Friday, January 18, 2013

ከዚህም በላይ ደስታ!



                                     
                       

                                        ቅዳሜ ጥር 11/2005 የምሕረት ዓመት


       ከእያንዳንዱ ሰው ጥረት ጀርባ ያለው ጥልቅ መሻት ደስታ እንደሆነ ሁሉ በእግዚአብሔር አሳብ ውስጥ ያለው ከፍታም ደስታ ነው፡፡ እርሱ በሰው ታሪክ ውስጥ ያዘጋጀው ትልቁ ነገር ደስታ ነው፡፡ እግዚአብሔር ማንንም ለሀዘን፣ ለሮሮረ፣ ለመከራና ስቃይ አልፈጠረም፡፡ ዛሬ የምናልፍበት የተበላሸ ነገር ሁሉ የሰው መበላሸት ውጤት ነው፡፡ ነገር ግን ሰው በየዘመናቱ በራሱ መንገድ ደስታን ሲያስስ ኖሮአል፡፡ የደስታ መገኛ ሀብት እንደሆነ ያሰቡ ሰዎች ለዚህ እስከ መጋደል ኖረዋል፣ የሰላም ምንጩ እውቀት እንደሆነ ያሰቡ ወገኖችም የቻሉትን ያህል ለመጠበብ ሞክረዋል፣ ደስታ የሚገኘው ሥልጣን በመያዝ እንደሆነ የተሰማቸው ሰዎችም ለዚህ ታምነው ኖረው አልፈዋል፡፡ ሁሉም በየተሰማራበት ተግባር ለመደሰት ዘወትር ይሻል፡፡

       ደስታን ስለ መፈለግ ስናስብ የጠቢቡ ሰሎሞንን ፍለጋ እናስታውሳለን፡፡ ብዙ ሰው ዝና ቢኖረው የማይቸገር፣ ሀብት ቢኖረው የማይርበው፣ ሥልጣን ቢኖረው የማያዝን ይመስለዋል፡፡ ከእነዚህ አንዱ እንኳ ቢኖረን እንባዎች ሁሉ ከአይኖቻችን እንደሚታበሱ እናስባለን፡፡ ዳሩ ግን ጠቢቡ ሰሎሞን እነዚህን ሁሉ ነገሮች በአንድነት ጠቅልሎ የያዘ ንጉሥ ነበር፡፡

       ኢትዮጵያዊቷ ንግሥተ ሳባ ዝናና ጥበቡን ሰምታ፣ ብዙ ጓዝና እጅ መንሻ ይዛ፣ ቀይ ባህርን አቋርጣ ነፍስ እስከማይቀርላት ድረስ የልቧን ሁሉ የገለጠችለት የእስራኤል ገዥ ነበር(1ነገ. 10÷1-10)፡፡ ለክብሩ የማይንበረከክና በጥበቡ የማይደመም ያልነበረለት ሰሎሞን የሕይወት ትርጉም የጠፋበት የደስታ አድራሻ ግር ያለው ሰው ነበር፡፡ መጽሐፈ መክብብ ምዕራፍ ሁለትን በመንፈስ ሆነን ስናጠና ጥበበኛው እንዴት ባለ ድካምና ጥረት ውስጥ እንዳለፈ የፍለጋውንም ከንቱነት እናስተውላለን፡፡

Tuesday, January 15, 2013

የቆቅ ትዳር



                                                                   

                                             ማክሰኞ ጥር 7/2005 የምሕረት ዓመት

         ከወደ አውሮፓ የሰማሁት አንድ ነገር ትዝ ይለኛል፡፡ ልጅቱ እና ልጁ በእጮኝነት የአራት አመታት እድሜ አስቆጥረዋል፡፡ በእነዚህ ጊዜያት ሁሉ በአንድ እጅ የመብላትና በአንድ አፍ የመናገርን ያህል የፍቅር ቅርበትና መዋደድ ነበራቸው፡፡ ታዲያ ለመጋባት ወስነው ቀን ይቆርጣሉ፡፡ በዚያም ቀን የቤተክርስቲያኑ አዳራሽ በታዳሚ ጢም ብሎ ሙሽራውና ሙሽሪት ለቀለበትና ለፊርማ ስነ ሥርዓት ወደተዘጋጀው መድረክና ይህንን ወደሚያስፈጽሙት የሃይማኖት አባት በእርጋታ ይቀርባሉ፡፡ ድንገት ባል ፊርማውን በተዘጋጀው ምስክር ወረቀት ላይ አስፍሮ እንደጨረሰ የሚስቲቱ ተራ ሲደርስ ቬሎዋን ሰብስባ ከፍ ባለ ድምጽ “አንተ አታገባኝም . . . . አዎ! አንተን አላገባም” እያለች ከአይን ያውጣሽ በሚያስብል ድፍረት በእድምተኛው መሐል ተወራጭታ ወጣች፡፡ ግን ምክንያቷ ምን ይመስላችኋል?

