Tuesday, May 15, 2012

“እናታችን ሆይ”


                     
         ትምህርት ቤት ሳለሁ የማማከር ስነ ልቡና (Counseling Psychology) መምህራችን የነገረንን ታሪክ አስታውሳለሁ፡፡ ልጅቷ መንፈሳዊ አማካሪዋ ወደሚሆኑ አባት መጥታ ስለ ጸሎት ሕይወቷ ጥያቄ ሲያቀርቡላት “አባታችን ሆይ” ብላ እንደማትጸልይ ይልቁንም በዚህ ፈንታ “እናታችን ሆይ” በማለት እንደምትጸልይ ነገረቻቸው፡፡ በምላሿ የተገረሙት አባት ከፊት ይልቅ ትኩረታቸውን በመስጠት እንዲህ ለመጸለይዋ ምክንያቱ ምን እንደሆነ ጠየቋት፡፡ እርሷም በልጅነቷ አባቷ እንደደፈራትና ለእናቷ የከፋ ጥላቻ እንደነበረው በዚህም ምክንያት ለአባቷ ብቻ ሳይሆን በአጠቃላይ ለአባት ያላት አመለካከት እንደተበላሸ በአባቷ ላይ ያላትም ጥላቻ እግዚአብሔርን አባት ብላ እንዳትጠራው በልጅነት መንፈስም በፊቱ እንዳትቆም እንዳደረጋት ነገረቻቸው፡፡

        አበው “እናትነት እውነት፣ አባትነት እምነት ነው” ይላሉ፡፡ ምክንያቱም እናት ከእርግዝናዋ ጀምሮ እስከ ምጧ ድረስ ያለው ሂደት ለማንም ግልጥ ነው፡፡ አባትን አባት ብሎ መጥራት ግን ማመንን ይጠይቃል፡፡ ብዙ ማስረጃዎች ጥቅም ላይ የሚውሉት የአባትን አባትነት (ወላጅነት) ለማረጋገጥ ነው፡፡ ስለዚህ ከእናት ይልቅ አባት አባትነቱን በተግባር መግለጽ አለበት፡፡ የሙሽራው ክርስቶስና የሙሽራይቱ ቤተ ክርስቲያን ሕብረት ለባልና ለሚስት ጥምረትና የኑሮ ስርዓት ከፍ ያለ ማሳያ እንደሆነ ሁሉ አባት ለልጁ ምን አይነት አባት፣ ልጅም ለአባቱ ምን አይነት ልጅ መሆን እንዳለባቸውም በብርቱ ያስረዳናል፡፡ አንድ አባት ለልጆቹ የሚያደርግላቸው የመጀመሪያው ነገር እናታቸውን መውደድ ሲሆን ለሚስቱ ሊያደርግላት የሚያስፈልገው ቀዳሚ ነገር ደግሞ ልጆቿን መውደድ ነው፡፡ አገራችን ላይ አባትነት ምን ያህል ሚዛን ይደፋል ብለን ብንጠይቅ ምናልባት የቀደመ ታሪክንም መፈተሽ ይኖርብናል፡፡ ዳሩ ግን ለተነሣንበት ርዕስ በሚመጥን መልኩ ዳሰሳ ስናደርግ ብዙ ልጆች እናታቸውንም አባት አድርገው የኖሩበት እንደውም አንዳንድ ልጆች በእናታቸው ስም ሁሉ እንደሚጠሩ መረዳት እንችላለን፡፡ ስለ ቤተሰብ ከሚዘፈኑት ዘፈኖች እንኳ አብላጫው የእናት ነው፡፡

        በአንድ ልጅ እድገት ላይ የቤተሰብ ተጽእኖ ለልጁ መልካም መሆን አልያም መጥፎ መሆን አብላጫውን ድርሻ ይወስዳል፡፡ ስለዚህ በልጆች አስተዳደግ ላይ የአባትና የእናት ሚና ቀላል አይባልም፡፡ በዚህ ርዕሰ ጉዳይ ላይ ለመጻፍ የተነሣሁት ያለፈውን የእናቶችን ቀን አስመልክቶ ነው፡፡ የበሽታ ቀን በሚከበርበት ዓለም ላይ ወደ እዚህ ምድር ስለምንቀላቀልባቸው ሁለተኛ ፈጣሪ እናቶች ቀን መሰየሙ ደግሞም መከበሩ ቢያንስ እንጂ አይበዛም ብዬ አስባለሁ፡፡ በተለይ ለኢትዮጵያውያን እንዲህ ያለው አጋጣሚ ትልቅ ስፍራ እንደሚኖረው አምናለሁ፡፡ የእኛ አገር እናቶች አባትም ጭምር ሆነው ያሳደጉን ናቸው፡፡ ጠቁረው እንድንቀላ፣ ደክመው እንድንጠግብ፣ ከስተው እንድንፋፋ፣ ኖረው ብቻ ሳይሆን ሞተውም ያኖሩን ናቸው፡፡

