Friday, July 18, 2014

ከፍ ብሎ መቀመጥን፤ ዝቅ ብሎ በመቀመጥ ሞክረው!

                             
                   ሐምሌ 11 ቀን 2006 የምሕረት ዓመት

      እውነተኛ ወዳጅ የሚታወቀው፤ የወዳጅነት መፈታተኛ በሆነው በጭንቅና በመከራ ጊዜ ነው፡፡ ቁጣ የአዋቂውን ሰው ዕውቀት ያጠፋል፡፡ ቁጣና ትውኪያ ካሰቡት አያደርስም የሚባለው ስለዚህ ነው፡፡ ራሱን በራሱ የሚያመሰግን ሰው ራሱን ባይታመንና ሰው የማያመሰግነው መሆኑን ስለሚያውቅ ነው፡፡ እንዲሁም እርሱ የሚሠራው ሥራ ሁሉ በሰዎች ዘንድ የማይመሰገን መሆኑን ስለሚያምን ነው፡፡ በተድላ ደስታ መኖር ከተፈለገ ከወንድም ቅናትና ከጠላት ሽንገላ መጠንቀቅ ነው፡፡ ጊዜ ሳለው አለሁልህ ማለትን ለማያውቅ ጊዜ ሲከዳው አለሁልህ የሚለው አይገኝም፡፡ ጠባየ ክፉ ለሆነ ሰው ፍቅር አይስማማውም፡፡ ወዳጁ የሚከብደው ሰው ሸክሙ የቀለለ ነው፡፡

      አንድ ፈላስፋ ከወንድምህና ከወዳጅህ ማናቸውን ትወዳለህ? ቢሉት ወዳጄ ከሆነ ወንድሜ ነው አለ፡፡ ሆኖም ከበጎ ባልንጀራ መልካም ጠባይ ይበልጣል አለ፡፡ ያልያዘውንና የማያገኘውን የሚመኝ ሰው የያዘውንና ያለውን እስከ ማጣት ይደርሳል፡፡ ጥቂት ገንዘብ ከምስጋና ጋር ታላቅ ሃብት ነው፡፡ የማይችለውን እሸከማለሁ የሚል ሰው ለመሸከም የሚችለውንም ያጣል፡፡ በሐሰት ከመናገር በእውነት ድዳ መሆን በዓመፅ በሰበሰቡት ገንዘብ ሃብታም ከመሆን ጽሮ ግሮ ባገኙት ገንዘብ ድኻ መሆን ይሻላል፡፡ ሃብት በማያውቅበት ሰው ዘንድ በሞተ ሰው መቃብር ላይ ምግብን እንደ ማስቀመጥ ያለ ነው፡፡