Monday, December 30, 2013

ለልደቴ

                      Please Read in PDF: Lelidete

‹‹ለሰብእ ሰብእ ዘየዐብዮ በምንት፤
አምጣነ ኩሉ ዕሩይ በጊዜ ልደት ወሞት፡፡››
ትርጉም፡ -
‹‹ሰው ከሰው በምን ይበልጣል፤
ልደትና ሞት አንድ ያደርገዋል፡፡››  

                           (አለቃ ጥበቡ ገሜ)

       ወደዚህ ምድር መምጣት ቀላል እንዳልሆነ የነገረችኝ እናቴ ናት፡፡ ያማጠ ያውራ፡፡ የወለደ ይናገር፡፡ መወለድ ጸጋ ነው፡፡ ወላጅ፣ ስፍራ፣ ሕዝብ፣ ሁኔታ መርጠን አልተወለድንም፡፡ ዳሩ ግን ወደ ማስተዋል ስንመጣ ራሳችንን እዚህ አግኝተነዋል፡፡ ተመስገን! እንደ አሳቡ ሁሉን የሚፈጽም፣ ለአድራጎቱ ከልካይ የሌለበት አምላክ ስሙ ብሩክ ይሁን፡፡ የአርያም ደጆች ተከፈቱ፡፡ ያበጃጀኝን መዳፍ አየሁት፡፡ ከምድር አፈር የሠራኝን፣ የሕይወት እስትንፋስ እፍ ያለብኝን፣ ለእኔ ተጠቦ ገነትን ስፍራ የሰጠኝን፣ መልክና ምሳሌው ያደረገኝን፣ ቢስት እመልሰዋለሁ፣ ቢጠም አቀናዋለሁ፣ ልጅነቱን አሳድጋለሁ፣ አለማወቁን አስተምራለሁ ብሎ ኑር ያለኝን ልብ አልኩት፡፡

        መጪውን እያየ፣ መዳረሻዬን እያወቀ የፈጠረኝን የአባቶች አባት፣ የወላጅ ጥግ፣ የመውደድ ዳርቻ ኤሎሂም ወሰን መስፈሪያ በሌለው ክብር በዙፋኑ ሆኖ አስተዋልኩት፡፡ የልቤን ዓይኖች ወደ ጸጋው ዙፋን ዘረጋሁ፡፡ አባባ እንዲህ አለኝ ‹‹አሳብ ሳለህ ያሰብኩህ፣ ጽንስ ሳለህ ሰው ያልኩህ እኔ ነኝ›› ገጹ በማይቆጠር እጥፍ ያበራል፡፡ ሁሉን የሚችል ብርታቱ፣ ደከመኝ ሳይል የሚሸከም ፍቅሩ፣ ያለመጥፋት ዋስትና ምህረቱ፣ የማይናድ የማይፈርስ ኪዳኑ፣ አመጽን የማያውቅ ጽድቁ በግልጥ ይነበባል፡፡

Wednesday, December 11, 2013

የንጉሡ ኢትዮጵያ

                                           Please Read in PDF: Yengusu etyopia

                             
                                    እሮብ ታህሳስ 2/2006 የምሕረት ዓመት

      ለመጀመሪያ ጊዜ የቅዱስ ጳውሎስን ሆስፒታል የረገጥኩበት ዕለት ነው፡፡ የሕዳር ወር መጨረሻ! እንደነዚህ ያሉ ስፍራዎችን በዋናነት ሦስት ሰዎች ማለትም ሕሙማን፣ አስታማሚ (ጠያቂ) እና የሕክምና ባለሙያዎች እንደሚገኙበት አስባለሁ፡፡ ታዲያ ከቀትሩ ለመሸሽ ማለዳውን እየተሽቀዳደምኩ ነበር ወደምጠይቀው ሰው ያቀናሁት፡፡ እኔ የምፈልገው ሰው ወደሚገኝበት ክፍል ስደርስ ጽዳት ላይ የነበሩ ሠራተኞች እንድታገስ ነገሩኝ፡፡ ከመቆም ብዬ ዘወር ዘወር ለማለት ወደ ታችኛው የቅጽሩ አካባቢ ወረድኩ፡፡ በግራና በቀኝ፣ በፊትና በኋላ ዙሪያዬ መፍትሔ ሽተው በዚያ የተገኙ ሕሙማንን ልማዳዊ ከሆነው ‹‹ይማራችሁ›› ባለፈ ስለ እነርሱ በልቤ እየጸለይኩ በእርጋታ በጥጋ ጥጉ ሳይቀር ተራመድኩ፡፡ ድንገት ዓይኔ አንድ ነገር አስተዋለና ይበልጥ ተጠግቼ ተመለከትኩት፡፡ ከዚህ ጽሑፍ በላይ የምታዩትን የንጉሡ የኃይለ ሥላሴን ስዕል ነበር ያየሁት፡፡ የመጣሁበትን ዓላማ የዘነጋሁ እስኪመስለኝ ድረስ ደጋግሜ በአግራሞት አስተዋልኩት፡፡ አሁንም ይበልጥ አስተዋልኩት፡፡

Tuesday, December 3, 2013

ለፍቅር የተከፈለ(ካለፈው የቀጠለ)


           
                            እሮብ ህዳር 25/2006 የምሕረት ዓመት
    ሚስቱን በሞት ያጣ አንድ ወጣት ከብዙ መፍትሔ ፍለጋ በኋላ ወደ አንድ የስነ ልቦና አጥኚ ዘንድ ሄዶ በሕይወት ላይ ተስፋ እንደቆረጠ፣ የሚስቱ ሀዘን ለመኖር ምክንያት እንዳሳጣው በእንባ ጭምር ይነግረዋል፡፡ የስነ ልቦና አማካሪውም ወደ ወጣቱ እየተመለከተ “ሚስትህ በሕይወት ብትኖርና አንተ ብትሞት ኖሮ ሚስትህ ምን የምትሆን ይመስልሃል?” ሲል ጠየቀው፡፡ ወጣቱ ፍም የመሰለ ፊቱን በእጁ እያሻሸ “በቁሟ ጨርቋን ጥላ፣ ሚዛኗን ትስታለች እንጂ በጤና የምትሆን አይመስለኝም” በማለት ጥርሱን ነክሶ መለሰለት፡፡

Monday, November 4, 2013

ለፍቅር የተከፈለ


                             ሰኞ ጥቅምት 25/2006 የምሕረት ዓመት

      በገጠሪቱ የአገራችን ክፍል የሆነ ነው፡፡ አብዝተው የሚዋደዱ ሁለት ጓደኛማቾች ሾላ ለመልቀም ዱር ይወጣሉ፡፡ በዚያም አንደኛው ከላይ አውራጅ  ሌላው ደግሞ ከታች ለቃሚ /ተቀባይ/ ለመሆን በቃል ተስማምተው የድርሻቸውን ማከናወን ጀመሩ፡፡ ከተወሰኑ ደቂቃዎች በኋላ ግን በሁለቱ ወዳጆች ፍቅር፣ በጓደኛማቾቹ የዘወትር መተጋገዝ ይፈነድቅ የነበረው ቀዬ ወደ ሀዘን ተቀየረ፡፡ ሕልውናን ሞት፣ ደስታንም እንባ ተካው፡፡ ከሁለቱ ጓደኛማቾች መሀል አንደኛው የስንብት ያህል አጣጥሮ ላይመለስ በዚያው አንቀላፋ፡፡ ባልንጀራ የጎዳችሁ፣ የወዳጅ ፍላፃ ያለፈባችሁ፣ አምኖ መከዳት፣ አጉርሶ መነከስ ቀለብ የሆናችሁ፣ አዝናችሁ የተጨከነባችሁ፣ በወርቅ ፈንታ ጠጠር፣ በፍቅር ፈንታ ጥላቻ የተመዘነላችሁ ቃየል በወንድሙ አቤል ላይ እንዳደረገው ያለ የሆነ ነገር ሊኖር እንደሚችል ትጠረጥሩ ይሆናል፡፡

     እነዚህ ጓደኛማቾች ለጸብ ተሰናዝረው፣ ቂም በቀል አሳድረው፣ ልዩነት አክርመው፣ በውል ተጣልተው አያውቁም፡፡ ሾላ ለመልቀም ብቻ ሳይሆን እውቀት ለመገብየትም ተነጣጥለው ሄደው አያውቁም፡፡ የአፋቸው ብቻ ሳይሆን የልባቸውም የጋራ ነው፡፡ አንዱ የሚናገረው ሌላውን የሚደግፍ፣ መተናነጽ የሞላበት ነው፡፡ ቁራሿን እየተካፈሉ፣ ዝግን ጥሬ እየተዘጋገኑ፣ በአንድ ዋንጫ እየተጎነጫጩ፣ ትንሽ አጎዛ ላይ እየተላፉ ያደጉ የሁለት ቤት ልጆች ናቸው፡፡ አብሮህ የሳቀውን ትረሳዋለህ፡፡ አብሮህ ያለቀሰውን ግን ፈጽሞ አትረሳውም እንደሚባለው አብሮ መጫወት ብቻ ሳይሆን አብሮ የማንባትንም ወራት በፍቅርና በደስታ አሳልፈዋል፡፡

     ታዲያ አሁን ምን ክፉ ገጠማቸው፣ መሀላቸው ምን ገባ ትሉ ይሆናል፡፡ ሾላ በመልቀሙ ሂደት ከላይ የነበረው ልጅ ድልጠት ይገጥመውና ተንሸራቶ ከሾላው ላይ ሲወድቅ አጎንብሶ ይለቅም የነበረው ጓደኛው ላይ በሙሉ አካሉ ይወድቅበታል፡፡ በአጋጣሚና በጓደኛው መሥዋዕትነት የተረፈው ልጅ በሕይወት መኖሩ መደነቅ ሞልቶት እያጣጣረ እጁ ላይ ያሸለበውን ጓደኛውን እየተመለከተው ወደ ውስጥ አለቀሰ፡፡ እጁ ላይ የያዘው ሬሳ ለእርሱ የሰጠውን ሕይወት፣ የተጨፈኑ ዓይኖቹ የሰጡትን ማየት፣ በድን አካሉ ለእርሱ የሰጠውን ሙቀት፣ የተሰበሰቡ እግሮቹ ለእርሱ የተዉለትን ትጋት እያሰበ አለቀሰ፡፡ ለእርሱ የመጣውን ሞት የወሰደለትን ጓደኛውን በስስት እያያየ ወደ ውጪ ጮሆ አለቀሰ፡፡ አንድ እናት ለአንድ ልጇ እንደምታለቅሰው ያለ አለቀሰ፡፡

