Tuesday, December 25, 2012

ሥራህን ሥራ!




                                         ማክሰኞ ታህሳስ 16/2005 የምሕረት ዓመት

           ጌታ ለእያንዳንዱ ሰው ሥራ ሰጥቶታል ያንን መሥራት የእርሱ ፈንታ ነው፡፡ ቢቻለው እሱን ማገድ የዲያቢሎስ ሥራ ነው፡፡ በእርግጥ ሥራውን እግዚአብሔር እንደሰጠህ ያህል ሰይጣን ሊያግድህ ይሞክራል ሌላ ነገር በበለጠ ደስ የሚያሰኝ ሊያቀርብልህ ይጥራል፡፡ በዓለማዊ ተስፋዎች ያባብልሃል የሃሜት ጎርፍ ያስወርድብሃል በሐሰተኛ ክስ ያሰቃይሃል ለክብርህ እንድትከላከል ያደርግሃል ደራሲያን እንዲጠይቁህ እጅግ ስመ ጥር ሰዎች በክፉ እንዲናገሩህ ይጠቀምባቸዋል፡፡
           ጲላጦስ፣ ሄሮድስ፣ አናንያ፣ ቀያፋ በአንተ ላይ ያድማሉ ይሁዳም በአጠገብህ ቆሞ በሰላሳ ብር ሊሸጥህ ይከጅላል፡፡ አንተም “ይኸ ሁሉ የመጣብኝ ለምንድን ነው?” በማለት ይደንቅሃል ይኸ ሁሉ የመጣብህ ሰይጣን በዘዴ ከሥራህ ሊስብህና እግዚአብሔርን ከመታዘዝ ሊያሰናክልህ መሆኑን ልትገነዘብ አትችልምን?
           ሥራህን ሥራ አንበሳው ቢያጓራ ፍንክች አትበል፣ የሰይጣንን ውሾች ለመውገር አትቁም፣ ጥንቸሎቹንም  በማባረር ጊዜህን አታጥፋ፣ ሥራህን ሥራ ዋሾቹ ይዋሹ ጠበኞቹ ይጣሉ ማኅበረኞቹ ይወስኑ፣ ደራሲዎቹ ይድረሱ፣ ሰይጣንም የፈለገውን ያድርግ አንተ ግን ምንም ነገር እግዚአብሔር የሰጠህን ሥራ ከመፈፀም እንዳያግድህ ተጠንቀቅ፡፡
           ገንዘብ እንድታተርፍ አልተላክም፣ እንድትበለፅግም አላዘዘህም፣ ሰይጣንና አገልጋዮቹ የሚነዙትን የሐሰት ወሬ እንድታስተባብል አልተጠየክም እነዚህን ሁሉ ነገሮች ብታደርግ ሌላ ሥራ ልትሠራ አትችልም፤ ይህም ብቻ ሳይሆን ለራስህ እንጂ ለጌታ አልሠራህም፡፡
           ሥራህን ሥራ ዓላማህ እንደ ኮከብ የፀና ይሁን፣ ተወው ዓለም እንደፈለገው ይነታረክ ይጨቃጨቅም፡፡ ጥቃት ይደርስብህ፣ ትበደል፣ ትሰደብ፣ ትታማ፣ ትቆስል፣ ትናቅ ይሆናል፡፡ ኃይለኛ ያጎሳቅልህ፣ ወዳጆችህ ይተዉህ፣ ሰዎች ይንቁህ ይሆናል፡፡ አንተ ግን የፀና ውሳኔ በማያወላውል ቅናት በመጨረሻ ላደርገው የሰጠኸኝን ሥራ ፈፀምኩ ለማለት እስክትችል ድረስ የሕይወትህን ዓላማና የተፈጠርክበትን ግብ ተከተል፡፡

Tuesday, December 11, 2012

ሰው አያክፋችሁ (ካለፈው የቀጠለ)



                                               
                                            ማክሰኞ ታህሳስ 2/2005 የምሕረት ዓመት

           ባለፈው ክፍል የአንዳችን እንቅስቃሴ በሌላው ሕይወት ላይ በበጎም ሆነ በክፉ ያለውን ከፍ ያለ ተጽእኖ ለመዳሰስ ሞክረናል፡፡ ሁላችንም ብንሆን በሰው ላይ የምንፈርድበት ብቻ ሳይሆን በእኛም ውስጥ የሚፈረድበት ኑሮ አለን፡፡ ብዙዎች ለራሳቸው እንኳ ደግመው ሊያስቡት ከሚያንገሸግሻቸው ነገር ጋር ይኖራሉ፡፡ እንዲህ ካለው ጠባይና አኗኗር ጋር ተፈጥረው ግን አይደለም፡፡ አብዛኛው ሰው ያከፋው ነው፡፡ ጥላቻን የሚያግቱ፣ ተንኮል የሚያስቀጽሉ፣ ዓመጽ የሚያሰለጥኑ እንደ ምድር አሸዋ በዙሪያችን ናቸው፡፡
           ባል ያከፋቸው ሚስቶች ጥሩ እናት መሆን ሲያቅታቸው፣ አሳዳጊ ያከፋቸው ልጆች ጥሩ ባልንጀራ መሆን ሲሳናቸው፣ ጓደኛ ያከፋቸው ወጣቶች መልካም አባት መሆን ሲቸገሩ፣ ኅብረተሰቡ ያከፋቸው ሰዎች በቅን መምራት ሲተናነቃቸው አስተውለናል፡፡ ክፉ የምንለው ያከፋነውን ነው፡፡ ርኩስ የምንለው ያረከስነውን ነው፡፡ ጠፋ የምንለው ያባረርነውን ነው፡፡ ከሀዲ የምንለው ያስካድነውን ነው፡፡ ጌታ ሆይ ይቅር በለን!
           የሮም ንጉሥ የነበረውን ኔሮን ቄሳር ክርስቲያኖችን እንደ ጧፍ ለኩሶ እንደ ሻማ በማቅለጥ፤ ከአንበሳና ከነብር ጋር በማታገል ይዝናና የነበረ ክፉ መሪ እንደነበር ታሪክ ያስታውሰናል፡፡ ኔሮን ወደ ሥልጣን የመጣበትን መንገድ ስንመለከት፤ እናቱ አግሪፒና በ12 ዓመቷ የ15 ዓመት ዕድሜ በነበረው በኋላም ንጉሥ በሆነው ወንድሟ ካሊጉላ ትደፈራለች፡፡ በ13 ዓመቷ ትዳር መስርታ የልጇ የኔሮን ጥብቅ ወዳጅ ሆናለች፡፡ አግሪፒን አጎቷ የነበረውን ንጉሥ ክላውዴዎስ (ቀዳማዊ) ከማግባቷ በፊት ሁለተኛ ባሏን በመድኃኒት ገድላለች፡፡ ከዚያም ክላውዴዎስን በመርዝ በመግደል ኔሮ ዙፋኑን ወርሶ ወደ ንግሥና እንዲመጣ አድርጋለች፡፡ ጨካኙን ኔሮን ስናስብ እንዴት ባለ ሁኔታ ውስጥ እንዳደገ ልብ ማለት ትምህርት ያተርፍልናል፡፡
        በዓለማችን ላይ ከተነሡ አያሌ ዓመፀኞች ጀርባ ያለው ነገር በኔሮን ቄሳር ካየነው ብዙም የሸሸ አይደለም፡፡ በወላጅ፣ በጓደኛ፣ በወዳጅ፣ በፍቅረኛ ዓላማቸውን የሳቱ፣ ከሕሊናቸው የተጣሉ፣ የሕይወት ታሪካቸው ጥላሸት የተለቀለቀ፣ ራሳቸውን እየፈሩ የሚኖሩ፣ የማንነት መቃወስ የገጠማቸው ከእነርሱ ስህተት በላይ ሰው አክፍቷቸው ነው፡፡
         በአገራችን የገጠሩ ክፍል ዛሬም ድረስ ሙሉ ለሙሉ ጠርቶአል በማይባልበት ሁኔታ ደም የመቃባት ክፉ ውርስ አለ፡፡ ለዚህ መባባስ እንደ አንድ ምክንያት ተደርጎ የሚቀርበው ደግሞ ወገኑ ሞቶበት ደም ያልመለሰ ወንድ እንደ ነውረኛ መቆጠሩና ሚስት ለማግባት እሺታን መነፈጉ ነው፡፡ እንዲህ ባለ ሁኔታ ውስጥ ሰው ሸሽቶ ካልሆነ በቀር አብሮ ሆኖ ሕሊናውን መጠቀም አይችልም፡፡ ባይወድም ይከፋል፡፡ አቅም ባይኖረውም ይሸፍታል፡፡ ታዲያ እድሜ ሰጥቷችሁ ከዓመታት በኋላ ብትገናኙ ያ መልካምነት ሞቶ ተቀብሮአል፡፡ ያ ትህትና አፈር ትቢያ ሆኖአል፡፡ ያ ርኅራሄ ላይመለስ እርቆ ሄዶአል፡፡ ለልቡ ተጠግታችሁ “ምነው? ምን ገጠመህ?” ብትሉት ልክ እንደ ሙሾ አውራጅ እየተንሰቀሰቀ “ሰው አከፋኝ” ይላችኋል፡፡ ሰው አያክፋችሁ!
         ሕይወት ቅብብሎሽ ናት፡፡ አንዱ ትውልድ ሲሄድ ያን ተከትሎ ሌላው ይመጣል፡፡ ታዲያ ይህኛው ሲከፋ ለመጪው ውርስ ሆኖ ይቀራል፡፡ ከዚያም ክፉና ደግ ምርጫ ሳይሆን የውርስ ቅብብሎሽ ይሆናል፡፡ በእርግጥም እውነታው እንዲሁ ነው፡፡ ከማይጠፋው ዘር የተወለዱ ሁሉ የማይጠፋ ነገር ሲቀባበሉ ይኖራሉ፡፡ ያለ ምርጫቸው በሰው ምርጫ፣ ያለ ፍላጎታቸው በሰው ፍላጎት፣ ያለ ውዴታቸው በሰው ግዴታ የኑሮ አቅጣጫቸው የተወሰነ ያላለቀ ነገር (unfinished business) አላቸውና ዛሬም ከብርቱ ፈተና ጋር ናቸው፡፡

መፍትሔ

         እኔ ከሞትኩ . . . አይነት ኑሮ ለምድሪቱ ጭንቅ ነው፡፡ የሆነ ቦታ የሚጨክን ሰው ያስፈልጋል፡፡ ከአያት ከቅድመ አያት የመጣ ነገር ሁሉ ለልጅ ልጅ አይተላለፍም፡፡ እኛ የተጫነንን ሌሎች ላይ መጫን የለብንም፡፡ እኛ የመረረን ሌሎችንም እንዲመራቸው ቸልተኛነት ልናሳይም አይገባም፡፡ የከፉብንን በመክፋት፣ የጠሉንን በመጥላት፣ ያንገላቱንንም በማንገላታት ምድሪቱን በጨለማ ልንለውሳት አይገባም፡፡ እናም እንደ ብርሃን ልጆች በመመላለስ ክፉውን እንዋጋ፡፡ ጸጋ ይብዛላችሁ!  

Tuesday, December 4, 2012

ሰው አያክፋችሁ



                                        ማክሰኞ ሕዳር 25/2005 የምሕረት ዓመት

        በሰው ልጅ ታሪክ ውስጥ ከመልካምነት ይልቅ ክፋት ዓለምን እንደገዛ እናስተውላለን፡፡ አለመታዘዝ ያመጣውን ውድቀት ተከትሎ የሰው ዝንባሌ “የማልወደውን ክፉን ነገር አደርጋለሁና ዳሩ ግን የምወደውን በጎውን ነገር አላደርገውም” (ሮሜ. 7÷19) ወደሚል ሙግት ገብቶአል፡፡ ከመምረጥ ጀምሮ እስከ ድርጊት ድረስ ሰዎች በብርቱ ይፈተናሉ፡፡ አንዳንድ ጊዜም ከነ አካቴው ሁሉን እርግፍ አድርጎ የመተው ውሳኔ ላይ ይደርሳሉ፡፡ ማለትም በጎም መጥፎም ያለመሆንና ያለማድረግ! ሰው ግን ከሁለት አንዱን ነው፡፡ ከእነዚህ ራሱን የሚያገልበት ሌላ ሦስተኛ ክልል የለም፡፡ ልክ እንደ አንድ ቀን ሁለት ገጽታ ብርሃንና ጨለማ ነው፡፡ በብርሃን እንመላለሳለን ወይም በጨለማ እንመላለሳለን፡፡ ክርስትና ግን እንደ ብርሃን ልጆች መመላለስ ነው፡፡ ከክፉ መራቅ ሰላማችንን የሚጸናበት ዋስትና ነው (ኢሳ. 48÷22)፡፡  
         በታሪክ ከተነሡ እጅግ ክፉና አምባገነን መሪዎች መካከል አንዱ ሂትለር ነው፡፡ በየዘመናቱ ብዙ አስጨናቂዎችን ሰዎች ርደውና ተንቀጥቅጠው አስተናግደዋል፡፡ ብዙዎች ሞተው፤ አንዳንዶች ደግሞ አጉል ነዋሪ ሆነው በዚያ አረመኔያዊ ሥርዓት ውስጥ አልፈዋል፡፡ አንዳንዴ ባለፈው የአገራችን ሥርዓት ውስጥ ጨካኝ የነበሩና የገዛ ጎረቤታቸውን በቁም የቀበሩ ሰዎች በዚህኛው ሥርዓት ውስጥ ሲሽቆጠቆጡ ስናያቸው የሥርዓቱ ለውጥ ጭካኔያቸውን እንዳዳፈነው እንጂ እንዳጠፋው አይሰማንም፡፡ የዚያ አምባገነናዊነት ግርሻት ያየለበባቸው ደግሞ ለዚህኛው ሥርዓት ተቆርቋሪ መስለው በዚያኛው አመጽ ይገለጣሉ፡፡ እናም ራሳቸውን ያረካሉ፤ ክፋት ያስገብራልና ዘመን ቢቀያየርም ክፉውን አያስረጀውም፡፡ እግዚአብሔር ግን ይለውጣል!
         ለዚህ ጽሑፍ ርዕስ ያደረኩትን ቃል ያገኘሁት ለልቤ እጅግ ቅርብ ከሆነ አባት (ከአንዱ እግዚአብሔር) ምክር መካከል ነው፡፡ ዘመኑ መካሪም ተመካሪም የሰለቸበት ነው፡፡ ከዚህ ይልቅ ሰው ሁሉ ወደ ልቡ አሳብ ተጠምዷል፡፡ ምን አልባት “ደግሞ በዚህ ዘመን ምን በጎ መካሪ አለ?” ልትሉ ትችላላችሁ፡፡ ነገር ግን ሰው አያስተውልም እንጂ እግዚአብሔር በአንድ በሌላም መንገድ ይመክራል፡፡ አንዳንዴ ሳት ብሏቸው እንኳ ጥሩ እንደማይናገሩ ከምናስባቸው ሰዎች ሕይወት ያለባቸው ቃላት ሲወጡ እናስተውላለን፡፡
         እግዚአብሔር የእስራኤልን ሕዝብ ይረግምለት ዘንድ ባላቅ የከፈለበትን የበልዓም አንደበት መርቆበታል (ዘኁ. 22)፡፡ በእርግጥ ተደላድለን ውሸት ከምንናገር እግዚአብሔር ጠምዝዞን ለእውነት ብንመሰክር ይበልጣል፡፡ በየአደባባዩ የሚጠፋውን መብል እያሰቡ፣ ሕሊናቸውን አራቁተው ሆዳቸውን እየሞሉ በዚህ ዓለም ከንቱ መለፍለፍ የተጠመዱ ሁሉ ከበለዓም ስሕተት (ይሁዳ 11) ሊማሩ ያስፈልጋቸዋል፡፡   
        የስነ ልቦና ባለሙያዎች እንደሚያስረዱት ልጆች እያለን ከቤተሰቦቻችና ከማኅበረሰቡ ጋር የነበረን ግንኙነት (Attachment) ወደ ማወቅ ደረጃ ከመጣን በኋላ በቀጣይ ኑሮአችን ላይ ከፍተኛ ተጽእኖ (በጥሩም በመጥፎም) ያሳድራል፡፡ የአንድ ሰው ክፋት የብቻው ክፋት፣ የአንድ ሰው መልካምነት የብቻው መልካምነት አይደለም የሚል መከራከሪያ የሚቀርበውም ለዚህ ነው፡፡ አብዛኛውን ጊዜ የምንመለከተው ወንጀል ተባባሪና አሰልጣኝ ያለው ነው፡፡ በጣም ጨዋ እንደነበሩ የምናውቃቸውን አልባሌ ቦታ ስናገኛቸው አድራሻ ለመለወጥ ያበቃቸው ክፉ ባልንጀርነት እንደሆነ እናያለን፡፡  
        ሰውና ሁኔታ ያከፋው ካልሆነ በስተቀር ማንም ክፉ ሆኖ የተፈጠረ የለም፡፡ ወድጄ መሰለህ እንዲህ ያለ ጠባይ የያዝኩት፣ አመል ያወጣሁት በማለት የሚናገሩ ወገኖች ብዙ ናቸው፡፡ ማንም በጥረት የተበላሸ የለም፡፡ አንዳንዱ እንጀራ በልቶ ለማደር፣ ሌላው ከሰው ተመሳስሎ ለመኖር፣ አንዳንዱ የእጁን ላለማጣት ብቻ ሁሉም ለከፋበት ምክንያት ያቀርባል (ምንም እንኳ ምክንያት ባይታደግም ግን እኮ ከፀሐይ በታች ባለው ኑሮ ምክንያተኝነት ስልጣኔ ነው እንጃ እንግዲህ አንዱን ምረጡ)፡፡    
      በጭካኔውና በአረመኔነቱ ከምናውቀው ሂትለር ጀርባ ያለውን ታሪክ በአጭሩ ለመመልከት ብንሞክር፤ እናቱ ክላራ ከእርሷ በ23 ዓመት እድሜ ለሚበልጣት ለአጎቷ የልጅ ልጅ ሦስተኛ ሚስት የነበረች ስትሆን በትዳር በቆየችባቸው ጊዜያት ሁሉ ባለቤትዋን ትጠራው የነበረው “አጎቴ” እያለች ነበር፡፡ ግንኙነታቸው የተጀመረውም በአጎቷ ቤት በቤት ሠራተኛነት ታገለግል በነበረበት ጊዜ ነው፡፡ ታዲያ ሂትለር ልጅ እያለ እናቱ ክላራ ብቸኛ ጓደኛው ነበረች፡፡
         አስራ ስምንት ዓመት ሲሞላው እናቱ በካንሰር ሞተችበት፡፡ በዚህም ምክንያት ለከፍተኛ የልብ ስብራትና ለበለጠ ብቸኝነት ተጋለጠ፡፡ አንዳንድ የታሪክ ምሁራን እንደሚያስረዱት ሂትለር በሴሜቲኮች በተለይም በአይሁዶች ላይ ጥላቻና የበቀል ስሜት ያደረበት የሚወዳት እናቱ አይሁዳዊ በሆነ ዶክተር የተደረገላት ሕክምና ውጤት አልባ በመሆኑ ነው፡፡ እንግዲህ በግፍና በሰው ሰቆቃ ራሱን ያረካ የነበረው አዶልፍ ሂትለር ወደዚህ የክፋት ጣሪያ የደረሰው በዚህ መንገድ ነው፡፡ እናንተስ እንዴት ታዩታላችሁ?
                መልካም የምንሆነው ለራሳችን ብቻ ብለን አይደለም፡፡ ሌሎችንም ከእሳት ነጥቆ ለማውጣት እውነተኛ መንገድ ስለሆነ ጭምር ነው፡፡ በጎ ነገር ዘር ነው፡፡ ዘር ደግሞ ከተዘራ በኋላ እንደ ዘራነው ልክ አይሆንም፡፡ ስለዚህ በጎነታችንም ሆነ ክፋታችን መሐን ሊሆን አይችልም፡፡ በጎ የዘራችሁ ደስ ይበላችሁ!
                                                          - ይቀጥላል -

