Tuesday, December 11, 2012

ሰው አያክፋችሁ (ካለፈው የቀጠለ)



                                               
                                            ማክሰኞ ታህሳስ 2/2005 የምሕረት ዓመት

           ባለፈው ክፍል የአንዳችን እንቅስቃሴ በሌላው ሕይወት ላይ በበጎም ሆነ በክፉ ያለውን ከፍ ያለ ተጽእኖ ለመዳሰስ ሞክረናል፡፡ ሁላችንም ብንሆን በሰው ላይ የምንፈርድበት ብቻ ሳይሆን በእኛም ውስጥ የሚፈረድበት ኑሮ አለን፡፡ ብዙዎች ለራሳቸው እንኳ ደግመው ሊያስቡት ከሚያንገሸግሻቸው ነገር ጋር ይኖራሉ፡፡ እንዲህ ካለው ጠባይና አኗኗር ጋር ተፈጥረው ግን አይደለም፡፡ አብዛኛው ሰው ያከፋው ነው፡፡ ጥላቻን የሚያግቱ፣ ተንኮል የሚያስቀጽሉ፣ ዓመጽ የሚያሰለጥኑ እንደ ምድር አሸዋ በዙሪያችን ናቸው፡፡
           ባል ያከፋቸው ሚስቶች ጥሩ እናት መሆን ሲያቅታቸው፣ አሳዳጊ ያከፋቸው ልጆች ጥሩ ባልንጀራ መሆን ሲሳናቸው፣ ጓደኛ ያከፋቸው ወጣቶች መልካም አባት መሆን ሲቸገሩ፣ ኅብረተሰቡ ያከፋቸው ሰዎች በቅን መምራት ሲተናነቃቸው አስተውለናል፡፡ ክፉ የምንለው ያከፋነውን ነው፡፡ ርኩስ የምንለው ያረከስነውን ነው፡፡ ጠፋ የምንለው ያባረርነውን ነው፡፡ ከሀዲ የምንለው ያስካድነውን ነው፡፡ ጌታ ሆይ ይቅር በለን!
           የሮም ንጉሥ የነበረውን ኔሮን ቄሳር ክርስቲያኖችን እንደ ጧፍ ለኩሶ እንደ ሻማ በማቅለጥ፤ ከአንበሳና ከነብር ጋር በማታገል ይዝናና የነበረ ክፉ መሪ እንደነበር ታሪክ ያስታውሰናል፡፡ ኔሮን ወደ ሥልጣን የመጣበትን መንገድ ስንመለከት፤ እናቱ አግሪፒና በ12 ዓመቷ የ15 ዓመት ዕድሜ በነበረው በኋላም ንጉሥ በሆነው ወንድሟ ካሊጉላ ትደፈራለች፡፡ በ13 ዓመቷ ትዳር መስርታ የልጇ የኔሮን ጥብቅ ወዳጅ ሆናለች፡፡ አግሪፒን አጎቷ የነበረውን ንጉሥ ክላውዴዎስ (ቀዳማዊ) ከማግባቷ በፊት ሁለተኛ ባሏን በመድኃኒት ገድላለች፡፡ ከዚያም ክላውዴዎስን በመርዝ በመግደል ኔሮ ዙፋኑን ወርሶ ወደ ንግሥና እንዲመጣ አድርጋለች፡፡ ጨካኙን ኔሮን ስናስብ እንዴት ባለ ሁኔታ ውስጥ እንዳደገ ልብ ማለት ትምህርት ያተርፍልናል፡፡
        በዓለማችን ላይ ከተነሡ አያሌ ዓመፀኞች ጀርባ ያለው ነገር በኔሮን ቄሳር ካየነው ብዙም የሸሸ አይደለም፡፡ በወላጅ፣ በጓደኛ፣ በወዳጅ፣ በፍቅረኛ ዓላማቸውን የሳቱ፣ ከሕሊናቸው የተጣሉ፣ የሕይወት ታሪካቸው ጥላሸት የተለቀለቀ፣ ራሳቸውን እየፈሩ የሚኖሩ፣ የማንነት መቃወስ የገጠማቸው ከእነርሱ ስህተት በላይ ሰው አክፍቷቸው ነው፡፡
         በአገራችን የገጠሩ ክፍል ዛሬም ድረስ ሙሉ ለሙሉ ጠርቶአል በማይባልበት ሁኔታ ደም የመቃባት ክፉ ውርስ አለ፡፡ ለዚህ መባባስ እንደ አንድ ምክንያት ተደርጎ የሚቀርበው ደግሞ ወገኑ ሞቶበት ደም ያልመለሰ ወንድ እንደ ነውረኛ መቆጠሩና ሚስት ለማግባት እሺታን መነፈጉ ነው፡፡ እንዲህ ባለ ሁኔታ ውስጥ ሰው ሸሽቶ ካልሆነ በቀር አብሮ ሆኖ ሕሊናውን መጠቀም አይችልም፡፡ ባይወድም ይከፋል፡፡ አቅም ባይኖረውም ይሸፍታል፡፡ ታዲያ እድሜ ሰጥቷችሁ ከዓመታት በኋላ ብትገናኙ ያ መልካምነት ሞቶ ተቀብሮአል፡፡ ያ ትህትና አፈር ትቢያ ሆኖአል፡፡ ያ ርኅራሄ ላይመለስ እርቆ ሄዶአል፡፡ ለልቡ ተጠግታችሁ “ምነው? ምን ገጠመህ?” ብትሉት ልክ እንደ ሙሾ አውራጅ እየተንሰቀሰቀ “ሰው አከፋኝ” ይላችኋል፡፡ ሰው አያክፋችሁ!
         ሕይወት ቅብብሎሽ ናት፡፡ አንዱ ትውልድ ሲሄድ ያን ተከትሎ ሌላው ይመጣል፡፡ ታዲያ ይህኛው ሲከፋ ለመጪው ውርስ ሆኖ ይቀራል፡፡ ከዚያም ክፉና ደግ ምርጫ ሳይሆን የውርስ ቅብብሎሽ ይሆናል፡፡ በእርግጥም እውነታው እንዲሁ ነው፡፡ ከማይጠፋው ዘር የተወለዱ ሁሉ የማይጠፋ ነገር ሲቀባበሉ ይኖራሉ፡፡ ያለ ምርጫቸው በሰው ምርጫ፣ ያለ ፍላጎታቸው በሰው ፍላጎት፣ ያለ ውዴታቸው በሰው ግዴታ የኑሮ አቅጣጫቸው የተወሰነ ያላለቀ ነገር (unfinished business) አላቸውና ዛሬም ከብርቱ ፈተና ጋር ናቸው፡፡