    አውቀው ያልከፈሉት ዋጋ እንኳ ይህንን ያህል ልብ ይነካል፡፡ በእርግጥ ተወዳጆች ሆይ ለፍቅር፣ ለይቅርታ፣ ለጽድቅ፣ ለቅድስና፣ ለወንጌል የከፈላችሁት ዋጋ እየቆጫችሁ ይሆን? የኃጢአትን ግብዣ እረግጣችሁ የወጣችሁበት፣ ወደ ዘላለም እቅፍ ጌታ የቀረባችሁበት፣ እንደ ቀድሞው ላትሆኑ እግዚአብሔርን ያወቃችሁበት ቀን እየቆጫችሁ ይሆን? ሰጥታችሁ መስጠታችሁ ባልገባቸው፣ ታግሳችሁ መታገሳችሁን ባልተረዱ፣ ዝምታችሁን እንደ ሞኝነት፣ ማለፋችሁን እንደ ውርደት በቆጠሩባችሁ ወገኖች ተመራችሁ ይሆን? በዘመናችን ሁሉ የማንቆጭበት ነገር ቢኖር ለፍቅር የምንከፍለው ነው፡፡ ፍቅር አውቀን ብቻ ሳይሆን ሳናውቅም የምንታዘዝበት፣ የማናዘው ግን የሚያዝዘን ኃይል ነው፡፡ ሊገድሉ ወጥተው ለወጡለት ሞተው፣ ሊቀሙ ተሰማርተው ያላቸውን ገፈው፣ ሊረግሙ ተንደርድረው ምርቃት ጨርሰው፣ ላለመተያየት ቆርጠው የቁርጥ ተቃቅፈው የተመለሱ ብዙ ናቸው፡፡

    ፍቅር የማይቆጥረው ለዚህ ነው፡፡ በፍቅር ውስጥ የሚቆጠረው ጉዳቱ ሳይሆን ራሱ ፍቅር ነው፡፡ የደረሰብን ሳይሆን በፍቅር የደረስናቸውን የምንቆጥርበት ሂደት ነው፡፡ ከጌታ የተማርነው ይህንንም አይደል? የዚያ ወጣት ሞት ለዚህኛው ጓደኛው ሕይወት ሆነው፡፡ ዳሩ ግን ሟች ይህንን የሚያስተውልበት እድሜ አልነበረውም፡፡ ጣሩ ለመኖር ያደረገው ትግል እንጂ ሞቶ ሕይወት የሰጠበትን ሂደት ያስተዋለበት አልነበረም፡፡ ግን ባይረዳውም፣ ፈቅዶ ባያደርገውም ለጓደኛው የፍቅር ዕዳ ነበር፡፡ ይህ ምንኛ እፁብ ድንቅ ነው? እንኳን በሞታቸው ቀርቶ በሕይወታቸው መልካም መተው የማይሆንላቸው ብዙ ሳሉ ይህ ግሩም ነው፡፡ ኖረውም ሞተውም የሚያዋጉ ሰዎችን ምድሪቱ ከስርም እንደተሸከመች እናውቃለንና፡፡

     ወዳጃችን ኢየሱስ ምንኛ ይልቃል? ሁሉን የሚያውቅ ከሆነውም ያለ እርሱ የሆነ አንድ ስንኳ የሌለ ሊወለድ በረትን ሊሞት መስቀልን መረጠ፡፡ በጊዜው ውስጥ ተንገላትቶ ለዘላለም ወለደን፣ የምድሩን ተቀላቅሎ ከሰማዩ ተካፋይ አደረገን፡፡ ዛሬም ከሾላው ላይ የሚወርዱትን ኃጢአተኞች የሚሸከም ትከሻ ያለው እርሱ ብቻ ነው፡፡ ዘኬዎስን የተሸከመው ውረድ ያለው ጌታ ነው፡፡ ማኅበረሰቡ ዓይንህን ለአፈር ያለውን፣ በነውርና በግፍ የፈረጀውን ቤትህ እገባለሁ! ከማለት የዘለለ ምን መሸከም አለ፡፡ ሰው ስለ ዘኬዎስ ላወራው ኃጢአት ብቻ ሳይሆን ራሱ ዘኬዎስ ለሚያውቀውም ኃጢአት የሞተው ክርስቶስ ነው፡፡ ሰዎች ለምናውቀው በደል እንጂ እነርሱ ለሚያወሩብንና ለሚያሶሩብን ኃጢአት ጌታ እንደሞተልን አይገባቸውም፡፡ ግን እያደር ይረዱታል፡፡ መውረድን ሰው ይፈራል፡፡ ብቻ ምንም ይሁን ሰው ለከፍታው ክብር ይሰጣል፡፡ ከፍ ከፍ ያለው ጌታ ግን ውረዱ ይላል፡፡ የእኛ ጥረት፣ በስንት መቧጠጥና መጫጫር ከወጣንበት ላይ ውረዱ የሚል የከፍታ ሁሉ ወሰን እርሱ ነው፡፡

    ከእውነት ተንሸራተን፣ ኃጢአት አዳልጦን ለወደቅነው በዚህ ፈራጅ ዓለም ውስጥ ክርስቶስ ኢየሱስ ትከሻ ነው፡፡ ክርስቲያን ክርስቲያንን በተጸየፈበት፣ መሸካከም እንደ ጉዳት በተቆጠረበት በዚህ ጊዜ ጌታ ከመቼውም ጊዜ በላይ ታዳጊያችን ነው፡፡ እናንት ደካሞች የራሳችሁን ሸክም ተሸክማችሁት እንኳ እረፍት ያላገኛችሁ እባካችሁ ወደ እግዚአብሔር ኑ፡፡ ሁሉን በሚችል በእርሱ ፊት ሸክም ይቅለልላችሁ፡፡ እርሱ ክርስቶስ ሞቶ ሕይወት፣ ተዋርዶ ክብር፣ ተጥሎ ትንሣኤ የሆነን ነው፡፡ እንደ እርሱ የሚሸከም ሸክሙ ከሞት የሚታደግ ከቶ ማን ነው? በየዕለቱ እኛን የሚያስመልጥ፣ ወጥመድ የሚሰብር፣ ከሰማይ የሆነ ረድኤታችን ስሙ ይቀደስ፡፡

     ወደ ጓደኛማቾቹ ታሪክ እንመለስ የለቅሶውን ጩኸት ተከትሎ ከምስራች ይልቅ መርዶ የሚያሻትተው ማኅበረሰብ ግልብጥ ብሎ ወጣ፡፡ እልልታ ከሚጠራውና እሪታ ከሚሰበስበው የቱ ይበልጣል? ተወለደ ከሚያስደግሰውና ሞተ ከሚያስደግሰው የቱ ይበዛል? ተገላብጦብን የምንገላበጥ ሰነፎች ነንና ጌታ ያስበን፡፡ ሾላው ስር የተሰበሰበው ሰው አንዳንዱ ድሮም አላማረኝም፣ ሌላው ምን ሰይጣን መሐላቸው ገባ?፣ ደግሞ ሌላው ሲያልቅ አያምር እያሉ ወሬ ተቀባበሉ፡፡ ከቁንጫ መላላጫ እንዲሉ ሁሉም የቻለውን ያህል ቦጨቁ፡፡ ያ እንዴት እንደወደቀና እንዴት እንደተረፈ የማያውቅ ምስኪን እንደ ነፍሰ ገዳይ ተቆጠረ፡፡

     መስጠት ብቻ ሳይሆን የለገስነው፣ መመገብ ብቻ ሳይሆን ያበላነው፣ መናገር ብቻ ሳይሆን ያወራነው ለጥፋት እንዳይሆን የምንጸልይ ስንቶቻችን ነን? ወጣቱ አስቦና አቅዶ፣ አውጥቶና አውርዶ፣ አድፍጦና ሸምቆ ጓደኛውን ለመግደል ያደረገው አንዳች ጥረት የለም፡፡ ሟችም በዓላማ አልሞተም፡፡ ታዲያ እንደ ዳኛ ምን ትፈርዳላችሁ?    
-      ይቀጥላል  -    



Tuesday, October 22, 2013

የእግዚአብሔርን አሳብ ማገልገል


                             ማክሰኞ ጥቅምት 12/2006 የምሕረት ዓመት

‹‹ . . . ዳዊትም በራሱ ዘመን የእግዚአብሔርን አሳብ ካገለገለ በኋላ አንቀላፋ፣ ከአባቶቹም ጋር ተጨምሮ መበስበስን አየ፤ ይህ እግዚአብሔር ያሥነሣው ግን መበስበስን አላየም›› (የሐዋ. 13፥36-39)

       ወዳጆች ሆይ ከሁሉ አስቀድሞ የጌታችንና የአምላካችን የመደኃኒታችንም የኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋና ሰላም ይብዛላችሁ፡፡ በዚህ የጽሑፍ አገልግሎት የእግዚአብሔርን አሳብ ማገልገል ማለት ምን እንደ ሆነ የእግዚአብሔርን ቃል መሠረት በማድረግ እንካፈላለን፡፡ የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ጸሐፊ በዚህ ክፍል ላይ ሁለት አገልጋዮችን በንጽጽር ያሳየናል፡፡ ይኸውም ነቢዩ ዳዊትንና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ነው፡፡ ስለ ዳዊት የእግዚአብሔርን አሳብ አገልግሎ መበስበስን እንዳየ ሲፃፍ፤ ስለ ክርስቶስ ደግሞ የእግዚአብሔርን አሳብ አገልግሎ መበስበስን እንዳላየ ያስረዳናል፡፡ በዚህ ክፍል የእግዚአብሔርን አሳብ ማገልገል ምን እንደ ሆነ እንመልከት፡፡ ከዚያ በፊት ግን ጥቂት ጥያቄዎችን ለመንደርደሪያ እናንሣ፡፡

አገልግሎት ምንድነው?
የእግዚአብሔር አሳብስ ምን ማለት ነው?
የሚያገለግለው ማን ነው?
ሁሉ ሰው አገልጋይ ነውን?

