Sunday, January 19, 2014

ልዩ፡ በመለኮት ጃን ሜዳ

                                       Pleas Read in PDF: Yemelekot Janmeda
                                                                     
      ‹‹የዚያን ጊዜ እኔ በእርሱ ዘንድ ዋና ሠራተኛ ነበርሁ ዕለት ዕለት ደስ አሰኘው ነበርሁ፥ በፊቱም ሁልጊዜ ደስ ይለኝ ነበርሁ፥ ደስታዬም በምድሩ ተድላዬም በሰው ልጆች ነበረ።›› (ምሳ. 8፥30-31)፡፡

       ቅዱሳት መጻሕፍት የዘላለም አባት፣ የዘላለም ልጅ እና የዘላለም መንፈስ እንዲሁም የዘላለም አሳብ እንዳለ በግልጥ ይናገራሉ (ዘዳ. 33፥27፣ ዮሐ. 1፥1-2፣ ዕብ. 9፥14፣ ኤፌ. 3፥11)፡፡ ፍጥረት በመለኮት ጉባኤ ውሳኔ ወደ ሕልውና ሳይመጣ፣ ሰው በእግዚአብሔር መልክና ምሳሌ ሳይሆን፣ ሰማያትና ምድር ሳይከናወኑ፣ ከዘመን መቆጠር አስቀድሞ ባልተፈጠሩ ሰማያት፣ ባልተቆጠሩ ዘመናት የአብ፣ የወልድና የመንፈስ ቅዱስን አኗኗር ስንመለከት በአካል ሦስትነት የባሕርይ አንድነታቸውን እናስተውላለን፡፡ ሦስት አካላት የሚደሰቱበት አንድ የመለኮት ደስታ ወደ ሕሊናችን ይመጣል፡፡ በጉባኤው መካከል የእርስ በእርስ ተድላቸውንም ልብ እንላለን፡፡  

      አባት በልጁ ደስ ሲሰኝ ልጅም በዚያው ልክ ያለመቀዳደምና መበላለጥ በአባቱ ደስ ይሰኛል፡፡ መንፈስ ቅዱስም እንዲሁ፡፡ ሕብረትን የሚሻ እግዚአብሔር ከፍቅሩ የተነሣ ደስታው በምድሩ፣ ተድላውም በሰው ልጆች መካከል እንዲሆን ወደደ፡፡ እግዚአብሔርም አለ፦ ሰውን በመልካችን እንደ ምሳሌአችን እንፍጠር የባሕር ዓሦችንና የሰማይ ወፎችን፥ እንስሳትንና ምድርን ሁሉ፥ በምድር ላይ የሚንቀሳቀሱትንም ሁሉ ይግዙ (ዘፍ. 1÷26)። ሰው እግዚአብሔር ያሰበለት አሳቡ፣ ያየለት ዕይታው፣ ያዘዘው ኑሮው አልሆን ብሎት ባለመታዘዝ አምላኩን በደለ፡፡ ጥንቱንም በምክሩ ቢበድል አድነዋለሁ፡፡ ለኃጢአቱም ቤዛ እከፍላለሁ ያለ ፈጣሪ ለሰው የመዳንን ተስፋ በበደለበት ሥፍራ ነገረው፡፡ እግዚአብሔር በመልኩ እንደ ምሳሌው የፈጠረው ሰው በመልኩ እንደ ምሳሌው ኃጢአተኛ እየወለደ ሁሉ ኃጢአትን ሰርተዋል ተባለ (ሮሜ. 3)፡፡ የእግዚአብሔርም ክብር እንደ ጎደለን የጎደለን እግዚአብሔር ነገረን፡፡

       የእግዚአብሔር ልጅ በሥጋ ተገለጠ፡፡ በመለኮት አስቀድሞ ማወቅ ለታየው የሰው በደል ‹‹እኔ ቤዛ እሆናለው›› ያለው ወልድ ከድንግል ተወለደ፡፡ የዚህችም ድንግል ስሟ ማርያም ነው፡፡ ‹‹ኮነ ወልደ እጓለ እመሕያው ዘበአማን ወውእቱ ፍኖት ዘይመርሀነ ኀበ አቡሁ ቅዱስ /እርሱም በእውነት ሰው የሆነ ወደ ቅዱስ አባቱ የሚመራን መንገድ ነው/››፡፡ በዘላለማዊ ልደት የአብ የዘላለም ልጅ የእግዚአብሔር ቃል ወልድ የሰው ጠባይዕ የሆኑትን ነፍስን ሥጋን መንፈስን ተገንዝቦ ከኃጢአት በቀር በነገር ሁሉ እኛን መሰለ፡፡ እኛም ፍጹማንና ምሉዓን የሆኑት መለኮቱና ሰውነቱ የባሕርይ መደባለቅና መለወጥ የአቅዋም ሽረትና ፍልሰት ሳይኖርባቸው ጭራሹን ያለመለየትና ያለመከፈል በአንዱ የአካል ተዋሕዶ አንድ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መሆኑን እናምናለን፡፡

