Wednesday, August 17, 2016

ሁለቴ የኔ ነሽ፡፡ (2)

/ካለፈው የቀጠለ/      
   

እሮብ ነሐሴ 11 ቀን 2008 የምሕረት ዓመት

       ኤሎሂም የእርሱ ሥራ በሆነው ፍጥረት በኩል የጥበቡ ኃይል ብርታት ይገለጣል፡፡ ስለ ፍጥረት በተጻፈበት ክፍል ‹‹አቤቱ ሥራህ እጅግ ብዙ ነው፤ ሁሉን በጥበብ አደረግህ፤ ምድርም ከፍጥረትህ ተሞላች፡፡›› (መዝ. 103፡24) ተብሏል፡፡ ተወዳጆች ሆይ፤ እጁ ሠርታናለችና (ዘፍ. 2፡7) ስለ እኛ ሕያው እግዚአብሔር እጅግ የተመሰገነ ይሁን፡፡

       ዓለም ከተፈጠረበት ይልቅ፤ የበደለው ዓለም የዳነበት የእግዚአብሔር ጥበብ እንደሚበልጥ ሲነገር ሰምታችሁ እንደ ሆነ አስባለሁ፡፡ የእግዚአብሔር የኃይሉ ታላቅነትና የብርታቱ ጉልበት የሚታይበትን ሁለተኛውን ታላቅ ጥበብ ስናነብ ‹‹እኛ ፍጥረቱ ነንና፤ እንመላለስበት ዘንድ እግዚአብሔር አስቀድሞ ያዘጋጀውን መልካሙን ሥራ ለማድረግ በክርስቶስ ኢየሱስ ተፈጠርን፡፡›› (ኤፌ. 2፡10) ተብሎ እናነባለን፡፡ ልብ በሉ! በዚህ ክፍል ላይ ያለው መፈጠር አስቀድሞ ካየነው የተለየና አዲስ ነው፡፡ መፍጠር የሚለውን ቃል በተመለከተ ግን በግሪኩ ተመሳሳይ ግስ የምናገኘው በሮሜው ባየነውና በዚህ በኤፌሶኑ ክፍል ብቻ ይሆናል፡፡

Thursday, August 11, 2016

ሁለቴ የኔ ነሽ፡፡

                         
            
             በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

ሐሙስ ነሐሴ 5 ቀን 2008 የምሕረት ዓመት

         ‹‹አንድ ትንሽ ልጅ በእጁ የሠራት ጀልባ ከዕለታት በአንዱ ቀን ተሰረቀችበት፡፡ እንዲህ ከሆነ ከብዙ ቀናት በኋላ፤ ዕቃ እያስያዘ ገንዘብ በሚያበድር ሰው ሱቅ በኩል ሲያልፍ ጀልባውን አያት፡፡ በደስታ ወደ ሰውየው ሮጦ ‹‹ያቺ የእኔ ትንሽ ጀልባ ናት›› አለው፡፡ ዕቃ አስይዞ አበዳሪውም ‹‹የለም፤ እኔ ስለገዛኋት የእኔ ናት›› ብሎ መለሰለት፡፡ ‹‹አዎ፤›› አለ ትንሹ ልጅ፤ ‹‹ግን የእጄ ሥራ ስለሆነች የእኔ ናት›› በማለት አስረዳው፡፡ ‹‹እንግዲያውስ›› አለ ዕቃ አስይዞ አበዳሪው፤ ‹‹ሁለት ዲናር ከሰጠኸኝ ልትወስዳት ትችላለህ›› አለው፤ ጀልባውን ዳግም የራሱ ለማድረግ በብርቱ የፈለገው ልጅ የተጠየቀውን ለመክፈል የጉልበት ሥራዎችን በመሥራት ገንዘቡን አገኘ፡፡

          ከዚያም ወደ ሱቁ በመሔድ ገንዘቡን ከፍሎ ጀልባውን አስመለሰ፡፡ በመጨረሻም ጀልባውን በእጆቹ አቅፎ እየሳመ ‹‹አንቺ ውድ ትንሽ ጀልባ፤ እወድሻለሁ፡፡ አንቺ ሁለቴ የእኔ ነሽ፡፡ በፊት ሠራሁሽ፤ አሁን ደግሞ ገዛሁሽ›› አለ፡፡ /William Moses Tidwell, Pointed Illustrations (Kansas City, Mo.; Beacon Hill Press, 1951) P. 97/.