         የጥርን ወር መበሰር ተከትሎ አንድ ነገር ያስተዋላችሁ ይመስለኛል፡፡ የጋብቻ ስነ ሥርዓት ! እንደ እግዚአብሔር ሰው በሁለት ሰዎች አንድ ሥጋ መሆን ደስታ ሲሰማን፤ በትዳር ውስጥ ለሚፈጠረው የከፋ ችግር በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ የጦሱ ሰለባ መሆናችንን ስናስብ ደግሞ ሥጋትና ሀዘን ይከብበናል፡፡ ውድ የቤተ ፍቅር ብሎግ ተከታታዮች ጋብቻን በተመለከተ ብዙ ችግሮች እንዳሉ ያለ ነጋሪ የምናውቀው ሐቅ ነው፡፡

         የአንድን ወንድና የአንዲትን ሴት ትዳር የተሻለ ውበትና ሰላም የሚሰጥ ጥቂት መፍትሔ በልባችሁ እንዳለ ከተሰማችሁ አልያም በዚህ ርዕስ ዙሪያ እኔ ላካፍል የምችለው አሳብና ገጠመኝ አለኝ የምትሉትን ከታች ባለው አስተያየት መስጫ ውስጥ በመፃፍ እንድትወያዩበትና ቆቅማ የሆነውን ግን ጥበብ የሌለውን የትዳር ኑሮ እንታደግ በማለት እንጋብዛለን፡፡ በሚቀጥለው ጽሑፍ ስንገናኝ ከላይ የጠየቅናችሁን ጥያቄ መልስና ሰፋ ያለ ማብራሪያ ለማቅረብ እንሞክራለን፡፡ በጸሎት አግዙን!

                                                               - ይቀጥላል -  
        

Tuesday, January 8, 2013

እንደ ገና ዳቦ . . .




                                    ማክሰኞ ታህሳስ 30/2005 የምሕረት ዓመት

       አንድ ቂመኛ ሰው “ክፉውን በመልካም እንጂ በክፉ አትቃወም” የሚለውን የፍቅር ትምህርት በመቃወም “እንዴት ይህ ሊሆን ይችላል?” በማለት ቡዳሃን (የቡድሂዝም እምነት መስራች) ጠየቀው፡፡ እርሱም ካደመጠው በኋላ “አንድ ሰው ለጓደኛው ስጦታ አዘጋጅቶ ወሰደ፡፡ ነገር ግን ጓደኛው ስጦታውን አልቀበልህም አለው፡፡ በዚህ ጊዜ ይህ ስጦታ ለማን የሚሆን ይመስልሃል?” አለው፡፡ ወጣቱም “ለዚያው ለራሱ ነዋ!” ሲል መለሰ፡፡ ቡዳሃም “መጥፎና ጠማማ ሰው ሰማይን በምራቁ ለማበላሸት ተንጋሎ እንደሚተፋ ሰው ነው፡፡ የጠማማው ሰው ምራቅ ተመልሶ ራሱን ያረክሰዋል እንጂ ሰማይን ማርጠብ አይችልም፡፡ ክፉም እንዲሁ በክፋቱ ሌላውን ከሚጎዳ ይልቅ ራሱን በይበልጥ ሲጎዳ ይኖራል” በማለት ቂመኛውን ሰው አስተማረው፡፡
       ከቡድሂዝም ትምህርት መካከል የማስታውሰውንና ከክርስትና አስተምህሮ ጋር በእጅጉ አንድ የሆነውን ክፍል እንዳስታውስ ያደረገኝ በአገራችን የተለመደ አንድ አባባል ወደ አእምሮዬ ስለመጣ ነው፡፡
“አንተም ክፉ ነበርክ ክፉ አዘዘብህ
እንደ ገና ዳቦ እሳት ነደደብህ፡፡” ይሰኛል፡፡
ሰውየው “የእጅህን ይስጥህ” የሚለው ርግማን እንደተፈፀመበትና ተመጣጣኝ ዋጋ እንደተከፈለው ሌላኛው ወገን “እሰይ” በሚሰኝ እርካታ ውስጥ ሆኖ የተናገረው ቃል እንደሆነ የኃይለ መለኮት ሹም ለነበሩት በዛብህ የተገጠመው ይህ ግጥም ያስረዳናል፡፡

