናዊ ከሆነ ነገር ጋር እንጂ ቁሳዊ ከሆነ ነገር ጋር ማያያዝ ትርፉ በጣም ትንሽ ነው፡፡ እኛም ልክ እንደ ዳዊት “በጎ ዘመንን ለማየት የሚወድድ ማነው?” (መዝ. 33÷12) ብልን እንጠይቅና በጎ ዘመንን ለማየት፡-
1. ላለፈው ስህተት ይቅርታ ማድረግ፡- አብሮን መሻገር የሌለበት ነገር ቢኖር በደል ነው፡፡ እኛ በሰው ላይ የሠራነውን ይቅርታ በመጠየቅ፣ ሌሎች በእኛ ላይ ላደረጉብን ደግሞ ይቅርታ በማድረግ እንዲሁም በእግዚአብሐር ላይ ላሳየነው አመጽ ንስሐ በመግባት ያለፈውን የዘመን ምእራፍ በመዝጋት አዲሱን መጀመር ይኖርብናል፡፡ ቤታችንን ስናድስ ቀለም ስንቀባ ቁሻሻውን ስናስወግድ የሕያው እግዚአብሔር ቤተ መቅደስ የሆነው ሰውነታችን ቅድሚያ ሊሰጠውና ሊታለፍ የማይገባው ነው፡፡  
2. እንደ ዘመኑ ሳይሆን እንደ ጌታ አሳብ መኖር፡- በየዘመኑ በኑሮአችን  ውስጥ የምናስተውላቸው በበጎም ይሁን በመጥፎ ለየት ያሉ ነገሮች አሉ፡፡ የሩጫ ሰሞን ሁሉም ለሩጫ በሚሆን መንገድ ትጥቁን አሟልቶ ሲሮጥ፣ የኳስ ወቅት ደግሞ ሁሉም መንደሩን በኳስ ሲያጥለቀልቀው ደግሞ ጊዜው የዘፈን እንደሆነ ሲታሰብ ሁሉም ሲያንጎራጉር እናስተውላለን፡፡ ብዙ ሰው እንደ ዘመኑ መኖርን ቋሚ የሕይወት መመሪያው አድርጓል፡፡ ሲሞቅ ሞቅ፣ ለብ ሲል ለብ፣ ሲቀዘቅዝ ደግሞ ቅዝቅዝ ማለት ለብዙኃኑ አልከበደም፡፡ ዘመንን በጎ ለማድረግ ግን በየትኛውም ሁኔታ ውስጥ እንደ እግዚአብሔር አሳብ መኖርን መለማመድ ያስፈልጋል፡፡
3. ተግባራዊ መሆን፡- በጎ ቃል ለመናገር ከምናሳየው ትጋት በበለጠ የተናገርነውን ተግባራዊ ለማድረግ ቆራጥነት ማሳየት ይኖርብናል፡፡ ሕይወት ጥልቅ ትርጉም ስለምትጠይቅ እያንዳንዱ ሰው በእድሜው ሁሉ ዓላማዬ ምንድነው? ማለት አለበት፡፡ ስለዚህ አስተዋይና ጥበበኛ ሰው በሕይወቱ ሊያሳካው የሚፈልገው ዓላማ ይኖረዋል፡፡ ነገር ግን መፈለግ ብቻውን በቂ አይሆንም፡፡ ተግባራዊ መሆንም ያስፈልጋል፡፡ በዚህ ምድር ላይ ሕይወት በጣም አጭር ናት፡፡ ቀኖቻችንን በማለም ብቻ ልናሳልፋቸው አግባብ አይደለም፡፡ ስለዚህ አጫጭር እቅዶቻችሁን ከረጅም ጊዜ ዓላማዎቻችሁ ጋር ለማዛመድ ሞክሩ፡፡ ሕይወት እናስተውላትና ሙሉ ትኩረታችንን እንሰጣት ዘንድ ከእግዚአብሔር የተቀበልናት አጭር፣ ውድና ድንቅ ስጦታ ናት፡፡ ስጦታ ደግሞ የተቀባዩን እንክብካቤና ትኩረት ይሻል፡፡ አማኝ፣ ብልህ፣ አስተዋይና ንቁ ሰው ደግሞ ዘመኑን ሙሉ ተግባራዊ ነው፡፡ በዘመን በረከት የተቀበለን ለእርሱ ዘመን የማይቆጠርለት ጌታ ስሙ ብሩክ ይሁን!