          ጆርጅ ዋሽንግተን ስለ እናቱ ሲናገር “እናቴ በሕይወት ዘመኔ ካየኋቸው ሴቶች ሁሉ እጅግ የተዋበች ናት፡፡ መላው እኔነቴ ሁሉ ለእናቴ የተሰጠ ነው፡፡ በሕይወት ዘመኔ ያገኘሁት ስኬት ሁሉ ከእናቴ ከተቀበልኩት ሞራላዊ፣ ስነ ልቦናዊና አካላዊ ትምህርት የተነሣ ነው” በዓለም ላይ እጅግ ተወዳጁ ቃል እናት የሚለው ነው፡፡ ይህም መስማማት ያመጣው ሳይሆን ተፈጥሮአዊ ነው፡፡ አንድ ወጣት ስለ እናቱ ሲናገር “ከጥቂት ዓመታት በፊት እናቴን በሞት አጥቻለሁ፡፡ በእናቴ ሞት የተነሣ የደረሰብኝ ጥልቅ ሀዘንና ውስጣዊ ሕመም ስር የሰደደ ከመሆኑ የተነሣ አሁንም ድረስ ጠባሳው አልሻረም፡፡ ነገር ግን መለስ እልና በእናቴ ልዩ ፍቅር እንዲሁም እንክብካቤ ያሳለፍኩትን ዘመን በማስታወስ ልጅነቴን እናፍቃለሁ” ብሏል፡፡ አንድ ያልታወቀ ሰው “ብዙ እናቶች እጅግ ደስ የሚሉ ናቸው፡፡ ግን የማንም እናት እንደ እኔ እናት ጽኑ አይደለችም፡፡ ነገሮች እየከበዱ ቢሄዱም፣ ችግሮች ቢከሰቱም እርሷ ግን ተስፋ አትቆርጥም ፈጽሞ አትወድቅም፡፡ በየዕለቱ ለእኔ ያላት ትምህርት ከሚሊዮን ጊዜ የሚበልጥ ማለቂያ የሌለው ነው፡፡ መክፈል የማልችለውን ፍቅርና ምቾት ከእርሷ አግኝቻለሁ፡፡ ለእርሷ ያለኝን ፍቅር ለመግለጽ አልጀምረውም፡፡ ይህ ልክ እንደ መስመር መጀመሪያና መጨረሻ የሌለው ነው፡፡ ግን የማንም እናት እንደ እኔ እናት የተለየች አይደለችም” በማለት ስለ እናቱ ተናግሮአል፡፡

         ሁላችንም ብንሆን ስለ እናት ጥቂት የማለቱን እድል ብናገኘው ማቋረጥ እንደሚሳነን እገምታለሁ፡፡ ስለ እናት የተባሉ ጥቂት የልብ መልእክቶችን እንመልከት፡-
·        የእናት ጥበብ የመኖርን ጥበብ ለልጆች ማስተማር ነው፡፡
·        የእናት ልብ የሕፃናት ትምህርት ቤት ነው፡፡
·        እናት ጉዳታችንን እና ጭንቀታችንን ሁሉ የምንቀብርበት ስፍራ ናት፡፡
·        እናት ምግብ ናት፣ ፍቅር ናት፣ ምድር ናት፡፡ በእርሷ መወደድ ማለት በሕይወት መኖር፣ ስር መስደድና መታነጽ ነው፡፡
·        አንድ ወቄት እናት ከአንድ ፓውንድ ካህናት ይልቅ ትመዝናለች፡፡
·        ከመላው ዓለም እጅግ ውብ የሆነ አንድ ሕፃን አለ፡፡ እያንዳንዷ እናት ደግሞ ይህ ሕፃን አላት፡፡

       ይህ ጽሑፍ የእናቶችን ቀን ምክንያት ያደረገ ቢሆንም በመግቢያው ላይ ለመጠቆም እንደተሞከረው አባቶች በሕብረተሰቡ ዘንድ ያላቸው ግምት በልጆቻቸው ልብ ውስጥ ያላቸው ስፍራ ከእናቶች አንፃር ስዕሉ የደበዘዘ ነው፡፡ ከዚህም የተነሣ ስለ አባትነት ሲነሣ ከደስታ ይልቅ ፍርሃት የሚነግስባቸው፣  ከደስታ ይልቅ ሀዘን የሚወራቸው ሰዎች ጥቂት አይደሉም፡፡ አባትነት ያለውን ትርጉም ከምንጩ ስንፈትሸው አባትነት እግዚአብሔር ራሱን ከእኛ ጋር ያስተሳሰረበት ሕብረት መገለጫ ነው፡፡ “በሰማይና በምድር ያለ አባትነት ሁሉ ከሚሰየምበት ከአብ ፊት እንበረከካለሁ” (ኤፌ. 3÷14-15)፡፡ ምድራዊ አባትነት መሰረቱ ሰማያዊ ነው፡፡ እግዚአብሔር በመፍጠር፣ ለእስራኤል ዘር፣  በልጁ በክርስቶስ ላመኑ አባት ነው፡፡ ይህም ለልጁ ለክርስቶስ ያለውን የባሕርይ አባትነት ሳይጨምር ነው፡፡ ክርስቶስ እንዴት እንጸልይ ዘንድ ሲያስተምረን “አባታችን ሆይ” በማለት እንድንጸልይ አስተምሮናል፡፡

