Tuesday, December 30, 2014

ዕድሜህ ስንት ነው?

              በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

ማክሰኞ ታህሳስ 21 ቀን 2007 የምሕረት ዓመት

     የሰው የተሰፈረ ዕድሜ የዘላለም እግዚአብሔር ስጦታ ነው፡፡ ሰው ስለተዋደደ የማይጨምረውና የማያዝበት ልዩ በረከት ልንኖርበት የተሰጠን ዘመናችን ነው፡፡ የሥጋ አባታችን አልያም እናታችን የቱንም ያህል ቢወዱን ከዕድሜያቸው ቀንሰው በእኛ ላይ አይጨምሩልንም፡፡ እየኖርን እንደሆነ በተሰማን ጊዜ ሁሉ እያኖረን ያለውን አምላክ ቸል ማለት በደል ነው፡፡ በዚህ መንገድ ለተባረክንበት መባረክ የመጀመሪያው ምላሽ ይህንን እውቅና መስጠት ነውና፡፡ ስለ ስጦታው በቂ ማስተዋል በውስጣችን ከሌለ፤ ለሰጪውም ሆነ ለስጦታው ክብር አይኖረንም፡፡ ተቀብለን ሰጪውን ልብ አለማለት መንፈሳዊ ድንዛዜ ነው!

      ከእግዚአብሔር የተሰጠንን ዕድሜ ሰዎች ‹‹ስንት ነው?›› ጥያቄ ሲያስጨንቃቸው፤ አሳንሰው ሲናገሩ አልያም ባልሰማ ሲያልፉ ብዙ ጊዜ መመልከት የተለመደ ነው፡፡ እንዲህ ያሉ ሰዎች ልኩን ለመናገር የሚቸገሩበትን የስነ ልቦና ትንታኔ ለጊዜው እንተወውና፤ በጀመርንበት መንፈሳዊ ቅኝት ወደ ፊት ለማየት እንሞክር፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ረጅም ዕድሜ የኖሩ፤ እንዲሁም አጭር ዘመን ኖረው ያለፉ ሰዎችን እናገኛለን፡፡ ለዚህ አሳብ በዘፍጥረት ምዕራፍ አምስት ላይ የምናገኛቸውን አባትና ልጅ እንይ፡፡