          

Tuesday, September 4, 2012

የተወጋ ሲረሳ (ክፍል ሦስት)


                
“ . . . . ዮፍታሔን፡- የልዩ ሴት ልጅ ነህና በአባታችን ቤት አትወርስም ብለው አሳደዱት፡፡ ዮፍታሔም ከወንድሞቹ ፊት ሸሽቶ በጦብ ምድር ተቀመጠ ምናምንቴዎችም ሰዎች ተሰብስበው ዮፍታሔን ተከተሉት” (መ. መሳ. 11÷2)፡፡
          በድህነት ውስጥ ባለጠግነት፣ በመዋረድ ውስጥ ክብረት፣ በመሰደድ ውስጥ ዕረፍት እንዳለ ማመን ለአብዛኛው የሰው ልብ ከባድ ነው፡፡ ነገር ግን በልቶ ጠጥቶ መራብ መጠማት፣ ለብሶ አንቀላፍቶ ሥጋት እርዛት ካለ፤ እየተራቡ መጥገብ፣ እየተጠሙ መርካት፣ እየተሰደዱ ማረፍ፣ እየተዋረዱ መክበር፣ እየሞቱም መኖር እንዳለ እናስተውላለን፡፡ በእምነት ስንኖር በመከራ ውስጥ ምቾትን የምናስተውልበት ኃይል እናገኛለን፡፡ በዮፍታሔ ሕይወት ውስጥ የምናየው ነገር ይህንን ይመስላል፡፡ የልዩ ሴት (የጋለሞታ) ልጅ ቢሆንም ነገር ግን ጽኑዕ ኃያል ሰውም ነበረ፡፡
          ሐዋርያው “ያልታወቁ ስንባል የታወቅን ነን፣ የምንሞት ስንመስል እነሆ ሕያዋን ነን፣ የተቀጣን ስንሆን አንገደልም፣ ሀዘንተኞች ስንሆን ዘወትር ደስ ይለናል፣ ድሆች ስንሆን ብዙዎችን ባለጠጎች እናደርጋለን፣ አንዳች የሌለን ስንሆን ሁሉ የእኛ ነው (2 ቆሮ. 6÷9)” እንዳለ ክርስትና በምድራዊው ልደት የምንብራራበት ሳይሆን በመንፈሳዊው ልጅነታችን የምንታይበት ኃይል ነው፡፡ በሰው ዘንድ አለመታወቅ ቢሆንም በሰማያዊው ስፍራ በሕይወት መዝገብ ላይ ስማችን ተጽፎአል፡፡ በሥጋ ከሚሆንብን ልዩ ልዩ መከራ የተነሣ ቀኑን ሁሉ ብንገደልም ነገር ግን ሕያዋን ነን፣ በሰው ፊት ዘወትር ሀዘን ቢከበንም በእግዚአብሔር ፊት ካለን መጽናናት የተነሣ ግን ሁል ጊዜ በጌታ ደስ ይለናል፡፡ በድህነታችን ውስጥ ለሌሎች የሚተርፍ ባለጠግነት አለ፣ አንዳች እንደሌለን ብንኖርም ሁሉ ግን የእኛ ነው፡፡
          ዮፍታሔ በሰው ፊት ያለውን እሳቤ ስንመለከት “የጋለሞታ ሴት ልጅ” ነው፡፡ ከእግዚአብሔር ዘንድ የነበረውን ምስክርነት ስንመለከት ደግሞ “ጽኑዕ ኃያል ሰው” ነበር፡፡ ምን ጊዜም ከራስ ጋር ጸብ የሚጀመረው ሰውና ልባችን ከሚነግረን ነገር ጋር ስንቆም ነው፡፡ እግዚአብሔር ከሚለው ጋር መስማማት ሲኖረን ግን ልካችንን የምናስተውልበት እድል ይኖረናል፡፡ ሰዎች የሚሉን፣ የሚያስታውሱን እንዲሁም እኛን የሚዳኙበት መንገድ ልባችንን የሚያደማ፣ ዓይናችንን የሚያስነባ ሊሆን ይችላል፡፡ ዳሩ ግን መቼም ቢሆን እግዚአብሔር ፊት ጌታ እግዚአብሔር ስለ ኢዮብ የሚናገረው እንጂ የሰይጣን ክስና ሙግት ልክ አይሆንም (ኢዮ. 1÷6)፡፡ የሚወራው ሁሉ እውነት አይደለም! እግዚአብሔር ያለው ግን የሰውን ልክ ይዳኛል፡፡
        ዮፍታሔ የልዩ ሴት ልጅ መሆኑ ከአባቱ ቤት ሊያገኝ የሚገባውን ውርስ አስከለከለው፡፡ ጌታ ከነገድ፣ ከቋንቋ፣ ከወገንና ከሕዝብ ዋጅቶ ለእግዚአብሔር ልጆች አድርጎናልና ወራሾች ነን፡፡ በእርሱ ዘንድ የቤትና የእንጀራ ልጅ የሚባል ልዩነት የለም፡፡ ዮፍታሔ እናቱን መርጦ አካባቢውን ወስኖ አልተወለደም፡፡ ነገር ግን እርሱ መርጦ ባላመጣው መጡበት የገዛ ወንድሞቹም አሳደዱት፡፡ ልክ እንደ እርሱ ሁሉ ሰላምታ የሚያስከለክሉ፣ በጎ ቃል የሚያስነፍጉ ብዙ ጉዳዮችን በኅብረተሰባችን መካከል እንታዘባለን፡፡
        ሰው ከተፈጥሮ በተቀበለው ነገር አይፈረድበትም፡፡ እንደ እውነት ከሆነም የዮፍታሔን ጽኑዕ ኃያልነት የጋለሞታ ሴት ልጅነቱ ሊሸፍነው አይገባም ነበር፡፡ ሰው ግን በሥጋና በደም ማስተዋል ውስጥ ብቻ ሲሆን ከዚህ ተሻግሮ ጽናትና ኃይልን ሊመለከት አይችልም፡፡ የዮፍታሔ ታሪክ ግን የልዩ ሴት ልጅ መሆኑ ብቻ አልነበረም፡፡ እርሱ ጽኑዕ ኃያል ሰውም ነበር፡፡ ስለ ሰዎች የድካም ታሪክ ስንሰማ የምንጠብቀው የበለጠ ድካምን ከሆነ ጨለምተኞች እንሆናለን፡፡ ሰው የኃይልና የጽናት ክፍልም አለው፡፡ ስለወደቀ ስናወራ መነሣትን እያሰብን፣ ስለተቸገረ ስንናገር ማግኘትን እያስተዋልን፣ ስለ ሞት ስንነጋገርም ትንሣኤን እያወጅን ከሆነ ለተስፋ መቁረጥ የእግር እሳት ነን፡፡
        ከጠላትህ አንድ ጊዜ ከወዳጅህ ደግሞ ሺህ ጊዜ ተጠንቀቅ እንደተባለ ሰምተናል እኔ ግን ልጠይቃችሁ “ከወንድምስ” ስንት ጊዜ እንጠንቀቅ? ሰዎች ጭንቅላታቸውን ይዘው፣ አፋቸውን ከፍተው፣ እንባቸውን እየረጩ የልባቸውን በአንደበት ሲጮኹ ምን እንደሆኑ ለመስማት ጓጉተን ስንጠጋቸው የወንድም ባዳ፣ የወገን ምድረ በዳ እንደገጠማቸው አምርረው ያወጉናል፡፡ ዮፍታሔ ወንድሞቹ ናቸው ያሳደዱት፡፡ እርሱም ከፊታቸው ሸሸ!