        ከላይ ያነበብነው ታሪክ የወጣ ሲመለስ፤ የጠፋ ሲገኝ፤ የወደቀ ሲነሣ . . ያለውን ደስታና እርካታ ቆም ብለን እንድናስብ ይጋብዘናል፡፡ ሁሉም ነገር ላይ ‹‹የማይዘልቅ›› የሚል በተለጠፈባት የአሁኗ ዓለም የኑሮ ሥርዓት ውስጥ ባትጠፉ እንኳ የጠፋ ፈልጋችሁ እንደምታውቁ ግልጥ ነው፡፡ የተወደደው ባለ መድኃኒቱ ሉቃስ (ቆላ. 414) በጻፈው የወንጌል ክፍል፤ ከዘኬዎስ መጎብኘት ጋር በተያያዘ ‹‹ኢየሱስም፡- . . የሰው ልጅ የጠፋውን ሊፈልግና ሊያድን መጥቶአልና›› /ሉቃ. 199/ ተብሎ ተጽፎ እናነባለን፡፡ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ፈላጊም አዳኝም›› ነው፡፡

Monday, May 30, 2016

መልእክት ፡ ኀበ ፡ ሰብአ ፡ ኤፌሶን፡፡ (2)

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!



የሐዋርያው ፡ የጳውሎስ ፡ መልእክት ፡ ወደ ፡ ኤፌሶን ፡ ሰዎች፡፡

ሰኞ ግንቦት 22 ቀን 2008 የምሕረት ዓመት

‹‹ወአርአየነ ምክረ ፈቃዱ በከመ ሥምረቱ›› (ኤፌ. 1፡9)!

v  የጥናቱ መግቢያ

·  የኤፌሶን ቤተ፡ ክርስቲያን የተመሰረተችው በሐዋርያው ጳውሎስ ሁለተኛ ሐዋርያዊ የአገልግሎት ጉዞ ነው፡፡

·  ሐዋርያው በቆሮንቶስ ከተማ ለ18 ወራት ከነበረው የአገልግሎት ቆይታ በኋላ (ሐዋ. 18፡11)፤ ከጵርስቅላና ከአቂላ ጋር በመሆን ኤፌሶንን ጎብኝቷል (ሐዋ. 18፡18)፡፡

·  ሐዋርያው በኤፌሶን የነበረው የመጀመሪያ ቆይታ ለአጭር ጊዜ የነበረ ሲሆን፤ ዳሩ ግን እንደሚመለስ ቃል ገብቶላቸው ነበር (ሐዋ. 18፡19-21)፡፡ ነገር አዋቂ፤ በመጻሕፍት እውቀት የበረታ፤ የጌታን መንገድ የተማረ፤ የዮሐንስን ጥምቀት የሚያውቅ፤ በመንፈስ የሚቃጠል፤ ስለ ኢየሱስ የሚናገርና በትክክል የሚያስተምር ለሆነው አጵሎስ ‹‹የእግዚአብሔርን መንገድ ከፊት ይልቅ በትክክል ገለጡለት›› የተባለላቸው ጵርስቅላና አቂላ በኤፌሶን ቆይተዋል (ሐዋ. 18፡24-26)፡፡

· ሐዋርያው በሦስተኛ ሐዋርያዊ ጉዞው ወደ ኤፌሶን የተመለሰ ሲሆን፤ በዚያም ለሦስት ዓመታት በአገልግሎት ቆይቶአል (ሐዋ. 19፡8-10፤ 20፡31)፡፡ አንደኛ እና ሁለተኛ የቆሮንቶስ መልእክታትን የጻፈው በእስያ ዋና ከተማ ከሆነችው ከኤፌሶን ነው (1 ቆሮ. 16፡8፤9)፡፡ በዚያ ብዙ ድንቅና ተአምራት በእርሱ በኩል ተከናውነዋል (ሐዋ. 19፡12)፡፡

· ሐዋርያው በእድሜው ማብቂያ ከኤፌሶን አስጠርቶአቸው ከመጡ ሽማግሌዎች (ባለ አደራ) ጋር በሚሊጢን እንደተገናኘ፤ ምክርና ማስጠንቀቂያ አዘል የስንብት መልእክት አስተላልፏል (ሐዋ. 20፡16-38)፡፡

Tuesday, May 3, 2016

ምስኪን ማነው?

             በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
             

ማክሰኞ ሚያዝያ 25 ቀን 2005 የምሕረት ዓመት


         በክርስትና መሠረተ ትምህርት ውስጥ የ‹‹ትንሣኤ ሙታን›› አሳብ በእጅጉ አስፈላጊ ነው፡፡  ሐዋርያው ጳውሎስ በመንፈስ ቅዱስ ምሪት የመጀመሪያይቱን የቆሮንቶስ መልእክት ሲጽፍ በጊዜው መፍትሔ ከተሰጠባቸው ችግሮች አንዱ ‹‹ትንሣኤ ሙታን የለም›› የሚለው የአንዳንድ የቆሮንቶስ ክርስቲያኖች መረዳት ነው፡፡ የቆሮንቶስ መልእክት በምሕረቱ ባለ ጠጋ (ኤፌ. 2፡4) የሆነውን የእግዚአብሔርን ጸጋ የምናስተውልበት መጽሐፍ ነው፡፡ በመልእክቱ መግቢያ ‹‹በቆሮንቶስ ላለች ለእግዚአብሔር ቤተ፡ ክርስቲያን፤ በክርስቶስ ኢየሱስ ለተቀደሱት›› (1፡2) የሚለው አገላለጽ እግዚአብሔር በክርስቶስ ያሉትን ምእመናን ድካም የሚመለከትበትን የጸጋ ዓይን እንድናይ ያደርገናል፡፡

ምእራፍ 15፡ 
ርዕስ፡ - ትንሣኤ እርግጥ ነው!

                       .  የክርስቶስ ትንሣኤ ወንጌል (1-11)
                       .  ክርስቶስ ባይነሣ ስፍራችን (12-19)
                       .  ክርስቶስ እንደ በኩራት (20-28)
                       .  ስለ ሙታን ትንሣኤ የቀረበ ተግባራዊ ማስረጃ (29-34)
                       .  ስለ አካል መነሣት የተሰጠ ትምህርት (35-49)
                       .  የጌታ መምጣትና በእርሱ በኩል ያለን ድል መንሣት (50-58)፡፡ 

Friday, April 29, 2016

አፋችሁን አትክፈቱ!

    በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!


                 

              ‹‹ኢከሰተ አፉሁ በሕማሙ›› እንዲል (ሐዋ. 832)::

  አርብ ሚያዚያ 21 ቀን 2008 የምሕረት ዓመት

          የአዲስ ኪዳን መጻሕፍት ሁለተኛው ክፍል ‹‹የታሪክ ክፍል›› በመባል ይታወቃል፡፡ ይህም ከአገልጋዮቹ አንጻር ‹‹የሐዋርያት ሥራ››፤ ከሥራው ባለቤት አንጻር ደግሞ ‹‹የመንፈስ ቅዱስ ሥራ›› በመባል የሚታወቀው መጽሐፍ ነው፡፡ ‹‹ለድፍርስ መፍትሔው ምንጭ መውረድ ነው›› የማወቅ መመሪያዬ ነው፡፡ የክርስትናን መሠረተ ጅማሬ ለሥጋና ደም አሳብ ክፍተት በማይሰጥ መልኩ ቁልጭ ብሎ በምንመለከትበት በዚህ መጽሐፍ ውስጥ፤ በሞተውና ከሙታንም በተነሣው በክርስቶስ ክርስቲያን የሆኑቱ በኅብረት የተቀበሉትን (ቤተ፡ ክርስቲያን) የመጀመሪያውን ታላቅ መከራና ስደት እናነባለን፤ ከእስጢፋኖስ መገደል በኋላ (ከሐዋርያት ሥራ ም. 7)፡፡


     ምእራፍ ስምንት ስደትና መከራውን (ክርስቶስ ስለ ጽድቅ የተቀበለውን መከራ መካፈል) ተከትሎ ወደ ይሁዳና ወደ ሰማርያ የሆነውን መበተን መርዶ በመንገር ይጀምራል፡፡ ይህንን ምእራፍ እንዲህ ከፍለን ልንረዳው እንችላለን፡ - 

