እሮብ ነሐሴ 11 ቀን 2008 የምሕረት ዓመት
ኤሎሂም የእርሱ ሥራ በሆነው ፍጥረት በኩል የጥበቡ ኃይል ብርታት
ይገለጣል፡፡ ስለ ፍጥረት በተጻፈበት ክፍል ‹‹አቤቱ ሥራህ እጅግ ብዙ ነው፤ ሁሉን በጥበብ አደረግህ፤ ምድርም ከፍጥረትህ ተሞላች፡፡››
(መዝ. 103፡24) ተብሏል፡፡ ተወዳጆች ሆይ፤ እጁ ሠርታናለችና (ዘፍ. 2፡7) ስለ እኛ ሕያው እግዚአብሔር እጅግ የተመሰገነ
ይሁን፡፡
ዓለም ከተፈጠረበት ይልቅ፤ የበደለው ዓለም የዳነበት የእግዚአብሔር
ጥበብ እንደሚበልጥ ሲነገር ሰምታችሁ እንደ ሆነ አስባለሁ፡፡ የእግዚአብሔር የኃይሉ ታላቅነትና የብርታቱ ጉልበት የሚታይበትን ሁለተኛውን
ታላቅ ጥበብ ስናነብ ‹‹እኛ ፍጥረቱ ነንና፤ እንመላለስበት ዘንድ እግዚአብሔር አስቀድሞ ያዘጋጀውን መልካሙን ሥራ ለማድረግ በክርስቶስ
ኢየሱስ ተፈጠርን፡፡›› (ኤፌ. 2፡10) ተብሎ እናነባለን፡፡ ልብ በሉ! በዚህ ክፍል ላይ ያለው መፈጠር አስቀድሞ ካየነው የተለየና
አዲስ ነው፡፡ መፍጠር የሚለውን ቃል በተመለከተ ግን በግሪኩ ተመሳሳይ ግስ የምናገኘው በሮሜው ባየነውና በዚህ በኤፌሶኑ ክፍል ብቻ
ይሆናል፡፡