        ዘመናችንን ስንዋጀው ሰው ከወንድሙ ፊት የሚሸሽበት ነው፡፡ ጌታ ወንድሞች ብሎ ሊጠራን አላፈረምና ወንድምነት ብርቱ ቅርበት ነው (ዕብ. 2÷13)፡፡ ደስታን እንደ ራስ ደስታ መቁጠር ብቻ ሳይሆን መከራንም እንደ ራስ መከራ የመቁጠር ሂደት ነው፡፡ ከሚያዝኑ ጋር የምናዝንበት ከሚደሰቱ ጋር የምንደሰትበት ምክንያትም ሌሎችን እንደ ወንድም መቁጠር ነው፡፡ ለዮፍታሔ ከወንድሞቹ ፊት ይልቅ የጦብ ምድር መሸሸጊያ ነበር፡፡ ወንድም ፊት ለነሳችሁ፣ ወዳጅ ለጎዳችሁ፣ ቀን ለጨለመባችሁ ሁሉን የሚችል ልዑል እግዚአብሔር የሚሸሽግ አምባ የሚያሳድር ጥላ ነው፡፡ እኛ ብንገፋም ጌታ ግን አይገፋም፡፡ እኛ ብንሰደድ እግዚአብሔር አይሰደድም፡፡ እኛ ብንታሠር ቃሉ ግን አይታሰርም (2 ጢሞ. 2÷9)!!
                                              - ይቀጥላል -  

Monday, August 20, 2012

የተወጋ ሲረሳ (ክፍል አንድ)



       የወደደንን መውደድ፣ የጠላንን መጥላት፣ ለዋለልን መስጠት፣ ለነፈገን መንሣት፣ ላሰበልን መራራት፣ ለዘነጋን መክፋት የብዙኃኑ የሰው ልጅ የአኗኗር መመሪያ ነው፡፡ ምንም እንኳን በጸጋ ዘመን ላይ ብንገኝም ዓለም ገና ዓይን ስለ ዓይን፣ ጥርስ ስለ ጥርስ፣ እጅ ስለ እጅ ከሚለው ምላሽ አልጸዳችም፡፡ እንዲያውም በዚህ ሕግ ግልጽ ሆኖ ከሚስተዋለው ለጠሉኝ እሬት አይነት አካሄድ በበለጠና በረቀቀ መንገድ ሰዎች የልባቸውን ፈቃድ እያረኩ ነው፡፡ ለብዙ ክርስቲያኖች እንዲህ ያለውን እሾህን በእሾህ፣ ደምን በደም የመመለስ ኑሮ ከእምነት ጋር አቻችሎ ማስኬድ አልከበዳቸውም፡፡ ክፉውም ጋር ደጉም ጋር ቋሚ ተሰላፊ የሆኑ ጥቂት ሆድ ሲብሳቸው “ያስቀመጥኩትን ቆንጨራ እንዳላመጣው?” በማለት የሚዝቱ ሁሉን ትተው ሳይሆን ሁሉን ለክፉ ቀን አስቀምጠው የተከተሉት አይናችን ስር ናቸው፡፡
         አብዛኞቻችን ሰው በሚለውና ክርስቲያን በሚለው መጠሪያ መካከል ያለውን ልዩነት ልብ አንለውም፡፡ ሰው ከምድራዊው ጥሪ ተካፋይ የሆንበት መንገድ ሲሆን፤ ክርስቲያን የሚለው ደግሞ ከሰማያዊው ጥሪ ተካፋይ የሆንበት መንገድ ነው፡፡ ሰው በመሆን ውስጥ በምድራዊ ስፍራና በሥጋዊ በረከት መርካት ሲስተዋልበት፡፡ (ማለትም በዚህ ምድር የምንሰበስበው ሁሉ ከፀሐይ በታች ሲሆን) ክርስቲያን በመሆን ውስጥ ደግሞ በሰማያዊ ስፍራና በመንፈሳዊ በረከት መባረክን እናስተውላለን (ኤፌ. 1÷3)፡፡
         ሰው በመሆን ልደት ይህንን ዓለም በሥጋና በደም አቋም ሆነን እንቀላቀላለን፡፡ ክርስቲያን በመሆን (ዳግም በመወለድ) ደግሞ የዘላለም ሕይወትን መቀላቀል ደግሞም የተዋረደው ሥጋችን የጌታን ክቡር ሰውነት መስሎ በሰማይ ከእርሱ ጋር እንነግሳለን፡፡ ስለዚህ ክርስቲያን ሁሉ ሰው መሆንን ቢጋራም ሰው ሁሉ ግን ክርስቲያን አይደለም፡፡ በዚህም ክርስቲያን መሆን ሰው ከመሆን በእጅጉ ከፍ ያለ እንደሆነ እንገነዘባለን፡፡
         “ቀኝ ጉንጭህን በጥፊ ለሚመታህ ሁሉ ሁለተኛውን ደግሞ አዙርለት፣ እንዲከስህም እጀ ጠባብህን እንዲወስድ ለሚወድ መጎናጸፊያህን ደግሞ ተውለት፣ ማንም ሰው አንድ ምእራፍ ትሄድ ዘንድ ቢያስገድድህ ሁለተኛውን ከእርሱ ጋር ሂድ” (ማቴ. 5÷38-42)፡፡ ጌታ በዚህ ክፍል  ላይ ያስተማረው ትምህርት ሰው በሚለውና ክርስቲያን በሚለው ስያሜ መካከል ያለውን ተግባራዊ ልዩነት ግልጽ ያደርግልናል፡፡ በመጀመሪያ እግዚአብሔር ለሚያዘን ነገር ሁሉ የምንፈጽምበትን ኃይል እንደሚሰጠን መተማመን በዚህ ክፍል የተገለጸውን ትምህርት በቅንነት ለመረዳት ወሳኝ ነገር ነው፡፡ ቀኝ ጉንጭን በጥፊ መመታት ውስጥ ያለው ክርስትና ሳይሆን ሰው መሆን ነው፡፡
            እጀ ጠባብን ለሚወስድ ያንኑ መተው ሰው በመሆን ደረጃ የሚከናወን ተግባር እንጂ ክርስቲያን መሆንን አይጠይቅም፡፡ አንድ ምእራፍ በመሄድ ውስጥም እንዲሁ ከክርስትና ይልቅ ያለው ሰው መሆን ነው፡፡ የክርስትናው የአኗኗር ልኬት የሚጀምረው ታዲያ የቱ ጋር ነው? ካልን ሁለተኛውን ጉንጭ በመስጠት፣ መጎናጸፊያን በመጨመር፣ ሁለተኛውን ምእራፍ በመሄድ የሚል ይሆናል፡፡ ከዚህ ያነሰው ግን ማንም ሰው ከሰብአዊ ርኅራኄ በመነሣት አልያም ከሥጋ ሕግ በመነጨ ሁኔታ የሚከውነው ነው፡፡ “የሚወዱአችሁን ብትወዱ ምን ዋጋ አላችሁ? ቀራጮችስ ያንኑ ያደርጉ የለምን? ወንድሞቻችሁንም ብቻ እጅ ብትነሡ ምን ብልጫ ታደርጋላችሁ? አሕዛብስ ያንኑ ያደርጉ የለምን?” (ማቴ. 5÷46)፡፡
         የነከሰንን ማጉረስ፣ የበደለንን መካስ፣ የተጣላንን ገፍቶ መታረቅ፣ የረገመንን ከልብ መመረቅ ተወግቶ እንደ መርሳት ነው፡፡ ጉዳቱ እያለ በደልን አለመቁጠር፣ ስቃዩ እየታየ ጥፋትን መተው፣ ጉድለቱ እየተስተዋለ ኪሳራን አለማስላት መንፈሳዊ የኑሮ ልዕልናን ይጠይቃል፡፡ ክርስትና የተወጋ ሲረሳ ነው!