Saturday, October 19, 2013

ከሻ . . . መልስ

                   

                          
                                ቅዳሜ ጥቅምት 9/ 2006 የምሕረት ዓመት

Saturday, October 12, 2013

Thursday, October 3, 2013

የስንኝ ገበታ 2


        ሐሙስ መስከረም 23/ 2006 የምሕረት ዓመት
 
ሕይወት እንቆቅልሽ ሕይወት አድር ባይ ናት፣
ኢየሱስ በደሙ ጨብጦ ካልያዛት፡፡
ሕሊና ተራቁቶ ማስመሰል ተላብሰን፣
እንዳንክድህ ጌታ ጸጋህ ይጠብቀን፡፡

የሄደ ላይመጣ ላለም ላይቀር መሄድ፣
 ሰው ሰውን ረግጦ አለፈው በመንገድ፣
 ልቤ እጄን ታዘበው ጨብጦ እንዳልሰጠ፣
 አካፍሎ የበላ ሰብስቦ ከራበው እጅጉን በለጠ፡፡

Wednesday, September 25, 2013

ድመራ (+)


                        
       መስቀል መደመር ነው፡፡ በክርስቶስ ኢየሱስ ያገኘነውን ሕይወት በፍሬ የምንገልጥበት መንገድ! ከትላንት ዛሬ፤ ከዛሬ ነገ የተሻለና የበለጠ ሆነን የምንገኝበት ኃይል ነው፡፡ በክርስቶስ ያየነውን ርኅራኄ ለሌሎች የምንገልጥበት በረከት ነው፡፡ ጥልን ከመካከላችን የምናስወግድበት እርቅ ነው፡፡ በዚህ ዓለም መከራና ፈተና ፊት ትምክህት ነው፡፡ ለምድሪቱ የምናቀርበው መፍትሔ ነው፡፡ እግዚአብሔር ምን ያህል እንደሰጠን ብቻ ሳይሆን ምን ያህል እንደወደደን የፍቅሩን ብርታት፣ የቃል ኪዳኑን ጽናት፣ የተስፋውን ፍፃሜ የምናይበት አደባባይ፤ ከምድር ከፍ ከሰማይ ዝቅ ያለ ቃል ኪዳን፣ ዘመንና ኑሮ ለሁለት የተከፈለበት ውለታ፣ ምሕረትና እውነት፣ ጽድቅና ሰላም የተስማሙበት ማሰሪያ መስቀል (ድመራ) ነው፡፡

       የክርስትናውን መልክ ከሚያደበዝዙ ነገሮች መካከል ዋናው በእግዚአብሔር ቃል ውስጥ የተገለጡትን አሳቦች በትክክል አለመተርጎምና አለመኖር ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ “የተሰቀለውን ኢየሱስን እንድትሹ . . . የተሰቀለውን ክርስቶስን እንሰብካለን . . . (ማቴ. 28÷5፣ 1 ቆሮ. 1÷3)” ተብሎ ተጽፏል፡፡ ለሰዎች መሻት ምላሽ የሚሆነው መሻታችን ሳይሆን ትክክለኛውን እርካታ ማቅረባችን ነው፡፡ የክርስቶስ መለያው መስቀል እንደ ሆነ ሁሉ የክርስትናውም መለያ መስቀል ነው፡፡ ከእግዚአብሔር ጋር ስለ ምቾታችን እየተሟገትን የምንኖርበት ሳይሆን ክርስቶስን በመከራው የምንመስልበትና የመስቀሉን ኃይል በኑሮ የምንመሰክርበት ነው፡፡ ክርስትና ዛሬ ላይ እንዴት እንደደረሰ ታሪክ ስንመረምር ብዙ እውነተኛ ክርስቲያኖች ዋጋ እየከፈሉ፣ የተሰጣቸውን የወንጌል አደራ በደም ጭምር እየተወጡ፣ በቃልና በኑሮ እየታመኑ ነው፡፡ በረከት የምንደምረው ነው፡፡ እግዚአብሔር በመስቀሉ በኩል በክርስቶስ ኢየሱስ ለእኛ የሠራው ሥራ ከንቱ በሆነችው ዓለም ፊት የምንቆጥረው ብልጥግናችን ነው፡፡

Thursday, September 19, 2013

የስንኝ ገበታ 1




            አርብ መስከረም 10/ 2006 የምሕረት ዓመት

ለእኔ ሲነጋ ለጠላት ጨልሟል፣
ጉልበቱ ቄጤማ ኃይሉም ከንቱ ሆኗል፡፡
ደኅንነት ዋስትና የያዘኝ መዳፍህ፣
ጌታ ነህ ኢየሱስ ማንም የማይደፍርህ፡፡


ከሰው የጨረሰ ልቡን ለሚያስታምም፣
ተስፋው ተጨልጦ ለመኖር ያጣ አቅም፡፡
 ትንሣኤና ሕይወት መንገድና እውነት፣
ክርስቶስ ኢየሱስ ፍቱን ነው መድኃኒት፡፡

Thursday, September 12, 2013

ዘመንሰ፡ የተዋጀ ይዋጃል


                                                ሐሙስ መስከረም 2/ 2006 የምሕረት ዓመት

        ዘመንን ያመጣ፣ ለዘመኖቻችን ዳርቻን ያበጀ፣ በእድሜ በረከት፤ በእርጅና ሽበት የሚባርክ፣ ሕፃናቱን አስተዋዮች፣ ጎበዛዝቱን ብርቱዎች የሚያደርግ እግዚአብሔር ብሩክ ነው፡፡ ተናግሮ የሚቀር፣ ትቶት የሚሆን፣ ይዞት የሚወድቅ፣ ጥሎት የሚነሣ፣ ዓይቶት የሚሰወር፣ ወድዶት የሚጠላ፣ ሰጥቶት የሚነፈግ፣ ምሕረት አድርጎለት የሚኮነን፣ ጠግኖት የሚሰበር፣ እንባ ታብሶለት የሚያዝን፣ ደግፎት የማይጸና አንድስንኳ የሌለ እግዚአብሔር አብ ስሙ ይቀደስ፡፡ እኛን ፈልጎ በአድራሻችን የመጣ፣ ሰው ሆኖ ሰዎችን የረዳ፣ ወደ ምድር ወርዶ ወደ ሰማይ ያደረሰን፣ ተዋርዶ ክብርን ለእኛ ያመጣ፣ ራሱን ባዶ አድርጎ ወደ እግዚአብሔር ሙላት ያሻገረን፣ እስከ መስቀል ሞት ታዝዞ በደሙ ያዳነን፣ ለእኛ ጽድቅ የደከመ፣ ለእኛ ትንሣኤ የሞተ፣ በረከታችንን መንፈሳዊ፤ ስፍራችንን ሰማይ ያደረገልን ኢየሱስ ጌታችን ነው፡፡

        የኩነኔውን ዘመን በምሕረት የቀየረ፣ ለዘላለም ያመለጥንበት ዐለት፣ ምድረ በዳውን የምናቋርጥበት ምንጭ፣ ፈተናዎቻችንን የምናልፍበት መውጫ፣ ይገለጥ ዘንድ ባለው ክብር ፊት የምንቆምበት ጽናት መድኃኔዓለም ስሙ ብሩክ ይሁን፡፡ የሚያጽናና ደግሞም የሚያጸና፣ የቃሉን ደጅ የሚከፍት፣ ፍቺውን የሚያበራ፣ መንፈሳዊ ፍሬዎችን እንድናፈራ የሚረዳን፣ ለሙሽራው እንደ ሙሽሪት የሚያስጌጥ፣ ድካማችንን የሚያግዝ፣ በጸጋ የሚያስተባብር፣ ለቤተክርስቲያን ሁለንተናዊ እድገት የሚተጋ መንፈስ ቅዱስ ይባረክ፡፡ እንዴት እንድንጸልይ ለማናውቅ በማይነገር መቃተት የሚናገር፣ ዓለማዊነትን ክደን የተባረከው ተስፋችንን እንድንናፍቅ የሚያበረታን፣ የእግዚአብሔር መንፈስ፥ የጥበብና የማስተዋል መንፈስ፥ የምክርና የኃይል መንፈስ፥ የእውቀትና እግዚአብሔርን የመፍራት መንፈስ ለዘላለም ይመስገን፡፡ አብ፣ ወልድ፣ መንፈስ ቅዱስ፣ አንድ አምላክ አሜን፡፡   

         ወዳጆቼ እንኳን አደረሳችሁ! ትላንት ዛሬ፣ ቅድም አሁን፣ ምሽት ንጋት ስለሆነላችሁ የምታምኑት ጌታ ይባረክ፡፡ ቀኑ በስሙ ይቀደስላችሁ፡፡ ዘመኑ በእርሱ እጆች ላይ ይለቅላችሁ፡፡ ሊመጡ ያሉት ቀናት እንደሚገባ ኖራችሁባቸው እንዲያልፉ ጸጋው ያግዛችሁ፡፡ ዛሬ ብዙ ለመናገር፤ እናንተም ብዙ ለመስማት እንዳልተዘጋጃችሁ ይሰማኛል፡፡ ቢሆንም ጥቂት የእግዚአብሔርን አሳብ እንጨዋወት፡፡ ጌታ ለደቀ መዛሙርቱ ባስተማራቸው ጸሎት ላይ “ፈቃድህ በሰማይ እንደሆነች እንዲሁ በምድር ትሁን” (ማቴ. 6፥10) ብለን እንድንለምን አዝዞናል፡፡ በሰማያት ያለው የእግዚአብሔር ፈቃድና የልቡ ምክር በዚህ ምድር ላይ ሊከናወንበት የሚችለው ትልቁ ስፍራ ክርስቲያን ነው፡፡

Wednesday, September 4, 2013

ዘመንሰ ለሊከ ውእቱ


 እሮብ ነሐሴ 29/ 2005 የምሕረት ዓመት
                                                 
        ተስዕለ አሐዱ እምነገሥት ወይቤ 
«እፎ ዘመን ሐለወት
         ወይቤልዎ «ዘመንሰ ለሊከ ውእቱ፤
          እስመ አንተ አሰነይካ ለሊከ ትሴኒ
             ወለእመ አንተ አህሰምካ ለሊከ ተሃስም፡፡
    ዘመንሰ ለሊከ ውእቱ . . . . »

ትርጉም፡-
ከነገሥታት አንዱ ለሊቃውንቱ እንዲህ የሚል ጥያቄ አቀረበላቸው፡-
ዘመን ማለት ምን ማለት ነው?”
ሊቃውንቱም፡- «ዘመን ማለት አንተ ነህ፣
አንተ ጥሩ ከሆንክ ዘመኑ ጥሩ ይሆናል፣
አንተ ክፉ ከሆንክ ዘመኑ ክፉ ይሆናል፡፡
ዘመን ማለት አንተ ነህ . . . »
      
       ጥሩ ዘመን ከተነሣ ጥሩ ሰዎች ይታወሳሉ፡፡ መጥፎ ዘመንም ከተወሳ መጥፎ ሰዎች ይዘከራሉ፡፡ ዘመኑ የትጋት ከሆነ ትጉ ሰዎች ይወደሱበታል፡፡ ዘመኑ የስንፍና ከሆነ ደግሞ ሰነፍ ሰዎች ይወቀሱበታል፡፡ ዘመን ጥሩም ሆነ ክፉ የሚሆነው ከእኛ ምግባር የተነሣ ነው፡፡ ጥሩ ከሆንን ጊዜው ጥሩ ሲሆን መጥፎ ከሆንን ግን ዘመኑ መጥፎ ይሆናል፡፡ ልክ እንደ መስታወት ራሳችሁን ይዛችሁለት ስትቀርቡ እድፉን እድፍ፣ ንጻቱን ንጹህ እንደሚለው ዘመን አደባባይ ነው፡፡ ገዥና ሻጭ፣ ትጉና ሰነፍ፣ አስተዋይና መሃይም፣ ብርቱና ድኩም፣ ዝንጉና ባለ ራዕይ . . . . ለሁሉም የእኩል እድል ዘመን ነው፡፡

ዘመን ሰውን ይመስላል
ሰውም ዘመኑን፡፡    

Thursday, August 22, 2013

እሸትና ቆንጆ (ካለፈው የቀጠለ)


                                
                               ሐሙስ ነሐሌ 16/ 2005 የምሕረት ዓመት

“ውበትህ ከሰው ልጆች ይልቅ ያምራል ሞገስ በከንፈሮችህ ፈሰሰ ስለዚህ እግዚአብሔር ለዘላለም ባረከህ” (መዝ. 44÷2)::

