Saturday, August 16, 2014

ፍቅርም እንደዚህ ነው!

                       Please Read in PDF: Fikirm Endezih New
                             
                                ነሐሴ 10 ቀን 2006 የምሕረት ዓመት

      ‹‹የሕይወታችን ምስጢር በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የተገለጠ መጽሐፍ ከሆነ ከሁለት ሺህ ዓመታት በላይ ሆኖታል፡፡ ያለፈው፤ የአሁኑ እና የወደፊቱ ሕይወታችን ሁሉ በእርሱ ተገልጧል፡፡ ያለፈው ሕይወታችን በእርሱ ስቃይና መከራ፤ የአሁኑ በእርሱ ጸጋ እና ምሕረት የተገለጠ ሲሆን፤ የወደፊቱ ደግሞ በዘላለማዊው ሕይወት ይገለጣል›› (ቶማስ አኩይናስ)፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ በማመናችን የምናገኘውን ትልቅ ነገር ሲናገር ‹‹ሕይወት›› በማለት ይገልጸዋል፡፡ የፍቅር ሐዋርያው ‹‹የዘላለም ሕይወት እንዳላችሁ ታውቁ ዘንድ በእግዚአብሔር ልጅ ስም ለምታምኑ ይህን ጽፌላችኋለሁ›› (1 ዮሐ. 5÷13) ሲል፤ የዘላለም ሕይወት ያላቸው ግን ያንን ያገኙትን የዘላለም ሕይወት የማያውቁትን ሰዎች እያስታወሰ ነው፡፡ እራሳችንን መርዳት በማንችልበት ‹‹ሙታን›› የተሰኘ ኑሮ ውስጥ ስንኖር ሳለ፤ ሕይወት እንዲሆንልን እንዲበዛልንም (ዮሐ. 10÷10) የእግዚአብሔር ልጅ በሥጋ ተገለጠ፡፡

     ተወዳጆች ሆይ፤ የዘላለምን ሕይወት እንዳገኛችሁ፤ ይህም ለእናንተ በክርስቶስ ክርስቲያን በመሆናችሁ እንደ ተሰጠ ታውቃላችሁን? ይህንን አለማወቅ አጉል ነዋሪ ያደርጋል፤ ተስፋ መቁረጥንና ለሞት ባርያ መሆንን ያመጣል፡፡ አዲስ ኪዳንን በደንብ ስናጠና ከምናስተውለው ነገር አንዱ ‹‹እግዚአብሔር ለእኛ የዘላለም ነገር እንዳለው›› ነው፡፡ ከእርሱ ጋር ሊኖረን የሚችለው ግንኙነት ከዚህ ባነሠ ነገር ላይ የተመሠረተ አይደለም፡፡ ሰው ኃጢአትን በማድረጉ፤ ተከትሎ የመጣው ደመወዝ ‹‹የዘላለም ሞት›› ነው (ሮሜ. 6÷23)፡፡ የዘላለም አባት እግዚአብሔር (ሮሜ. 16÷25)፤ የዘላለም ልጁን (ሮሜ. 9÷5)፤ በዘላለም መንፈስ (ዕብ. 9÷14) ለእኛ ምትክ አድርጎ በመስጠቱ የዘላለም ሕይወትን በጸጋ ተቀበልን (ኤፌ. 2÷5)፡፡ ይህም እግዚአብሔር ለእኛ ያለው የዘላለም አሳቡ ነው (ኤፌ. 3÷12)፡፡ እግዚአብሔር ለእኛ የማይቆጠር ነገር ማድረጉ ምንኛ ድንቅ ነው?