Tuesday, November 6, 2012

የማታውቂው ባዶ



                                         ማክሰኞ ጥቅምት 27/2005 የምሕረት ዓመት


          ባል ከሚስቱ የሚደብቃት ምንም ነገር የለም፡፡ አሳቡን የምታስብ፣ የልብ ምቱን የምትመታ፣ ንግግሩን የምታወራ እስክትመስል የገንዘብ ብቻ ሳይሆን የኑሮ ወጪና ገቢውንም ታውቃለች፡፡ ነገር ግን ሚስትን ጨምሮ ማንም የማያየው ቁልፉም በእርሱ እጅ ብቻ የሆነ አንድ መሳቢያ አለው፡፡ ሚስት እንዲያሳያት የጠየቀችው ቢሆንም እምቢታው ግን አላስቻላትም፡፡ ብዙ ጊዜ ክልከላውን ብታከብርለትም አንዳንዴ ግን አክርራ ትጠይቀዋለች፡፡ ታዲያ አንድ ቀን የመሳቢያውን ቁልፍ ረስቶ ከቤት ይወጣል፡፡ ሚስትም የዘወትር ትጋቷ ምላሽ ያገኝና ከኮቱ ኪስ ቁልፉን ወስዳ መሳቢያውን ታየዋለች፡፡
          ባል ከሥራ መልስ ወደ ቤት ሲመጣ ሚስት ፊቷ ፍም እስኪመስል ታለቅሳለች፡፡ የተደናገጠው ባል ምክንያቷ ምን እንደሆነ ቢጠይቃት “ለባዶ መሳቢያ ይህንን ያህል ጊዜ ያስለመንከኝ ለምንድነው?” የሚል መጠይቃዊ ምላሽ ያገኛል፡፡ ባልም ትህትና በተሞላበት አነጋገር “የማታውቂው ባዶ እንኳ ይኑረኝ ብዬ ነው” አላት፡፡    
         ድብቅነት አንዱ የኑሮ መስፈርት እየሆነ መጥቶአል፡፡ ለዚህም እንደ ምክንያት የሚቀመጡት ማሳመኛዎች ብዙ ናቸው፡፡ አብዛኞቹ ድብቅነት አያስፈልግም! የሚል አቋም ሲኖራቸው እንደ መከራከሪያ የሚያቀርቡትም አሳብ ደግሞ “ድብቅነት ሕይወትን ከባድና ውስብስብ ያደርጋታል” የሚል ይሰኛል፡፡ አንዳንዶች ደግሞ እንደ አስፈላጊነቱ ድብቅነት መኖር አለበት ባይ ናቸው፡፡ እንደ መከራከሪያነት ከሚያቀርቡት ምሳሌ መካከል ሰይጣንን ያጣቅሳሉ! ምክንያቱም ውድቀቱ የእግዚአብሔርን መደበቅ ተከትሎ የመጣ ነው፡፡ ስለዚህ ቢያንስ ሰውን ለመፈተንና በጎውን አቅርቦ ክፉውን ለማራቅ የምንሸሽገው ባዶ እንኳ ያስፈልገናል የሚል ነው፡፡ ሌሎች ደግሞ “ድብቅነት ምን ጊዜም አስፈላጊ ነው” የሚል አመለካከት ያላቸው ናቸው፡፡ እነዚህ “በተኩላ ዓለም በግ መሆን ለእራስ በገዛ እጅ መቃብር መቆፈር ነው” የሚሉ አሉታውያን (ጠርጥር) ናቸው፡፡ እናንተስ?   
          እውቀት በሰው ልጅ ታሪክ ውስጥ ቋሚ ጥማት ነው፡፡ የሚሰወረን ነገር ባይኖር የሁላችንም መሻት ነው፡፡ ስለ ሰው ማወቅ ብቻ ሳይሆን የሰውንም ማወቅ እንፈልጋለን፡፡ ድብቆች ብንሆንም ከሰው የተገላለጠ ነገር እንጠብቃለን፡፡ ነገር ግን ተግባራዊ በሆነ መንገድ የአብሮነት ኑሮአችን የተያያዘበት ሰንሰለት ብዙ መሰብሰብ ጥቂት መገለጥ ነው፡፡ በአካባቢያችሁ ያሉ ሰዎች “ምነው ሰሞኑን በዛህ/ሽ?” ብለዋችሁ አያውቁም? ይህ በሌላ መንገድ “አይኔ ሰልችቶሃል” ማለት ነው፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞን እንዲህ ስላለው ሁኔታ “እንዳይሰለችህ እንዳይጠላህም እግርህን ወደ ባልንጀራህ ቤት አታዘውትር” (ምሳ. 25÷17) በማለት ምክሩን ይለግሰናል፡፡
          በሰው ታሪክ ውስጥ አንዱ ለሌላው ግልጽ አለመሆንና ነገሮችን መሸሸግ ውድቀትን ተከትሎ ወዲያው በዔደን ገነት ውስጥ የተስተዋለ ሐቅ ነው፡፡ የአዳምና ሔዋን መተፋፈር አንዳቸው ለሌላቸው እንዳይገለጡ አደረጋቸው፡፡ ደግሞም እግዚአብሔርን ተጠያቂ ወደ ማድረግ የመራቸውንም ምክንያት ስንመረምረው የጋራ መወያየት የታየበት ሳይሆን የየግል ልብ ወለድ እንደሆነ እናስተውላለን(ዘፍ. 3)፡፡ አዳም ለመብላት የሚስቱን ቃል ቢሰማም ለመፍትሔ ግን አልሰማትም፡፡ ሔዋንም ለማብላት ቃላትን ለአዳም ብትናገርም ለመፍትሔ ግን አላናገረችውም፡፡ ይህንን ተከትሎ ነው እንግዲህ ቃየን አቤልን ተደብቆ የገደለው፡፡ እንዲህ ያለው የድብቅነት ዝንባሌ እኛም ጋር የደረሰው በቅብብሎሽ ነው፡፡   
          ሰው የቱንም ያህል ድብቅ ቢሆን ከሰው የሚያስቀረው እንጂ ከእግዚአብሔር የሚሰወረው ነገር የለም፡፡ አይኖቹ እንደ እሳት ነበልባል በሆኑት ጌታ ፊት ሁሉ የተራቆተ ነው፡፡ እግዚአብሔር የማያውቀው ድርጊት ቀርቶ የማያውቀው ባዶ እንኳ የለንም፡፡ ውድ የቤተ ፍቅር ብሎግ ተከታታዮች በዚህ ርዕሰ ጉዳይ ላይ በተረዳችሁበት መንገድ ያላችሁን አሳብ እንድትገልፁና ለውይይት እንድትሳተፉ በትህትና እንጋብዛለን፡፡

Tuesday, October 30, 2012

መልከኞቹ (ማጠቃለያ)



               ማክሰኞ ጥቅምት 20/2005 የምሕረት ዓመት

6. የማያመሰግኑ፡ - እግዚአብሔርን አለማማረር ብቻ ሳይሆን ማመስገን አለመቻልም ኃጢአት ነው፡፡ በደሙ ዋጋ የገዛንን ጌታ ተመስገን ማለት ዋጋው ብዙ ነው፡፡ ሌሎች የሰጡን ቁሳዊ እርሱ ግን የሰጠን መንፈሳዊ በረከት ነው፡፡ ሰዎች ስለ እኛ ገንዘባቸውን፣ ጊዜያቸውን፣ አሳባቸውን ሰጥተው ይሆናል፡፡ እርሱ ግን ነፍሱን ስለ እኛ አኑሯል (ዮሐ. 15÷13)፡፡ በሰዎች ዘንድ ስለተደረገልን ነገር የምንሰጠው የምስጋና ምላሽ “ኪስ አይገባም” በሚል ማራከሻ ይጣጣል ይሆናል፡፡ እግዚአብሔር ግን ምስጋናችንን የመሥዋዕት ያህል በፊቱ ልክ እንደተወደደ መዓዛ ይቀበለዋል (ዕብ. 13÷15)፡፡  
         በአስተሳሰብ ብስለት ውስጥ ባሉ ሰዎች መካከል ምስጋና የመልካም ሰብእና አንዱ መለኪያ ነው፡፡ ተቀብሎ ያላመሰገነ እንደ ቀማኛ ይቆጠራል፡፡ ምስጋና ሰጭውን ለበለጠ ልግስና ሲጋብዝ አመስጋኙን ደግሞ ከቁራሽ ላይ የሚቆርስ አዛኝ ያደርገዋል፡፡ በመንፈሳዊ ሕይወትም አመስጋኝነት ከእግዚአብሔር ጋር ያለንን ግንኙነት የሚያሳይ ልኬት ነው፡፡ እንደውም የምትቀበለው በአመሰገንከው ልክ ነው የሚባል አባባል አለ፡፡ በእርግጥም ምስጋና ሰብእናችንን የምናስውብበት ጥሩ መዋቢያ ነው፡፡
        ዙሪያችንን ስንቃኘው ሰዎች ከምስጋና ቃል ይልቅ በብዙ የምሬት ንግግር የተሞሉ ናቸው፡፡ በቤት በአደባባይ፣ በጉዞ በመንደር የምንሰማው ሁሉ ከመዓት ቀጥሎ ያለ ሌላ መዓት ነው፡፡ አንዳንዴ በአፋችን እንደተናገርነው እንደዚያው እየተደረገብን እንደሆነ አስባለሁ፡፡ በየዕለቱ ለእግዚአብሔር ከምናቀርበው ውዳሴ በላይ ወቀሳችን የበዛ ነው፡፡ ኢዮብ ሁሉን አጥቶ “ይባረክ” (ኢዮ. 1÷21) ያለውን እግዚአብሔር እኛ ባናመሰግነው ያ ሁኔታ ምን ያህል ይወቅሰናል?
         ተወዳጆች ሆይ ምስጋና ጥቂቱን ብዙ የሚያደርግ ኃይል ነው፡፡ በሆነው ብቻ ሳይሆን ባልሆነውም፣ በተቀበላችሁት ብቻ ሳይሆን ምላሽ በዘገየባችሁ ነገር፣ አለኝ በምትሉት ብቻ ሳይሆን ነበረኝ በሆነባችሁም ነገር ሁሉ ጌታን አመስግኑ፡፡
7. ዕርቅን የማይሰሙ፡ - እንደዚህ ዘመን ሰው ከራሱ ጋር የተጣላበት ጊዜ ያለ አይመስልም፡፡ ሁሉም ራሱን እያስታመመ፣ እያባበለ፣ ለማስተራረቅ እየሞከረ ነው፡፡ ነገር ግን ከራሳችን ፀብ ጋር ለመታረቅ እንኳ የእግዚአብሔር መሐል መግባት ያስፈልገናል፡፡ ሁሉ ቢጣላ ኖሮ ማን ያስታርቅ ነበር? ብላችሁ አስባችሁ ታውቃላችሁ? የእግዚአብሔር ቃል “የሚያስተራርቁ ብፁዓን ናቸው የእግዚአብሔር ልጆች ይባላሉና” (ማቴ. 5÷9) ይላል፡፡
         የእግዚአብሔር ልጅ በመሆን ውስጥ ካሉት ትልልቅ ደስታዎች አንዱ ማስታረቅ ነው፡፡ ዛሬ መለያየትን ወደ አንድነት ለማምጣት፣ ጠላትነትን ወደ ወዳጅነት ለመቀየር የሚጠይቀው ድካም ቀላል የሚባል አይደለም፡፡ እስከ ዛሬ ድረስ ለስንት ዓመታት የሚሸመገሉ ሰዎች አሉ፡፡ እንዲህ ያለው ውኃ ቅዳ ውኃ መልስ የሃይማኖት ሰዎች የሚባሉትን ሳይቀር ይጠቀልላል፡፡ አንዳንዴ ምን አለ የጊዜውን ርዝማኔ እንኳ አክብረው ቢታረቁ ያሰኛል፡፡ እግዚአብሔር እንደ መፍትሔ አስቀምጦን እንደ ችግር ኖሮ ከማለፍ ይጠብቀን፡፡
          አንዳንዶች ለበቀል የእኔ የሚሉትን አንድ ቀን በመጠባበቅ ላይ ናቸው፡፡ ሌሎች ደግሞ ቀኑን በሙሉ በደፈጣ ያሳልፋሉ፡፡ ብዙ ሊታረቅልን የሚገባ ነገር ያለን ሰዎች ነን፡፡ እንግዲህ እርቅን አለመስማት በፀብ እንደጸኑ መቀጠል ነውና ጌታ ከሚያስተራርቁት ወገን ያድርገን፡፡
8. መልካሙን የማይወዱ፡ - መልካም አለማድረግ ምርጫ ነው፡፡ መልካሙን መቃወም ግን ከዚህ ይከፋል፡፡ በመልካምነት ላይ ውጊያ የተጀመረው ምድር ላይ አይደለም፡፡ ገና ከስነ ፍጥረት ጅማሬ አንሥቶ በሰማይ የፈነዳ አብዮት ነው፡፡ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ መልካምነትና መልካሞች ሲሰደዱ ኖረዋል እየኖሩም ነው፡፡ በዚህም ዓለም እየሆነ ያለው ይኼው ነው፡፡ መልካም የምንሆነው ጠላት ላለማፍራት አይደለም፡፡ ምርጫችን ስለ ሆነ ግን መልካም እንሆናለን፡፡ ሰው በምርጫው ደጉን ብቻ ሳይሆን ክፉውንም ያስተናግዳል፡፡ እናም ጽኑ!
         መልከኛው ክርስትና ከተገለጠባቸው ጠባያት ትልቁ ይህ ይመስለኛል፡፡ የመልካም ጥግ እግዚአብሔር ነው፡፡ ሰው የቱንም ያህል መልካም ቢሆን እግዚአብሔርን አልፎ መልካም አይሆንም፡፡ ታዲያ እንዲህ ያለውን ጌታ በመልካምነት ኃይል ሳይሆን በመልካምነት መልክ (በውስጠ ምስጢር ክፉ) ለማክበር መሞከር ምን ያህል ድፍረት ነው፡፡ ሰዎች አህዛብ ጋር ያገኙትን መልካምነት እኛ ጋር መጥተው ካጡት “ታዲያ ምን ብልጫ ታደርጋላችሁ” (ማቴ. 5÷46) የተባለው ለዚህም አይደል?
9. ከእግዚአብሔር ይልቅ ተድላን መውደድ፡ - እግዚአብሔርን የምንወድበት መንገድ የሥጋ ወላጆቻችንን እንኳ ከምንወድበት ፍቅር  ይለያል፡፡ እነርሱን በሥጋ ልደት ይህንን ዓለም እንድንቀላቀል መንገድ ስለሆኑን እንወዳቸዋለን፡፡ እርሱን ደግሞ በመልኩ እንደ ምሳሌው ስለ ፈጠረን በሰውም መካከል ሰው ሆነን እንድንገኝ ስለ ፈቀደ እንወደዋለን፡፡ ከዚህ ሁሉ በላይ በውድ ልጁ ከዘላለም ሞት ስላዳነን እንወደዋለን፡፡ በዚህም ዓለም በሚኖረን የእግረ መንገድ ቆይታ በእያንዳንዱ የሕይወት ክፍላችን ውስጥ የምናገኛቸውን ሰዎች (ትዳርንም ጨምሮ) እንወዳቸዋለን፡፡ ዳሩ ግን የእግዚአብሔርን የመወደድ ስፍራ ማንም ሊይዘው አይገባም፡፡  
        በዚህ ክፍል ላይ ሐዋርያው የሚወቅሳቸው ሰዎች እግዚአብሔርን በዚህ ዓለም ተድላ የለወጡ ናቸው፡፡ ዴማስ የአሁኑን ዓለም ተድላና ደስታ ወዶ ከእውነት እንዴት ፈቀቅ እንዳለ እናውቃለን (2ጢሞ. 4÷10)፡፡ በዘመናችንም ሰዎች ተድላንና እንደ ዓለም የሆነውን ደስታ ዋጋ ከፍለው እየወደዱ ነው፡፡ የእግዚአብሔርንም ነገር እንዲህ ባለው መንገድ ለመሸፈን እየተሞከረ ነው፡፡ ያንን የቀራንዮ ደስታ ግን የትኛውም የዚህ ዓለም ከንቱ ነገር ሊጋርደው አይችልም፡፡ ጌታን የጋረደብን ማንኛውም ተድላና ደስታ ቢኖር ግን በስሙ ሥልጣን እንዲወገድም መጸለይ ይኖርብናል፡፡   
         እግዚአብሔር ከየትኛውም ነገራችን በላይ እንድንወደው ይጠይቀናል (ዮሐ. 21÷15)፡፡ እርሱ በእኩል ፍቅር ከሌሎች ጋር የምንወደውና የምናመልከው አምላክ አይደለም፡፡ ነፍስን እስከ መስጠት ደግሞም እስከ መስቀል ሞት ታዝዞ የወደደንን ጌታ በሚበልጥ ፍቅር እንድንወደው ጸጋ ይብዛልን፡፡
መፍትሔ፡ - በአብዛኛው የአምልኮት መልክ አላቸው ኃይሉን ግን ክደዋል ተብሎ ስለ ተነገረባቸው የአፍ አማኞች ጠባይ ለመዘርዘር ሞክረናል፡፡ አሁን ደግሞ ቅዱስ ጳውሎስ ለእውነተኛ ምዕመናን ያስቀመጠውን መፍትሔ እናያለን፡፡
ሀ. ቃሉ፡ - የእግዚአብሔር ቃል ጥሩ መንሽ ነው፡፡ እውነቱን ከሐሰት፣ ቅዱሱን ከርኩሰት፣ ጽድቁን ከኃጢአት አጥርተን እንድንለይ ይረዳናል፡፡ አብዛኛውን ጊዜ መደናገርና ለስሕተት አሠራር መመቸት የሚመጣው ቃሉን በሙላት ባለመረዳት ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ መፍትሔው ቃሉን ዕለት ዕለት መመርመር ነው (ሐዋ. 17÷10)፡፡ ይህ ከሆነ ኃይለኛ እንጂ መልከኛ በሆነ አምልኮ ውስጥ አንወድቅም፡፡
ለ. እውነቱን መከተል፡ - ሰዎች እውነትን መረዳት ብቻ ሳይሆን የተረዱትንም እውነት መከተል ይቸግራቸዋል፡፡ ጌታ የሚወደኝ ቢኖር ይከተለኝ ሲል በእውነተኛነቴ የተስማማ ቢኖር ይከተለኝ ማለቱ ነው፡፡ ለተረዳነው የእግዚአብሔር ቃል ምላሽ የምንሰጠው እውነቱን በመከተልና በቃል ብቻ ሳይሆን በሥራ ላይም በማዋል ነው፡፡
ሐ. መራቅ፡ - መራቅን በትንሹ በሁለት መንገድ ልናየው እንችላለን፡፡ የልብና የአካል በሚል! ሁለቱም ችግሩ በሚጠይቀው መጠን አስፈላጊ ናቸው፡፡ “የጌታን ስም የሚጠራ ሁሉ ከዓመፅ ይራቅ” (2ጢሞ. 2÷19) የሚለው ማኅተም ያለበት የተደላደለ የእግዚአብሔር መሠረት እስካለ ድረስ ክርስትናን በእውነተኛ ኑሮ መግለጥ ለሚፈልጉ ሁሉ ጠንካራ ትዕዛዝ ነው፡፡ ክፉ ባልንጀርነት መልካሙን የክርስትና ኑሮአችንን የሚያጠፋው ከሆነ ጊዜ መስጠት ለቀብር መሰናዳት ነው፡፡ ማስተዋል ይብዛላችሁ!
            