Tuesday, January 1, 2013

የእድሜ በረከት




                                                                                                                              

                                 ማክሰኞ ታህሳስ 23/2005 የምሕረት ዓመት


        እግዚአብሔርን እናመሰግነው ዘንድ ካሉን ምክንያቶች ሁሉ የላቀው ምክንያት ይመስለኛል፡፡ መቼም ሰው ነንና ስለ በላነው ምግብ እንጂ ስላላመጥንበትና ስለዋጥንበት እድሜ ለማመስገን ግንዛቤውም ሆነ ፍላጎቱ የለንም፡፡ እረ እንደውም! ለምንበላውና ለበላነው ለማመስገንም እንፈተናለን፡፡ ማን ነበሩ “ማምሻም እድሜ ነው” ያሉት፡፡ እውነታቸውን ነው ሰው ጥርሱ ያኘከውን፣ አፉ ያመላለሰውን፣ ምላሱ ያጣጣመውን በጉሮሮው የሚያወርደው እድሜው ካለው ነው፡፡ ብዙዎች በአፍና በጉሮሮ ድንበር ላይ በተፈጠረ ፍጥጫ በአይን ተሰናብተውን መቃብር ወርደዋል፡፡ አደራ! የምለውን ከምግብ አንፃር ብቻ እንዳታዩብኝ፡፡ ምክንያቱም ወሬም ያንቃል፡፡ በዚህ የተጎዱ ብዙ ናቸው፡፡ ጌታ ከዚህ ውርደት ይጠብቃችሁ፡፡
         አሁን ምን እያሰብኩ መሰላችሁ የምጽፈው ጣቶቼ በአድማ እንቢ ቢሉ (ባረገው ለምትሉ ይቅር ይበላችሁ)፣ አንደበት ለመናገር ባይታዘዝ፣ ጆሮም ቢተባበራቸው በየትኛው መንገድ እንገናኝ ነበር? መቼም የአይን ጥቅሻ ወረቀት ላይ አይሰፍር? ግን ከዚህ ሁሉ ሥጋት በላይ እድሜው ባይኖርስ? እንኳን ማውራት መሰማማት፣ እንኳን መተያየት መደባበስ፤ መተሳሰብም ሲዳላ ይሆን ነበር (እየዬ ሲዳላ ነው እንዲሉ)፡፡
         ገንዘብና ቁሳቁስ እንደ ትልቅ በረከት በሚቆጠሩበት ማኅበረሰብ መካከል እድሜን እንደ በረከት ማውራት “ከሌለህ የለህም” በሚለው አሳብ ላይ ጅሐድ እንደማወጅ ነው፡፡ መቼም ይህ ብሒል ምንጩ ስለደረቀ በዚህ አንጣላም፡፡ እስቲ አንድ ጊዜ ወንዶች ብቻ “እድሜያችሁ ስንት ነው?” . . . እሺ ጥግ ላይ ያለኸው . . . “ሴቶችን ለምን አትጠይቅም?”፡፡ እሺ እህቶችስ “እድሜያችሁ ስንት ነው?” . . . እሺ መሐል ያለሽው . . . “የእኛ እድሜና ደመወዝ አይጠየቅም”፡፡ የተቀበልነውን መካድ ሰጪውን አያሳስተውም፡፡ የሆነልንን አለመመስከራችን አድራጊውን ከክብር አያሳንሰውም፡፡ ብዙ ከተቀበለ ግን ብዙ ይጠበቅበታልና ስለ እድሜያችሁ ጌታን አክብሩት፡፡