         ኑሮአችንን ትዝብት ላይ ስንጥለው “ሁሉ አያምልጠኝ” ይሆንብናል፡፡ ከዚህም የተነሣ እንዳያልፉን ዋጋ የምንከፍልባቸው ነገሮች ሁሉ ሕይወታችንን የሚቀራመቱና እድሜያችንን የሚሻሙ ኃይሎች ይሆናሉ፡፡ ሰው የሚኖረው ለተያዘበት ለዚያ ነገር ነውና፡፡ በአንድ ቤተሰብ ውስጥ ያሉ ወላጆች ልጃቸው ሲያድግ ምን ሊሆን እንደሚችል አሳሰባቸው፡፡ ስለዚህም ከወዲሁ የልጁን የነገ ማንነት ለማወቅና የልጃቸውን ቀጣይ ሕይወት ለማስተካከል ፈተና ሊፈትኑት ወሰኑ፡፡ በአንድ ጠረጴዛ ላይ የተወሰኑ ብሮች፣ ውድ የሆነ የመጠጥ አይነት፣ የሙዚቃና ዳንስ ጥበብ የሚያስተምሩ መጻሐፎች እንዲሁም መጽሐፍ ቅዱስ ደረደሩ፡፡ በመቀጠልም ታዳጊ ልጃቸው ወደ ክፍሉ እንዲገባ በማድረግ በፊቱ ከሚመለከታቸው የተለያዩ ነገሮች አንዱን እንዲመርጥ በመጠባበቅ በስውር ይከታተሉት ጀመር፡፡

         እንደ ቤተሰቡ አስተሳሰብ ብሩን ከመረጠ የቢዝነስ ሰው፣ መጠጡን ከወሰደ ጠጪና አባካኝ፣ የሙዚቃና ዳንስ መጽሐፉን ከመረጠ ዘፋኝ፣ መጽሐፍ ቅዱሱን ካነሣ ደግሞ የእምነት መምህር እንደሚሆን ተማምነው ነበር፡፡ ልጅ ወደ እነዚህ ነገሮች ተጠግቶ ምርጫውን በጉጉት ተሰውረው የሚከታተሉትን እናትና አባት በሚያስደንቅ ሁኔታ ቀስ እያለ ከሁሉም አንሥቶ ቀኝና ግራ እጁን በመሙላት ቤቱን ለቀቀ፡፡ ከዚህ በኋላ ወላጅ አባት ወደ ሚስቱ ጠጋ ብሎ “የእግዚአብሔር ያለህ! ልጃችን ያለ ጥርጥር ለሁሉም ይሆናል”አላት፡፡    

         ለሰው ሕይወት አደገኛው ነገር “ምንም መሆን አልችልም” እና “ሁሉንም መሆን እችላለሁ” የሚሉ ሁለት አሳቦች ናቸው፡፡ ሰው ወደዚህ ምድር የመጣው ከነመምረጥ አቅሙ ጋር ከሆነ፤ አልያም ነፃ ፈቃድ አለን ካልን የምንኖረው እየመረጥን ነው፡፡ ከሁሉም ማንሣት ልክ እንደማይሆን ሁሉ ምንም አለማንሣትም እንዲሁ ነው፡፡ ልከኛ ኑሮ የቱን ይዞ የቱን መተው እንዳለብን ማወቅ ነው፡፡ ወደ ሠርግ ቤት ስንሄድ በአንድ ጠረጴዛ ላይ ልዩ ልዩ የምግብ ዓይነቶች ተደርድረው እንመለከታለን፡፡ አስተውለነው ከሆነ እንደዚህ ያለው አቀራረብ አንድ መልእክት አለው፡፡ እርሱም “መርጠህ አንሣ” የሚል ነው፡፡ ነገር ግን ሰዎች ከሁሉም አንሥተው ሰሃናቸው ተጨንቆ ወደ መቀመጫቸው ይሄዳሉ፡፡ እንደነዚህ ያሉቱ ልዩ ልዩ የሆነውን እንደ አንድ ወጥ ለመጨለፍ ጥረት የሚያደርጉ ናቸው፡፡ ታዲያ እንደዚህ ያለው መስገብገብ ዘግየት ብሎ ከበዪነት ወደ ተመልካችነት፣ ከተጠቃሚነት ወደ አባካኝነት ያሻግራል፡፡

         ሕይወትም ልክ እንደ ሠርግ ቤቱ ግብዣ ናት፡፡ ከሁሉም ልናነሣ አግባብ አይሆንም፡፡ የምንመርጠውን የምናስተውል ልከኛ መራጮች መሆን ያስፈልገናል፡፡ ወደዚህ የተመጠነ ኑሮ ለመምጣት ደግሞ “ሁሉ አያምልጠኝ” ከሚል እብሪተኝነት መላቀቅ አለብን፡፡ አንዳንድ ሰዎች እነርሱ ያልወጠወጡት ወጥ እንደሚጎረና፣ እነርሱ ያልተገኙበት እቅድ እንደማይሳካ፣ እነርሱን ያላካተተ ተግባር እንደሚከሽፍ ያምናሉ፡፡ የሰዎችን ድርሻና የመሥራት አቅምም ቶሎ አይቀበሉም፡፡ ከዚህ የተነሣ ራሳቸውን ሁሉም ቦታ የመፈለግ አባዜ ይጠናወታቸዋል /ልክ እንደ ጆከር/፡፡

         ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በመልእክታቱ ውስጥ አጉልቶ የሚያንጸባርቀው ነገር ቢኖር “አንድ አሳብ” የሚለውን ነው፡፡ እርሱ ለብዙ አሳብ የኖረ አልነበረም፡፡ ለአንዱ ለዚያ የክርስቶስ አሳብ ግን የኖረ ብቻ ሳይሆን የሞተም ነው፡፡ የእግዚአብሔር ቃል ስለ ጸጋ ስጦታ በተናገረበት ክፍል ላይ “የጸጋም ስጦታ ልዩ ልዩ ነው መንፈስ ግን አንድ ነው” ይላል (1 ቆሮ. 12÷4)፡፡ ጸጋ ለቤተ ክርስቲያን (ምእመናን) መታነጽ አንዱ መንፈስ ቅዱስ ለሰው የሚሰጠው ስጦታ ነው፡፡ ያመኑቱ እንዲጸኑ፤ ያላመኑቱ ወደ ማመን እንዲደርሱ የምንተጋበት ማትረፊያ ነው፡፡ ልዩ ልዩ የሚለው አገላለጽ አንዱ የሚያከናውነውን ሌላው እንደማያደርገው የሚያመላክት አሳብን የያዘ ነው፡፡ ልክ የአካል ክፍሎቻችን የየራሳቸው ውበትና ተግባር እንዳላቸው ሁሉ ማለት ነው፡፡

         የአካል ክፍሎቻችንን ስናስተውላቸው ለዘመናት የተሰጡበትን ዓላማ ያለ መሰልቸት ሲፈጽሙ እናያቸዋለን፡፡ አፍንጫ ማሽተት መሮት መስማት የጀመረበት፣ ዓይን ማየት ታከተኝ ብሎ መናገር የፈለገበት፣ እጅም መጨበጥ ሰለቸኝ ብሎ ሊረግጥ የዳዳበት ዘመን የለም፡፡ ለተሰጣቸው ለአንዱ ተግባር ተሰጥተው ይኖራሉ፡፡ ለሁሉም መሆን አንችልም! የምንሆንለት ግን አለ፡፡ ሁሉም ሰው የበለጠ ውጤታማ ሊሆንበትና በተሻለ ሁኔታ ሊያከናውነው በሚችለው ተግባር ላይ መሰማራቱ የሚመጣውን ውጤት ማኅበራዊ ያደርገዋል፡፡ ጆሮ ሎቲ ማንጠልጠል ቢፈልግ ዓይን ይመርጣል፣ እግር ይሄዳል፣ አፍ ግዢው ላይ ይግባባል፣ እጅ ለማስጌጥ ይራዳል . . . በመጨረሻ ግን አካል ይሞገሳል፡፡

         ኑሮአችን ውስጥ ከእያንዳንዱ ትጋት ጀርባ ያለው መሻት በልጦ መታየት አልያም አንሶ አለመታየት ስለሆነ “አይታለፍም” የሚለው መፈክር ሁልጊዜ ያስተጋባል፡፡ እንዲህ ያለው አባባል በተግባራዊ ሁኔታ ለእሸትና ቆንጆ ብቻ የሚውል አይደለም፡፡ ሰዎች እንደ ዋዛ የማያልፏቸው ብዙ ከንቱ ነገሮች አሉ፡፡ ይህ ዓለም ያስጌጣቸው፣ ከፍታ የሰጣቸው፣ የሰዎች ሽሚያ የከበባቸው ነገሮች እንዳያልፉን የምንናጥባቸው ናቸው፡፡ የዚህ ዓለም አንዱ ማጃጃያ ውበት ነው፡፡ ተረታችን እንኳ “ሲያዩት ያላማረ . . . ” የሚል ነው፡፡ የዕብራውያን ፀሐፊ “ኢየሱስ ክርስቶስን ተመልከቱ” (ዕብ. 3÷1) በማለት ሰው ሁሉ “አይለፈኝ” የሚለውን ውበት ያመላክተናል፡፡ መቼም ይህ ሁሉ ወገን ቀን ከሌሊት የሚፍጨረጨረው ለምንድን ነው? ብለን ስንጠይቅ ከጌታ አንፃር ስንዳኘው “ባነሰው ለመርካት” የሚል ምላሽ እናገኛለን፡፡

         ጌታ የዓይናችን ማረፊያ፣ በልተነው ብርዱን ማለፊያ እሸት ነው፡፡ ዝናብ እየዘነበ፣ ብርዱም እየበረታ፣ ሰማዩም እየጠቆረ ሲመጣ ጥላቸውን ይዘው እሸት የሚጠብሱ ወገኖች ጌታን እንድናስበው በብዙ የሚረዱን ናቸው፡፡ ስቃይና ፈተና በላያችን ሲወርድ፣ የመከራ ኃይልና ብርታቱ ሙቀታችንን ሲያቀዘቅዘው፣ የሁኔታ መጥቆርና የቀን መክፋፋት ሲከበን አዎ! ሁሉን የምንረሳበት፣ ውስጣዊ ሙቀታችን የሚመለስበት ሲመሽ ታርዶ የተጠበሰው መሥዋዕት ኢየሱስ ነው! እርሱ ውበታችን የሆነበትን መንገድ ስንመረምር “መልክና ውበት የለውም፤ ባየነውም ጊዜ እንወድደው ዘንድ ደም ግባት የለውም፡፡ የተናቀ ከሰውም የተጠላ የሕማም ሰው ደዌንም የሚያውቅ ነው” (ኢሳ. 53÷2-3) ተብሎለት ነው፡፡ ደመ ግቡን ማንም ይወድደዋል፡፡ ጌታ ግን እንወድደው ዘንድ ደም ግባት አልባ ሆኗል፡፡ እኛ ወደ ክብር የመጣንበት መንገድ የእርሱ መናቅና መጠላት፣ ሕማም መልበስና ደዌን ማወቅ ነውና፡፡