         ከብሉይ ኪዳን በዳዊትና በሳኦል መካከል የነበረው የገፊና ተገፊ፣ ያሳዳጅና ተሰዳጅ፣ የጠዪና ተጠይ ታሪክ ለተነሣንበት ርእስ ጥሩ ማሳያ ነው፡፡ የመጀመሪያው የእስራኤል ንጉሥ ሳኦል ወደ ንግሥና የመጣበትን መንገድ የስነ መለኮት አዋቂዎች ሲያስረዱ “እግዚአብሔር ከሕዝቡ ጋር የተስማማበት ሂደት ነው” ይላሉ፡፡ ለዚህም ምክንያቱ ሳኦል የእስራኤል ንጉስ የሆነው እንደ እግዚአብሔር ፍላጎት ሳይሆን በሕዝቡ ፍላጎት ተመርጦ በእግዚአብሔር አጽዳቂነት መሆኑ ነው፡፡
          እግዚአብሔር ሳሙኤልን “እንደጠየቁ ቀባላቸው” በማለት ከሕዝቡ አሳብ ጋር ተስማማ፡፡ ይህም በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ብቸኛው ክፍል እንደሆነ ይነገራል (1 ሳሙ. 15)፡፡ ምን ጊዜም ቢሆን እግዚአብሔር ከአሳባችን ጋር ከተስማማ ኪሳራው የሰው ነው፡፡ ወደኋላ መለስ ብለን ያለፈውን ፍላጎታችንን እና ዛሬ በዚያ ፍላጎት ላይ ያለንን አተያየት ብንመለከተው ለየቅል ነው፡፡ ያኔ እግዚአብሔር በፊቱ ካቀረብነው አሳብ ጋር ተስማምቶ ቢሆን፤ እንደጠየቅነው ሁሉን ቢሰጠን ኖሮ ዛሬ ከምናፍርበት ነገር ጋር ለመኖር  በተገደድን ነበር፡፡
          እግዚአብሔር ሲሰጥ ብቻ ሳይሆን ሲከለክል፣ ሲመልስ ብቻ ሳይሆን ዝም ሲል፣ ሲያኖር ብቻ ሳይሆን ሲገድልም አይሳሳትም፡፡ የእርሱ ጌትነት ምቾትን ብቻ ሳይሆን ጉስቁልናንም ያጠቃልላል፡፡ ክርስትና መብዛትን ብቻ ሳይሆን መዋረድን፣ መጥገብን ብቻ ሳይሆን መራብን፣ ከፍታን ብቻ ሳይሆን መጉደልንም ማወቅ ጭምር ነው (ፊል. 4÷12)፡፡ ስለዚህም አሳቡን እንስማማበት፣ መንገዱን እንጓዝበት ዘንድ እግዚአብሔር ከእኛ አሳብና መንገድ እጅግ የራቀ ነው፡፡ እርሱ ከፍላጎቶቻችን ጋር ሳይሆን እኛ ከእርሱ ፍላጎት ጋር፤ ከምርጫዎቻችን ጋር ሳይሆን እኛ ከእርሱ ፈቃድ ጋር፣ ከልባችን ጋር ሳይሆን እኛ ከልቡ ምክር ጋር  እንስማማ ዘንድ አግባብ ነው፡፡
           ዳዊት እግዚአብሔር በጠላቶቹ ፊት ለፊት በዘይት የቀባው፣ ከወንድሞቹ መካከል ለይቶ በአባቱ ንቀት ፊት ያከበረው ሰው ነው፡፡ ትልቁ እግዚአብሔር በብላቴናው ሕይወት ኃይሉንና ክብሩን ይገልጥ ዘንድ ስለወደደ ከበጎች ጥበቃ ወደ ንግሥና አመጣው፡፡ ሰው እኛን ወደተሻለ ነገር ለማምጣት ደረጃ በደረጃ ይሠራ ይሆናል፡፡ እግዚአብሔር ግን ከትቢያ አንስቶ ወደ ልዕልና ለማምጣት እርከን አያስፈልገውም፡፡ ዳዊት በሳኦል መንግሥት ዘመን ለሕዝቡ ፍርሃት፤ ለመንግስቱ ሥጋት የሆነውን ጎልያድ በእግዚአብሔር ስም በማሸነፍ ባለ ውለታ ነው፡፡ ከድሉ በኋላም ቤተ መንግሥት ውስጥ በገና በመደርደር የሳኦልን ርኩስ መንፈስ በማውጣት ለሳኦል ባለ ውለታ ነው፡፡ የሳኦል ምላሽ ግን ዳዊት ካደረገው ቅንነት ፍፁም ተቃራኒ ነበር፡፡ ሳኦልን ሊቀበል የወጣው ሕዝብ ለዳዊት በመዘመሩ (እልፍ ገደለ) እጅግ ተቆጣ፡፡ በገናምም እየደረደረ ሳለ ከግንቡ ጋር አጣብቀዋለሁ በማለት በእጁ የያዘውን ጦር ወረወረበት፡፡   
          በክፉዎችና በበጎዎች ላይ ፀሐይን የሚያወጣ እግዚአብሔር ሁሉ በፊቱ የተራቆተለት አምላክ ነው፡፡ የአመፀኛውን አመጽና የትሁቱን ትህትና የእርሱ ጽድቅ በእውነት ይዳኛል፡፡ ዳዊት እንዲህ ባለው ጌታ ፊት አንደኛ ሳኦል የሚያደርግበትን ክፉ፤ ሁለተኛ ለሳኦል የሚያደርግለትን መልካም ነገር አይቆጥርም ነበር፡፡ ለዳዊት ጤና ይህ ነበር!