Tuesday, October 23, 2012

መልከኞቹ (ካለፈው የቀጠለ)

                                                    ማክሰኞ ጥቅምት 13/2005 የምሕረት ዓመት 

“እግዚአብሔርን እንዲያውቁ በግልጥ ይናገራሉ፡፡ ዳሩ ግን የሚያስጸይፉና የማይታዘዙ ለበጎ ሥራም ሁሉ የማይበቁ ስለ ሆኑ በሥራቸው ይክዱታል” (ቲቶ. 1÷17)፡፡
          ባለፈው ንባብ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የእምነት ልጁ ለሚሆን ጢሞቴዎስ የአምልኮት መልክ ካላቸው ነገር ግን ኃይሉን ከካዱት ሰዎች እንዲርቅ የመከረበትን ክፍል መነሻ አድርገን መንፈስ ቅዱስ ለልባችን ያለውን የልቡን ምክር ለማየት ሞክረናል፡፡ እንደ ተናገሩ አለመኖርና ያመኑበትን በተግባር ምስክርነት አለማጽናት የክርስትናው ፈተና ብቻ አይደለም፡፡ አላመኑም ብለን በምንፈርጃቸው ከክርስትናው ጥሪ ተካፋይ ባልሆኑ ወገኖች ዘንድም ብርቱ ችግር ነው፡፡ ማኅበራዊ ኑሮአችን ላይም መራርነት የሚሞጅርበት እንዲህ ያለው ነገር ነው፡፡ በንግግራቸው ውስጥ መስማማት ያስተዋልንባቸው ሰዎች በተግባር ግን ሲጣሉ ተመልክተናል፡፡ ምክንያቱም በተግባር መገለጥ በቃል ከማብራራት በብዙ ከፍ ያለ ስለ ሆነ ነው፡፡
          ከእግዚአብሔር ጋር ባለን ግንኙነት ቀርቶ ሰው ከሰው በሚኖረው አብሮነት ውስጥ እንኳን መልከኛ እንጂ ኃይለኛ (የተግባር ሰው) አለመሆን ጉዳቱ የከፋ ነው፡፡ ብዙ ቤተሰባዊነት፣ ጓደኝነት፣ ወዳጅነት፣ ትዳርና ማኅበራዊነት በመልከኝነት በሽታ የተጠቁ ናቸው፡፡ ለዚህ ምክንያቱ ደግሞ ልክ በጢሞቴዎስ ዙሪያ እንደነበረው ሁሉ የሐሰተኞች ትምህርት መበራከት ነው፡፡ ሐዋርያው ይህንን መልእክት እንዲልክ ግድ ያለው በጊዜው የነበሩ የስህተት አስተማሪዎች ምእመናኑ ክርስትናን በኃይሉ (በትንሣኤው) ከመኖር ይልቅ በመልኩ (ማስመሰል) ወደ መኖር ዝቅታ እንዲመለሱ ተጽእኖ ያደርጉ ስለነበር ነው፡፡
          እንደ እውነተኛ የእግዚአብሔር አገልጋይ ሐዋርያው ያሳይ የነበረው ትጋት በእጅጉ የተገባ ነበር፡፡ በእውነት ላይ ከፍ ከፍ የሚል የትኛውንም የስህተት ትምህርትና የሥጋ ትምክህት በእግዚአብሔር አሳብ መቃወም ቅዱስ ተጋድሎ ነው፡፡ በመጨረሻው ቀን የሚያስጨንቅ ዘመን እንዲመጣ ይህንን እወቅ የሚለው አሳብ የእግዚአብሔር ሰዎች እያንዳንዱን ዘመን መዋጀት እንዳለባቸው የሚያነቃቃ ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ የአምልኮት መልክ እንዳላቸው ነገር ግን ኃይሉን እንደካዱ የሚነግረን ሃይማኖተኞች ጠባይ በጥቂቱ ሲቃኝ፡ -  
1. ራስ ወዳድነት፡ - መወደድና መውደድ በሰው ታሪክ ውስጥ ቋሚ ተግባር ነው፡፡ የማኅበራዊነት ማጣፈጫው ቅመምም ይህ በፍቅር ላይ የተመሰረተ ግንኙነት ነው፡፡ አብዛኛውን ጊዜ ራስ ወዳድነት አሉታዊ ጎኑ ብቻ ሲጠቀስ እናስተውላለን፡፡ ነገር ግን ራስን መውደድ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተነቀፈው ባልንጀራችንን በዚያው ልክ ካልወደድን ነው (ማር. 12÷31)፡፡ ከዚህም ባለፈ ሰው ራሱን ካልወደደ ከክፉ እንዴት መራቅ ይችላል?
             ክርስትና በክርስቶስ ወንድማማቾች የሆኑ ልዩ ልዩ ወገኖች ሕብረት ነው፡፡ በዚህ ውስጥ ደግሞ የተወሰደብን መብት አለ፡፡ ያውም እውነተኛ ክርስቲያን የሆነ አንድ ሰውን “ወንድሜ አይደለህም” ማለት አለመቻል ነው፡፡ በሥጋ ከአባችን የተወለደ ወንድማችንን ወንድሜ አይደለህም ማለት በሕግም በሕሊናም አግባብ እንደማይሆነው ማለት ነው፡፡ ራስ ወዳድነት እኛን በምንወድድበት ልክ ሌላውን መውደድ አለመቻል፣ እኛን የሚያስፈልገን ነገር ሌላውንም እንደሚያስፈልገው አለማሰብ ነው፡፡
2. ገንዘብን ወዳድነት፡ - በእግዚአብሔር ቃል ውስጥ የክፋት ሁሉ ስር የሚለውን ስፍራ የያዘው ገንዘብን መውደድ ነው (1 ጢሞ. 6÷10)፡፡ ጌታ በትምህርቱ አንድ ሰው ለሁለት ጌቶች መገዛት እንደማይችልና ወይ አንዱን መውደድና ሌላውን መጥላት አልያም አንዱን ንቆ ሌላውን መጠጋት እንዳለበት አስረድቶአል (ማቴ. 6÷24)፡፡ ስለዚህም ለእግዚአብሔርና ለገንዘብ መገዛት አትችሉም! በማለት ይደመድማል፡፡ ብዙዎቻችን ከእግዚአብሔር ሌላ የዚህ ዓለም ገዥ የሆነውን ዲያብሎስ ብቻ ነው የምናውቀው፡፡ ዳሩ ግን ቃሉ ገንዘብንም እንደ ሌላ ጌታ ያቀርብልናል፡፡ ጌታ የምንገዛለት አካል ነው፡፡ ገዢ ደግሞ በሙሉ ነገራችን ላይ አዛዥ ነው፡፡
            ለአንድ ክርስቲያን ገንዘብ በአግባቡ ጥቅም ላይ የሚያውለው ምድራዊ ነገር ነው፡፡ የሚያስተዳድረው እንጂ የሚተዳደርለት፣ የሚገዛው እንጂ የሚገዛለት ሊሆን ግን አይገባም፡፡ ገንዘባቸው የሚመራቸውን ሰዎች ማሰብ የምድሪቱን መከራ የማሰብ ያህል ነው፡፡ በምድራችን ላይ ከሚሠራው ከየትኛውም አመጽ ጀርባ ያለው ደጀን ገንዘብ ስለሆነ፡፡ (መልካሙን ለማድረግ የሚተጉ እንዳሉ ሆነው) ገንዘብን መውደድ የሚለው አሳብ ገንዘብን ወደ መጥላት መፍትሔ ባያደርሰንም የክፋት ስር የሚሆንበትን ሁኔታ በማስተዋል የሕይወታችንን ጌታ በገንዘባችንም ላይ ጌታ እንድናደርገው ያስገነዝበናል፡፡  
3. ትምክህትና ትዕቢት፡ - ባላቸው ነገር የሚመኩ ሰዎች እንደ አገልጋይ ያሳዝኑናል፡፡ ምክንያቱም ዓለምና ሞላዋ የእነርሱ ብትሆን እንኳ አንድ ቀን (በእግዚአብሔር የትግበራ ጊዜ) እንደ መጎናፀፊያ ልትጠቀለል የተፈረደባት በመሆኑ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ቃል እንኳን ኃጢአት የሆነውን የዚህ ዓለም ነገር ቀርቶ ጽድቃችን የምንለውን የእኛን ትምክህት የዘጋው የመርገም ጨርቅ ብሎ ነው፡፡ ሰው ይመካ ዘንድ ለሰው የተተወ አንዳች ነገር በእግዚአብሔር ዘንድ የለም፡፡ እግዚአብሔር የማንም ባለ ዕዳ ስላይደለ የሚመካ ቢኖር በእግዚአብሔር ይመካ!
            በየዘመናቱ የእግዚአብሔር ቅጣት ፍጥነትና ኃይል ከተገለጠባቸው ነገሮች አንዱ ትዕቢት ነው፡፡ አብዛኛውን ጊዜ ትምክህትና ትዕቢት ልክ እንደ ጨው ይዋዋሳሉ፡፡ የብዙ ጎበዞች ውድቀት መጀመሪያው ትዕቢት ነው፡፡ ትዕቢት ሌላውን አሳንሶ ራስን ኮፍሶ መኖር ነው፡፡ ታዲያ የእግዚአብሔር ክንድ በየጊዜው እንዲህ ያለውን ክምር ሲንድ ነው የኖረው፡፡ ትዕቢት ራስን ላለመግዛት ትልቅ አርነት ነው፡፡ በክርስቶስ ኢየሱስ የነበረውን አሳብ ልብ ካልነው “ትህትና” የሚል ነው (ፊል. 2÷5)፡፡ ትዕቢት የእግዚአብሔር ልጅ ራሱን ባዶ ባደረገበት በዚህ አሳብ ፊት እንዴት የሚብስ ቅጣት ይቀበል ዘንድ ይገባዋል?   
4. ሐሜትና ስድብ፡ - “ለቀብር የሄዱ ሰዎች አስከሬን ቀርቶባቸው “በሕይወትም እያለ አርፋጅ ነበር፡፡ ዛሬ እንኳ ምናለ በሰዓቱ ቢገኝ?” እየተባባሉ ያሙታል፡፡ ታዲያ ገና ሳይጨርሱ በለቀስኛ ታጅቦ ይደርሳል፡፡ እነዚያው ያሙት ሰዎች “ውይ እድሜው ረጅም ነው፡፡ ስናነሳው መጣ” ተባብለው በውሸት እንባ እውነተኞቹን ተቀላቀሉ፡፡” የሚል ታሪክ ባልንጀራዬ አጫውቶኛል፡፡ የሞተን ሰው እድሜው ረጅም ነው! ያሰኛቸው የሐሜት አመል ነው፡፡ ለብዙዎች ሐሜትና ስድብ ፈቃድ ያላቸው ኃጢአቶች እንደሆኑ ይሰማቸዋል፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር በዚህ ላይ ምንም አይነት ቅራኔ እንደሌለው ስለሚያስቡ ነው፡፡
            አሉ አሉ! የብዙ ሰዎችን ኑሮና ትዳር አናግቷል፡፡ ቡና አፍልተው ማማትም ማሳማትም የማለዳ ተግባራቸው የሆነ ሰዎችንም እናውቃለን፡፡ እድሜው ይጠር እያሉ ተብዬው ሲደርስ እድሜህ ረጅም ነው የሚሉ ሸንጋዮች ብዙ ናቸው፡፡ ስድብንም ስናይ ከሰዎች ክፉ ንግግር ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ሁለቱም በአፍ መበደል ናቸው፡፡ የእግዚአብሔር ቃል ስለ ስድብ ብርቱ ትምህርትን ይሰጠናል፡፡ “የመላእክት አለቃ ሚካኤል ግን ከዲያቢሎስ ጋር በተከራከረ ጊዜ ስለ ሙሴ ሥጋ ሲከራከር፡- ጌታ ይገሥጽህ አለው እንጂ የስድብን ፍርድ ሊናገረው አልደፈረም” (ይሁዳ 9) ተብሎ ተጽፏል፡፡ እውነተኛ አማኝ ለአፉ ጠባቂ አለው፡፡     
5. አለመታዘዝ፡ - መታዘዝ ከመሥዋዕት እግዚአብሐርን ማዳመጥም የአውራ በግ ስብ ከማቅረብ ይበልጣል (1 ሳሙ. 15÷22)፡፡  ቅዱስ ጳውሎስ መታዘዝን እዚህ ቦታ ላይ ያቀረበው ከወላጆች ጋር በማያያዝ ነው፡፡ ቃሉ እግዚአብሔር የሕፃንነታችን ወዳጅ እንደሆነ ቢናገርም ተግባራዊ በሆነ ሁኔታ እኛ ከእግዚአብሔር ጋር ሕብረት ከማድረጋችን በፊት ከወላጆቻችን ጋር ያለን ግንኙነት ይቀድማል፡፡ መንፈሳዊውን ልደት (ዳግም መወለድ) የሥጋ ልደት ይቀድመዋልና፡፡ ለወላጆች መታዘዝ አምላካዊ መመሪያ ያለው ትዕዛዝ ነው፡፡ የምናያቸውን የሥጋ ወላጆች መታዘዝን ካልተማርን የማናየውን የመንፈስ ወላጅ እግዚአብሔርን እንዴት እንታዘዘው ዘንድ ይቻለናል?
         ልጆች እውነትን መሰረት ባደረገ መልኩ ወላጆቻቸውን መታዘዝ ይኖርባቸዋል፡፡ ነገር ግን የእግዚአብሔርን ቃል በሚቃወምና መመሪያውን በሚጥስ መልኩ ልጆች ወላጆቻቸውን እንዲታዘዙ አግባብ አይደለም፡፡ ምክንያቱም ስለ ስሜ ቤቶችን ወይም ወንድሞችን ወይም እኅቶችን ወይም አባትን ወይም እናትን ወይም ሚስትን ወይም ልጆችን ወይም እርሻን የተወ ሁሉ መቶ እጥፍ ይቀበላል የዘላለምንም ሕይወት ይወርሳል (ማቴ. 19÷29) የሚለው የጌታ ቃል የታመነ ነው፡፡ (በዚህ ብሎግ “እሺታ ያለ ቦታው” የሚለውን ርዕስ እንድታነቡት እንጋብዛለን)!
                                                                - ይቀጥላል - 

Wednesday, October 17, 2012

መልከኞቹ

                                        ማክሰኞ ጥቅምት 6/2005 የምሕረት ዓመት

       
“የአምልኮት መልክ አላቸው ኃይሉን ግን ክደዋል፤ ከእነዚህ ደግሞ ራቅ፡፡ (2 ጢሞ. 3÷5)”
           