         እሸት በእሳት ተጠብሶ፣ እንደ ወተት ያለ ውበቱ ጠቁሮ፣ ተንገላቶና ተሰቃይቶ ወደ ሰው ለመብል እንዲደርስ ለእግዚአብሔር እንደ ተወደደ መሥዋዕት ራሱን ያቀረበ፣ ሥጋዬ ብሎ ብሉኝ፣ ደሜ ብሎ ጠጡኝ ያለ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ እስራኤል በአብ የትእዛዝ ቃል በብሉይ ኪዳን ተጠብሶ የበሉት ፋሲካ፣ የግብጽን ጨለማ ያመለጡበት የብርሃን ዓምድ፣ የሞት መልአክ እንዲያልፋቸው የሆነበት ደም፣ ነውር የሌለበት ጠቦት፣ ሲመሽ ያረዱት በግ ኢየሱስ ነው (ዘጸ. 12)፡፡ በእርግጥም ክርስትና የማናልፈው እሸትና ቆንጆ አለው፡፡ ነቢዩ በመዝሙሩ “ውበትህ ከሰው ልጆች ይልቅ ያምራል ሞገስ በከንፈሮችህ ፈሰሰ ስለዚህ እግዚአብሔር ለዘላለም ባረከህ” በማለት ስለ ክርስቶስ ውበት የተናገረበትን ክፍል ስናስብ ውበት ላጣነው ለእኛ እውነተኛው ውበታችን ማን እንደ ሆነ ያስረዳናል፡፡ ነቢዩ ኤርሚያስ ደግሞ እግዚአብሔር “በውኑ ቆንጆ ጌጥዋን ወይስ ሙሽራ ዝርግፍ ጌጥዋን ትረሳለችን? ሕዝቤ ግን የማይቈጠር ወራት ረስቶኛል” (ኤር. 2÷32) ያለበትን አሳብ ያቀርብልናል፡፡          


         ጌታ እንኳን ከኑሮው ከከንፈሩም ቃል ሞገስ ይፈስስ ነበር፡፡ ቆንጆ ያሰኘን ጌጥ፣ ለሙሽራይቱ ቤተክርስቲያን ዝርግፍ ጌጥ ክርስቶስ ነው፡፡ በእርሱ ሕይወት አለ፡፡ ሕይወትም ትበዛለች፡፡ ይህ እንዲበዛልን የመጣው ጌታ አይለፈን፡፡ ሰው የሰው ነገር አልፎት ከተቆጨ ሕይወት የሆነ መድኃኒትን ቸል ማለት እንዴት አያስቆጭም? ለሚያልፈው ተሽቀዳድሞ ለሚዘልቀው መቦዘኑ ምነው አይሰማው? ከበቆሎ እሸት ወደ ቆንጆ፤ ከቆንጆም ወደ እሸት ስትገላበጡ ለቤዛ መሥዋዕት የሆነልንን እሸት፣ ደም ግባት አልባ ሆኖ የወደደንን ሕይወት ጌታ እንዳታልፉት ልብ አድርጉ፡፡ ክረምቱን በእርሱ አሳብ እንድንሻገር ጸጋ ይብዛልን!! 

Thursday, August 8, 2013

እሸትና ቆንጆ


                                ሐሙስ ነሐሌ 2/ 2005 የምሕረት ዓመት



“እሸትና ቆንጆ አይለፍ ብላችሁ፤ ይኸው ወንዱ አለቀ ሴቶቹ ቆማችሁ፡፡”

       ክረምቱን ተከትሎ መሬትን የሚያረሰርሰው ዝናብ በመካከላችን ምን ትሠራለህ? በሚል ይመስላል እኔንም ያቀዘቅዘኛል፡፡ ከአገልግሎት ወጥቼ ታክሲ የምጠብቅበት ቦታ ላይ ከዚህ ዶፍ የሚሸሽገኝን አንዳች ነገር በመናፈቅ የሚርገፈገፍ ሰውነቴን፣ የሚንቀጠቀጥ ከንፈሬን፣ ኩምትር ጭምድድ ያለ ፊትና መዳፌን እያሻሸሁ ቆሜ አለሁ፡፡ ታዲያ አንድ ታክሲ አጠገቤ መጥቶ ድቅን አለ፡፡ በር ተከፍቶ ወራጆች ሲወርዱ አንዲት ልጅ ዓይኔ እየተመለከተው ያለውን፣ ጎኗ የነበረ የማውቀውን፣ አንድ ወጣት እየተሳደበች ወረደች፡፡ እርሱም ከውስጥ ሆኖ መልስ እየሰጠ ስለ ነበር ሴቲቱ እንደመሄድ እያለች ተመልሳ ትሳደባለች፡፡ እኔም ወደ ታክሲው ውስጥ ለመግባት እየሞከርኩ “በቃ ተዪው . . . ለመሆኑ ምን አድርጎሽ ነው?” አልኳት፡፡ እርሷም “እንኳን ጠየከኝ!” በሚል ስሜት “ጠይቆኝ ነዋ!” ብላ መንቀር መንቀር እያለች መንገዱን አቋርጣ ወደ መንገዷ ሄደች፡፡ በታክሲው ውስጥ የቀረው ሕዝብ ሰምቶ ኖሮ አንድ ጊዜ ሳቃቸውን ለቀቁት፡፡ የማውቀውም ልጅ ተሸማቀቀ፡፡ ታዲያ ወደ ውስጥ ገብቼ ሰላምታ ከተለዋወጥን በኋላ ለዚህ ጽሑፍ መነሻ የሆነኝን ነገር ተናገረ፡፡ እርሱም፡- “ምን እባክህ እሸትና ቆንጆ አይታለፍም ብዬ እርሜን የክረምቱን ብርድ መርሻ ብላከፍ ስድቤን ጠጣሁ” ብሎ ፈገግ አለ፡፡

      በማኅበረሰባችን መካከል ከሚነገሩ ልማዳዊ ብሒሎች መካከል “እሸትና ቆንጆ አይታለፍም” የሚለው በክረምቱ ወቅት ተዘውታሪ አባባል ነው፡፡ መቼም የተረትና ወግ፣ የስነ ቃልና የአበው ብሒል ባለ ጠጎች መሆናችን እሙን ነው፡፡ ነገር ግን እነዚህ ተዘውታሪ አባባሎችና ተረቶች በሰብእና አቀራረጽ ላይ ሊኖራቸው የሚችለውን አዎንታዊና አሉታዊ ተጽእኖ ማስተዋል መቻል ተገቢ ነው፡፡ ምክንያቱም እንደነዚህ ያሉት በቀላሉ ወደ ሰው ጆሮ ብቻ ሳይሆን ወደ ሰዎች ልብ ዘልቀው የመግባት፣ ኮርኩሮ ስሜትን የመንካት አቅማቸው ከፍተኛ ስለሆነ ነው፡፡ ድሮ ድሮ በገጠር አካባቢ (ምናልባት አሁንም ጭምር) ሁኔታው በሚጠይቀው መንገድ የተለያዩ አባባሎችን መናገር ልማድ ነበር፡፡ ለምሳሌ ሥራ ላይ ሲሆኑ የበለጠ የሚያተጋ፣ የታመቀ ኃይልን ተግባር ላይ ለማዋል የሚያበረታ አባባል ይነገራል፡፡ በሐዘን ላይ ደግሞ የሚያጽናና፣ ያለፈውን ትቶ ለፊቱ የሚያሳስብ፣ ለሞተው ቆርጦ ለቆመው የሚያዝን ስነ ቃል ይመዘዛል፡፡ በተለይ ቅኔያዊ የሆኑ ንግግሮች መሞካሻም መዳሚያም በመሆናቸው ትልቁን ድርሻ ይወስዳሉ፡፡

Wednesday, July 31, 2013

ካፈርኩ አይመልሰኝ (ካለፈው የቀጠለ)


                                እሮብ ሐምሌ 24/2005 የምሕረት ዓመት

“ቃየንም ወንድሙን አቤልን፡- ና ወደ ሜዳ እንሂድ አለው። በሜዳም ሳሉ ቃየን በወንድሙ በአቤል ላይ ተነሣበት፥ ገደለውም” (ዘፍ. 4÷8)፡፡

        ግንኙነትን አስመልክቶ የሚያሻክሩ ምክንያቶችን ከአንድ እስከ አምስት ነጥቦች ባለፈው ንባባችን ለማየት የሞከርን ሲሆን በዚህ ክፍል ደግሞ ቀሪ ምክንያቶችን የምንዘረዝርና ርእሳችንን በደንብ የምናብራራ ይሆናል፡፡

6. ሁሉም ጥሩ ወይም ሁሉም መጥፎ፡- እንደዚህ ያሉ ሰዎች ማንኛውንም ነገር ነጭ ነው አልያም ጥቁር ነው፣ መልካም ነው አልያም መጥፎ ነው ከማለት ውጪ ነገሮችን በሚዛናዊነት ለመዳኘትና ከተለያየ አቅጣጫ ለማየት ጥረት አያደርጉም፡፡ ሁሉም ነገር ለእነርሱ ከሁለት አንዱ ነው፡፡ እንዲህ ያለው አመለካከት ግንኙነትን ሚዛን ያሳጣል፡፡ ሁሉም መጥፎ እንደ ሆነ በምናስብበት ሁኔታ ውስጥ ስንሆን ደጉን ነገር ለመመልከት ጭፍኖች እንሆናለን፡፡ ሁሉም ጥሩ እንደ ሆነ በምናስብበት ሁኔታ ደግሞ ኑሮአችን ጥንቃቄ የጎደለው “በሬ ከአራጁ ጋር ይውላል” አይነት ይሆንብናል፡፡ ተወዳጆች ሆይ ሚዛናዊ ሁኑ!

7. ለፍርድ መቸኮል፡- በሰው የመፍረድ ዝንባሌ ግንኙነትን ጉዳት ላይ ይጥለዋል፡፡ አብዛኛውን ጊዜ በዚህ መንገድ የመተያየት ልማዳዊ አለማስተዋል ይስተዋላል፡፡ ነገር ግን በዚህ መንገድ ሰዎችን ማስተካከል አይቻልም፡፡ ደግሞ አብዝተን በምንፈርድባቸው ነገሮች ዘግይቶም ቢሆን ራሳችንን እናገኘዋለን፡፡ ታዲያ እውነተኛነት እኛ በደከምን ጊዜ ለድካማችን የምናሳየውን ርኅራኄ ለሌሎችም ውድቀት እንዲሁ ማሳየት ማለት ነው፡፡ ለመፍረድ አለመቸኮል ያበላሸ እንዲያስተካክል እድል መስጠት ነው፡፡ አለመፍረድ የወደቀ እንዲቆም መደገፍ ነው፡፡ እስቲ በዛላችሁባቸው ወራቶች በቁስላችሁ ላይ እንጨት የሰደዱባችሁን አስቡ፡፡ ምን ያህል ከባድ ነበር? እናንተ ግን ፈጽማችሁ እንዲህ አታድርጉ፡፡ ፍርድን ለጌታ ስጡ!     

