Tuesday, February 12, 2013

ሁሉ አይከፋም


                                ማክሰኞ የካቲት 5/ 2005 የምሕረት ዓመት

          በአንድ ምሽት በአላባማ አደባባይ አንዲት ጥቁር አሜሪካዊት ሴት በብርቱ ከሚዘንበው ንፋስ የቀላቀለ ዝናብ ራሷን ለማስጠለል እየጣረች ሊፍት የሚሰጣት ሰው በመፈለግ ቆማለች፡፡ ጉልበቶቿ እየተብረከረኩ፣ ንፋስ እያንገዳገዳት፣ በድንግዝግዝ አጥርታ ለማየት እየሞከረች የሚያልፈውን ሁሉ መኪና እጇን ዘርግታ እርዳታ ትጠይቃለች፡፡ ብዙዎች ለተማጽኖዋ ምላሽ ሳይሰጡ ሄዱ፡፡ አንዳንዶቹም ከለሯን እያዩ “ይበልሽ” አይነት ገላምጠዋትና የመንገዱን ዳር ውሃ እየረጩባት አለፉ፡፡ በመኪናዋ ብልሽት ምክንያት እንዲህ ላለ ጉስቁልና መዳረጓና እንደ እርሷ ሰው የሆኑ ሰዎች ሊረዱዋት አለመቻላቸው አበሳጫት፡፡ ድንገት ግን ጭብጥ ብላ በቆመችበት አንድ ነጭ ወጣት በ1960ዎቹ የነበረውን ግጭትና በመካከላቸው የተፈጠረውን ልዩነት እንደማያውቅ ሆኖ መኪናውን ፊት ለፊትዋ አቆመ፡፡ ከሞቀው ውስጠኛ ክፍል ወደ ቀዝቃዛው ወርዶ ሁኔታዋ የሚጠይቀውን ያህል እረዳት፡፡
          በተረበሸና በተጣደፈ ስሜት ውስጥ ብትሆንም ከልብ አመስግናው አድራሻውን ተቀብላ ተለያዩ፡፡ ታዲያ ከሳምንት በኋላ የዚህ ሰው ቤት ተንኳኳ፡፡ በሩን ሲከፍት በስጦታ መጠቅለያ የተሸፈነ ውድ ዕቃ ደጃፉ ላይ ተመለከተ፡፡ ከጎኑ ደግሞ ልዩ ማስታወሻ የሚል ፖስታ ተቀምጦአል፡፡ በውስጡም ያለው መልእክት እንዲህ ይላል፡- “በዚያች ምሽት፣ በዚያ አውራ ጎዳና፣ እንደዚያ ባለ ሁኔታ  ውስጥ አንድ ትልቅ ትምህርት በልቤ ላይ አስቀምጠሃል፡- “ሁሉ እንደማይከፋ ተረዳሁ” የአንተ መድረስ እኔን ከጨለማና ከብርድ መታደግ ብቻ ሳይሆን ባለቤቴ በሞትና በሕይወት መካከል ሳለ ከአልጋው አጠገብ ሆኜ እንድረዳው አድርጎኛል፡፡ ከሁሉ በላይ “ሰው ሁሉ ክፉ” እንዳልሆነ ተረድቼብሃለሁና ብሩክ ሁን”!

Tuesday, February 5, 2013

የቆቅ ትዳር (ክፍል ሁለት)


                                                             