         ምድራዊ አባትነት ሰማያዊውን የሚያጣቅስ እንደመሆኑ የእግዚአብሔርን ፍቅር፣ ርኅራኄና አሳቢነት ማሳየት አለበት፡፡ በጸሎት ወደ እግዚአብሔር ፊት ስንቀርብ ብዙዎቻችን በአባትና በልጅ መካከል እንዳለ የቤተሰባዊነት መንፈስ መቆም እንፈተናለን፡፡ ይህንን ተጽእኖ ያመጣው ደግሞ በሥጋ ያሉንን አባቶች በምናይበት አይን እግዚአብሔርን ለማየት መሞከራችን ነው፡፡ ነገር ግን ምድራዊው አባትነት በሰማያዊው ይመዘናል እንጂ ሰማያዊው አባትነት በምድሩ አይለካም፡፡ እግዚአብሔር በመልኩ እንደ ምሳሌው ፈጠረን እንጂ እኛ በመልካችን እንደ ምሳሌያችን እርሱን አላስገኘነውም፡፡ በእንጀራ አባት ብታድጉም እግዚአብሔር የእንጀራ ልጅ የለውም፡፡ እርግጥ ነው! በምድራዊው ስርዓት ዳቦ ለለመነው ልጁ ድንጋይ፣ ዓሣ ለለመነው እባብ የሚሰጥ አባት ይኖር ይሆናል፡፡ እግዚአብሔር ግን ፍቅር ነው! አንኳኩ ያለን ይከፍታል፣ ፈልጉ ያለን ይገኛል፣ ጠይቁ ያለንም ይመልሳል፡፡

        የአባትነት ጸጋ ለተሰጣችሁ ሁሉ እግዚአብሔርን በሰው ፊት ለማሳየት ትልቁ አገልግሎት ያለው በዚህ ውስጥ ነውና አክብሩት፡፡ አንድን ሴት ልጅ መውለዷ ብቻ እናት እንደማያደርጋት ሁሉ አንድን አባትም ልጅ ማስወለዱ ብቻ አባት አያሰኘውም፡፡ ስለዚህ አባትነት በሚጠይቀው መጠን እንድንኖር መትጋት አለብን፡፡ ጽሑፋችንን አንድ የአሥራ አምስት ዓመት ልጅ ስለ እናቱ በተናገረው እንፈጽም፡፡ “እናቴ ቤታችንን ምድር ላይ ካሉ ቦታዎች ሁሉ ይልቅ ምርጥና የደመቀ ታደርገዋለች፡፡ ምክንያቱም እናቴ እጅግ አዛኝ፣ ቸር፣ የምትረዳ፣ አሳቢና በፍቅር የተሞላች ናት! ካለችኝ እናት የተሻለ እንዲሰጠኝ ጌታን የምለምነው ምንም የለም፡፡ እናቴ ማለት ለእኔ፡-
የምንጣጣም እውነተኛ ጓደኛ
አብረን ልንጓዝ የምንችል ምቹ ወዳጅ
ደስታን የምትፈጥርልኝ አጋር፣ ለመኖር የምታጓጓኝ ልብ ማለት ናት፡፡ ድፍን ዓለም ቢታሰስ የእርሷን ያህል ፍቅርና ርኃራኄ በተሻለ የሚሰጥ አይገኝም፡፡ እርሷ ለእኔ የፈጣሪ ምርጥ ጥረት ናት” እናቶቻችንን ጌታ አብዝቶ ይባርክልን!!!

4 comments:

  1. Truly, It is "betefikir". Continue posting the good message. God bless

    ReplyDelete
  2. Amen! Edmena ena tena Egziabherin kemefrat gar yibzalachew!

    ReplyDelete
  3. Le abatochachin ye getan fikir ena rihrahe yemiyasayubetin birtat yadililn! Betesebochachinin Egziabher yitebkilin!

    ReplyDelete
  4. እኗት እናት
    እድሜ አይንሳት

    ReplyDelete