                  1. በክርስትና የመጀመሪያው ታላቅ መከራ (ከቁ. 1-3)
                  2. የተበተኑት ምእመናን ወንጌልን መስበካቸውና ፊልጶስ በሰማርያ (4-8)
                  3. የሰማርያው ጠንቋይ ሲሞን እና በዚያ የሆነው (9-24)
                  4. ወንጌል በሳምራውያን ብዙ መንደሮች መሰበኩ (ቁ. 25)
                  5. ፊልጶስና ኢትዮጵያዊው ጃንደረባ (26-40)

መልእክት ፡ ኀበ ፡ ሰብአ ፡ ኤፌሶን፡፡ (1)

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!


የሐዋርያው ፡ የጳውሎስ ፡ መልእክት ፡ ወደ ፡ ኤፌሶን ፡ ሰዎች፡፡

አርብ ሚያዚያ 21 ቀን 2008 የምሕረት ዓመት

    ‹‹ወአርአየነ ምክረ ፈቃዱ በከመ ሥምረቱ›› (ኤፌ. 1፡9)!

·        የመልእክቱ ጸሐፊ፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ
መልእክቱ የተጻፈበት ጊዜ፡ ከ61-63 ዓ/ም ባሉት ዓመታት
·        መልእክቱ የተጻፈበት ቦታ፡ ሮም
በጊዜው የመልእክቱ ተቀባዮች፡ የኤፌሶን ቤተ፡ ክርስቲያን (ማኅበረ ምእመናን)
·        የመልእክቱ ጭብጥ፡ የክርስቶስ ባለ ጠግነት በቤተ፡ ክርስቲያን 
(The Orthodox study Bible) 

Saturday, April 9, 2016

መልእክት ኀበ ፊልሞና፡፡ (8)

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! 


ቅዳሜ ሚያዚያ 1 ቀን 2008 የምሕረት ዓመት

(መልእክት ወደ ፊልሞና)

‹‹እምጳውሎስ ሙቁሐ ለኢየሱስ ክርስቶስ፡ (ኤፌ. 3፡1)!››

No. 14-17, ‹‹While the master-slave relationship continues, it is transcended by brotherhood in Christ.›› /The Orthodox Study Bible; New Testament and Psalms New King James Version/.

‹‹አምኀከ ኤጳፍራስ ዘተጼወወ ምስሌየ በኢየሱስ ክርስቶስ፡፡››
‹‹በክርስቶስ ኢየሱስ ከእኔ ጋር የታሰረ ኤጳፍራ . . ››፡-

          ሐዋርያው ጳውሎስ በዚህ መልእክት የስንብት ክፍል የጠቀሰው ሌላው የተወደደ አገልጋይ ኤጳፍራ ነው፡፡ ሐዋርያው ይህንን መልእክት የጻፈው በእስር ቤት ሆኖ እንደ መሆኑ፤ አብሮት ስለ ክርስቶስ የታሠረ ሌላውን አገልጋይ ይጠቅሳል፡፡ ባለፈው ጥናታችን ሐዋርያው ከእስር ተፈትቶ በፊልሞና ቤት ያለችውን ቤተ ክርስቲያን እንደሚጎበኛት ያለውን ተስፋ ለተወደደውና አብሮት ለሚሠራ ለፊልሞና ሲገልጽለት አይተናል፡፡

        በእግዚአብሔር ቃል ውስጥ ስለ ኤጳፍራ የምናገኘውን ምስክርነት በመመልከት የእግዚአብሔር መንፈስ የሚያስተምረንን እንወስዳለን፡፡ በቆላስይስ መልእክት ‹‹ከተወደደ ከእኛም ጋር አብሮ ባሪያ ከሆነው ከኤጳፍራ እንዲህ ተማራችሁ፤ እርሱም ስለ እናንተ ታማኝ የክርስቶስ አገልጋይ ነው፡፡ ደግሞም በመንፈስ ስለሚሆን ስለ ፍቅራችሁ አስታወቀን፡፡›› (ቆላ. 1፡7-8) የሚል ምስክርነት በሐዋርያው ተጽፎ እናነባለን፡፡