8. አሳብ ማንበብ፡- ብዙ ሰዎች የሌሎችን አሳብ ማንበብ እንደሚችሉ ይሰማቸዋል፡፡ ነገር ግን እንዲህ ያለው ሁኔታ በእለት ከእለት ግንኙነቶቻችን ላይ ተጽእኖው ከፍተኛ ነው፡፡ ልትል የፈለከው ገብቶኛል . . . ገና ሳትናገር ሁኔታህ ይነግረኛል . . . ብዙ አትድከም አሳብህን መቼ አጣሁት . . . የሚሉት ቃላቶች ባይሰሙንም ግንኙነቶቻችንን እንደ ብል በልተው ለጉዳት የሚዳርጉ ልማዶች ናቸው፡፡ ማንም ሰው የሌላውን አእምሮ (አሳብ) የማንበብ አቅም የለውም፡፡ ባልተገለጠ አሳብ ውስጥ ያለው መብት የአሳቢው ብቻ ነው፡፡ በቃል አልያም በአካል እንቅስቃሴ (በተግባር) መገለጥ ያልቻለ አመለካከት ምስጢር ነው፡፡ አፍ ሲከፈት ጭንቅላት ይታያል እንዲሉ የሰዎች አሳብ ሲገለጥ ብቻ የምናየው ነገር ይኖራል፡፡ ከዚህ ባለፈ ግን ያውም አቅማችን ባልሆነ ነገር ግንኙነቶቻችንን መጉዳት አይኖርብንም፡፡

Wednesday, July 24, 2013

ካፈርኩ አይመልሰኝ!


                                  እሮብ ሐምሌ 17/2005 የምሕረት ዓመት

“ቃየንም ወንድሙን አቤልን፦ ና ወደ ሜዳ እንሂድ አለው። በሜዳም ሳሉ ቃየን በወንድሙ በአቤል ላይ ተነሣበት፥ ገደለውም” (ዘፍ. 4÷8)፡፡

       በሰው ልጆች የእለት ከእለት ኑሮ ውስጥ ትልቁም ከባዱም ነገር ግንኙነት ነው፡፡ ብዙ ወገኖች በዚህ መንገድ ይፈተናሉ፡፡ በአንድ የጦር ሜዳ ውስጥ ከጠላት ትልልቅ ዒላማዎች መካከል የግንኙነት መስመሩን ማቋረጥ ቀዳሚ አጀንዳው ነው፡፡ እግዚአብሔር እንኳ ምድርም ሁሉ በአንድ ቋንቋና በአንድ ንግግር ነበረች (ዘፍ. 11) በተባለበት ዘመን በሰናዖር ሜዳ በእግዚአብሔር አሳብ ላይ በጠላትነት በተነሡት ሕዝቦች ፊት የሰማይና የምድር ጌታ የወሰደው እርምጃ ቋንቋቸውን መደባለቅ ነበር፡፡ በሌላ አነጋገር የግንኙነት መስመራቸውን አቋረጠው ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ና የተባለው እየሄደ፣ ሂድ የተባለው እየመጣ፣ ውጣ የተባለው እየገባ፣ ቁም የተባለው እየተቀመጠ ጤናማ ግንኙነት ጠፋ፡፡ እናም መጨረሻቸው ጥፋት ነበረ፡፡

       የነገሮች ሁሉ መፍረስ ጅማሬን አስተውላችሁ እንደ ሆነ “ግንኙነት” ተጠቃሽ ነው፡፡ ውጣ ውረድ በበዛበት፣ መውጣትና መግባታችን በብዙ እንቅፋቶች በተሞላበት ዓለም ሰው በሰላም ለመገናኘቱ ዋጋ ቢሰጥ ሲያንስ ነው፡፡ ምክንያቱም መገናኘት ቀላል አይደለምና፡፡ እኛ ስንተያይ ሌሎች ጋር መለያየት፣ እኛ ሰላምታ ስንለዋወጥ ሌሎች ጋር መነካከስ፣ እኛ ጤና ይስጥልኝ ስንባባል ሌሎች ቀብር ላይ መሆናቸውን መዘንጋት የለብንም፡፡ አዘውትሬ ከእንቅልፍ ስነሣ መንጋቱን እንደተመለከትኩ በአእምሮዬ የሚመላለስ ነገር ቢኖር “መንጋት ቀላል አይደለም” የሚለው ቃል ነው፡፡ በእርግጥም እውነቱ ይህ ነው፡፡ ሌሊት ስንት አንቡላንስ ጮኋል፣ ሌሊት ስንቶች በጥይት እሩምታ ያለ በደላቸው ሞተዋል፣ ሌሊት ስንቶች ከጨለማና ከሰው ጅብ ጋር ሲታገሉ አድረዋል፣ ሌሊት ለስንቶች ሲለቀስ ታድሯል፣ ሌሊት ስንት ሰው መርዶ ሰምቷል፣ ሌሊት . . . . አዎ መንጋት ቀላል አይደለም፡፡ እያንዳንዱ ሌሊት ልክ እንደ እናት ምጥ ነው፡፡ ቀኑን የምንቀበለውም ልክ እንደ አዲስ በመወለድ ነው፡፡ ሰው በቀን ላይ የመቅጠር አቅም የለውም፡፡ እግዚአብሔር ግን በቀጠረው ቀን ሁሉን ያደርግ ዘንድ ቻይ ነው፡፡ አሁን አብራችሁ ያላችሁ እንኳን ደስ አላችሁ፡፡ ይህም ስለኖራችሁ ነው፡፡

Wednesday, July 17, 2013

የንጉሥ እልልታ (ካለፈው የቀጠለ)


               
                                እሮብ ሐምሌ 10/2005 የምሕረት ዓመት

“በያዕቆብ ላይ ክፋትን አልተመለከተም፡፡ በእስራኤልም ጠማምነትን አላየም፡፡ አምላኩ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ነው፡፡ የንጉሥም እልልታ በመካከላቸው አለ (ዘኁ. 23÷21)”

       ከዚህ በፊት በተነጋገርንበት ክፍል ድብልቅ ሕዝብ እግዚአብሔር “የእኔ” ብሎ በለየው ሕዝብ መንፈሳዊ ሁኔታ ላይ የነበረውን ተጽእኖ በዚህ ዘመን ካለው የክርስቲያናዊ ኑሮ ፈተናዎች ጋር በማዛመድ ለማየት ሞክረናል፡፡ በዚህ ክፍል በቀጥታ ከርእሳችን ጋር ወደሚዛመደው አሳብ እንገባለን፡፡ ነህምያ ባነበበው የሕጉ ክፍል ላይ ድብልቁ ሕዝብ ወደ እግዚአብሔር ጉባኤ እንዳይገባ ትዕዛዝ የተሰጠበት አንዱ ምክንያት “ይረግማቸው ዘንድ በለዓምን ስለ ገዙባቸው ነው” የሚለው ይጠቀሳል (ከሞዓብ አንፃር)፡፡ ይህ አገላለጽ ደግሞ በቀጥታ ወደ ኦሪት ዘኁልቍ መጽሐፍ ምእራፍ 23 እና 24 አሳብ ይወስደናል፡፡ የሴፎር ልጅ ባላቅ የሞዓብ ንጉሥ በነበረበት ዘመን በለዓም የእስራኤልን ሕዝብ እንዲረግምለት የተስማማበት የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ነው፡፡

       ስለ ሞዓብ ጥቂት ለማስታወስ ብንሞክር ሞዓብ ሎጥ ከታላቅ ሴት ልጁ የወለደው የሞዓባውያን አባትና የሰዶም ፍሬ ሲሆን (ዘፍ. 19÷37)፡፡ ሞዓባውያን ለእስራኤል በመንገዳቸው ሁሉ ብርቱ ፈተናና እንቅፋት የሆኑ ሕዝቦች ነበሩ (መሳ. 11÷17)፡፡ ከተግባሮቻቸውም መካከል በለዓም ሕዝቡን እንዲረግም በጀት በጅተው የተንቀሳቀሱበት ታሪክ በብዙ የአዲስ ኪዳን መጽሐፍት ውስጥ ይታወሳል፡፡ በእግዚአብሔር አሳብ ላይ የሰይጣን ብልሃትና የሥጋ ጠላትነት በግልጥ የሚስተዋል ብርቱ ተግዳሮት ነው፡፡ እንደ ሞዓብ ያለ የአሮጌው ሰው ጠባይና እንደ በለዓም ያለ የመናፍስት ሟርታዊና ሰይጣናዊ አሠራር የተቀደሰውን ማንነት ያለማቋረጥ የሚታገሉ ፈተናዎች ናቸው፡፡

       በለዓምና ባላቅ እስራኤልን ለመርገም የተጓዙበት መንገድ በፊታችን አስደናቂ ትምህርትን ያስቀምጥልናል፡፡ “በለዓምም ባላቅን፦ ሰባት መሠዊያ በዚህ ሥራልኝ፥ ሰባትም ወይፈን ሰባትም አውራ በግ በዚህ አዘጋጅልኝ አለው” (ዘኁ. 23)፡፡ ጠላት የእግዚአብሔርን ሕዝብ ለመርገም በእግዚአብሔር ፊት መሠዊያንና መሥዋዕትን መጠቀሙ በእጅጉ አስገራሚ ነው፡፡ ብዙ ማደናገሪያዎችና አመፃዎች በሃይማኖት ሽፋንና በእግዚአብሔር ስም መደረጋቸውን ስናስብ እናዝናለን፡፡ ዛሬም እንኳ በሚያፋቅረው ክርስትና መጠላላታችን፣ በረከትን እንወርስ ዘንድ ክርስቶስ በሞተለት ክርስትና ጥላ ስር ሆነን መረጋገማችን፣ እግዚአብሔርን እየጠራን ጉድጓድ መማማሳችን የምንወቀስበት ነው፡፡

       “ባላቅም በለዓም እንደ ተናገረ አደረገ ባላቅና በለዓምም በየመሠዊያው ላይ አንድ ወይፈንና አንድ አውራ በግ አሳረጉ።” ከስጦታው ባለፈ የሰጪውን ልብ የሚመረምር እግዚአብሔር ፃድቅ ነው፡፡ እግዚአብሔር በስጦታዎቻችን የሚደለል ሕፃን አይደለም፡፡ እርሱ ለእውነቱ የጨከነ ነው፡፡ ባለ ጠጋ፣ ባለ ሥልጣን፣ ባለ እውቀት፣ ባለ ጥበብ፣ ባለ ዝና፣ ባለ ኃይል . . . እነዚህ ሁሉ የእግዚአብሔርን ተግባር ቀርቶ አሳብ የማስለወጥ አቅም የላቸውም፡፡ እርሱ ለሚሠራው ነገር አማካሪ፣ ለሠራው ነገርም አስተያየት ሰጪ አያሻውም፡፡ በለዓምና ባላቅ ግን ሁሉን በሚችል አምላክ ፊት እቃቃ የመጫወትን ያህል እግዚአብሔርን እንደ እግዚአብሔርነቱ አልቆጠሩትም፡፡ እነርሱ በዘረጉት መሠዊያና ባቀረቡት መሥዋዕት ተደልሎ ሕዝቡን ለእርግማን የሚሰጥ፣ የልባቸውን እሺ የሚል አምላክ እንዲሆን አስበዋል፡፡ እርሱ ከመረጃም ከግምታችንም ልዩ ነው፡፡ እርሱ ስለ ራሱ የተናገረው ብቻ ምን ጊዜም ልክ ነው፡፡