         በአንድ አጋጣሚ ከባልንጀራዬ ጋር የተገኘሁበት ቤት ውስጥ ያየኋቸው ስድስት ልጆች ትዝ ይሉኛል፡፡ ታዲያ የልጆቹ ውበት ልዩ ነው፡፡ አንዱን አይታችሁ ወደ ሌላዋ ስትዞሩ የባሰ እንጂ ያነሰ ቁንጅና አታዩም፡፡ እኛ በዚያ ቤት ውስጥ በተቀመጥንበት ትንሽ ሰዓት የመጡ ሁሉ ሰዎች ለአባትየው ስለ ልጆቻቸው ቁንጅና ሳይናገሩ አይወጡም፡፡ ስለ ትልቁ ልጃቸው ግርማ ሞገስ፣ ስለ ተከታይዋ ሸንቃጥነት፣ ስለ ትንሹ ልጃቸው ቅላት ብቻ አንዱ ከሌላው አፍ እየነጠቀ የልቡን አድናቆት ይገልጣል፡፡
            አባት ስለ ልጆቻቸው የተባለውን ሁሉ ከሰሙ በኋላ “ልክ ናችሁ ልጆቼ መልከኛ ናቸው፡፡ ነገር ግን ኃይለኛ አይደሉም” ብለው ከአንገታቸው አቀረቀሩ፡፡ ለረጅም ሰዓት ቤቱን ዝምታ ወረሰው፡፡ እኛም በዚህ ተሸኘን፡፡ እንደወጣን ለባልንጀራዬ “ለማለት የፈለጉት ገብቶሃል?” ስል ጠየኩት፡፡ እርሱም “ሁለተኛ ጢሞቴዎስ ሦስተኛው ምእራፍ ነው” አለኝ፡፡
         የሰዎች ልብ ከሚሸነፍበት ነገር አንዱ ውበት ነው፡፡ የሌላቸው ለማምጣት ያላቸው ደግሞ ለመጠበቅ ዋጋ የሚከፍሉበትም የኑሮ ክፍል ነው፡፡ አብዛኛውን ጊዜ ከውስጥ ይልቅ ለውጪያዊ ውበትና መልክ ሰዎች ሲንበረከኩ፣ እራሳቸውንም በሚፈልጉት የውበት ደረጃ ላይ ለማግኘት ጥረት ሲያደርጉ ማየት የተለመደ ነው፡፡ ዓለም በዚህ መንገድ በትጋት ብዙ ምስጉን ሰዎች አሏት፡፡ የማያስነቅፍ ደምግባት፣ የማያስነቅፍ ቁመት፣ የማያስነቅፍ ቅርጽ በብዙዎች ላይ ይታያል፡፡ የዚህም ስስት የያዛቸው በዝተዋል፡፡ ትልቁ ጥያቄ ግን የማያስነቅፍ ኑሮ ምን ያህል ሰዎች ላይ ይስተዋላል? የሚለው ነው፡፡
            ከላይ ቤተሰባቸውን እንደ መግቢያ የተጠቀምንበት አባወራ የተናገሩት ከመልክ ጋር ከተያያዘው ነገር ይልቅ ከኃይል ጋር የተያያዘው እንደሚበልጥ ነው፡፡ በእርግጥም ኃይልን ስናስብ ብዙ ነገሮች ወደ አእምሮአችን ይመጣሉ፡፡ ኃይል የብዙ ክንውኖች መሰረት ነው፡፡ ኃይል ሕልውናም ጭምር ነው፡፡ አለ! የምንለው ሰው መኖር የሚጠይቀውን መሰረታዊ ኃይል ያሟላ ነው፡፡ ሰው ብዙ ነገሮችን የሚከውነው በመልኩ አይደለም፡፡ መልካችንን ተከትሎ የሚሳብ ይኖር ይሆናል፡፡ መልክ ውስጥ ግን ኃይል የለም፡፡
            ሕሊና እንጂ መልክ አያስብም፡፡ አንደበት እንጂ መልክ አይናገርም፡፡ መልካምነት እንጂ መልክ ከሰው አያኖርም፡፡ ስነ ምግባር እንጂ መልክ አያስከብርም፡፡ እምነትና ፍቅር እንጂ መልክ ሞትን አያሻግርም፡፡ መልክ የላይ ማንነትን እንጂ የውስጥ ሰብእናን አይገልጥም፡፡ ፊት ቀልቶ ውስጥ ሊጠቁር፣ ውጪ አጊጦ ልብ ሊቆሽሽ ይችላል፡፡ ምድራችን የመልከኞች ሆናለች፡፡ ማስመሰል ቀላሉ የኑሮ ዘይቤ ተደርጎ እየተቆጠረ ነው፡፡ ገጣሚው፡ -
አርሜ ኮትኩቼ የሎሚ ዘንጓን
መልከኛ ወሰዳት ወይ ገባር መሆን፡፡ እንዳለ . . .
            ድካሙና ኃይሉ ያለው አራሚ ኮትኳቹ ጋር ነው፡፡ ሴቲቱ የተሸነፈችው ግን ለመልከኛው ነው፡፡ በመፍጠርና በማዳን ዋጋ የከፈለብን እግዚአብሔር ነው፡፡ የተወደደው ልጁ እስከ መስቀል ሞት በመታዘዝ ለመዳናችን መከራን ተቀብሏል፡፡ ዛሬም በቃሉ በኩል የሚረባንን ወደ ሕይወታችን ለማድረስ በመንፈሱ በኩል ይተጋልናል፡፡ ብዙዎች ግን የመልከኛዋ ዓለም ሆነዋል፡፡ በፍቅር ኃይለኛ፣ በማዳን ኃይለኛ፣ በምሕረት ኃይለኛ፣ በፍርዱ ኃይለኛ የሆነው እግዚአብሔር ወደ ጎን ተትቶ ሰዎች በፊታቸው መልካም መስሎ የታያቸውን ሁሉ በትጋት እያደረጉ ነው፡፡
             ዓለም የሆኑ ሳይሆን እንደሆኑ መስለው የሚታዩ የሚፋንኑባት አደባባይ ናት፡፡ ከፍቅር ይልቅ ፍቅር ለሚመስል፣ ከሰላም ይልቅ ሰላም ለሚመስል፣ ከእውነት ይልቅ እውነት ለሚመስል፣ ከኃይል ይልቅ ኃይል ለሚመስል መልክ ምድሪቱ ተገዝታለች፡፡ ያለ ጭንብል መኖር የማንችለውም ለዚሁ ነው፡፡ መልክ እንጂ ኃይል፣ ቅብ እንጂ የጨከነ እውነት፣ የምድሩ እንጂ የሰማዩ አያስደስተንም፡፡ የክርስትና ውድቀት ትልቁ ልኬት ያለው እዚህ ላይ ነው፡፡     
            ክርስትና በመልኩ ሳይሆን የተብራራው በኃይሉ (በተግባሩ) ነው፡፡ ያውም የትንሣኤው ኃይል! (ፊል. 3÷10)፡፡ “ከእግዚአብሔር የተወለደ ሁሉ ዓለምን ያሸንፋልና ዓለምንም የሚያሸንፈው እምነታችን ነው” ተብሎ እንደተፃፈ አውርተን እንኳን ያልዘለቅነውን ዓለም የምናሸንፍበት፣ ከክፋትና ከርኩሰቱ የምናመልጥበት ኃይል ያለው እምነታችን ውስጥ ነው፡፡ ይህም እምነት በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ላይ የተመሰረተ ነው፡፡ መልከኛ ክርስትና ግን የሚመስል እንጂ የሆነ ነገር አይታይበትም፡፡ ውጫዊ ገጽታው ያመነ ውስጡ ግን የካደ ነው፡፡ በቃል ብዙ ጥበብ በኑሮ ብዙ ስንፍናን ይገልጣል፡፡ መሳይ ክርስቲያኖች!
           ምላስ ረዝሞ እጅ ከተሰበሰበ፣ የምናወራው እግዚአብሔር እንጂ የምንኖረው እግዚአብሔር ከሌለ፣ የምናቅደው እንጂ የምንተገብረው መልካም ካነሰ መልከኞች እኛ ነን፡፡ በእውነትና በመንፈስ ስለማምለክ ተረድተን እንደ ፈቃዳችን ካመለክን፣ በመንፈስ ጀምረን በሥጋ ከጨረስን፣ ከእግዚአብሔር የልቡ ምክር አፈንግጠን ለዚህ ዓለም ከንቱ መለፍለፍና በብልሃት ለተፈጠረ ተረት ከተገዛን በእርግጥም መልከኞቹ እኛ ነን፡፡ ተራቁተን እንደለበስን፣ ደህይተን እንደበለፀግን፣ ታውረን እንደተኳልን፣ አንሶን እንደተረፈን ከተሰማን ተወዳጆች ሆይ መልከኞች እንጂ ኃይለኞች አይደለንም፡፡ “ቃሉን የምታደርጉ ሁኑ እንጂ እራሳችሁን እያሳታችሁ የምትሰሙ ብቻ አትሁኑ” (ያዕ. 1÷23) ተብሎ እንደተፃፈ ተግባራዊ የሆነ መንፈሳዊ ኑሮ ሊታይብን አግባብ ነው፡፡
           አንድ ሰው በሠራው ቤት ውስጥ የሚሰቅለው የእራሱን ፎቶ ነው፡፡ መታየት ያለበትም ባለ ቤቱ (የቤቱ ጌታ) ነው፡፡ እኛ የሕያው እግዚአብሔር ቤተ መቅደሶች (1 ቆሮ. 3÷16) እንደመሆናችን በቤቱ ውስጥ መታየት እንዲሁም በሙላት ማዘዝ ያለበት የቤቱ ሠሪና ጌታ የሆነው እግዚአብሔር ነው፡፡ በእምነት ጉዞም ሆነ በአገልግሎት እንደ እግዚአብሔር ቃል መሆን ያለበት ከዚህ የተለየ አይሆንም፡፡ ነገር ግን ጌታ እንደሆነ እየተናገርን በቤቱ ላይ ግን እኛ ካዘዝን፣ አፍአዊ በሆነ መንገድ ስለ እርሱ አብዝተን እየመሰከርን በተግባር ግን እራሳችንን የምንገልጥ ከሆነ መልከኝነት እንደተጠናወተን ኃይሉ ግን እንደራቀን ማሳያ ነው፡፡ ምሕረቱን ያብዛልን!
           አምልኮ አምላክነት ላለው አካል የሚደረግ መረዛት ነው፡፡ እንደ እግዚአብሔር ያለ ሕያው አምላክ ስለሌለ ሁለንተናዊ መገዛት ለእርሱ እናሳይ ዘንድ የተወደደ ነው፡፡ እግዚአብሔር አምልኮ የግል ገንዘቡ ስለሆነ ለማንም አያጋራውም (ዘፀ. 20÷1)፡፡ በዚህ መንገድ የሚተካከለው፣ ጎን ለጎን አልያም ተክቶት ይህንን ክብር የሚወስድ ሌላ ማንም ሊኖር አይችልም (ኢሳ. 42÷8)፡፡ ለዘመናችን ትልቁ ፈተና ግን ለእግዚአብሔር ብቻ አለመገዛት ነው፡፡ ስለዚህም ጎን ለጎን የምንገዛላቸው ከውስጥም ይሁን ከውጪ ምንጫቸውን ያደረጉ ብዙ ደባሎች አሉ፡፡ ይህ የእግዚአብሔርን ኃይል ተግባራዊ በሆነ መንገድ መካድ ነው፡፡
           እግዚአብሔር ሰዎች እንዴት እንደሚከተሉትና እንደሚያመልኩት በቃሉ ውስጥ ግልጽ መመሪያ አለው፡፡ መልከኝነት ከዚህ አሳብ ማነስ አልያም በዚህ ላይ መጨመር ነው፡፡ ይህ ደግሞ ኃይል አልባ ሞቅታ ነው፡፡ በእምነት ስንኖር እራሳችንን እንድንመረምር ቃሉ ስለሚያዝ ኑሮ መፈተሸ አለበት፡፡ ዛሬ ዓለም በክርስትናው ተጽእኖ ስር መሆንዋ ቀርቶ ክርስቲያኖች በዓለም ተጽእኖ ስር ወድቀዋል፡፡ እንደ ጨው ማጣፈጫ መሆን ቀርቶ አጣፍጡኝ አይነት አልጫ ሆኗል፡፡
           በብዙ ጨለማዎች ፊት ብርሃን መሆን አልተቻለም፡፡ አልቅሰው መጥተው አልቅሰው የሚመለሱ፣ በጉድለት መጥተው በጉድለት የሚሸኙ፣ ከእነርሱ መንፈሳዊነት የእኔ ዓለማዊነት ይሻላል የሚሉ በዝተዋል፡፡ ክርስትናው መፍትሔ መሆኑ ቀርቶ ችግር፣ መልስ መሆኑ ቀርቶ ጥያቄ እየሆነ መጥቷል፡፡ ለዚህ ብቸኛው ምክንያት ደግሞ መልከኛ እንጂ ኃይል ያለው ክርስትና መዳከሙ ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የእምነት ልጁ ጢሞቴዎስን በብርቱ ይመክረዋል፡፡ በሚቀጥለው ጊዜ የመልከኛ ክርስትና ዋና ዋና ጠባያትንና መፍትሔውን እንመለከታለን፡፡ ጌታ እግዚአብሔር መልከኛ ፍቅር፣ እምነት፣ ይቅርታ፣ ቅድስና፣ ጽድቅ . . . በበዛበት በዚህ ዘመን እንደ እርሱ መንግሥት ልጆች በኃይሉ እንድንገለጥ ጸጋውን ያብዛልን!!
                                                         