                                  ማክሰኞ ጥር 28/2005 የምሕረት ዓመት

      በመጀመሪያው ክፍል ንባባችን በጋብቻው ቀን ትታው ዕጩ ባሏን በሰው ሁሉ ፊት እንደማታገባው ነግራው ስለሄደች ሴት አውርተን ነበር፡፡ ወደ ዛሬው አሳብ ከመሸጋገራችን በፊት ያለፈውን ጥያቄ እንመልስላችሁ፡፡ ሴቲቱ ጥላው እንድትሄድ ምክንያት የሆናት ነገር ምን መሰላችሁ? በእጮኝነት አብረው ባሳለፉባቸው ጊዜያት ሁሉ መደበኛ ፊርማው ምን ይመስል እንደነበር ስለምታውቅ የጋብቻቸው ቀን የፈረመው ፊርማ ትልቅና ደማቅ በመሆኑ ይህም ከሁል ጊዜው የተለየ አዲስ በመሆኑ ምክንያት ነው፡፡ ይህ ለብዙዎቻችን ስሜት አይሰጥ ይሆናል፡፡ ዳሩ ግን ለዚህች ሴት ትልቅ መልእክት ነበረው፡፡ የመጀመሪያው “በዚህ ሰው ውስጥ የማላውቀው አዲስ ጠባይ አለ ማለት ነው” የሚል ሲሆን፤ ሁለተኛው ደግሞ “በትዳር ውስጥ ሊያሳየኝ ያለውን አምባገነናዊ አባወራነት የሚጠቁም ነው” የሚል ይሰኛል፡፡ በዚህ ሰው እውነተኛ ጠባይ ላይ የተደረገ በቂ ጥናት ይኑር አይኑር ባናውቅም በዚህች ሴት ስነ ልቦና መሠረት ግን የእጮኛዋ ጊዜ ጠብቆ ፊርማ መለወጥ ትልቅ መልእክት አስተላልፎላታል፡፡   

     የብዙ ባለ ትዳሮች አንዱ ሙግት “አዲስ ጠባይ” ነው፡፡ ካገባሁት በኋላ አዲስ ሆነብኝ፣ የማልላመደው ጠባይ ገጠመኝ የሚል ሮሮ፡፡ ነገር ግን ምን ያህል ሰዎች ናቸው ከጋብቻ በፊት በሚኖረው አብሮነት (በተአቅቦ) እንደሚገባ የሚተያዩት? በሰውየው ከሚሸሸገው ጠባይ በላይ በእኛ አለማስተዋል ምክንያት በቸልታ የሚታለፍ የተገለጠ ጠባዩ ይበልጣል፡፡ በሕብረት ውስጥ ሁሉንም ማጥራት ባይቻልም ቢያንስ ችግሮቹን በአግባቡ ለይቶ ማወቅ ባያሳርፍ እንኳ ያዘጋጃል፡፡ ነገር ግን ስሜታችንን ብቻ እያዳመጥን ቸል የማይባሉ ነገሮችን (ትንንሾቹን ጨምሮ) ብንዘነጋቸው ዋጋ መክፈላችን አይቀሬ ነው፡፡ ከዚህ በታች የሳይኮሎጂ ባለ ሙያ የሆነ አንድ ወንድም የላከልንን እናስነብባችኋለን፡፡
 


   Commitment                              intimacy


                                         Passion

“ፍቅር በሳይኮሎጂ እይታ

         ስለ ፍቅር መጽሐፍ ቅዱስ፣ የተለያዩ ባለ ሙያዎች እንዲሁም ግለሰቦች ብዙ ብለዋል፤ እኛም ብዙ ሰምተናል ብዙ ብልናል፡፡ ለዛሬ ግን የሳይኮሎጂ ባለ ሙያዎች ስለ ፍቅር የሰጡትን ሙያዊ ትንታኔ ከራሳችን ነባራዊ ሁኔታ ጋር እያነጻጸርን እንመለከታለን፡፡ ከብዙዎቹ የስነ ልቦና ባለ ሙያዎች መካከል ግልጽ በሆነና በማያሻማ ሁኔታ ስለ ፍቅር ትንታኔ የሰጠ ባለ ሙያ ስተርንበርግ ይባላል፡፡ ይህ ባለ ሙያ እንደሚነግረን አንድ ሰው እየተሰማው ያለው ስሜት ፍቅር ይሁን አልያ ተራ ስሜት ማወቅ የሚቻለው እነዚህ ሦስት የፍቅር መሰረታዊያን መኖር ሲችሉ ነው፡፡ እነዚህ የፍቅር መሰረታዊያን ምን ምን ናቸው? በማለት ስንዘረዝራቸው፡ -