       በሕይወታችን ውስጥ ከሚስተዋለው ድካም መካከል ያደረግነውን መልካም መተሳሰብና የተደረገብንን ክፉ መቁጠር በጉልህ የሚስተዋል ነው፡፡ የእግዚአብሔር ሰው ዳዊት የወንድሞቹን ጥላቻ፣ የአባቱን መናቅ፣ የሳኦልን ማሳደድ የተበቀለበት ትልቁ መንገድ መርሳት (አለመቁጠር) ነው፡፡ ሰው በቀል የተጠማ ልቡን የሚያረካበት መንገድ በደልን መቁጠር እንዲሁም ለበደሉ ተመጣጣኝ ምላሽ በመስጠት ነው፡፡ ነቢዩ ግን ሁሉን ማድረግ በሚችል እግዚአብሔር ፊት የተደረገበትን ይተወው ነበር፡፡ ሳኦል ጦርን ያህል ነገር ወርውሮበት ምድረበዳ ለምድረበዳ ሲያሳድደው የሚያደርገውን እንደማያውቅ ምስኪን ሰው ይቆጥርለት ነበር፡፡ እግዚአብሔር ከእኔ ጋር ነው! ብሎ ጉልበቱን ለማጥፋት አልተጠቀመበትም፡፡ ለሚያምኑ ሁሉ የእግዚአብሔር ኃይል ለማዳን ነው (ሮሜ. 1÷16) ተብሎ እንደተፃፈ የእግዚአብሔር የሆኑቱ ጉልበታቸውን በደልን ለመርሳት እንጂ ለመቁጠር አያውሉትም፡፡
                                                                               - ይቀጥላል -
      
     ውድ የቤተ ፍቅር ብሎግ ተከታታዮች በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስና በክቡር ጠቅላይ ሚኒስትራችን ሞት የተሰማንን ሀዘን ለመግለጽ እንወዳለን፡፡ ጌታ እግዚአብሔር ምድሪቱንና ሕዝቡን ይባርክ!!    

Wednesday, August 15, 2012

የግያዝ ዓይኖች


             
         ከሆነብን በላይ የሆነውን የምንተረጉምበት፣ ከሰማነው በላይ ያደመጥነውን የምንረዳበት፣ ከመጣው ፈተና በላይ መከራውን የምናስተናግድበት መንገድ ጽናታችንንም ሆነ መብረክረካችንን ይወስነዋል፡፡ ልጅ እያለን በጨለማ ስንሄድ አንዱ ዛፍ እንደ ብዙ ዛፍ፣ አንድ ድምጽ ልክ እንደ ብዙ ውኃዎች ድምጽ፣ አንድ ሰውም እንደ ትንሽ መንጋ ሆኖ ይታየን ነበር፡፡ በብዛት ብቻ ሳይሆን በኃይልም የምንረዳበት መንገድ ከሆነው በእጅጉ የተጋነነ ነው፡፡ የቅጠል መተሻሸት፣ የነፋስ ሽውታ፣ የሌሊት ወፍ ድምጽ ልክ እንደ አንበሳ ግሳት፣ እንደ ነብር ፍጥነት፣ እንደ ዲያብሎስ ትጋት ተቆጥሮ ልባችን ይሸነፍበታል፡፡ በሕይወታችን ድንግዝግዝ ነገር ሲበዛ አጥርቶ ማየት ከባድ ነው፡፡ በልኩም መረዳት አስቸጋሪ ነው፡፡ ከከበበን ብዙ መፍትሔ ይልቅ ጥቂት ችግራችንን እሽሩሩ ማለት ይቀናናል፡፡
         በአካል ካደግን፣ በአእምሮ ከበሰልን፣ የኑሮ ተግዳሮቶችን መጋፈጥ ከጀመርን በኋላ የምንፈተነው የሆነውን በሆነው ልክ ማየት ባለመቻል ነው፡፡ መከራ አይለመድም፡፡ የሕይወት ዘመን እንግዳ፤ የየማለዳው አዲስ ነው፡፡ ሰው ወድዶ አለመደሰት ይችላል፡፡ አለመፈተን ግን ከቶ አይችልም፡፡ በደስታ ላይ በርን መዝጋት ይቻላል፤ ችግር ግን የተዘጋውንም ጥሶ ይዘልቃል፡፡ የምስራቹን አልቀበልም ያሉ ዛሬ የበዪ ርሀብተኛ፣ የአዋቂ መሀይም፣ የብልጥ ተላላ፣ የዘናጭ ታራዥ፣ የትጉህ ብኩን ሆነዋል፡፡ ጌታ ግን በተዘጋው ደጅ የሚያልፍ መፍትሔ አለው፡፡ እርሱም “ሰላም ለእናንተ ይሁን” (ዮሐ. 20÷19) አላቸው፡፡
       በማንኛውም አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ሰይጣን የሚዘጋቸው፤ ሥጋም መጋረጃ ሆኖ የሚከልላቸው ነገሮች ይኖራሉ፡፡ እምነት ግን ከተዘጋው ባሻገር ማየት ነው፡፡ ከሚታየው አልፎ የማይታየውን መመርመር ነው፡፡ ከሥጋ ሁኔታ ወደ መንፈሳዊው ሁኔታ፤ ከዚህ ዓለም አሳብ ወደ ሰማያዊው አሳብ ከፍ ማለትም ነው፡፡ እምነት ከሥጋ አይን ልኬት፣ ከጆሮ የመስማት ደረጃ፣ ከአካልም የመስራት ኃይል በላይ ነው፡፡ ግዙፉን ጎልያድ በአንድ እዚህ ግባ በማይባል ብላቴና ፊት ያሳነሰው እምነት ነው፡፡ ለአሥሩ ሰላዮች በከነዓን የሚኖሩትን ሕዝብ ያገነነው ደግሞም ለእስራኤል ማኅበር ፍርሃትን እንዲያወሩ ያደረገው የእምነት ማነስ ነው፡፡ እነርሱም ሲናገሩ “በዓይናችን ግምት እንደ አንበጣዎች ነበርን ደግሞ እኛ በዓይናቸው ዘንድ እንዲሁ ነበርን አሉ” (ዘኁ. 13÷33)፡፡ እግዚአብሔር ደግሞ  ”“እኔ ሕያው ነኝና በጆሮዬ እንደተናገራችሁት እንዲሁ በእውነት አደርግባችኋለሁ” (ዘኁ. 14÷28) አለ፡፡ እንደ ቃሉም ሁሉን በሚችል አምላክ ፊት ያጉረመረሙት በሙሉ በምድረ በዳ ሞቱ፡፡