መፍትሔ

         እኔ ከሞትኩ . . . አይነት ኑሮ ለምድሪቱ ጭንቅ ነው፡፡ የሆነ ቦታ የሚጨክን ሰው ያስፈልጋል፡፡ ከአያት ከቅድመ አያት የመጣ ነገር ሁሉ ለልጅ ልጅ አይተላለፍም፡፡ እኛ የተጫነንን ሌሎች ላይ መጫን የለብንም፡፡ እኛ የመረረን ሌሎችንም እንዲመራቸው ቸልተኛነት ልናሳይም አይገባም፡፡ የከፉብንን በመክፋት፣ የጠሉንን በመጥላት፣ ያንገላቱንንም በማንገላታት ምድሪቱን በጨለማ ልንለውሳት አይገባም፡፡ እናም እንደ ብርሃን ልጆች በመመላለስ ክፉውን እንዋጋ፡፡ ጸጋ ይብዛላችሁ!  

8 comments:

  1. ይህን ፅሑፍ ሳነብ በእኔ ምክንያት የከፉ ሰዎች ይኖሩ ይሆን? ብዬ አሰብኩ
    አንዳንድ ጊዜ ከእኛ ዘንድ መልካምነት ሲያጡ የእነሱ እምነት በአፍንጫዬ ይውጣ ያሉብን ፤ ከእሷ ወዲያ ሰው አላምንም፣ በእሱ ተምሬያለሁ፤ ብለው የተማረሩብን አይጠፉም፡፡ የማይለወጠውን እግዚአብሔርን ብቻ የምናይበትን ፀጋ ያድለን፡፡ የሐሳቡ ባለቤት እግዚአብሔር ይመስገን፡፡ የዚህን መልዕክት ጸሐፊም ቃለ ህይወት ያሰማልን፡፡

    ReplyDelete
    Replies
    1. Amen! egna sanastewilew begna mikinyat silekefubin sewoch hulu yemihiret amlak yikirtan yisten!

      Delete
  2. besew lay kemefired takiben besew ena be Egziabher fit bemoges endeg!

    ReplyDelete
  3. amen! yerasachinin dikam titen besew lay kemefired endinkoteb egziabher yirdan!

    ReplyDelete
  4. betam astemari hasab new. egziabher yibarkachu!

    ReplyDelete
  5. BETE FEKER EWUNETEM FEKER BETAM DES YEMILNA BETAM ASTEMARE SELEHON EBAKWO SEHUFOCHUN BEMULU BE MESHAF MELK AZEGAGETEWU BEYAKERBUT LEHULACHINE TEKAMI NEWU BETAM WEDE EGZEABEHER MENGED YEMIMERANA SELAMIN YEMISET KAL NEWU YAGEGEHUBET DERE GESUN SAYEWU YEMEGEMRIYAYE NEWU EMBETE LEDETA MARIYAM BELETE KNUA ENDEH YAL KIDUS YEHONE KAL ASNEBEBECHIG kEBER LELEGUA LE EYESEU KIRSTOS YEHUN AMEN.

    ReplyDelete
  6. EGZIABHER bandem belelam yenageral EGZIABHER yemesgen EGZIABHER yestelen

    ReplyDelete
  7. አምላከ አበው አምላከ ቅዱሳን ጸጋውን ያብዛላችው!!!!!!ዘለአለማዊ የህይወትንቃል ያሰማልን ያቆይልን!!!!!

    ReplyDelete