Wednesday, June 26, 2013

የንጉሥ እልልታ


                          እሮብ ሰኔ 20/2005 የምሕረት ዓመት

“በያዕቆብ ላይ ክፋትን አልተመለከተም፡፡ በእስራኤልም ጠማምነትን አላየም፡፡ አምላኩ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ነው፡፡ የንጉሥም እልልታ በመካከላቸው አለ (ዘኁ. 23÷21)”

         በምድሪቱ ላይ መኖርን የታደሉ ሰዎች ሁሉ አንዱ ከሌላው ጋር አብሮ በመኖር ውስጥ ያለውን ጣዕምና ምሬት በአግባቡ ያውቃሉ፡፡ እንደ ሰው እንዲኖሩን ከምንፈልጋቸው ቁሳቁሶች በላይ ሰዎች በዙሪያችን መኖራቸው እጅግ አስፈላጊ ነው፡፡ አውራኝና ደስ ይበለኝ፤ አናግሪኝና እንቅልፍ ይውሰደኝ የሚሉ ሰዎችን ሳስባቸው አንዳችን በሌላችን ላይ ሊኖረን የሚችለውን አዎንታዊም ሆነ አሉታዊ ተጽእኖ አስተውላለሁ፡፡ እስቲ ለመኖር እንድትጓጉ፣ ለመሥራት እንድትተጉ፣ በፍቅር እንድትመላለሱ፣ ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም እንድትኖሩ በምክርና በምሪት የተጉላችሁን ሰዎች አስቧቸው፡፡ በምታምኑት አምላክ ስምም ባርኳቸው፡፡

         ሰዎች ከእኛ ጋር መሆናቸው፣ በሀዘንና በደስታ ዙሪያችንን መክበባቸው ምንኛ ግሩም ነው? አንዳንዴ አፋችንን ሞልተን በመተማመን የምንደገፍባቸው ሰዎች እንኳ በቁጥር ብዙ ናቸው፡፡ ታዲያ እንደማይጥሉን ተማምነን በመንገድ የተካካዱን፣ ላንለያይ በቃል ኪዳን ተሳስረናቸው በጥላቻ የተቆራረጡን፣ ብዙ ጠብቀንባቸው የውኃ ሽታ የሆኑብን የዚያኑ ያህል ናቸው፡፡ በእርግጥም ሰውን ክንድ ማድረግ እርግማን ነው (ኤር. 17÷5)፡፡ የእግዚአብሔር ኪዳን ግን የማይሻገረው የለም፡፡ ክንዱ የዘላለም ዋስትና ነው፡፡ እርሱ ከእኛ ጋር ያለው ኪዳን በደም የሆነ ነው፡፡ ሁኔታዎች ቢቀያየሩ፣ ነገሮች እንደ ነበሩ ባይቀጥሉ፣ የሰዎችን ብርታት ድካም ቢፈራረቀው፣ ጠላት ለእልልታ አፉን ቢያሰፋ፣ ከሥጋና ከደም አልቆ ቢቆረጥ ተስፋ እርሱ እግዚአብሔር ያውና ሕያው ነው፡፡ እውነቱ በሰዎች እውነተኛነት ላይ፣ ጽድቁ በሰው ጽድቅ ላይ፣ ቅድስናው በሰዎች ቅድስና ላይ የተመሰረተ አይደለም፡፡ እርሱ ሁሉን የሚቀድስ ቅዱስ፣ የሚያጸድቅ ፃድቅ፣ የምናውቅበት ሀቅ ነው፡፡

Wednesday, June 5, 2013

የሚያስመካ እኔነት


                                እሮብ ግንቦት 29/2005 የምሕረት ዓመት

         እግዚአብሔር ለሙሴ “ያለና የሚኖር እኔ ነኝ” ብሎ ያህዌ የሚለውን ስሙን በብሉይ ኪዳን እንደ ገለጠለት ከቃሉ እንረዳለን (ዘፀ. 3÷14)፡፡ ጌታ ደግሞ ለአይሁድ ሲናገር፡- “አብርሃም ሳይወለድ እኔ አለሁ (እኔ ነኝ)” (ዮሐ. 8÷58) በማለት አምላክ የሆነ የአምላክ ልጅ መሆኑን አስረዳቸው፡፡ እርሱ ጌታ፡-
1. በልቶ አለመጥገብ በሚስተዋልበት፣ ሰው ከብዙ እንጀራው ጋር ሆኖ በጠኔ በሚሰቃይበት በዚህ ዓለም ምድረ በዳ ውስጥ የማይቋረጥ እንጀራ ኢየሱስ ነው፡፡ ለርሀባችን መጥገብ ልኩ ይህ እንጀራ ነው፡፡ ለሕይወት ዋስትናን፣ ለዕድሜ ልምላሜን፣ ለትጋታችን ፍፃሜን የሚሰጥ እንዲህ ይላል፡-
Ø “የሕይወት እንጀራ እኔ ነኝ” (ዮሐ. 6÷35)!

2. ምድሪቱ ላይ ፀሐይ ስትወጣና ስትጠልቅ ማየት ልባችን በተለየ ሁኔታ የማያስተውለው ልምምድ ነው፡፡ ዳሩ ግን በብዙ ሰዎች ልብ ላይ ፀሐይ ብርሃኗ ስፍራን አላገኘም፡፡ የጭፍን አስተሳሰብና የጭፍኖች ተግባር ምድሪቱን ማስጨነቁም ከዚህ ገሀድ የተነሣ ነው፡፡ ሰው ውጫዊ አካባቢው ቢጨልም፣ የእጁ ሥራ መኖሪያ ቤቱን ጨለማ ቢሞላው ሻማ ይለኩሳል፡፡ ሰው ግን ከልቡ ጨለማ ጋር እስከ ሞት ለሞኖር መቁረጡ ምንኛ ያሳዝናል? ዙሪያ ገባው ለጨላለመባችሁ፣ የጠራ የነፃ አልታይ ላላችሁ፣ ዓይን ፈጥጦ ልብ ለታወረባችሁ ጨለማን የሚያጋልጠው፣ ከዚህ እስራት ለዘላለም የሚፈታው እንዲህ ይላል፡-

Ø “እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ” (8÷12)!

3. ለዓለም ሁሉ ኃጢአት የመሥዋዕት በግ ሆኖ ራሱን ያቀረበው ጌታ የወዳጅ ልክ ነው፡፡ ወዳጅነት ሁሉ በእርሱ ይለካል፡፡ የፍቅር ሚዛን እርሱ ነው፡፡ የመውደዱ ፍፃሜ እኛን በእርሱ መጠቅለል ነው፡፡ በእውነተኛ ፍቅር እጮኛውን የሚወድ ባል የልብ ናፍቆቱ ሴቲቱን መጠቅለል(የብቻ) ነው፡፡ እርሱ የልቡን እልፍኝ፣ የሰማይን ደጆች የከፈተልን ነው፡፡  በዚህ ምድር ላይ ብዙ የተዘጉብን ነገሮች ይኖራሉ፡፡ አንዳንዴ መኖራችንን የሚወስኑልን ነገሮች እስኪሆኑ ድረስ በተስፋ መቁረጥ እንሞላለን፡፡ ክርስቶስ ግን ለእኛ ማንም የማይዘጋው በር አለው፡፡ የማንም ጣልቃ ገብነትና ሰብቅ እርሱን አያስጨክነውም፡፡ በጎቹን የሚወድድ፣ በስስት ዓይንና በፍቅር ልብ የሚመለከተን እንዲህ ይላል፡-

Wednesday, May 29, 2013

እየሆነ ያለው . . . (ክፍል ሁለት)


                                            እሮብ ግንቦት 22/2005 የምሕረት ዓመት

       ተወዳጆች ሆይ እንደምን ለዛሬ ደረሳችሁ? ዛሬ ብዙ ናት፡፡ በእጃችን እንዳሉ ከምናስባቸውና በብዙ ዋጋ ከማይተመኑ ነገሮች ሁሉ በላይ ናት፡፡ ለዛሬ ክብር ያልሰጡ በትላንት እየተጸጸቱ፣ በነገ ደግሞ እየሠጉ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ቃል መዳንን የሚያህል ስጦታ ያኖረው “ዛሬ” ላይ ነው (2 ቆሮ. 6÷2)፡፡ ዛሬ ለምትወዷቸው ፍቅራችሁን፣ ለበደሏችሁ ይቅርታችሁን፣ ለዕለቱ ትጋታችሁን፣ ለሚፈልጓችሁ ቸርነታችሁን የምታሳዩበት ዕድል ነው፡፡ ጌታን ለማመስገን ይህ ምንኛ የላቀ ምክንያታችን ይሆን?

      በፍቅር የምወዳችሁ ሆይ ስለ ዘላለም የሚያወራን እግዚአብሔር ነው፡፡ የዘላለም ወሬም ተግባርም የእርሱ ብቻ ነው፡፡ ሰው እንኳ ተግባሩ ንግግሩም አይጸናም፡፡ ዘመናችን ሰው በሰው ከመቼውም ይልቅ ያዘነበት፣ የተዛዘበበትና ለክፉ የተሰጣጠበት ነው፡፡ ጊዜያዊው ነገር የዘላለም ያህል ተስሎብናል፡፡ ለሚያልፈው እየተጣላን ለቋሚው መሽቶብናል፡፡ እንደ ልባችን የሆኑ ነገሮች የማያፈናፍኑ እሾህና አሜኬላ ሆነውብናል፡፡ እርሱ ጌታ ግን የዘላለም መሠወሪያ ነው፡፡ ስለ ዘላለማዊው መኖሪያ የነገረን የዘላለም መጠጊያችን ነው፡፡ ብዙ ሰው እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ያለው ግንኙነት በሚታየውና በሚያልፈው ነገር ላይ እንደተመሠረተ በተግባር ያስባሉ፡፡ እግዚአብሔር ግን የዘላለም አምላክ ነው፡፡ ምክርና ተግባሩም እንደዚሁ ነው፡፡ እርሱ ለእኛ ያለው አሳብ ጊዜያዊ ቢሆን ሰውን እንደ ሆነ ባሰብነው ነበር፡፡ ዳሩ ግን ለእኛ ያለው አሳብ ዘላለም ነው፡፡ የእርሱ ነገሮች ሁሉ ይህንን ያህል ዋጋ የተሸከሙ ናቸው፡፡