         እየተማርን፣ እየለበስን፣ እየሠራን፣ እየበላን፣ እየወጣን እየገባን፣ በጎ ብቻ ሳይሆን ክፉም እያቀድን ያልከፈልንበት ትልቅ ሀብት እድሜ ነው፡፡ ትላንት አጥታችሁ ዛሬ ያገኛችሁ፣ ትላንት አግኝታችሁ ዛሬ ያጣችሁ፤ ትላንት ተወዳችሁ ዛሬ የተተዋችሁ፣ ትላንት ተጠልታችሁ ዛሬ የተፈቀራችሁ፣ ትላንት ተገፍታችሁ ዛሬ የተከበራችሁ፣ ትላንት ታቅፋችሁ ዛሬ የተዋረዳችሁ እድሜ ባይኖራችሁ ይህንን ፈረቃ እንዴት ታዩት ነበር? እንኳንም ኖረን ከፋን፣ እንኳንም ኖረን ተጠላን፣ እንኳንም ኖረን አጣን፣ እንኳንም ኖረን ታማን፣ እንኳንም ኖረን ተንገዳገድን፤ እንኳንም ኖራችሁ ተሰደዳችሁ፣ እንኳንም ኖራችሁ አለቀሳችሁ፣ እንኳንም ኖራችሁ ሁሉ ሆነ፡፡ “. . . . ሞቴን እመርጣለሁ” ለማን ብላችሁ? እድሜ ውድ ነው! እስኪንጠፈጠፍ ትጉ፣ እስኪሟጠጥ በርቱ፡፡ ታዲያ አደራ ሰጪውን እያመሰገናችሁ!
         አንድ ሰው ሞቶ ቀብር ሄደን መቃብሩ ሥፋራ ስንደርስ አንድ ሰው አለፍ ብሎ ቆሞ ሲቃ እየተናነቀው፣ ጎንበስ ቀና እያለ፣ እንደ መቀነት እጁን ወገቡ ላይ ጠምጥሞ ያለቅሳል፡፡ እኔም ምናልባት በሰው ሀዘን ላይ የራሱን እያዘነ ይሆን በማለት የጆሮዬን ኃይል ጨመርኩ፡፡ ብዙ ጊዜ ሀዘን ላይ ምን ይገርመኛል መሰላችሁ አባታችሁ ሞቶ ለእናታቻው የሚያለቅሱ፣ እህታችሁ ሞታ ለወንድማቸው የሚያነቡ ሰዎች (እነዚህ ሁሉ የሌሏቸውስ? ለምትሉኝ ለቅም አያታቸው)፡፡ ታዲያ እንዲህ ያሉ ሰዎች ሀዘን ቤቱን የለቅሶ ቢፌ (እንደ ምግቡ ያለ) ያስመስሉታል፡፡ አንድ ሞቶባችሁ ምን አልባት ለማረጋገጥ ቀሪዎቹን መቁጠር ይጠበቅባችኋል፡፡ ወደ ወጣቱ ስንመለስ አብዝቶ እያለቀሰ አንድ ነገር ይላል፡ -“ምን አለ ጥቂት ብትታገሽኝ፣ ምን አለ ኖረሽ በተበሳጨሁ፣ ምን አለ ቆመሽ ሳስታምምሽ በኖርኩ . . . .” ወጣቱ ከነባልንጀሮቼ አስለቀሰን፡፡ ለካ የወዳጅ ጭቅጭቁም ይናፍቃል፣ ለካ የአፍቃሪ ቁጣውም ያሳርፋል፣ ለካ የባልንጀራ ተግሳጹም አምሮት ነው . . . . በእርግጥም ያ ቀን ብዙ አስተማረን፡፡
1. እድሜ ዕድል ነው፡-  እያንዳንዱ ቀን ወደ ግባችን፣ ወደ ስኬታችን፣ ወደ መሻታችን እንደርስበት ዘንድ ትልቅ ስጦታ ነው፡፡ የስጦታው ሕልውና ደግሞ በሰጭው እግዚአብሔር እጅ ላይ ነው፡፡ የእኛ ድርሻ በተሰጠን እድሜ በአግባቡ መጠቀም ነው፡፡ ሞትን የሚፈራ በእድሜው ያልተጠቀመ ብቻ ነው፡፡ እድሉን ያላባከነ ሞትን በደስታ ይጋፈጣል፡፡ ሰዎች እድል እንዲሰጡን ብዙ ጊዜ ደክመናል፡፡ ብዙዎች ከስህተታቸው ለመማር፣ የበደሉትን ለመካስ እድሉን ሳያገኙ በምኞት አልፈዋል፡፡ እግዚአብሔር እንዴት ያለ ነገር እንዳደረገልን ልብ በሉ! በእድሜ ባርኮናል፡፡ ስሙ ብሩክ ይሁን፡፡