Thursday, January 16, 2014

ከዛፉ ውረዱ


                                  Please Read in PDF: Kezafu Weredu


                     
                                         ሐሙስ ጥር 8/ 2006 የምሕረት ዓመት

        ለአገልግሎት ወደ አንድ ከተማ ሄጄ ካሰብኩበት ቦታ እንዲያደርሰኝ በፈረስ ተጎታች ጋሪ ላይ ተሳፈርኩ፡፡ እስቲ እኔም ወግ ይድረሰኝ፣ ኮንትራት ልያዝ ብዬ ሙሉ ሂሳቡን ልከፍለው ተስማምቼ መንገድ ቀጠልን፡፡ ትንሽ በሄድን ቁጥር ሾፌሬን ሰዎች በተደጋጋሚ ሰላምታ ይሰጡታል፡፡ ታዲያ ማን ብለው እየጠሩ መሰላችሁ ‹‹ዶክተር›› በጣም ተገርሜ ‹‹ያሉት እውነት ነው?›› ብዬ ጠየኩት፡፡ እርሱ ግን እየሳቀ ‹‹ቆጥረውኝ ነው›› አለኝ፡፡ እኛ ማኅበረሰብ ውስጥ እየተቆጠረላቸው ከሆኑት በላቀ፣ ከጨበጡት ባለፈ የሚታሰቡ ብዙ ሰዎችን አስተውያለሁ፡፡ ይህ ግን አግራሞቴን አገሸበው፡፡ ሰዉ ለዓመታት ቀን ከሌሊት ደክሞ የሚደርስበትን ሙያ እርሱ እያፌዘ ሲጠራበት ተደነኩ፡፡ በሙያ ስሞች የሚደረጉ ማጭበርበሮችን ሰምቻለሁ፡፡ ቢያንስ እንደዚህ የሚጠራው ጋሪ ነጂ (ዶ/ር) ማኅበረሰቡን ልብላው፣ ላጭበርብረው፣ ላምታታው፣ ቀን ልውጣበት ብሎ አለመነሣቱ፤ ያለውን ኑሮ ተቀብሎ ለሥራ መልፋቱ በልቤ መደነቅ፣ ከንፈሬ ላይ አግራሞት፣ ኮንትራቱ ላይ ደግሞ ተጨማሪ አንድ ብር አስገኘለት፡፡

        መንደሮቹን ስናሳብር ‹‹ዶክተሬ›› ብላ አንዲት መልከ መልካም ሸንቃጣ ወጣት ‹‹ስትመለስ›› አይነት እጇን አወዛወዘች፡፡ ደግሞ እሷን ‹‹ምኗን አክመሃት ነው?›› አልኩት፡፡ እንደ ማፈር ሲል ‹‹ግድ የለም ንገረኝ ያለው ጋሪና ፈረሱ ነው፡፡ ይታዘበኛል ካልክ ያለ ሰው ምስክር እኔን ነው›› ብዬ አደፋፈርኩት፡፡ ከጠየከኝማ ብሎ ነው መሰል ያስነወራቸውን፣ ሲያልፍም ልጅ ያስወለዳቸውን፣ እንደ ሕመምተኛ ተቅለስልሰው የቀረቡትንና የፈወሳቸውን (በሱ ቤት) ዘረዘረልኝ፡፡ እጅብ ያለ ማሳ የመሰለ ጠጉሩን፣ በሻርብ የተጠቀለለ ፊቱን፣ አቧራ የተኳለ ዓይኑን አፍጥጬ አየሁት፡፡ እሺ! ዶክተር በሚል ስሜት ራሴን ወዘወዝኩለት፡፡ ብዙ እንደ ሰማሁ የማልጽፈውን ቀዶ ጥገና ነገረኝ፡፡ በገባው ላናግረው ብዬ ‹‹ለመሆኑ የካርድ ይከፍላሉ›› አልኩት፡፡ ተያይተን ተሳሳቅን፡፡