       በጌታ የተወደዳችሁ ሆይ ከሚናፍቃችሁ ልብ ሰላም ይብዛላችሁ፡፡ ዛሬ ዋጋዋ የዘላለምን ያህል እንደ ሆነ ተረድታችሁልኛል ብዬ በጌታ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ዛሬ ጀርባ ላይ ከዘላለም ሞት ወደ ዘላለም ሕይወት ሰዎች ሁሉ የሚሻገሩበት እድል መኖሩ ነው፡፡ እስቲ ደግሞ እግዚአብሔር ከበትሩ ጋር በበጎች መሐል ዱር ያገኘውን ብላቴና ከኑሮአችን ጋር አያይዘን እንማርበት፡፡ ስለ ነቢዩ ዳዊት መጠራትና ለእግዚአብሔር ዓላማ በተግባር ወደ መለየት የመጣበትን መንገድ ብዙዎቻችሁ ወይ ተሰብካችሁ አልያም አንብባችሁ እንደማትስቱት ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ እግዚአብሔር ይህንን ብላቴና በአባቱ መረሳትና በወንድሞቹ ቸል መባል (በሚጠሉት) መሐል ራሱን እንዴት ባለ ሁኔታ በዘይት እንደቀባ ለእናንተ መንገር ለቀባሪው እንደማርዳት ነው፡፡ በመሐል የሚገርመኝ አንድ ነገር አሳቤን ወደ ፊት አላራምድ አለውና ላካፍላችሁ ታዘዝኩት፡፡ ምን መሰላችሁ! ብዙ ጊዜ በየምሕረት አደባባዩ ሰዎችን እልል ስለሚያሰኛቸው አገልግሎት ሳስብ ዳዊትና ጎልያድ፣ ጠጠርና ሰይፍ ይታወሱኛል፡፡

Wednesday, May 22, 2013

እየሆነ ያለው . . . (ክፍል አንድ)


                             እሮብ ግንቦት 14/2005 የምሕረት ዓመት

         የእግዚአብሔር ጸጋና ሰላም፤ ምሕረትና ፍቅር የበዛላችሁ፤ መኖራችሁ ከዚህ የተነሣ እንደ ሆነ የአፍና የልብ ምስክርነት ያላችሁ ተወዳጆች ሆይ ሕይወት እንዴት ነው? መቼም ሰው ሁሉ እንደ አንድ የሚጠላው ጥያቄ ይህ ይመስለኛል፡፡ በእርግጥ ጥያቄው ከተሸከመው ቁም ነገር የተነሣ ቢከብደን የሚገርም አይሆንም፡፡ በዚህ ምድር ከሕይወት በላይ የበለጠ ምን ርዕስ ሊኖር ይችላል፡፡ የእግዚአብሔር ልጅ ራሱን ያብራራበት ትልቁ መንገድ “ሕይወት ነኝ” የሚል ነው (ዮሐ. 14÷6)፡፡ የየትኛውም ቤተ እምነት አስተምህሮ ለሕይወት ዋጋ ይሰጣል፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ልክ እንደ መጽሐፉ “ወልድ የሌለው ሕይወት የለውም” (1 ዮሐ. 5÷2) በማለት ዕለት ዕለት ትመሰክራለች፡፡

         በእድሜያችሁ ከሰዎች ጋር በብዙ ዓይነት ርዕስ እንዳወራችሁ እገምታለሁ፡፡ ዳሩ ግን ምን ያህሉ ሕይወት ነበረበት? አልያም ምን ያህሉ የሕይወትን ያህል ዋጋ ነበረው? የእግዚአብሔር ቃል “አንተ ግን ሕይወት ለሚገኝበት ትምህርት የሚገባውን ተናገር” (ቲቶ. 2÷1) በማለት ያስጠነቅቀናል፡፡ ይህ ቃል ተናጋሪውን ብቻ እንደሚመለከት ልታስቡ ትችላላችሁ፡፡ ዳሩ ግን ለሰሚውም የዚያኑ ያህል መልእክት አለው፡፡ የስንቶች ጆሮ ስለ ሕይወት ለመስማት ወኔው አለው? ብለን ብንጠይቅ መልሱ ምላሳችን ላይ ነው፡፡ እንዲህ ያለውን ጥያቄ ለራሳችን ባቀረብንባቸው ጊዜያቶች ሁሉ ከውስጠታችን ጋር ተዛዝበናል፡፡

       አሁን በዚህ ሰዓት በሚሊዮን የሚቆጠር ሕዝብ በአንድም በሌላም ምክንያት ተገናኝቶ በብዙ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ያወራል፡፡ መረጃ ይለዋወጣል፡፡ ይከራከራል፡፡ ደግሞም ይካሰሳል፡፡ እባካችሁ በሁላችንም ሞት ይሁንባችሁና አሁን በዚህ ቅጽበት በምን ርዕሰ ጉዳይ ላይ እያወራችሁ እንደ ሆነ ቆም ብላችሁ አስተውሉ፡፡ የማታወሩ ደግሞ ካላስቸገርኳችሁ በምን ርዕሰ ጉዳይ ላይ እያሰባችሁ እንደ ሆነ አስተውሉ፡፡ በዚያ በምታስቡት አልያም በምታወሩት ውስጥ ሕይወት የሆነው ነገር ምን ያህል ይሆናል፡፡ እግዚአብሔር ሚዛን ላይ ይቅርና እናንተ ሚዛን ላይ እንኳ ክብደቱ ስንት ነው? ብዙ ዜናዎችን የምትከታተሉ ከሆነ የሰዎች ቀልብ የሚሰለብበት፣ ዓይን ፈጦ ጆሮ የሚቆምበት ምን ዓይነቱ የወሬ ርዕስ ነው? መርዶ መርዶው አይደለምን? ሰውን እንዲህ ካለው የሞት ወሬ ጋር ያያዘው ጉዳይ ምን ይሆን? ድህነት ነውን? አለመሰልጠን ነውን? ወይስ አማራጭ ማጣት ይሆን? ወይስ . . . . !

Wednesday, May 15, 2013

የሰው ልጅ እንጀራ



                                 እሮብ ግንቦት 7/2005 የምሕረት ዓመት

         አገልግሎት አንድ አካል ብቻውን የሚያደርገው ነገር ሳይሆን ሁሉም ምዕመን ተገናዝቦና ተባብሮ የሚያከናውነው ተግባር ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን እንደ ክርስቶስ አካል በምትተረጎምበት ሁኔታ እኛ ሁላችን የክርስቶስ አካል ብልቶች ነን (ሮሜ. 12÷5)፡፡ ሁላችንም በአንዱ ክርስቶስ አንድ ልብ አለን (1 ቆሮ. 2÷16) አንዲሁም አንዱን ምግብ (የእግዚአብሔር ቃል) ሁላችን እየተመገብን በህብረት እናድጋለን፡፡ ነገር ግን ጤነኛ ምግብ መመገባችንን እርግጠኛ ልንሆን ይገባል፡፡ መመገብ ውድቀትን ተከትሎ የመጣ እርግማን አይደለም፡፡ ከሰው ተፈጥሮ ጋር የተያያዘ የእለት ከእለት ተግባር እንጂ፡፡ በውኑ ምንድነው የምንመገበው? ክርስቶስ በምድር  ላይ ሲመላለስ በአንድ ወቅት በሰማርያ ደክሞት አረፍ ብሎ ነበር፡፡ ያን ጊዜ ደቀ መዛሙርቱ እንጀራ ሊገዙ ሄደው ነበር መጥተውም ብላ ብለው ይለምኑት ጀመር፡፡ እርሱም የበላ መሆኑን ሲገልጽላቸው ሰው አምጥቶለት ይሆንን ተባባሉ እርሱ ግን የእኔስ መብል የላከኝን ፈቃድ አደርግ ዘንድ ሥራውንም እፈጽም ዘንድ ነው አላቸው (ዮሐ. 4÷34)፡፡

         እንግዲህ ክርስቶስ ሊያገለግል እንጂ ሊገለገል አልመጣም (ማቴ. 20÷8) እንደተባለው እርሱ በምድር በተመላለሰበት የሥጋው ወራት ሁሉ የአባቱን ፈቃድ ማድረግ ቋሚ ትጋቱ ነበረ፡፡ ወደዚህ ዓለም የመጣበትን እውነተኛ ዓላማ እስኪፈጽም ድረስም እረፍት አልነበረውም፡፡ መብሉ የአብን ፈቃድ መፈጸም ነበርና መንፈሳዊ ርሀብ አልነበረበትም፡፡ ጌታ በቃልና በኑሮ አባቱን ደስ ያሰኘ ልጅ ነበር፡፡ በሙላት የተመገበ ሰው ለአባቱ ደስታ ነው፡፡ እኛም ይሄ ነው! የተጠራንለት ዓላማ ሁሌም ፈቃዱን መፈጸም ሁሌም ቃሉን መመገብና በቃሉ መሞላት፡፡

Friday, May 10, 2013

የእንባ መባ


                  አርብ ግንቦት 2/2005 የምሕረት ዓመት



እንባ ነው መባዬ አንተን መቅረቢያዬ
እንባ ነው መባዬ ውዴን መቅረቢያዬ
ሌላማ ምን አለኝ የምከፍልህ የለኝ /2/

                                  ገና በማህፀን የምታውቀኝ
                                  ከእናቴ አስቀድመህ ያየኸኝ
                                  የዘመኔ ጌታ የእድሜዬ
                                  መከበሪያዬ ነህ ግርማዬ

Wednesday, May 8, 2013

የቀርሜሎሱ ጽናት



                                        እሮብ ሚያዝያ 30/2005 የምሕረት ዓመት      

    በዕብራይስጥ ቀርሜሎስ ማለት ፍሬያማ ማለት ሲሆን ኤልያስ በተገለጠ ሁኔታ ብቻውን ከእግዚአብሔር ጋር የቆመበት፣ አምላኩን እንደማያሳፍረው የተወራረደበት ተራራ ነው (1 ነገ. 18)፡፡ ታዲያ በዚህ ተራራ ላይ የኤልያስን ጽናት በግልጥ እንመለከታለን፡፡ በተለይ ከዝሙት ጋር በተያያዘ በአምላኩ ፊት ያሳየውን የእምነት ብርታት እናስተውላለን፡፡ ምክንያቱም እስራኤላውያን ለእግዚአብሔር ጀርባቸውን ሰጥተው ያመልኩት የነበረው በኣል (ጣዖት) አምልኮ ይፈጸምለት የነበረው በዝሙት፣ ራስን በማጎሳቆልና ሰውን መሥዋዕት አድርጎ በማቅረብ ነበር፡፡ ታዲያ ኤልያስ ለእግዚአብሔር እስራኤል ለጣዖታቸው የአምልኮ ሥነ ስርዓት ለመፈጸምና መሥዋዕት ለማቅረብ ተራራው ላይ በተሰበሰቡ ጊዜ የእግዚአብሔር ሰው ኤልያስ እያንዳንዱን ትዕይንት በዓይኑ ተመልክቶአል፡፡