                                                         - ይቀጥላል -

Tuesday, October 9, 2012

እግዚአብሔር ሲገልጥ



         “ከዚህም ወራት በኋላ ሚስቱ ኤልሳቤጥ ፀነሰችና፡፡ ነቀፌታዬን ከሰው መካከል ያስወግድልኝ ዘንድ ጌታ በተመለከተበት ወራት እንዲህ አድርጎልኛል ስትል ራስዋን አምስት ወር ሰወረች” (ሉቃ. 1÷24-25)፡፡        
           እግዚአብሔር የመገለጥ አምላክ ስለሆነ ሰው በራሱ መንገድ ሊያስተውለው ደግሞም ፈልጎ ሊደርስበት አይችልም፡፡ እርሱን የሥጋ ለባሽ ጥረትም ሆነ ግምት አያገኘውም፡፡ ነገር ግን “መቼም ቢሆን እግዚአብሔርን ያየው አንድ ስንኳ የለም፤ በአባቱ እቅፍ ያለ አንድ ልጁ እርሱ ተረከው (ዮሐ. 1÷18)” ተብሎ እንደተፃፈ እግዚአብሔር አንድያ ልጁ እንደተረከልን እንዲሁ ነው፡፡ አምላክነቱን እንደፈቃዱ ካላብራራልን “በአማልክት መካከል እንደ አንተ ያለ ማን ነው?” ልንለው አንችልም፡፡ እርሱ ፍቅሩን ለልባችን ካልገለጠ አፋችን ስለ ፍቅር ማውራቱ የእግዚአብሔርን ፍቅር ወደ ማስተዋል አያደርሰንም፡፡
            እግዚአብሔር ጽድቁን ካላሳየን ለራሳችን ጽድቅ መሸነፋችን አይቀርም፡፡ እግዚአብሔር የእውነትን ፍቺ በልባችን ላይ ካላበራ በሚያባብል ቃል እየተሸነገልን መኖራችን በግልጥ የሚታይ ነው፡፡ በእግዚአብሔር ጽድቅና መንግስት የእኛ አቅም የመሻትን ያህል ነው (ማቴ. 6÷33)፡፡ እግዚአብሔር እንደ እግዚአብሔርነቱ እንረዳውና እናምንበት ዘንድ በቃሉ በኩል ራሱን አሳይቶናል፡፡ ከሚያስፈልገን የተሸሸገ፣ ከሚረባን የቀረ ምንም የለም፡፡ ስለዚህም ጌታ ስሙ ብሩክ ይሁን!
            ለዚህ ርእስ መነሻ የሆነን የኤልሳቤጥ ታሪክ ነው፡፡ ባሏ ዘካርያስ የእግዚአብሔር ቤት አገልጋይ  ነበር፡፡ ደግሞም በጌታ ትእዛዝና ሕግጋት ሁሉ ያለ ነቀፋ እየሄዱ እግዚአብሔርን በኑሮአቸው ያከብሩ ነበር፡፡ ነገር ግን ለብዙ ዘመናት ልጅ አልነበረውም፡፡ እግዚአብሔር እንድናገለግለው ሲጠራን እንደማንቸገርና እንደማይጎድለን ተስፋ አልሰጠንም፡፡ ሁሉን ለእርሱ ክብር እንድናደርገውና በጊዜውም ያለ ጊዜውም እንድንጸና ግን አዝዞናል፡፡ በመከራም ጭምር!
            በብዙ ክርስቲያኖች ዘንድ የእውነተኛ አገልጋይን ኑሮ የመረዳት ችግር ይስተዋላል፡፡ ለዚህም ይመስላል ብዙዎች አገልጋይ የሚያጽናና እንጂ የሚጽናና፣ የሚያስተምር እንጂ የሚማር፣ የሚያሳርፍ እንጂ የሚራብ የማይመስላቸው፡፡ ነገር ግን ሐዋርያው እንዳለ “አምላኬም እንደ ባለ ጠግነቱ መጠን በክብር በክርስቶስ ኢየሱስ የሚያስፈልጋችሁን ሁሉ ይሞላባችኋል” (ፊል. 4÷19) የሚለው የተስፋ ቃል በየትኛውም ሁኔታና ዘመን በእውነትና በመንፈስ ለሚያገለግሉት ሁሉ የታመነ ነው፡፡ ለአገልግሎቱ ታማኝ አድርጎ የቆጠራቸው ሁሉ በዚህ ደስ ይላቸዋል፡፡
            ካህኑ ዘካርያስ እያገለገለ ጥያቄ ነበረው፡፡ በመቅደሱ እየተመላለሰ ያጣው ነገር ነበረ፡፡ እግዚአብሔርን የሚያገለግሉት ጥያቄያቸው ሁሉ የተመለሰላቸው፣ ጉድለታቸው ሁሉ የሞላላቸው፣ ሩጫቸው ሁሉ የተሳካላቸው አይደሉም፡፡ አገልግሎት ማጣት እያለ የበጎ ስጦታና የፍጹም በረከት ባለቤት የሆነውን፣ አለመመቸት ከብቦን አእምሮን የሚያልፍ ሰላም ባለቤት የሆነውን፣ ሀዘን ኑሮአችን ላይ አጥልቶ በእርሱ ደስ የሚለኝ የተባለለትን፣ ጠላት ተሰልፎብን የምወደው ልጄ ይህ ነው የተባለውን ጌታ በማንኛውም ሁኔታ ውስጥ በመታዘዝ ታማኝነት የመጽናት ትጋት ነው፡፡ ዘካርያስ የእድሜው መግፋት፣ የሚስቱ ምክነት በአገልግሎት ጌታ ፊት እንዳይቆም አላደረገውም፡፡ እኛ ከዚህ ላነሱ ምክንያቶች ከእግዚአብሔር ጋር ያለንን መልካም ግንኙነት ብናበላሽ ይህ የጥላ አገልግሎት ብቻውን ይወቅሰናል፡፡
            በብሉይ ኪዳን ለአንዲት ሴት መውለድ አለመቻል የሚያስነቅፍና የሚያገልል ጉዳይ ነበር፡፡ ከሌሎች የሚመጣውን ንቀት፣ ከውስጥ የሚሰማን የበታችነት ስሜት መጋፈጥን የሚጠይቅ ተግዳሮትም ነበር፡፡ የሕልቃና ሚስት ሐና ማኅፀንዋ ዝግ በነበረበት ዓመት ሁሉ ነቀፌታዋን ተሸክማ ጣውንቷ እያሽሟጠጠቻት ካህኑ ዔሊ እንደ ሰካራም እስኪቆጥራት ድረስ በእግዚአብሔር ፊት እንዴት ታነባ እንደነበር ቃሉ ይነግረናል (1ሳሙ. 1÷7)፡፡ በዚያ ዘመን መውለድ አለመቻል የኃጢአትን ያህል ተቆጥሮ ነቀፌታ መሸከምን ያስከትል ነበር፡፡ ኤልሳቤጥም መውለድ አለመቻል የሚያስከፍለውን ዋጋ ስትከፍል ኖራለች፡፡ እግዚአብሔር እንዲያስባትም በመቅደሱ በፀሎትና በምልጃ ትተጋ ነበር፡፡
            እግዚአብሔር አብርሃም ልጅ ሳይኖረው የዘጠና ዘጠኝ ዓመት አዛውንት ሳለ እኔ ኤልሻዳይ ነኝ በፊቴ ተመላለስ (ዘፍ. 17÷1) አለው፡፡ ከእግዚአብሔር ስሞች መካከል አንዱ ኤልሻዳይ የሚለው ነው፡፡ እግዚአብሔር ራሱን ኤልሻዳይ ብሎ ያቀረበው ከአብርሃም ሁኔታ አንፃር ነው፡፡ አብርሃም ከዚህ በኋላ መውለድ አልችልም ብሎ ተስፋው የተሟጠጠበት፣ ልቡ የዛለበት ጊዜ ስለነበር እግዚአብሔር እኔ ሁሉን እችላለሁ! በሚል አለመቻሉን በተስፋ ሞላው፡፡ አብዛኛውን ጊዜ በብሉይ ኪዳን እግዚአብሔር ስሞቹን የተጠቀመው ከሁኔታው አንፃር ነው፡፡
           እግዚአብሔር ሁሉን እንደሚችል ስናምንበት በማንኛውም ሁኔታ ውስጥ ሆነን ያለ መጨነቅ በፊቱ መመላለስ ይሆንልናል፡፡ በኃይልም በፍቅርም ብርቱ እርሱ ብቻ ነው፡፡ ይህም ብርታት ሌላ ተቀራራቢ ብርታት የለውም፡፡ ለመታሰብ በሚከብዱ ነገሮች ላይ እንኳ እግዚአብሔር ተግባራዊ ነው፡፡ እንዳልቻልነው በተሰማን ሥራ አንድ ሰው አይዞህ እኔ እወጣዋለሁ ቢለን ምን ያህል ያሳርፋል? ሰው እንዲህ ካስመካ እግዚአብሔር ምን ያህል ልባችንን እንጥልበት ዘንድ የተገባ ነው፡፡
          እግዚአብሔር የምክነትን ወራት አሳልፎ በልጅ በረከት የተነቀፉትን አፍ በእልልታ ይሞላል፡፡ በሕይወት ውስጥ ላሉ ልዩ ልዩ ምክነቶት (ፍቅር እየቀዘቀዘ ነው፣ መተማመን አላፊ እየሆነ ነው፣  ሥነ ምግባር እንደ ኋላቀርነት እየተቆጠረ ነው) መፍትሔው ኤልሻዳዩ ጌታ ነው፡፡ ዛሬም ብዙ ሙከራ፣ ብዙ መጠበብ ምድሪቱን አላስተካከላትም፡፡ አሁን እንኳን በዚህ ሰዓት ብዙ ነገሮች እየተሞከሩ ነው፡፡ እግዚአብሔር ግን ባልቻልነውና ባቃተን ነገር ላይ ሁሉ ኤልሻዳይ ነው፡፡ የዕብራይስጥ ትርጉም አዋቂዎች የዚህን ስም ትርጉም ከእናት ጡት ማጥባት ጋር አያይዘው ያብራሩታል፡፡ እንደውም እግዚአብሔር ራሱን እንደ እናት ያቀረበበት መንገድ እንደሆነም ይጠቀሳል፡፡ ለአንድ ልጅ የጡት ወተት እናቱ ውስጥ የተሸሸገ በረከቱ ነው፡፡ ነገር ግን ምድራዊ እናቶቻችን ከተወሰኑ ዓመታት በኋላ ጡት ማጥባት ያቆማሉ፡፡ ልጁም ወደ ማደግ ከፍታ ሲመጣ ይተወዋል፡፡ የእግዚአብሔር መጋቢነት ግን ለዘላለም ነው፡፡ የትኛውም የእድገት ደረጃ ተመጋቢነታችንን አያቋርጠውም፡፡
          አብርሃምን በይስሐቅ፣ መካኒቱን ሐና በሰባት ልጅ ደስ ያሰኘ ጌታ ኤልቤጥንም አሰባት፡፡ የመታሰብ ወራት መጣ፡፡ እንባን ከአይኗ፣ ነቀፌታን ከልቧ ላይ አበሰ፡፡ እግዚአብሔር አስታዋሽ አምላክ ነው፡፡ ስለራሳችን ጉዳይ በረሳንበት ወራት እርሱ ግን ያለፈ ልመናችንን ቸል አላለም፡፡ የካህን ሚስት ለነበረችው ኤልሳቤጥ መውለድ አለመቻል ቀላል ነገር አልነበረም፡፡ ነቀፌታን ያሸክማል! ልጆች የእግዚአብሔር ስጦታ አይደሉምን?
         ኤልሳቤጥ ታሪኳ ሲለወጥ፣ ነቀፌታዋ ሲንከባለል፣ በሁሉን ቻዩ ስትታሰብ ይህንን ባደረገላት ጌታ ፊት አምስት ወር ራስዋል ሰወረች፡፡ እግዚአብሔር ስላደረገላት ነገር ለመደነቅ ይህም ትንሽ ነው፡፡ የሞተውን ህይወት ዘርቶበት፣ የደረቀውን አለምልሞት፣ የተተወውን ወደ ሕልውና አምጥቶት እርሱ ያልተደነቀ ማን ይደነቃል? እግዚአብሔር ግን ከምንልለት ከዚህም ያልፋል፡፡
         ኤልሳቤት የሚያሳፍር ሳይሆን የሚያስመካ፣ የሚሸሸግ ሳይሆን የሚገለጥ ነገር በሆዷ ተሸክማ ለሰው በማይታይ ለእግዚአብሔር ግልጥ በሆነ መንገድ በምስጋና እየተጋች ራስዋን ሰውራ ነበር፡፡ ዘመናችንን ስናየው በዓለምም ሆነ በቤተ ክርስቲያን ሁሉም ለመታየት የሚጥርበት፣ ማማው ላይ ለመቀመጥ የሚጋደልበት ነው፡፡ ሰዎች ከዓላማቸው ይልቅ ስለ ራሳቸው በማውራት፣ በተግባር ከመታየት ይልቅ በሰው ለመታየት ጥረት በማድረግ ተጠምደዋል፡፡ እንኳ ለሌሎች የሚተርፈውን ለራሳቸው የማይበቃውንም ጨማምረው ለታይታ ያቀርቡታል፡፡
         ስለ ጌታ ብዙ ጊዜ እንዳይገልጡት አዘዛቸው (ማቴ. 12÷15፣ ማር. 3÷12) ተብሎ ተጽፎአል፡፡ ኢየሱስን ያህል ንፁሕ ጌታ (ለሁሉ ሊሞት የመጣ አንድ መፍትሔ) ወደ እርሱ የመጡትን ሁሉ ፈውሶ ዳሩ ግን አትግለጡኝ ይል ነበር፡፡ ከሥራቸው ስንጠቀም ኖረን ከሞቱ በኋላ አልያም ግድ ሲሆን የተገለጡ መልካም ሰዎች አሉ፡፡ ሳይታወቁ ብዙ ጠቅመው ሰው ገልጦአቸው አድንቀን ሳንጨርስ የሞቱም አሉ፡፡ በመንፈሳዊ አገልግሎት ውስጥ ውድቀት የሚጀምርበትን ነጥብ አስተውለነው ከሆነ መሰማራት ሲገባን የተሰበሰብንበት፣ መገለጥ ሲገባን ያንቀላፋንበት ደግሞ መደበቅ ሲገብን የተገላለጥንበት፣ መጸለይ ሲገባን አደባባይ የፎከርንበት ያ ሰዓት ነው፡፡ ብዙዎች በዚህ ኪሳራ ውስጥ ሲያልፉ አይተናል፡፡ ያለነው ካለፉት ካልተማርን የረገጡትን መርገጥ፣ ያጨዱትን ማጨድ አይቀርም፡፡
        “ጌታ ሆይ እኔ ልሰወር አንተ ብቻ ታይ” የሚል የአገልጋይ ጸሎት አውቃለሁ፡፡ እንደ ጸሎቱ ቢሆን ኖሮ አጨብጭቦ የሚያወጣ አጨብጭቦ የሚያወርድ፣ እልል ብሎ የሚያከብር እልል ብሎ ሰቅሎ የሚያዋርድ፣ ወደድኩ ብሎ የሚስም እዚያው ቦታ ላይ ጠላሁ ብሎ የሚነክስ፣ ነፋስን የሚከተል ሕዝብ ባላተረፍን ነበር፡፡ ሰው ሰውን አይቶ ወደ ሌላ ሰው ይገላበጥ ይሆናል፡፡ ሰው ጌታን አይቶ ግን ወዴት ይገላበጣል? የሚያምረው እርሱን ስናሳይ ነው!
         ክርስትና እግዚአብሔርን ማሳየት ነው፡፡ እኛን እግዚአብሔር ከገለጠን መታዘዝ እውነት ነው፡፡ ኤልሳቤጥ እራሷን ሰውራ አምስት ወር ቆየች፡፡ በስድስተኛው ወር መልአኩ ገብርኤል ድንግል ማርያምን ሊያበስራት ሲመጣ “ዘመድሽ ኤልሳቤጥ” ብሎ ገለጣት፡፡ ነቢዩ ዳዊት እንደ እግዚአብሔር ልብ የሆንኩ ብሎ ሲናገር አናነብም፡፡ እግዚአብሔር ግን እንደልቤ የሆነ ዳዊት ብሎ ሲናገር እናያለን (የሐዋ. 13÷22)፡፡ ኢዮብ በምድር ላይ እንደ እኔ ፍጹምና ቅን እግዚአብሔርንም የሚፈራ ከክፋትም የራቀ ሰው የለም ብሎ ሲናገር አናነብም፡፡ እግዚአብሔር ኢዮብን ሲገልጠው በሰይጣንም ፊት ሲመሰክርለት ግን እናነባለን (ኢዮ. 2÷3)፡፡ ታዲያ ተወዳጆች ሆይ ማን ይግለጠን?
         ሰው ተሰውሮ ክፉ አያድርግ እንጂ መልካምን መሥራት መዝገብን በላይ በሰማይ መሰብሰብ ነው፡፡ ብዙ ሰው በእጁ ያደረገውን አውርቶ በመርካት ዋጋውን ይቀበላል፡፡ የማቴዎስ ስድስት አሳብ እንዲህ ያለውን መገላለጥ አጥብቆ ይኮንነዋል፡፡ እኛ ስለ ራሳችን የምንገልጠው መልካም ልኩ የመርገም ጨርቅ ነው፡፡ እግዚአብሔር ከገለጠን ግን በእርሱ ሚዛን ተለክቶአልና እርሱ ጽድቃችን ነው፡፡
         ራሳቸውን ሰውረው ደግሞም ላመኑበት እውነት እስከ ሞት ድረስ ዋጋ ከፍለው ጌታን በቃልና በኑሮ እንዳከበሩት (እንደገለጡት)፣ በሰው መፍትሔ መካከል የእግዚአብሔርን መፍትሔ እንዳሳዩት እውነተኞች እንድንኖር በጥበብና በማስተዋል ጸጋውን ያብዛልን፡፡  

Thursday, September 27, 2012

የገላትያ አዚም



          የእግዚአብሔርን ሕልውና የተቀበልንበት መንገድ እምነት ነው፡፡ እርሱን ያየውና የዳሰሰው የለም፡፡ ስለ እርሱ ከሰማነው ቃል የተነሣ ግን ወደ ማመን ከፍታ መምጣ ሆኖልናል፡፡ በእርሱና በእኛ መካከል ያለው መግባባት የተመሰረተው በእምነት ላይ እንደሆነ ለልባችን ማስረገጥ እንችላለን፡፡ እግዚአብሔርን ብቻ ሳይሆን የእግዚአብሔር የሆነውን ሁሉ በረከት የምንቀበለው የእግዚአብሔርን ሕልውና በተቀበልንበት መንገድ ነው፡፡ ራሱን በማመን ሰጥቶን የእርሱ የሆነውን እንደ ትጋታችን መጠን ሊሰጠን አይችልም፡፡ ምክንያቱም ስጦታው ጸጋ (የማይገባ) ነው!
          ሐዋርያው ለገላትያ ሰዎች በፃፈው መልእክት “የማታስተውሉ የገላትያ ሰዎች  ሆይ በአይናችሁ ፊት ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ተሰቀለ ሆኖ ተሥሎ ነበር ለእውነት እንዳትታዘዙ አዚም ያደረገባችሁ ማን ነው? (ገላ. 3÷1)” በማለት መጠይቃዊ ተግሳጽ ሲያስተላልፍ እናስተውላለን፡፡ የገላትያ ሰዎች ከሚያስመካው የእግዚአብሔር ጽድቅ ይልቅ በራሳቸው ጥረት የተመኩ ነበሩ፡፡ በሕግና በነቢያት የተመሰከረለትን ነገር ግን ያለ ሕግ የተገለጠውን የመለኮት ጽድቅ በሥጋቸው ውስጥ ካለው ትምክህት የተነሣ ገፍተውት ነበር፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ እንግዲያማ ክርስቶስ በከንቱ ሞቶአል? እስኪል ድረስ የሕዝቡ ድንዛዜ የክርስቶስን ሞትና ትንሣኤ ዋጋ ያሳጣ ነበር፡፡ ከዚህም የተነሣ ለእውነት እንዳይታዘዙ ልባቸው ደነደነ፡፡
          ለእነርሱም የእግዚአብሔር ምሳሌ የሆነ የክርስቶስ የክብሩ ወንጌል ብርሃን እንዳያበራላቸው የዚህ ዓለም አምላክ የማያምኑትን አሳብ አሳወረ (2 ቆሮ. 4÷4) ተብሎ እንደተፃፈ የዲያብሎስ ውጊያ ከአሳባችን ጋር ነው፡፡ አሳባችንን ማሳወር! ሰው ደግሞ ልቡ (አሳብ) ካላየ አይኑ አያስተውልም፡፡ በተለይ በእምነት ውስጥ ስንኖር የዚህ እውነት ተግባራዊነት ግልጽ ይሆናል፡፡ በአንድ ሰው ውስጥ ያለው ትልቁ ሐብት አሳቡ ነው፡፡ ለዚህም ነው በጉብዝናህ ወራት ፈጣሪህን አስብ የተባለው፡፡ ጉብዝናችንን እግዚአብሔርን ካላሰብንበት ሽምግልናችን የጸጸት ይሆናል፡፡ የምድሪቱ ጩኸት ምንድነው ካልን መልሱ “የአስተሳሰብ ለውጥ” የሚል ነው፡፡ ሐዋርያው የማታስተውሉ የገላትያ ሰዎች ሲል አእምሮ የሌላችሁ ማለቱ አይደለም፡፡ እየሰማችሁ የማትረዱ፣ እያያችሁ የማትቀበሉ፣ በተገለጠው እውነት የማታምኑ ማለቱ ነው፡፡
          ተግባራዊ ወደሆነው ሕይወታችን ስንመጣ የገላትያ አዚም በግልጥ ይስተዋላል፡፡ አዚም መፍዘዝንና መደብዘዝን የሚያመለክት ቃል ሲሆን ይህም ከድግምት ኃይል ጋር የተቆራኘ ነው፡፡ የሥራ ብዛት፣ የጤና መቃወስ፣ የእድሜ ሕፃንነት ያመጣው መንፈሳዊ ችግር ሳይሆን እግዚአብሔር በልጁ የሠራውን ማዳን ባለማስተዋል፣ ከመንፈሳዊ ጤና ማጣትና በቃሉ ካለማደግ ጨቅላነት የሚመጣ ድንዛዜ ነው፡፡ ይህም የዚህ ዓለም አምላክ በተባለው ሰይጣን አጋዥነት የሚከወን ድርጊት ነው፡፡
         ኢየሱስ ክርስቶስ እንድናስታውሰው ያዘዘን ሞቱንና ውርደቱን ነው፡፡ ምክንያቱም የእኛ ታሪክ መቀየር ያለው እርሱ በመስቀል ላይ ኃጢአታችንን ተሸክሞ የሕግ እርግማን ሆኖ በመሞቱ ነው (ዘዳ. 21÷23)፡፡ እኛ የተዋረድንበትን ቀን ሌሎች አይደሉም እኛው ራሳችን እንኳን ልናስበው አንፈልግም፡፡ ቤታችን ላይ የሚሰቀለው ፎቶ እንኳ ምቾታችንን የሚያሳየው ተመርጦ ነው፡፡ ከስተን ጠቁረን የተነሣነው የት ነው የሚቀመጠው? ጌታ ግን በእጅና በእግሮቹ ላይ ችንካር እንዳለፈ፣ ፊቱ ላይ ምራቅ እንደተተፋ፣ ራሱ ላይ የእሾህ አክሊል እንደደፋ፣ ጀርባው በጅራፍ እንደተገረፈ፣ በየሸንጎው እንደተንገላታ፣ እርጥብ እንጨት ተሸክሞ ተራራው ላይ ደፋ ቀና እንዳለ አስቡት ሲል አላፈረም፡፡
          ለጠፋው መልካችን መልክ የሆነን ባየነው ጊዜ እንወድደው ዘንድ ደምግባት የለውም ተብሎለት ነው (ኢሳ. 53÷2)፡፡ የተናቀ ከሰውም የተጠላ የሕማም ሰው ደዌንም የሚያውቅ ስለ መተላለፋችን የቆሰለ ስለ በደላችን የደቀቀ እርሱ ነው፡፡ ከመስቀሉ ጋር የተያያዘው ሕይወት ሕይወቱን ለእኛ አሳልፎ የሰጠው ጌታ ነው፡፡ የምናከብረውም እንደ ወንበዴ የተሰቀለልንን ፃድቅ ክርስቶስን ነው፡፡ በኃጢአት ምክንያት ያጣነው መልካችን ጽድቅ፣ ቅድስና እና እውቀት የተመለሰው ክርስቶስ መልክ ሆኖልን ነው፡፡ እርሱ ደምግባት የለውም ቢባልለትም መልካችን ነውና አናፍርበትም፡፡ በመልኩ የሚያፍር የለምና፡፡
          በኃጢአት ምክንያት በእኛና በእግዚአብሔር መካከል የነበረው የጥል ግድግዳ (ኤፌ. 2÷14) የፈረሰው እርሱን እግዚአብሔር በእምነት የሚገኝ በደሙም የሆነ ማስተስሪያ አድርጎ ስላቆመው ነው (ሮሜ. 3÷25)፡፡ ሁላችንም እንደሚገባን በሁለት ሰዎች መሐል ለረጅም ጊዜ ጸብ ቆሞ ከነበረ የሚፈርሰው እርቅ በመካከላቸው ሲቆም ነው፡፡ አለዚያ ቦታው ባዶ ሊሆን አይችልም፡፡ በእግዚአብሔር ፊት ተቀባይነት ያገኘነው በልጁ በክርስቶስ ክርስቲያን በሆንበት መታወቅ ነው፡፡ ሁላችንም ዳግም የእግዚአብሔር የሆነው በልጁ በክርስቶስ ቤዛነት በኩል ነው፡፡ ስለዚህም ክርስቶስ መታወቂያችን ነው፡፡ ታዲያ ልጁ የሌለው ሕይወት የለውም ቢባል ምን ይደንቃል?
           ዳሩ ግን ይህንን ሁሉ የእግዚአብሔር ባለ ጠግነት እንዳናስተውል ደግሞም ለእውነቱ እንዳንታዘዝ በኑሮአችን ውስጥ ልዩ ልዩ አዚም ጋርዶን ይስተዋላል፡፡ ሐዋርያው በፊታችሁ እንደተሰቀለ ሆኖ ይላል፡፡ እለት እለት በፊታችን እናስተውለው ዘንድ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ያደረገልን ውለታ በግልጥ ተስሏል፡፡ የእግዚአብሔር ውለታ ደግሞ ወቅት እየጠበቅን የምንዘክረው ሳይሆን በየጊዜው የምናከብረውና ልባችን ላይ ትልቁን ስፍራ የያዘ ሐቅ ሊሆን አግባብ ነው፡፡
            እርሱ ስለ እኛ በመስቀል ላይ እንዴት ራሱን እንዳዋረደ ስናስተውል ክብሬ ብለን አንሟገትም፡፡ እርሱ ሕማማችንን እንዴት እንደተሸከመ ስናስተውል ሕመማችንን ቆጥረን አንማረርም፡፡ እርሱ በመከራ እንዴት እንደደቀቀ ስንረዳ የሰዎች ማሳዘን፣ የኑሮ ውጣ ውረድ፣ የሕይወት ፈተናችን ሁሉ ይፈወሳል፡፡ ተወዳጆች ሆይ የተሰቀለውን እዩ! ደግሞም ስላደረገው ሁሉ ልባዊ በሆነ መንገድ ስሙን አክብሩ፡፡ በገላትያ ምእመናን ላይ የተስተዋለው አዚም ግን ለዘላለም አይግዛን!!      
            