       በመጽሐፈ ነገሥት ካልዕ ምእራፍ 6 ላይ የሶርያ ንጉሥ ከእስራኤል ጋር ሊዋጋ ወደ ሕዝቡ እንደመጣ እናነባለን፡፡ ንጉሡም ፈረሶችንና ሰረገሎችን እጅግም ጭፍራ ሰደደ በሌሊትም መጥተው ከተማይቱን ከበቡ፡፡ የእግዚአብሔር ሰው ኤልሳዕ ሎሌ የሆነው ግያዝም “ጌታዬ ሆይ ወዮ ምን እናደርጋለን?” አለው፡፡ ግያዝ እንዲህ ሊናገር የቻለው ኤልሳዕ እንደሚያይ ማየት ባለመቻሉ ነው፡፡ የኤልሳዕ ዓይኖች ግን ከተማይቱን በከበቡት የሶርያ ንጉሥ ጭፍሮችና ድቅድቅ በሆነው ጨለማ ላይ ሳይሆን ያረፉት ከከበባቸው ሠራዊት በላይ በሆነው እግዚአብሔር ላይ ነበር፡፡ “ክርስቶስን ተመልከቱ” (ዕብ. 3÷2)!
       በኑሮ ውስጥ ብዙ የሚከቡን ነገሮች አሉ፡፡ የዚህ ዓለም ከንቱ አሳብ፣ የሰይጣን ውጊያ፣ የሕይወት ውጣውረድ፣ ድካምና ኃጢአት እነዚህ ሁሉ በዙሪያችን ያሉ የዕለት ከዕለት ፈተናዎች ናቸው፡፡ እምነት ግን ከሁኔታ ባላይ መኖር የምንችልበት ኃይል ነው፡፡ በእምነት ዓይን ፊት የማይቀልና የማያንስ ነገር የለም፡፡  ተወዳጆች ሆይ እኛ በኑሮ ሠልፍ ላይ ያለን ዓይን የግያዝ አይነት ነው ወይስ የኤልሳዕ? በዙሪያችን ያለው ችግር ወይስ ከእኛ ጋር ያለው እግዚአብሔር ነው የሚበልጥብን? ችግር ተኮፍሶ መፍትሔው ካነሰ ውጤቱ እንደ ሎሌው መፍራት ነው፡፡ ነቢዩ ዳዊት “መክበቡንስ ከበቡኝ በእግዚአብሔርም ስም አሸነፍኋቸው” (መዝ. 117÷11) ይላል፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞን ደግሞ  “የእግዚአብሔር ስም የጸና ግንብ ነው ጻድቅ ወደ እርሱ ሮጦ ከፍ ከፍ ይላል” (ምሳ. 18÷10) ይለናል፡፡ ከዚህ ዓለም ጥበብ የእግዚአብሔር ሞኝነት እጅግ እንደሚበልጥ ስናስተውል በአባትና ልጅ የተናገሩት እነዚህ ቃላት ለልባችን ይጠጋሉ፡፡
         የእግዚአብሔር መቻል የማይቻለውንም ይጠቀልላል፡፡ እርሱ እንዲያደርግልን የምንፈልገውን ሁሉ ቢያደርግልን እንኳ መቻሉ እዚያ ጋር አይቆምም፡፡ ከዚያም በብዙ ያልፋል፡፡ ኢዮብ ስለ እግዚአብሔር መቻል “ሰሜንን በባዶ ስፍራ ላይ ይዘረጋል ምድሪቱንም በታችዋ አንዳች አልባ ያንጠለጥላል ውኆችን በደመናዎቹ ውስጥ ያስራል ደመናይቱም ከታች አልተቀደደችም፡፡ . . . . ይህም የሰማነው ነገር ምንኛ ጥቂት ነው!” (ኢዮ. 26÷7) በማለት ይናገራል፡፡ በእርግጥም ሰማያት በመንፈሱ ውበት ያገኙበት፣ ምድር ከተግሣጹ የተነሣ የምትደነግጥለት፣ ስሙን ሰምቶ ሞት የሚብረከረክለት፣ ክብሩን አይተው ቀላያት የሚሰነጣጠቁለት ጌታ ሁሉን ያደርግ ዘንድ እንዴት አይችልም? አባቱን እንደሚገባ ያልተረዳው ልጅ የአባቱን አቅም በሁኔታ፣ በሰውና በቦታ መገደቡ የሚደንቅ ሊሆን አይችልም፡፡ እግዚአብሔርን የምናርፍበት በእምነት የተረዳነውን ያህል ነው፡፡  
            ግያዝ በእግዚአብሔር ፊት እንደ አገልጋይ ቢኖርም እግዚአብሔርን ግን እንደሚያገለግል ባሪያ አልተረዳውም፡፡ እግዚአብሔርን እንደሚያገለግል ተገልጋዩን መረዳት በሚያጸድቅና በሚኮንን በእርሱ ፊት ለመቆም ቀዳሚው ነገር ነው፡፡ ግያዝ እግዚአብሔር ለሶርያው ንጉሥ አለቃ ንዕማን የሰጠውን ደኅንነትና የገለጠውን ኃይል ተመልክቶአል፡፡ ዳሩ ግን በሶርያ ወታደሮች ፊት በእምነት እንዲቆም አላስቻለውም፡፡ አልዓዛር ከመሞቱ በፊት ማርያም በጌታ እግር ስር ቁጭ ብላ እንደተማረች ቃሉ ይነግረናል (ሉቃ. 10÷38)፡፡ ነገር ግን አልዓዛር ከሞተ በኋላ ማርያም በጌታ እግር ስር እንደተማረ ስትመልስ አናያትም፡፡ በሀዘን ሠልፍ ፊት አይኖችዋ ልክ እንደ ግያዝ ያሉ ነበሩ፡፡ ጌታ ግን አላት ትንሣኤና ሕይወት እኔ ነኝ በእኔ የሚያምን ቢሞት እንኳን ሕያው ነው፡፡ (ዮሐ. 11÷25)