Tuesday, January 7, 2014

እንኳን አልደረሳችሁ

                        Please Read in PDF: Enkuan Alderesachw

                             ታህሳስ 29 ቀን 2006 የምሕረት ዓመት

         ከሚታየው በሌላኛው ጎን መመልከት፣ ግዙፉን አልፎ ረቂቁን ማስተዋል ከበዓላቶቼ መካከል አንዱ ነው፡፡ ቃሉም ‹‹የሚታየው የጊዜው ነውና የማይታየው ግን የዘላለም ነው›› (2 ቆሮ. 4÷17) ይለናል፡፡ ሰዎች በተስማሙባቸው የተለዩ ቀናቶች ውስጥ ደስታ ብቻ ሳይሆን ሀዘን፣ እረፍት ብቻ ሳይሆን ሁከት፣ ሰላም ብቻ ሳይሆን ክርክርም ይስተዋላል፡፡ የመመገብ ሽር ጉድ እንዳለ ሁሉ ያለመብላት ፍላጎት፣ የመንቀሳቀስና ወዳጅ ዘመድን የመጠየቅ ዝንባሌ እንደሚስተዋል ሁሉ እግርና እጅን አጣጥፎ ከቤት ያለመውጣት ሲያልፍም የመተኛት ሁኔታ ይታያል፡፡ ሰዎች ሁሉ እንደዚህ ያሉት ቀናት የደስታ እንደሆኑ ቢስማሙም እንኳ ሁሉ ግን አይደሰትም፡፡

          ለዚህ ርእሰ ጉዳይ መነሻ የሆነኝ ከተወሰኑ ዓመታት በፊት ለአገልግሎት ሄጄ ቤታቸውን ማረፊያ አድርገው በእንግድነት በተቀበሉኝ ቤተሰቦች ዘንድ ያስተዋልኩት አሳዛኝ ታሪክ ነው፡፡ እማወራዋ ከተቀመጡበት ለመነሣት፣ ከሰው ጋር ብዙ ለማውራት፣ የቀረበላቸውን ምግብ ለመብላት አቅሙም ሆነ ፍላጎቱ የላቸውም፡፡ አብዝቶ መተከዝ፣ ሲያልፍም ማንባት፣ ብቻ መቀመጥ፣ ስልቹነት የቀን ውሏቸው ነው፡፡ የልጆች ከበባ፣ የአባወራው ቁልምጫ፣ የእኛ የእንግዶቹ ማባበያ የሀዘናቸውን ክምር፣ የትካዜያቸውን ቁልል አልፎ ሊዘልቅ አልቻለም፡፡ አልፎ አልፎ ከሚቀምሱት ምግብ ውጪ ቀለባቸው መቆዘም ነው፡፡

        ለዚህ የዳረጋቸው የበዓልን ዋዜማ ለሥራ ወጥቶ፣ ከሽፍቶች በተተኮሰ ጥይት ጭንቅላቱን የተመታ ሬሳ (ልጃቸው) በዚያው ምሽት መኖሪያ ቤታቸው ድረስ መጥቶላቸው ነው፡፡ ከዚያን ቀን ጀምሮ ለእርሳቸው በዓል የሚባል ነገር ትርጉም አይሰጣቸውም፡፡ እርሳቸውን ‹‹እንኳን አደረሰዎ›› ማለት ለትካዜ ርእስ መስጠት፣ ላለፈ ሀዘናቸው ግርሻት መሆን ነው፡፡ እንደ ትኩስ ሬሳ ብቸኛ ወንድ ልጃቸውን ስላጡበት ክፉ አጋጣሚ ይተርኩላችኋል፡፡ ዓመታት ቢያልፉም እርሳቸው መቃብሩ ስር ያሉ ያህል በአሳብ ያምጣሉ፡፡ አለማልቀስ እርሳቸው ፊት አይቻልም፡፡ እንኳን ዕንባ ከዓይናቸው ፈስሶ ፍም የሚመስለው ፊታቸውንም ማየት ለወዮታ ይጋብዛል፡፡ ከብዙ ዓመታት በኋላም ፊቴ ላይ ድቅን ይሉብኛል፡፡