2. ኃላፊነት ነው፡- ኃላፊነትን ከቁሳቁስ ጋር ያያዙ እድሜያቸውን ከስረው የማይከተላቸውን ሰብስበው ያልፋሉ፡፡ በእድሜአቸው አመሻሽ ላይ ጸጸት እንደ እግር እሳት ያንገበግባቸዋል፡፡ በማይመልሱት ትላንት ይቆዝማሉ፡፡ የማይለውጡትን ያመነዥጋሉ፡፡ ዛሬ በዋዛ ላለፋቸው ነገ ኪሳራ ነው! ጌታ ለተፈጠርንለት ነገር ኖረን እንድናልፍ ይርዳን፡፡  
3. ሀብት ነው፡- በዓለም ላይ ትልቁ የሀብት ስፍራ መቃብር ነው ሲባል ሰምቻለሁ፡፡ ሰዎች እውቀታቸውን፣ ልምዳቸውን፣ ፍቅራቸውን፣ መፍትሔያቸውን፣ ጉልበታቸውን፣ ቃላቸውንና ተግባራቸውን ሁሉንም ይዘው ከአፈር ጋር ኑሮ ይመሰርታሉ፡፡ ውጤቱ ሞት ቢሆንም ምክንያቱ ግን የእድሜ ማብቃት ነው፡፡ እድሜ ሲያበቃ ምክር የለውም፡፡ ጅምሩ እንደተጀመረ፣ ዝርክርኩ እንደተዝረከረከ፣ የጎደለው እንደጎደለ ብቻ ሁሉም ባለበት ነው፡፡ እድሜ ሀብት ነውና የሥጋቸውን እየሰጡ በነፍሳችሁ ለመጫወት ከሚከጅሉ ተጠበቁ፡፡ ኢየሩሳሌም ውስጥ የአይሁድ ሰንበት ከመግባቱ ጥቂት ደቂቃዎች በፊት ረቢው (መምህሩ) በከተማውና በየገበያው እየዞረ መለከት ከነፋ ገዥ ለሰጠው ብር መልስ እንኳ ሳይቀበል እየሮጠ ይሄዳል፡፡ ሻጭም እየሸጠ መለከት ከተነፋ ዕቃውን አይቀበልም፡፡ ተወዳጆች ሆይ እድሜያችሁን ዘርዝሩት!  
ከልቤ ምስጋና፡-
           አባት ሆይ እንኳንም አሰብከን፣ እንኳንም ፈጠርከን፣ እንኳንም በሰው መሐል ሰው ሆነን ተገኘን፡፡ ስምህ ይባረክ! ይህንን ቢጤያችን ሰው ሥልጣን ቢኖረው ኖሮ እንደማያደርገው እናውቃለን፡፡ ወላጅ እንኳ ልጁን የሚወልደው ነገን ስለማያውቅ ነው፡፡ አንተ ግን የዛሬ ማንነታችንን ቀድመህ እያወከው ፈጥረኸናል፡፡ የሥጋ ወላጆች በባለገ ልጃቸው ተጸጽተው በማኅፀን ሳለህ በሟሟህ ብለው ይቆጫሉ፡፡ አንተ ግን የመንፈስ አባት (አበ ነፍስ) ሁሉን ችለህ ሁሉን ተሸክመህ አለህ፡፡ ጌታ ሆይ መኖራችን በሰዎች አለመቻል ነው፡፡ ዛሬ ቢችሉ የሚጠሉን፣ ዛሬ ቢችሉ ኖሮ የሚያጠፉን፣ ዛሬ ቢችሉ ታሪካችንን የሚያበላሹ፣ ዛሬ ቢችሉ ኖሮ ካንተ የሚለዩን አድፋጮች ብዙ ናቸው፡፡ አንተ ግን መቻልህን ለማዳን አድርገኸዋል፡፡ ሰውን ወዳጅ ሆይ ጸጋህ አቁሞናልና ምሕረትህ እድሜ ሰጥቶናልና ስምህ ይቀደስ፡፡