       ችግር ወደ ሕይወታችን ሲመጣ “በኤልሳዕ ዙሪያ ያሉት የእሳት ፈረሶችና ሰረገሎች ተራራውን ሞልተውት ነበር” የሚለውን ማስተዋል ያቅተናል፡፡ ከሶርያ ጭፍሮች መክበብ በላይ በኤልሳዕና በሎሌው ዙሪያ ያሉት ይበልጡ ነበር፡፡ በግልጥ የምናየው በሥጋና በመንፈስ ሠራዊት መካከል ያለ ልዩነት ነው፡፡ በሰማያዊ ኃይልና በምድራዊ አቅም መካከል የነበረ ፍጥጫ ነው፡፡ በእምነትና በራስ ትምክህት መካከል በግልጥ የሚስተዋል ልዩነትም ነበር፡፡ ግያዝ በመንፈስ ከማስተዋል ይልቅ በሥጋ ለመዳኘት የቀረበ ነበር፡፡ ከሰማዩም ይልቅ የምድሩ የቀረበው ነበር፡፡ እግዚአብሔር ግን የብላቴኖችን ዓይን ይከፍታል፡፡ “የቃልህ ፍቺ ያበራል ሕፃናትንም አስተዋዮች ያደርጋል” (መዝ. 119÷130)፡፡
        ተወዳጆች ሆይ በዙሪያችሁ ካሉት ጠላቶች ይልቅ ወዳጆቻችሁ ብዙ ናቸው፡፡ ከከበባችሁ ችግር የከበባችሁ መፍትሔ ይበልጣል፡፡ ከሚወረወረው ቀስት ከሚበረው ፍላፃ ይልቅ እንደ ጋሻ የከበበን እውነት ኃያል ነው፡፡ የምትኖሩበት አገርና መንደር ላልተመቻችሁ እግዚአብሔር በተኩላና በእባብ ላይ ያጫማል፡፡ ባርነት ላንገሸገሻችሁ፣ የሰው ፊት ለጠቆረባችሁ፣ ነፃነት ብርቱ ናፍቆት ለሆነባችሁ እግዚአብሔር አንበሳውንና ዘንዶውን ያስረግጣል፡፡ ጌታ ያለማመንን ቅርፊት ከልባችን ላይ ያንሣ፣ በዓይናችን ላይ ያለውን የኃጢአት ሞራ ይግፈፍ፡፡ ሁሉም የሚያየው ገደል በሆነበት ዘመን ተራራው ላይ ያለውን ከፍታ፣ ከትንሽ እስከ ትልቅ በራደበት በዚህ ጊዜ በዙሪያችን ያለውን የእሳት ሠራዊትና መንፈሳዊ ኃይል በእምነት እንድናስተውል ጸጋ ይብዛልን፡፡                               

Friday, August 3, 2012

ለአፍንጫ ጥላ



       አንድ አባት ለሕፃናት በሚገባቸው መንገድ ለማስተማር የተጠቀሙበት ምሳሌ ነው፡፡ አብዛኛውን ጊዜ በአገልግሎት ውጤታማ ላለመሆን እንደ ምክንያት ከሚጠቀሱ ነገሮች መካከል በእድሜ ከፋፍሎ አለማስተማር ዋንኛው ነው፡፡ በእርግጥም ይህንን አስተያየት መሮንም ቢሆን ልንቀበለው ግድ ይሆንብናል፡፡ የእግዚአብሔር ቃል በወተትና በአጥንት ደረጃ ለሰዎች እንደሚቀርብ ስናስብ ሕፃናትና አዋቂዎች በአንድነት በተቀመጡበት ጉባኤ ላይ የትኛውን ዓይነት መልእክት ማስተላለፍ እንዳለብን ግራ ያጋባል፡፡ ምክንያቱም ወተት ብናቀርብ አዋቂዎቹን ወደኋላ እንጎትታቸዋለን፤ አጥንት ብናቀርብ ደግሞ ልጆቹን እንገድላቸዋለን፡፡ በዓለም የትምህርት ስርዓት እንኳን ያለውን የማስተማር ሂደት ስንመለከት በእድሜና በተቀራራቢ የማገናዘብ ደረጃ የተከፋፈለ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ተፈጥሮአዊውን ምክንያት የተከተለ ነው፡፡
        ምሳሌያቸው ለዚህ ጽሑፍ መነሻ የሆነንም አባት ከሁሉም አይነት እድሜ የተውጣጡ ሰዎች (ሕፃን፣ ወጣት፣ ሽማግሌ) ባሉበት ጉባኤ ላይ ተገኝተው በትምህርት ሰዓት ሕፃናቱ ከጨዋታና ከረብሻ ውጪ ምንም ተሳትፎ እንዳልነበራቸው አስተውለው ለልጆቹ ብቻ መልእክት አስተላለፉ፡፡ መልካም አስተማሪ የሚያሰኘው ትምህርትን ማክበድ ሳይሆን በተቻለ መጠን አሳቡ በሰሚው ልብ ውስጥ በግልጽ መቅረት እንዲችል ማስቻል ነው፡፡ ይህ ማለት ግን ቋንቋና የአቀራረብ ዘዴን ማስተካከል እንጂ የእግዚአብሔርን አሳብ ማስተካከል ማለት አይደለም፡፡ አብዛኛውን ጊዜ የምንመለከተው ግን የእግዚአብሔርን አሳብ እንደግል አሳብ አቅልሎ የማቅረብ ሂደት ነው፡፡ እንዲህ ያለው መንገድ እግዚአብሔር የሚለውን ሳይሆን እኛ መናገርና ሕዝቡ መስማት የሚፈልገውን ነገር በአቅርቦት ማርካት ነው፡፡ ይህ ተናጋሪውንና ሰሚውን ደስ ቢያሰኝም በእግዚአብሔር ዓይኖች ፊት ግን ከፍርድ አያመልጥም፡፡