Tuesday, September 18, 2012

የተወጋ ሲረሳ (ክፍል አራት)


                    
“ዮፍታሔም የገለዓድን ሽማግሌዎች፡- የጠላችሁኝ ከአባቴም ቤት ያሳደዳችሁኝ እናንተ አይደላችሁምን? አሁን በተጨነቃችሁ ጊዜ ለምን ወደ እኔ መጣችሁ? አላቸው” (መ. መሳ. 11÷7)፡፡
        ተስፋ መቁረጥ ማለት ከጨለማ ቀጥሎ ብርሃን፣ ከመጨነቅ ቀጥሎ ሰላም፣ ከድካም ቀጥሎ ድል፣ ከርሀብ ቀጥሎ ጥጋብ፣ ከስደት ቀጥሎ እረፍት እንደሚመጣ አለማስተዋል ነው፡፡ የጠሉን እንደጠሉን፣ ያሳደዱን እንዳሳደዱን፣ የናቁን እንደናቁን፣ ያሳዘኑን እንዳስነቡን፣ ያስቸገረን እንዳማረረን አለመቀጠሉ ለመኖር የምንናፍቅበት ጥቂቱ ምክንያታችን ነው፡፡ ያስጨነቁን አንድ ቀን ይጨነቃሉ፣ ያሳደዱን አንድ ቀን ይሰደዳሉ፣ ያስቸገሩን አንድ ቀን ይቸገራሉ፡፡ ያን ጊዜ እኛን እግዚአብሔር መፍትሔ ያደርገናል፡፡ ያስከፉን ተከፍተው ይመጣሉ፡፡ ያን ጊዜ እኛ መጽናናት ነን፡፡ ያቆሰሉን ታመው ይመጣሉ፡፡ ያን ጊዜ መፈለግንም ማድረግንም በእኛ ከሚሠራው ጌታ የተነሣ ፈውስ ነን፡፡ የነቢዩ የዳዊት ታላቅ ወንድም ኤልያብ ዳዊትን እንደ ችግር ቢቆጥረውም እግዚአብሔር ግን እርሱን ለእስራኤል መፍትሔ አድርጎት ነበር (1 ሳሙ. 17÷28)፡፡  
        የዮፍታሔ ሕይወት ተወግቶ መርሳትን፣ ተበድሎ መማርን፣ ተንቆ ማክበርን የምንማርበት ነው፡፡ የልዩ ሴት ልጅ መሆኑ በአባቱ ቤት ካለው ሀብት እንዳይካፈል አደረገው፡፡ ከዚህም በላይ ከአካባቢው እንዲሰደድ ሆነ፡፡ ይህ የሆነው ደግሞ ከአንድ አባት በተወለዱ ወንድሞቹ ነው፡፡ እንዲህ ያለው መወጋት ሕመሙ ምን ያህል እንደሆነ በዚህ ያለፉ ሁሉ አይስቱትም፡፡ የሰው ፊት ለጠቆረብን፣ ጥላቻቸው እንደ ሳማ ቅጠል ለሚለበልበን፣ ወድደን መከዳት፣ ፈልገን መገፋት፣ ተጠንቅቀን መረሳት ለገጠመን ይህም ዘመን አልፎ የመወደድ ጊዜ ይመጣልና በዚህ ቃል ተጽናኑ፡፡
        የመጣል ዘመን አልፎ የመፈለግ ጊዜ ይመጣል፡፡ ገፍተው ያባረሩን ለምነው ይገናኙናል፡፡ አዋርደው የሰደዱን አክብረው ይቀበሉናል፡፡ በዮፍታሔ የሆነው ልክ እንደዚህ ነው! ከአባቱ ቤት ያሳደዱት፣ ከጋለሞታ ሴት በመወለዱ የናቁት፣ በእግዚአብሔር ዘንድ ያለውን ሞገስ ሳያስተውሉ ቁሳዊውን ነገር የከለከሉት ሰዎች የዮፍታሔን ጽናትና ኃይል የሚፈልጉበትና የሚያስተውሉበት ሁኔታ ተፈጠረ፡፡ እግዚአብሔር ሲገልጠን የትኛውም የሰው አሳብ ሊሸፍነን አይችልም፡፡ ጸጋው በድካማችን ይገለጣልና በዚህ እንመካለን፡፡
        ለሰው ከባዱ ነገር መጠበቅ ነው፡፡ በተለይ በጭንቀትና በብዙ ውጣ ውረድ ውስጥ እያለፍን የእግዚአብሔርን ምላሽ በእምነት መታገስ ጭንቅ ይሆንብናል፡፡ በማርቆስ ወንጌል ምእራፍ አምስት ላይ ኢያኢሮስ የተባለ የምኩራብ አለቃ ልጁ ታማበት ጌታ እንዲፈውስለት ተማጸነው በመንገድም ሳሉ አሥራ ሁለት ዓመት ደም የሚፈስሳት ሴት ጌታን አዘገየችው፡፡ ኢየሱስም ቆመ! የነካውም ማን እንደሆነ ጠየቀ፡፡ እንዲህ ያለው ሁኔታ የአለቃውን እምነት ምን ያህል እንደሚፈትነው አስቡ፡፡ በቤቱ ውስጥ በሞትና በሕይወት መካከል ያለች ልጁን እያሰበ በተመሳሳይ ሁኔታ ደግሞ ጌታን ቆሞ መጠበቅ ነበረበት፡፡ ይህ ምንኛ የሚያስደንቅ እምነት ነው?
          ከቤቱ ሰዎች መርዶ ይዘው ሲመጡ እርሱ ያመነ እንጂ የፈራ አልነበረም፡፡ ክርስቶስ እስኪመጣ ድረስ ታሪካችን በበደልና በኃጢአት ምክንያት የዘላለም ሙታን የሚል ነበር፡፡ በየትኛውም አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የምናልፈው እርሱ በአስቸጋሪ ሁኔታዎቻችን ላይ በኃይልና በብርታት እስኪገለጥ ድረስ ነው፡፡ የሚያምኑ ሁሉ የሚያስመካውን ጌታ ታምነው ይጠብቁታል፡፡ ጨለማ ቢያስፈራችሁ እርሱ የማይጠፋ ብርሃን ነው፡፡ የእንጀራ ዋስትና ቢያሻችሁ እርሱ የሕይወት እንጀራ ነው፡፡ መከዳት ቢሰብራችሁ እርሱ የእስከ መጨረሻ ወዳጅ ነው፡፡ የጠላት ፍላፃ ቢከብባችሁ እርሱ የማይደፈር የበጎች በር ነው፡፡ የሞት ጣር ቢያስጨንቃችሁ እርሱ ትንሣኤና ሕይወት ነው፡፡ በእርግጥም ጌታ ለሚጠብቁት ከግምት በላይ ይሠራል፡፡ በእኛም ሕይወት ጌታ ከዚህ በላይ ይሠራል፡፡ በየትኛውም ሁኔታ ውስጥ የእርሱን አሠራርና ጊዜ በጽናት መጠበቅን መለማመድ ይኖርብናል፡፡ ቢዘገይም የእግዚአብሔር ይበልጣል፡፡
          ተወዳጆች ሆይ ከፍርሃቶቻችሁ ጋር ሳይሆን ከተስፋዎቻችሁ ጋር ተወያዩ፡፡ ስለ ሰዎች ማሳደድ ሳይሆን ተቀባይ ስለሆነው የእግዚአብሔር ብርቱ ክንድ አስቡ፡፡ በአጣችሁት ነገር መብሰልሰሉን ትታችሁ በምሕረቱ ባለ ጠጋ የሆነውን ጌታ ታመኑት፡፡ አስተዋይ ሰው በፊቱ ያለውን መከራ ሳይሆን በልቡ ያለውን ራዕይ እየተከተለ በትዕግስት ይጓዛል፡፡ ተስፋ የሕይወት ዘመናችን ብቸኛው ወዳጅ ነው፡፡ የሚበልጠው ተስፋችን ደግሞ ክርስቶስ ኢየሱስ ነው!
          በፈተና ውስጥ ስትሆኑ ከሁሉም ነገር በላይ የልባችሁን ሰላም ጠብቁ፡፡ ከማንኛውም ሀብት ይልቅ የከበረ ነውና፡፡ ዛሬ ያጣነው ነገር ነገ በተሻለ ይኖረን ይሆናል፡፡ ዛሬ ራሳችንን ከከሰርን ግን ነገ ባዶአችንን ነን፡፡ ስለዚህ ራሳችሁን ለእግዚአብሔር ስጡ፡፡ ሰዎች ከሚበድሉን በላይ እኛ በደሉን በማሰላሰል የምንከፍለው ዋጋ ይከፋል፡፡ ለራሳችንና ለሌሎች ምሕረት ስናደርግ ግን ተወግቶ የመርሳትን በረከት እንለማመዳለን፡፡
          ዮፍታሔ የጠሉት ሰዎች በጠላት እጅ ሲወድቁ “የዘሩትን ይጨዱ” በማለት በተማጽኗቸው ላይ አልጨከነም፡፡ የገዛ ወገኖቹ ወግተውት ቢረሱም እርሱ ግን ተወግቶ አላስታወሰውም፡፡ የእርሱ ወደ ሆነው መጣ÷ የገዛ ወገኖቹም አልተቀበሉትም (ዮሐ. 1÷11) ተብሎ እንደተፃፈ ክርስቶስ በገዛ ወገኖቹ ተቀባይነትን አጥቶአል፡፡ እስከ መስቀል ሞትም አሳድደውታል፡፡ እርሱ የናዝሬቱ ኢየሱስ ቢሆንም በዚያው ልክ ደግሞ የነገሥታት ንጉስ የጌቶችም ጌታ ነው፡፡ መልካም ነገር አይወጣብሽም ከተባለችው ከተማ የመልካምነት ልክ፣ የደግነት ዳርቻ፣ የሕግ ሁሉ ፍፃሜ የሆነው ክርስቶስ ተገኝቶአል፡፡ ከዚህ ጌታ ጽናትና ኃይል መካፈል የሚፈልጉ ሁሉ ነቀፋውን ተሸክመው ዮፍታሔን እንደተከተሉት ምናምንቴ ሰዎች ከሰፈር ውጪ (ከሥጋ አሳብ) እርሱን መከተል አለባቸው፡፡ ተወግቶ መርሳት ቀላል አይደለም፡፡ ግን ደግሞ በዚህ ውስጥ ያለው ትርፍም ቀላል አይደለም፡፡ ለዚህ ያለ ልክ ከፍ ከፍ ያለው፣ ከአለቅነትና ከሥልጣንም ከኃይልም ከጌትነትም ሁሉ በላይ ከዚህና ከሚመጣው ዓለም የሚልቅን ስም የያዘው ጌታ ሕያው ትምህርት ነው፡፡   
                                                              - ይቀጥላል -


Tuesday, September 11, 2012

እቅድ በአረቄ


  
         ዘመን የማይቆጠርለት እግዚአብሔር የዘመኖቻችንን ርዝማኔ ወስኖ ለእድሜያችን ዳርቻ አበጅቶ ሁሉን በሚችለው ኃይሉ ፍጥረትን ያኖራል፡፡ ታዲያ ከዘመን ለውጥ ጋር ተያይዞ ሰዎች ኑሮአቸውን ሲፈትሹ የጎደለውን ለመሙላት፣ ያረጀውን ለማደስ፣ የጠመመውን ለማቅናት፣ የሚናፍቁትን ለመያዝ ያለፈውን ገምግመው ለወደፊቱ እቅድ ያወጣሉ፣ ያንንና ይህንን ለመሥራት ይወጥናሉ፡፡ ሰው እንስሳ ስላልሆነ በዘፈቀደ ሊኖር አይችልም፡፡ መብላት መጠጣት፣ መንቃት ማንቀላፋት፣ መውለድ ማሳደግ እግረ መንገድ እንጂ የተፈጠርንበት ብቸኛ ምክንያት አይደለም፡፡ ስለዚህ በእቅድና በዓላማ መኖር እንደ አማኝ መኖር ሳይሆን አንደ ሰው የመኖር ጥበብ ነው፡፡  
         ዘመን ስጦታ ነው፡፡ የምንፎክርበት ሳይሆን የምንሠራበት፣ የምንዝናናበት ሳይሆን የምንዘጋጅበት፣ የምንበድልበት ሳይሆን በንስሐ የምንታጠብበት ነው፡፡ እግዚአብሔር በእድሜ በረከት የሚጎበኘን የሥጋን አሳብ ወደ ፍፃሜ እንድናደርስ ሳይሆን ሥጋን ከነመሻቱ ሰቅለን ስለ በደላችን የሞተውን ደግሞም እኛን ስለማጽደቅ የተነሣውን የእግዚአብሔር ልጅ በማመን የዘላለም ሕይወት እንዲሆንልን ነው፡፡ ዘመንን እግዚአብሔር በእኛ ላይ ካለው ዓላማ አንፃር ማየት መቻል በብዙ ማትረፍ ነው፡፡ ዘመንን እንደ ስጦታ ካሰብነው በየትኛውም ጊዜ ሊወሰድ ይችላል ማለት ነው፡፡ ሙሉ ሥልጣኑም በሰጪው ዘንድ ነው፡፡ ስለዚህ የተሰጠንን ዕድሜ በእግዚአብሔር አሳብ፣ በፍቅር፣ በጤና፣ በይቅርታ፣ በለጋስነት . . . . ልንከባከበው ይገባል፡፡ በእድሜአችን ምሽት ላይ የማናፍርበትን ነገር ለማየት ቀን ሳለ እንደሚገባ ልንሠራና እንደ ታማኝ ሎሌ ልንተጋ ያስፈልገናል፡፡
         በሌላ ጎን የአዲስ አመት መምጣትን ለሞት ከፊት ይልቅ መቅረብ እንደሆነ ልናስተውል ይገባናል፡፡ ሃምሳ ዓመት የሚኖር አንድ ሰው አርባኛ አዲስ አመቱን ቢያከብር የቀረው አሥር ዓመት ይሆናል፡፡ ይህ ሰው በሕይወት ዘመኑ ሊሠራው የሚገባውን በቀልድ ቢያሳልፍ አሥሩ ዓመት ቀልዱን ለማረም እንኳን አይበቃውም ማለት ነው፡፡ ለዚህ ጽሑፍ መነሻ የሆኑኝ ሰው እቅድን ከአረቄ ጋር ያያዙ ሰው ናቸው፡፡ ለዚህም ቅዱስ ጳውሎስ ለጢሞቴዎስ የተናገረውን ምክር ይጠቅሳሉ፡፡
          ብዙ ጊዜ የሚስተዋለው ችግር ከራስ አሳብና ፈቃድ ተነሥቶ ወደ እግዚአብሔር ቃል የሚደረግ ጉዞ ላይ ነው፡፡ ምክንያቱም የምናጣቅሰው ሁሉ የራሳችንን አሳብ እንዲደግፍልን በመሻት ስሜት ውስጥ ሆነን ነው፡፡ ይህ ቃሉን ከልባችን ምክር ጋር እንዲስማማ በግድ መጠምዘዝ ነው፡፡ ነገር ግን ከቃሉ ተነሥተን ወደ ራሳችን ሕይወት ብንመለከት እንደ ቃሉ ራሳችንን ማስተካከልና መታዘዝን እናሳያለን፡፡ ለእነዚህ ሰው አረቄ ከሌለ እቅድ የለም፡፡ አዲስ አመት ያለ አረቄ እርሳቸው ጋር ትርጉም የለውም፡፡ ሲጠጡ የማያፈርሱት ጎጂ ነገር፣ የማይገነቡት በጎ ነገር የለም፡፡ ከጠጡ ሰፈራቸው ኒዮርክ፣ መዝናኛቸው ባንኮክ ነው፡፡
         የማይሰጡት ተስፋ፣ ቃል የማይገቡት ነገር የለም፡፡ የድህነት ወሬአቸው እንኳን የሀብትን ያህል ያስፈነድቃል፤ ልክ እንደ አመት በዓል ሆያ ሆዬ ለአንዱ መኪና ለሌላው መርከብ፣ አንዱን ዘፋኝ ሌላውን መሪ፣ አንዱን ዶክተር ሌላውን መሃንዲስ ብቻ የሚሰጡት እንደ ቸርነታቸው ነው፡፡ መመረቅ ከፈለጋችሁ መለኪያ አረቄ በተኮማተሩት እጆቻው ማስያዝ ነው፡፡ ለአሜንታ እንኳን ክፍተት ለምናችሁ ካልሆነ በቀር ፍንክች የለም፡፡ አንዳንዴ እንዲህ ያለውን እቅድ ሳይሰክሩ ቢያቅዱት ኖሮ ብዬ እቆጫለው፡፡ ሲጠጡ ባለ ብዙ ራዕይ ባለ ብዙ ዓላማ፤ ከመለኪያው ሲርቁ ከስካር ሲነቁ ደግሞ ቀልደኛ ነዋሪ ናቸው፡፡ (አንድምታው ቁጭ ሲል ይነፋዋል ሲቆም ይጠፋዋል እንዲል) የአረቄ ዕቅድ ይሏችኋል እንግዲህ ይህ ነው!
         ለብዙ ሰው አዲስ ዓመት ከእቅድ አንፃር ብቻ ሳይሆን ከመጠጣት፣ ከመልበስ፣ ከዝሙት እንዲሁም ከብዙ ምድራዊ ክፉ ነገሮች ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ለመኖር ብቻ ሳይሆን ለማጥፋትም ይታቀዳል፡፡ አዲስ ዓመትን ሕሊናዊ ከሆነ ነገር ጋር እንጂ ቁሳዊ ከሆነ ነገር ጋር ማያያዝ ትርፉ በጣም ትንሽ ነው፡፡ እኛም ልክ እንደ ዳዊት “በጎ ዘመንን ለማየት የሚወድድ ማነው?” (መዝ. 33÷12) ብልን እንጠይቅና በጎ ዘመንን ለማየት፡-
1. ላለፈው ስህተት ይቅርታ ማድረግ፡- አብሮን መሻገር የሌለበት ነገር ቢኖር በደል ነው፡፡ እኛ በሰው ላይ የሠራነውን ይቅርታ በመጠየቅ፣ ሌሎች በእኛ ላይ ላደረጉብን ደግሞ ይቅርታ በማድረግ እንዲሁም በእግዚአብሐር ላይ ላሳየነው አመጽ ንስሐ በመግባት ያለፈውን የዘመን ምእራፍ በመዝጋት አዲሱን መጀመር ይኖርብናል፡፡ ቤታችንን ስናድስ ቀለም ስንቀባ ቁሻሻውን ስናስወግድ የሕያው እግዚአብሔር ቤተ መቅደስ የሆነው ሰውነታችን ቅድሚያ ሊሰጠውና ሊታለፍ የማይገባው ነው፡፡  
2. እንደ ዘመኑ ሳይሆን እንደ ጌታ አሳብ መኖር፡- በየዘመኑ በኑሮአችን  ውስጥ የምናስተውላቸው በበጎም ይሁን በመጥፎ ለየት ያሉ ነገሮች አሉ፡፡ የሩጫ ሰሞን ሁሉም ለሩጫ በሚሆን መንገድ ትጥቁን አሟልቶ ሲሮጥ፣ የኳስ ወቅት ደግሞ ሁሉም መንደሩን በኳስ ሲያጥለቀልቀው ደግሞ ጊዜው የዘፈን እንደሆነ ሲታሰብ ሁሉም ሲያንጎራጉር እናስተውላለን፡፡ ብዙ ሰው እንደ ዘመኑ መኖርን ቋሚ የሕይወት መመሪያው አድርጓል፡፡ ሲሞቅ ሞቅ፣ ለብ ሲል ለብ፣ ሲቀዘቅዝ ደግሞ ቅዝቅዝ ማለት ለብዙኃኑ አልከበደም፡፡ ዘመንን በጎ ለማድረግ ግን በየትኛውም ሁኔታ ውስጥ እንደ እግዚአብሔር አሳብ መኖርን መለማመድ ያስፈልጋል፡፡
3. ተግባራዊ መሆን፡- በጎ ቃል ለመናገር ከምናሳየው ትጋት በበለጠ የተናገርነውን ተግባራዊ ለማድረግ ቆራጥነት ማሳየት ይኖርብናል፡፡ ሕይወት ጥልቅ ትርጉም ስለምትጠይቅ እያንዳንዱ ሰው በእድሜው ሁሉ ዓላማዬ ምንድነው? ማለት አለበት፡፡ ስለዚህ አስተዋይና ጥበበኛ ሰው በሕይወቱ ሊያሳካው የሚፈልገው ዓላማ ይኖረዋል፡፡ ነገር ግን መፈለግ ብቻውን በቂ አይሆንም፡፡ ተግባራዊ መሆንም ያስፈልጋል፡፡ በዚህ ምድር ላይ ሕይወት በጣም አጭር ናት፡፡ ቀኖቻችንን በማለም ብቻ ልናሳልፋቸው አግባብ አይደለም፡፡ ስለዚህ አጫጭር እቅዶቻችሁን ከረጅም ጊዜ ዓላማዎቻችሁ ጋር ለማዛመድ ሞክሩ፡፡ ሕይወት እናስተውላትና ሙሉ ትኩረታችንን እንሰጣት ዘንድ ከእግዚአብሔር የተቀበልናት አጭር፣ ውድና ድንቅ ስጦታ ናት፡፡ ስጦታ ደግሞ የተቀባዩን እንክብካቤና ትኩረት ይሻል፡፡ አማኝ፣ ብልህ፣ አስተዋይና ንቁ ሰው ደግሞ ዘመኑን ሙሉ ተግባራዊ ነው፡፡ በዘመን በረከት የተቀበለን ለእርሱ ዘመን የማይቆጠርለት ጌታ ስሙ ብሩክ ይሁን!
          