         ታዲያ እኚህ አባት መንጋትና መምሸትን የሚያዘው ማነው? መፍጠርና ማኖርስ ሥልጣኑ የማን ነው? በሚል ጀምረው ክረምትንም የሚሰጥ፣ ዝናምንም የሚያዘንብ እግዚአብሔር እንደሆነ ተናገሩ፡፡ በልጆቹ ፊት ላይ ይነበብ የነበረው ደስታና የ“ተረድተናል” ምላሽ አስገራሚ ነበር፡፡ በማስከተልም ከዝናብ ጋር አያይዘው ስለ ተፈጥሮአችን ለልጆቹ ማውጋት ቀጠሉ፡፡ “እግዚአብሔር አፍንጫችንን ወደ ላይ አድርጎ ቢሠራው ኖሮ ዝናብ ሲዘንብ ትንንሽ የአፍንጫ ጥላ እንገዛ ነበር፡፡ ታዲያ ድሀ ከየት ያመጣ ነበር?” ሲሉ ሕፃናቱን ጨምሮ ሁላችንም ሳቅን፡፡ መልእክቱ ለሕፃናቱ ተብሎ የተነገረ ቢሆንም እንኳን አዋቂዎችንም የመስበር (የመንካት) አቅም ነበረው፡፡ ከዚህ ምን ተረዳችሁ? እግዚአብሔርን ለማመስገን ከበቂ በላይ ምክንያት አልታያችሁም? ትንንሽ የሚመስሉን ነገሮች ለእግዚአብሔር ትልልቅ ምስጋና የያዙ ስውር ምክንያቶች ናቸው፡፡
        የመገብከኝ እግዚአብሔር ተመስገን ስንል ስለጎረስኩበት እጅና ስለጎረሰው አፌ ተመስገን የምንል ስንቶቻችን ነን? ስለሰማነው የምስራች በእግዚአብሔር ደስ ስንሰኝ ስለሰማንበት ጆሮ የምናመሰግን ምን ያህሎቻችን ነን? ለሚያስተውል ሰው መራመድ፣ ማላመጥ፣ መናገር፣ ማየት ቀላል ሊሆን አይችልም? እኛ ምግቡ ብቻ፣ መሬቱ ብቻ ነው የእግዚአብሔር የሚመስለን፡፡ በእርግጥ እንደ ተባለው አፍንጫ ወደ ላይ ቢሆን ኖሮ ለዚህም መፍትሔ አፈላላጊ ይቋቋም ነበር፡፡ ድሀ ደግሞ በጥላ ካልተሸሸገ አፍንጫን በመኪና ማስጠለል ከየት ይመጣል? እግዚአብሔር በማንኛውም ነገር ላይ አዋቂ ነው!
        አስባችሁት ከሆነ እኛ መቃብር እስክንገባ እንኳን በአግባቡ የማናውቀው የሰውነት ክፍሎች ያሉን ሰዎች ነን፡፡ ምግብ መመገብ የጀመርነው ጨጓራ እንደሚፈጭ በማናውቅበት ሰዓት ነው፡፡ ከመተንፈስ ጋር የተዋወቅነው ስለ ልብ ምት የሰናፍጭ ቅንጣት የምታህል እውቀት ሳይኖረን በፊት ነው፡፡ እግዚአብሔር ምን ለምን እንዳደረገ በሙላት ያውቃል፡፡ አንዳንዴ አንዱ የአካል ክፍላችን ከሌላው ጋር ቦታ ቢቀያየር ምን ዓይነት ገጽታ እንደሚኖረን ስናስበው እንደመማለን፡፡ ሰይጣን የእግዚአብሔርን ምስጋና የሚሰርቅበት መንገድ ያለንን አሳንሶ የሌለንን በማብዛት፣ የያዝነውን አደብዝዞ የሌለንን በማጉላት ነው፡፡ ከዚህ ሁሉ ትበላላችሁ የሚለው ካላረካን ከዚህች አትብሉ ላይ መውደቃችን የተፈተነ እውነት ነው፡፡
        አንድ ትጉህ አመስጋኝና ዋዘኛ ተገናኙ፡፡ ታዲያ ትጉሁ እግዚአብሔር እስራኤልን በኤርትራ ባህር ያሻገረበትን ታሪክ እያሰበ ሁሉን ቻይነቱን ያመሰግናል፡፡ ይህንን የሰማው ዋዘኛ እርሱ አመስጋኙ እንደሚለው ባህር እንዳልነበረና አነስተኛ ጉድጓድ እንደነበረ በመሆኑም ለዚህ ምንም ማመስገን እንደማይገባ ተናገረ፡፡ ትጉሁም አመስጋኝ ከልብ በሆነ ፈገግታ ውስጥ ሆኖ “አሁን ደግሞ የደነቀኝ እግዚአብሔር ፈርዖንና ሠራዊቱን በጠባብ ጉድጓድ ውስጥ ማስጠሙ ነው” በማለት የዋዘኛውን ተቃውሞ ለበለጠ ምስጋና ተጠቀመበት፡፡ እኛ አጥተን የምናማርረውን ምሬት ተርፎአቸው የሚያማርሩ አሉ፡፡ ክርስትናውን ልዩ የሚያደርገው ግን በመብዛት ብቻ ሳይሆን በመጉደልም ውስጥ ለጌታ የምስጋናን ነዶ ማቅረብ መቻሉ ነው፡፡ እኛ አጠገባችን ላለ ነገር ሩቅ፣ ለጨበጥነውም ነገር ስውር ነን፡፡ ስለዚህ ኑሮዬ ይበቃኛልን መለማመድ ለእኛ ከባድ ነው፡፡
         ለዝናም እንጂ ለብርድ፤ ለፀሐይ እንጂ ለሙቀት፣ ለአካል እንጂ ለነፍስ ገበያ ጥላ የለውም፡፡ ልዑል ግን መጠጊያችን ነው፡፡ ሁሉን የሚችል አምላክ ጥላም ማደሪያችን ነው፡፡ ላባዎቹ ይጋርዱናል፡፡ በክንፎቹም በታች ለዘላለም እንተማመናለን፡፡ ምስጋና ይብዛላችሁ!