Tuesday, September 4, 2012

የተወጋ ሲረሳ (ክፍል ሦስት)


                
“ . . . . ዮፍታሔን፡- የልዩ ሴት ልጅ ነህና በአባታችን ቤት አትወርስም ብለው አሳደዱት፡፡ ዮፍታሔም ከወንድሞቹ ፊት ሸሽቶ በጦብ ምድር ተቀመጠ ምናምንቴዎችም ሰዎች ተሰብስበው ዮፍታሔን ተከተሉት” (መ. መሳ. 11÷2)፡፡
          በድህነት ውስጥ ባለጠግነት፣ በመዋረድ ውስጥ ክብረት፣ በመሰደድ ውስጥ ዕረፍት እንዳለ ማመን ለአብዛኛው የሰው ልብ ከባድ ነው፡፡ ነገር ግን በልቶ ጠጥቶ መራብ መጠማት፣ ለብሶ አንቀላፍቶ ሥጋት እርዛት ካለ፤ እየተራቡ መጥገብ፣ እየተጠሙ መርካት፣ እየተሰደዱ ማረፍ፣ እየተዋረዱ መክበር፣ እየሞቱም መኖር እንዳለ እናስተውላለን፡፡ በእምነት ስንኖር በመከራ ውስጥ ምቾትን የምናስተውልበት ኃይል እናገኛለን፡፡ በዮፍታሔ ሕይወት ውስጥ የምናየው ነገር ይህንን ይመስላል፡፡ የልዩ ሴት (የጋለሞታ) ልጅ ቢሆንም ነገር ግን ጽኑዕ ኃያል ሰውም ነበረ፡፡
          ሐዋርያው “ያልታወቁ ስንባል የታወቅን ነን፣ የምንሞት ስንመስል እነሆ ሕያዋን ነን፣ የተቀጣን ስንሆን አንገደልም፣ ሀዘንተኞች ስንሆን ዘወትር ደስ ይለናል፣ ድሆች ስንሆን ብዙዎችን ባለጠጎች እናደርጋለን፣ አንዳች የሌለን ስንሆን ሁሉ የእኛ ነው (2 ቆሮ. 6÷9)” እንዳለ ክርስትና በምድራዊው ልደት የምንብራራበት ሳይሆን በመንፈሳዊው ልጅነታችን የምንታይበት ኃይል ነው፡፡ በሰው ዘንድ አለመታወቅ ቢሆንም በሰማያዊው ስፍራ በሕይወት መዝገብ ላይ ስማችን ተጽፎአል፡፡ በሥጋ ከሚሆንብን ልዩ ልዩ መከራ የተነሣ ቀኑን ሁሉ ብንገደልም ነገር ግን ሕያዋን ነን፣ በሰው ፊት ዘወትር ሀዘን ቢከበንም በእግዚአብሔር ፊት ካለን መጽናናት የተነሣ ግን ሁል ጊዜ በጌታ ደስ ይለናል፡፡ በድህነታችን ውስጥ ለሌሎች የሚተርፍ ባለጠግነት አለ፣ አንዳች እንደሌለን ብንኖርም ሁሉ ግን የእኛ ነው፡፡
          ዮፍታሔ በሰው ፊት ያለውን እሳቤ ስንመለከት “የጋለሞታ ሴት ልጅ” ነው፡፡ ከእግዚአብሔር ዘንድ የነበረውን ምስክርነት ስንመለከት ደግሞ “ጽኑዕ ኃያል ሰው” ነበር፡፡ ምን ጊዜም ከራስ ጋር ጸብ የሚጀመረው ሰውና ልባችን ከሚነግረን ነገር ጋር ስንቆም ነው፡፡ እግዚአብሔር ከሚለው ጋር መስማማት ሲኖረን ግን ልካችንን የምናስተውልበት እድል ይኖረናል፡፡ ሰዎች የሚሉን፣ የሚያስታውሱን እንዲሁም እኛን የሚዳኙበት መንገድ ልባችንን የሚያደማ፣ ዓይናችንን የሚያስነባ ሊሆን ይችላል፡፡ ዳሩ ግን መቼም ቢሆን እግዚአብሔር ፊት ጌታ እግዚአብሔር ስለ ኢዮብ የሚናገረው እንጂ የሰይጣን ክስና ሙግት ልክ አይሆንም (ኢዮ. 1÷6)፡፡ የሚወራው ሁሉ እውነት አይደለም! እግዚአብሔር ያለው ግን የሰውን ልክ ይዳኛል፡፡
        ዮፍታሔ የልዩ ሴት ልጅ መሆኑ ከአባቱ ቤት ሊያገኝ የሚገባውን ውርስ አስከለከለው፡፡ ጌታ ከነገድ፣ ከቋንቋ፣ ከወገንና ከሕዝብ ዋጅቶ ለእግዚአብሔር ልጆች አድርጎናልና ወራሾች ነን፡፡ በእርሱ ዘንድ የቤትና የእንጀራ ልጅ የሚባል ልዩነት የለም፡፡ ዮፍታሔ እናቱን መርጦ አካባቢውን ወስኖ አልተወለደም፡፡ ነገር ግን እርሱ መርጦ ባላመጣው መጡበት የገዛ ወንድሞቹም አሳደዱት፡፡ ልክ እንደ እርሱ ሁሉ ሰላምታ የሚያስከለክሉ፣ በጎ ቃል የሚያስነፍጉ ብዙ ጉዳዮችን በኅብረተሰባችን መካከል እንታዘባለን፡፡
        ሰው ከተፈጥሮ በተቀበለው ነገር አይፈረድበትም፡፡ እንደ እውነት ከሆነም የዮፍታሔን ጽኑዕ ኃያልነት የጋለሞታ ሴት ልጅነቱ ሊሸፍነው አይገባም ነበር፡፡ ሰው ግን በሥጋና በደም ማስተዋል ውስጥ ብቻ ሲሆን ከዚህ ተሻግሮ ጽናትና ኃይልን ሊመለከት አይችልም፡፡ የዮፍታሔ ታሪክ ግን የልዩ ሴት ልጅ መሆኑ ብቻ አልነበረም፡፡ እርሱ ጽኑዕ ኃያል ሰውም ነበር፡፡ ስለ ሰዎች የድካም ታሪክ ስንሰማ የምንጠብቀው የበለጠ ድካምን ከሆነ ጨለምተኞች እንሆናለን፡፡ ሰው የኃይልና የጽናት ክፍልም አለው፡፡ ስለወደቀ ስናወራ መነሣትን እያሰብን፣ ስለተቸገረ ስንናገር ማግኘትን እያስተዋልን፣ ስለ ሞት ስንነጋገርም ትንሣኤን እያወጅን ከሆነ ለተስፋ መቁረጥ የእግር እሳት ነን፡፡
        ከጠላትህ አንድ ጊዜ ከወዳጅህ ደግሞ ሺህ ጊዜ ተጠንቀቅ እንደተባለ ሰምተናል እኔ ግን ልጠይቃችሁ “ከወንድምስ” ስንት ጊዜ እንጠንቀቅ? ሰዎች ጭንቅላታቸውን ይዘው፣ አፋቸውን ከፍተው፣ እንባቸውን እየረጩ የልባቸውን በአንደበት ሲጮኹ ምን እንደሆኑ ለመስማት ጓጉተን ስንጠጋቸው የወንድም ባዳ፣ የወገን ምድረ በዳ እንደገጠማቸው አምርረው ያወጉናል፡፡ ዮፍታሔ ወንድሞቹ ናቸው ያሳደዱት፡፡ እርሱም ከፊታቸው ሸሸ!
        ዘመናችንን ስንዋጀው ሰው ከወንድሙ ፊት የሚሸሽበት ነው፡፡ ጌታ ወንድሞች ብሎ ሊጠራን አላፈረምና ወንድምነት ብርቱ ቅርበት ነው (ዕብ. 2÷13)፡፡ ደስታን እንደ ራስ ደስታ መቁጠር ብቻ ሳይሆን መከራንም እንደ ራስ መከራ የመቁጠር ሂደት ነው፡፡ ከሚያዝኑ ጋር የምናዝንበት ከሚደሰቱ ጋር የምንደሰትበት ምክንያትም ሌሎችን እንደ ወንድም መቁጠር ነው፡፡ ለዮፍታሔ ከወንድሞቹ ፊት ይልቅ የጦብ ምድር መሸሸጊያ ነበር፡፡ ወንድም ፊት ለነሳችሁ፣ ወዳጅ ለጎዳችሁ፣ ቀን ለጨለመባችሁ ሁሉን የሚችል ልዑል እግዚአብሔር የሚሸሽግ አምባ የሚያሳድር ጥላ ነው፡፡ እኛ ብንገፋም ጌታ ግን አይገፋም፡፡ እኛ ብንሰደድ እግዚአብሔር አይሰደድም፡፡ እኛ ብንታሠር ቃሉ ግን አይታሰርም (2 ጢሞ. 2÷9)!!
                                              - ይቀጥላል -  

Monday, August 20, 2012

የተወጋ ሲረሳ (ክፍል አንድ)



       የወደደንን መውደድ፣ የጠላንን መጥላት፣ ለዋለልን መስጠት፣ ለነፈገን መንሣት፣ ላሰበልን መራራት፣ ለዘነጋን መክፋት የብዙኃኑ የሰው ልጅ የአኗኗር መመሪያ ነው፡፡ ምንም እንኳን በጸጋ ዘመን ላይ ብንገኝም ዓለም ገና ዓይን ስለ ዓይን፣ ጥርስ ስለ ጥርስ፣ እጅ ስለ እጅ ከሚለው ምላሽ አልጸዳችም፡፡ እንዲያውም በዚህ ሕግ ግልጽ ሆኖ ከሚስተዋለው ለጠሉኝ እሬት አይነት አካሄድ በበለጠና በረቀቀ መንገድ ሰዎች የልባቸውን ፈቃድ እያረኩ ነው፡፡ ለብዙ ክርስቲያኖች እንዲህ ያለውን እሾህን በእሾህ፣ ደምን በደም የመመለስ ኑሮ ከእምነት ጋር አቻችሎ ማስኬድ አልከበዳቸውም፡፡ ክፉውም ጋር ደጉም ጋር ቋሚ ተሰላፊ የሆኑ ጥቂት ሆድ ሲብሳቸው “ያስቀመጥኩትን ቆንጨራ እንዳላመጣው?” በማለት የሚዝቱ ሁሉን ትተው ሳይሆን ሁሉን ለክፉ ቀን አስቀምጠው የተከተሉት አይናችን ስር ናቸው፡፡
         አብዛኞቻችን ሰው በሚለውና ክርስቲያን በሚለው መጠሪያ መካከል ያለውን ልዩነት ልብ አንለውም፡፡ ሰው ከምድራዊው ጥሪ ተካፋይ የሆንበት መንገድ ሲሆን፤ ክርስቲያን የሚለው ደግሞ ከሰማያዊው ጥሪ ተካፋይ የሆንበት መንገድ ነው፡፡ ሰው በመሆን ውስጥ በምድራዊ ስፍራና በሥጋዊ በረከት መርካት ሲስተዋልበት፡፡ (ማለትም በዚህ ምድር የምንሰበስበው ሁሉ ከፀሐይ በታች ሲሆን) ክርስቲያን በመሆን ውስጥ ደግሞ በሰማያዊ ስፍራና በመንፈሳዊ በረከት መባረክን እናስተውላለን (ኤፌ. 1÷3)፡፡
         ሰው በመሆን ልደት ይህንን ዓለም በሥጋና በደም አቋም ሆነን እንቀላቀላለን፡፡ ክርስቲያን በመሆን (ዳግም በመወለድ) ደግሞ የዘላለም ሕይወትን መቀላቀል ደግሞም የተዋረደው ሥጋችን የጌታን ክቡር ሰውነት መስሎ በሰማይ ከእርሱ ጋር እንነግሳለን፡፡ ስለዚህ ክርስቲያን ሁሉ ሰው መሆንን ቢጋራም ሰው ሁሉ ግን ክርስቲያን አይደለም፡፡ በዚህም ክርስቲያን መሆን ሰው ከመሆን በእጅጉ ከፍ ያለ እንደሆነ እንገነዘባለን፡፡
         “ቀኝ ጉንጭህን በጥፊ ለሚመታህ ሁሉ ሁለተኛውን ደግሞ አዙርለት፣ እንዲከስህም እጀ ጠባብህን እንዲወስድ ለሚወድ መጎናጸፊያህን ደግሞ ተውለት፣ ማንም ሰው አንድ ምእራፍ ትሄድ ዘንድ ቢያስገድድህ ሁለተኛውን ከእርሱ ጋር ሂድ” (ማቴ. 5÷38-42)፡፡ ጌታ በዚህ ክፍል  ላይ ያስተማረው ትምህርት ሰው በሚለውና ክርስቲያን በሚለው ስያሜ መካከል ያለውን ተግባራዊ ልዩነት ግልጽ ያደርግልናል፡፡ በመጀመሪያ እግዚአብሔር ለሚያዘን ነገር ሁሉ የምንፈጽምበትን ኃይል እንደሚሰጠን መተማመን በዚህ ክፍል የተገለጸውን ትምህርት በቅንነት ለመረዳት ወሳኝ ነገር ነው፡፡ ቀኝ ጉንጭን በጥፊ መመታት ውስጥ ያለው ክርስትና ሳይሆን ሰው መሆን ነው፡፡
            እጀ ጠባብን ለሚወስድ ያንኑ መተው ሰው በመሆን ደረጃ የሚከናወን ተግባር እንጂ ክርስቲያን መሆንን አይጠይቅም፡፡ አንድ ምእራፍ በመሄድ ውስጥም እንዲሁ ከክርስትና ይልቅ ያለው ሰው መሆን ነው፡፡ የክርስትናው የአኗኗር ልኬት የሚጀምረው ታዲያ የቱ ጋር ነው? ካልን ሁለተኛውን ጉንጭ በመስጠት፣ መጎናጸፊያን በመጨመር፣ ሁለተኛውን ምእራፍ በመሄድ የሚል ይሆናል፡፡ ከዚህ ያነሰው ግን ማንም ሰው ከሰብአዊ ርኅራኄ በመነሣት አልያም ከሥጋ ሕግ በመነጨ ሁኔታ የሚከውነው ነው፡፡ “የሚወዱአችሁን ብትወዱ ምን ዋጋ አላችሁ? ቀራጮችስ ያንኑ ያደርጉ የለምን? ወንድሞቻችሁንም ብቻ እጅ ብትነሡ ምን ብልጫ ታደርጋላችሁ? አሕዛብስ ያንኑ ያደርጉ የለምን?” (ማቴ. 5÷46)፡፡
         የነከሰንን ማጉረስ፣ የበደለንን መካስ፣ የተጣላንን ገፍቶ መታረቅ፣ የረገመንን ከልብ መመረቅ ተወግቶ እንደ መርሳት ነው፡፡ ጉዳቱ እያለ በደልን አለመቁጠር፣ ስቃዩ እየታየ ጥፋትን መተው፣ ጉድለቱ እየተስተዋለ ኪሳራን አለማስላት መንፈሳዊ የኑሮ ልዕልናን ይጠይቃል፡፡ ክርስትና የተወጋ ሲረሳ ነው!
         ከብሉይ ኪዳን በዳዊትና በሳኦል መካከል የነበረው የገፊና ተገፊ፣ ያሳዳጅና ተሰዳጅ፣ የጠዪና ተጠይ ታሪክ ለተነሣንበት ርእስ ጥሩ ማሳያ ነው፡፡ የመጀመሪያው የእስራኤል ንጉሥ ሳኦል ወደ ንግሥና የመጣበትን መንገድ የስነ መለኮት አዋቂዎች ሲያስረዱ “እግዚአብሔር ከሕዝቡ ጋር የተስማማበት ሂደት ነው” ይላሉ፡፡ ለዚህም ምክንያቱ ሳኦል የእስራኤል ንጉስ የሆነው እንደ እግዚአብሔር ፍላጎት ሳይሆን በሕዝቡ ፍላጎት ተመርጦ በእግዚአብሔር አጽዳቂነት መሆኑ ነው፡፡
          እግዚአብሔር ሳሙኤልን “እንደጠየቁ ቀባላቸው” በማለት ከሕዝቡ አሳብ ጋር ተስማማ፡፡ ይህም በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ብቸኛው ክፍል እንደሆነ ይነገራል (1 ሳሙ. 15)፡፡ ምን ጊዜም ቢሆን እግዚአብሔር ከአሳባችን ጋር ከተስማማ ኪሳራው የሰው ነው፡፡ ወደኋላ መለስ ብለን ያለፈውን ፍላጎታችንን እና ዛሬ በዚያ ፍላጎት ላይ ያለንን አተያየት ብንመለከተው ለየቅል ነው፡፡ ያኔ እግዚአብሔር በፊቱ ካቀረብነው አሳብ ጋር ተስማምቶ ቢሆን፤ እንደጠየቅነው ሁሉን ቢሰጠን ኖሮ ዛሬ ከምናፍርበት ነገር ጋር ለመኖር  በተገደድን ነበር፡፡
          እግዚአብሔር ሲሰጥ ብቻ ሳይሆን ሲከለክል፣ ሲመልስ ብቻ ሳይሆን ዝም ሲል፣ ሲያኖር ብቻ ሳይሆን ሲገድልም አይሳሳትም፡፡ የእርሱ ጌትነት ምቾትን ብቻ ሳይሆን ጉስቁልናንም ያጠቃልላል፡፡ ክርስትና መብዛትን ብቻ ሳይሆን መዋረድን፣ መጥገብን ብቻ ሳይሆን መራብን፣ ከፍታን ብቻ ሳይሆን መጉደልንም ማወቅ ጭምር ነው (ፊል. 4÷12)፡፡ ስለዚህም አሳቡን እንስማማበት፣ መንገዱን እንጓዝበት ዘንድ እግዚአብሔር ከእኛ አሳብና መንገድ እጅግ የራቀ ነው፡፡ እርሱ ከፍላጎቶቻችን ጋር ሳይሆን እኛ ከእርሱ ፍላጎት ጋር፤ ከምርጫዎቻችን ጋር ሳይሆን እኛ ከእርሱ ፈቃድ ጋር፣ ከልባችን ጋር ሳይሆን እኛ ከልቡ ምክር ጋር  እንስማማ ዘንድ አግባብ ነው፡፡
           ዳዊት እግዚአብሔር በጠላቶቹ ፊት ለፊት በዘይት የቀባው፣ ከወንድሞቹ መካከል ለይቶ በአባቱ ንቀት ፊት ያከበረው ሰው ነው፡፡ ትልቁ እግዚአብሔር በብላቴናው ሕይወት ኃይሉንና ክብሩን ይገልጥ ዘንድ ስለወደደ ከበጎች ጥበቃ ወደ ንግሥና አመጣው፡፡ ሰው እኛን ወደተሻለ ነገር ለማምጣት ደረጃ በደረጃ ይሠራ ይሆናል፡፡ እግዚአብሔር ግን ከትቢያ አንስቶ ወደ ልዕልና ለማምጣት እርከን አያስፈልገውም፡፡ ዳዊት በሳኦል መንግሥት ዘመን ለሕዝቡ ፍርሃት፤ ለመንግስቱ ሥጋት የሆነውን ጎልያድ በእግዚአብሔር ስም በማሸነፍ ባለ ውለታ ነው፡፡ ከድሉ በኋላም ቤተ መንግሥት ውስጥ በገና በመደርደር የሳኦልን ርኩስ መንፈስ በማውጣት ለሳኦል ባለ ውለታ ነው፡፡ የሳኦል ምላሽ ግን ዳዊት ካደረገው ቅንነት ፍፁም ተቃራኒ ነበር፡፡ ሳኦልን ሊቀበል የወጣው ሕዝብ ለዳዊት በመዘመሩ (እልፍ ገደለ) እጅግ ተቆጣ፡፡ በገናምም እየደረደረ ሳለ ከግንቡ ጋር አጣብቀዋለሁ በማለት በእጁ የያዘውን ጦር ወረወረበት፡፡   
          በክፉዎችና በበጎዎች ላይ ፀሐይን የሚያወጣ እግዚአብሔር ሁሉ በፊቱ የተራቆተለት አምላክ ነው፡፡ የአመፀኛውን አመጽና የትሁቱን ትህትና የእርሱ ጽድቅ በእውነት ይዳኛል፡፡ ዳዊት እንዲህ ባለው ጌታ ፊት አንደኛ ሳኦል የሚያደርግበትን ክፉ፤ ሁለተኛ ለሳኦል የሚያደርግለትን መልካም ነገር አይቆጥርም ነበር፡፡ ለዳዊት ጤና ይህ ነበር!
       በሕይወታችን ውስጥ ከሚስተዋለው ድካም መካከል ያደረግነውን መልካም መተሳሰብና የተደረገብንን ክፉ መቁጠር በጉልህ የሚስተዋል ነው፡፡ የእግዚአብሔር ሰው ዳዊት የወንድሞቹን ጥላቻ፣ የአባቱን መናቅ፣ የሳኦልን ማሳደድ የተበቀለበት ትልቁ መንገድ መርሳት (አለመቁጠር) ነው፡፡ ሰው በቀል የተጠማ ልቡን የሚያረካበት መንገድ በደልን መቁጠር እንዲሁም ለበደሉ ተመጣጣኝ ምላሽ በመስጠት ነው፡፡ ነቢዩ ግን ሁሉን ማድረግ በሚችል እግዚአብሔር ፊት የተደረገበትን ይተወው ነበር፡፡ ሳኦል ጦርን ያህል ነገር ወርውሮበት ምድረበዳ ለምድረበዳ ሲያሳድደው የሚያደርገውን እንደማያውቅ ምስኪን ሰው ይቆጥርለት ነበር፡፡ እግዚአብሔር ከእኔ ጋር ነው! ብሎ ጉልበቱን ለማጥፋት አልተጠቀመበትም፡፡ ለሚያምኑ ሁሉ የእግዚአብሔር ኃይል ለማዳን ነው (ሮሜ. 1÷16) ተብሎ እንደተፃፈ የእግዚአብሔር የሆኑቱ ጉልበታቸውን በደልን ለመርሳት እንጂ ለመቁጠር አያውሉትም፡፡
                                                                               - ይቀጥላል -
      
     ውድ የቤተ ፍቅር ብሎግ ተከታታዮች በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስና በክቡር ጠቅላይ ሚኒስትራችን ሞት የተሰማንን ሀዘን ለመግለጽ እንወዳለን፡፡ ጌታ እግዚአብሔር ምድሪቱንና ሕዝቡን ይባርክ!!    

Wednesday, August 15, 2012

የግያዝ ዓይኖች


             
         ከሆነብን በላይ የሆነውን የምንተረጉምበት፣ ከሰማነው በላይ ያደመጥነውን የምንረዳበት፣ ከመጣው ፈተና በላይ መከራውን የምናስተናግድበት መንገድ ጽናታችንንም ሆነ መብረክረካችንን ይወስነዋል፡፡ ልጅ እያለን በጨለማ ስንሄድ አንዱ ዛፍ እንደ ብዙ ዛፍ፣ አንድ ድምጽ ልክ እንደ ብዙ ውኃዎች ድምጽ፣ አንድ ሰውም እንደ ትንሽ መንጋ ሆኖ ይታየን ነበር፡፡ በብዛት ብቻ ሳይሆን በኃይልም የምንረዳበት መንገድ ከሆነው በእጅጉ የተጋነነ ነው፡፡ የቅጠል መተሻሸት፣ የነፋስ ሽውታ፣ የሌሊት ወፍ ድምጽ ልክ እንደ አንበሳ ግሳት፣ እንደ ነብር ፍጥነት፣ እንደ ዲያብሎስ ትጋት ተቆጥሮ ልባችን ይሸነፍበታል፡፡ በሕይወታችን ድንግዝግዝ ነገር ሲበዛ አጥርቶ ማየት ከባድ ነው፡፡ በልኩም መረዳት አስቸጋሪ ነው፡፡ ከከበበን ብዙ መፍትሔ ይልቅ ጥቂት ችግራችንን እሽሩሩ ማለት ይቀናናል፡፡
         በአካል ካደግን፣ በአእምሮ ከበሰልን፣ የኑሮ ተግዳሮቶችን መጋፈጥ ከጀመርን በኋላ የምንፈተነው የሆነውን በሆነው ልክ ማየት ባለመቻል ነው፡፡ መከራ አይለመድም፡፡ የሕይወት ዘመን እንግዳ፤ የየማለዳው አዲስ ነው፡፡ ሰው ወድዶ አለመደሰት ይችላል፡፡ አለመፈተን ግን ከቶ አይችልም፡፡ በደስታ ላይ በርን መዝጋት ይቻላል፤ ችግር ግን የተዘጋውንም ጥሶ ይዘልቃል፡፡ የምስራቹን አልቀበልም ያሉ ዛሬ የበዪ ርሀብተኛ፣ የአዋቂ መሀይም፣ የብልጥ ተላላ፣ የዘናጭ ታራዥ፣ የትጉህ ብኩን ሆነዋል፡፡ ጌታ ግን በተዘጋው ደጅ የሚያልፍ መፍትሔ አለው፡፡ እርሱም “ሰላም ለእናንተ ይሁን” (ዮሐ. 20÷19) አላቸው፡፡
       በማንኛውም አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ሰይጣን የሚዘጋቸው፤ ሥጋም መጋረጃ ሆኖ የሚከልላቸው ነገሮች ይኖራሉ፡፡ እምነት ግን ከተዘጋው ባሻገር ማየት ነው፡፡ ከሚታየው አልፎ የማይታየውን መመርመር ነው፡፡ ከሥጋ ሁኔታ ወደ መንፈሳዊው ሁኔታ፤ ከዚህ ዓለም አሳብ ወደ ሰማያዊው አሳብ ከፍ ማለትም ነው፡፡ እምነት ከሥጋ አይን ልኬት፣ ከጆሮ የመስማት ደረጃ፣ ከአካልም የመስራት ኃይል በላይ ነው፡፡ ግዙፉን ጎልያድ በአንድ እዚህ ግባ በማይባል ብላቴና ፊት ያሳነሰው እምነት ነው፡፡ ለአሥሩ ሰላዮች በከነዓን የሚኖሩትን ሕዝብ ያገነነው ደግሞም ለእስራኤል ማኅበር ፍርሃትን እንዲያወሩ ያደረገው የእምነት ማነስ ነው፡፡ እነርሱም ሲናገሩ “በዓይናችን ግምት እንደ አንበጣዎች ነበርን ደግሞ እኛ በዓይናቸው ዘንድ እንዲሁ ነበርን አሉ” (ዘኁ. 13÷33)፡፡ እግዚአብሔር ደግሞ  ”“እኔ ሕያው ነኝና በጆሮዬ እንደተናገራችሁት እንዲሁ በእውነት አደርግባችኋለሁ” (ዘኁ. 14÷28) አለ፡፡ እንደ ቃሉም ሁሉን በሚችል አምላክ ፊት ያጉረመረሙት በሙሉ በምድረ በዳ ሞቱ፡፡
       በመጽሐፈ ነገሥት ካልዕ ምእራፍ 6 ላይ የሶርያ ንጉሥ ከእስራኤል ጋር ሊዋጋ ወደ ሕዝቡ እንደመጣ እናነባለን፡፡ ንጉሡም ፈረሶችንና ሰረገሎችን እጅግም ጭፍራ ሰደደ በሌሊትም መጥተው ከተማይቱን ከበቡ፡፡ የእግዚአብሔር ሰው ኤልሳዕ ሎሌ የሆነው ግያዝም “ጌታዬ ሆይ ወዮ ምን እናደርጋለን?” አለው፡፡ ግያዝ እንዲህ ሊናገር የቻለው ኤልሳዕ እንደሚያይ ማየት ባለመቻሉ ነው፡፡ የኤልሳዕ ዓይኖች ግን ከተማይቱን በከበቡት የሶርያ ንጉሥ ጭፍሮችና ድቅድቅ በሆነው ጨለማ ላይ ሳይሆን ያረፉት ከከበባቸው ሠራዊት በላይ በሆነው እግዚአብሔር ላይ ነበር፡፡ “ክርስቶስን ተመልከቱ” (ዕብ. 3÷2)!
       በኑሮ ውስጥ ብዙ የሚከቡን ነገሮች አሉ፡፡ የዚህ ዓለም ከንቱ አሳብ፣ የሰይጣን ውጊያ፣ የሕይወት ውጣውረድ፣ ድካምና ኃጢአት እነዚህ ሁሉ በዙሪያችን ያሉ የዕለት ከዕለት ፈተናዎች ናቸው፡፡ እምነት ግን ከሁኔታ ባላይ መኖር የምንችልበት ኃይል ነው፡፡ በእምነት ዓይን ፊት የማይቀልና የማያንስ ነገር የለም፡፡  ተወዳጆች ሆይ እኛ በኑሮ ሠልፍ ላይ ያለን ዓይን የግያዝ አይነት ነው ወይስ የኤልሳዕ? በዙሪያችን ያለው ችግር ወይስ ከእኛ ጋር ያለው እግዚአብሔር ነው የሚበልጥብን? ችግር ተኮፍሶ መፍትሔው ካነሰ ውጤቱ እንደ ሎሌው መፍራት ነው፡፡ ነቢዩ ዳዊት “መክበቡንስ ከበቡኝ በእግዚአብሔርም ስም አሸነፍኋቸው” (መዝ. 117÷11) ይላል፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞን ደግሞ  “የእግዚአብሔር ስም የጸና ግንብ ነው ጻድቅ ወደ እርሱ ሮጦ ከፍ ከፍ ይላል” (ምሳ. 18÷10) ይለናል፡፡ ከዚህ ዓለም ጥበብ የእግዚአብሔር ሞኝነት እጅግ እንደሚበልጥ ስናስተውል በአባትና ልጅ የተናገሩት እነዚህ ቃላት ለልባችን ይጠጋሉ፡፡
         የእግዚአብሔር መቻል የማይቻለውንም ይጠቀልላል፡፡ እርሱ እንዲያደርግልን የምንፈልገውን ሁሉ ቢያደርግልን እንኳ መቻሉ እዚያ ጋር አይቆምም፡፡ ከዚያም በብዙ ያልፋል፡፡ ኢዮብ ስለ እግዚአብሔር መቻል “ሰሜንን በባዶ ስፍራ ላይ ይዘረጋል ምድሪቱንም በታችዋ አንዳች አልባ ያንጠለጥላል ውኆችን በደመናዎቹ ውስጥ ያስራል ደመናይቱም ከታች አልተቀደደችም፡፡ . . . . ይህም የሰማነው ነገር ምንኛ ጥቂት ነው!” (ኢዮ. 26÷7) በማለት ይናገራል፡፡ በእርግጥም ሰማያት በመንፈሱ ውበት ያገኙበት፣ ምድር ከተግሣጹ የተነሣ የምትደነግጥለት፣ ስሙን ሰምቶ ሞት የሚብረከረክለት፣ ክብሩን አይተው ቀላያት የሚሰነጣጠቁለት ጌታ ሁሉን ያደርግ ዘንድ እንዴት አይችልም? አባቱን እንደሚገባ ያልተረዳው ልጅ የአባቱን አቅም በሁኔታ፣ በሰውና በቦታ መገደቡ የሚደንቅ ሊሆን አይችልም፡፡ እግዚአብሔርን የምናርፍበት በእምነት የተረዳነውን ያህል ነው፡፡  
            ግያዝ በእግዚአብሔር ፊት እንደ አገልጋይ ቢኖርም እግዚአብሔርን ግን እንደሚያገለግል ባሪያ አልተረዳውም፡፡ እግዚአብሔርን እንደሚያገለግል ተገልጋዩን መረዳት በሚያጸድቅና በሚኮንን በእርሱ ፊት ለመቆም ቀዳሚው ነገር ነው፡፡ ግያዝ እግዚአብሔር ለሶርያው ንጉሥ አለቃ ንዕማን የሰጠውን ደኅንነትና የገለጠውን ኃይል ተመልክቶአል፡፡ ዳሩ ግን በሶርያ ወታደሮች ፊት በእምነት እንዲቆም አላስቻለውም፡፡ አልዓዛር ከመሞቱ በፊት ማርያም በጌታ እግር ስር ቁጭ ብላ እንደተማረች ቃሉ ይነግረናል (ሉቃ. 10÷38)፡፡ ነገር ግን አልዓዛር ከሞተ በኋላ ማርያም በጌታ እግር ስር እንደተማረ ስትመልስ አናያትም፡፡ በሀዘን ሠልፍ ፊት አይኖችዋ ልክ እንደ ግያዝ ያሉ ነበሩ፡፡ ጌታ ግን አላት ትንሣኤና ሕይወት እኔ ነኝ በእኔ የሚያምን ቢሞት እንኳን ሕያው ነው፡፡ (ዮሐ. 11÷25)
       ችግር ወደ ሕይወታችን ሲመጣ “በኤልሳዕ ዙሪያ ያሉት የእሳት ፈረሶችና ሰረገሎች ተራራውን ሞልተውት ነበር” የሚለውን ማስተዋል ያቅተናል፡፡ ከሶርያ ጭፍሮች መክበብ በላይ በኤልሳዕና በሎሌው ዙሪያ ያሉት ይበልጡ ነበር፡፡ በግልጥ የምናየው በሥጋና በመንፈስ ሠራዊት መካከል ያለ ልዩነት ነው፡፡ በሰማያዊ ኃይልና በምድራዊ አቅም መካከል የነበረ ፍጥጫ ነው፡፡ በእምነትና በራስ ትምክህት መካከል በግልጥ የሚስተዋል ልዩነትም ነበር፡፡ ግያዝ በመንፈስ ከማስተዋል ይልቅ በሥጋ ለመዳኘት የቀረበ ነበር፡፡ ከሰማዩም ይልቅ የምድሩ የቀረበው ነበር፡፡ እግዚአብሔር ግን የብላቴኖችን ዓይን ይከፍታል፡፡ “የቃልህ ፍቺ ያበራል ሕፃናትንም አስተዋዮች ያደርጋል” (መዝ. 119÷130)፡፡
        ተወዳጆች ሆይ በዙሪያችሁ ካሉት ጠላቶች ይልቅ ወዳጆቻችሁ ብዙ ናቸው፡፡ ከከበባችሁ ችግር የከበባችሁ መፍትሔ ይበልጣል፡፡ ከሚወረወረው ቀስት ከሚበረው ፍላፃ ይልቅ እንደ ጋሻ የከበበን እውነት ኃያል ነው፡፡ የምትኖሩበት አገርና መንደር ላልተመቻችሁ እግዚአብሔር በተኩላና በእባብ ላይ ያጫማል፡፡ ባርነት ላንገሸገሻችሁ፣ የሰው ፊት ለጠቆረባችሁ፣ ነፃነት ብርቱ ናፍቆት ለሆነባችሁ እግዚአብሔር አንበሳውንና ዘንዶውን ያስረግጣል፡፡ ጌታ ያለማመንን ቅርፊት ከልባችን ላይ ያንሣ፣ በዓይናችን ላይ ያለውን የኃጢአት ሞራ ይግፈፍ፡፡ ሁሉም የሚያየው ገደል በሆነበት ዘመን ተራራው ላይ ያለውን ከፍታ፣ ከትንሽ እስከ ትልቅ በራደበት በዚህ ጊዜ በዙሪያችን ያለውን የእሳት ሠራዊትና መንፈሳዊ ኃይል በእምነት እንድናስተውል ጸጋ ይብዛልን፡፡