Wednesday, November 30, 2011

የቱ ይሻላል?


      የሌሎችን ስህተት መዳኘቱ ቀላል ሲሆን የራሳችንን ድካም ማስተዋሉ ደግሞ ከባድ ነው፡፡ ቀላሉ ሳያገናዝቡ ማውራት ሲሆን ከባዱ ደግሞ ምላስን መግታት ነው፡፡ የሚወደንን ሰው መጉዳት ቀላል ሲሆን የሚከብደው ደግሞ ያንን ቁስል ማዳኑ ነው፡፡ ሌሎችን ይቅር ማለት ቀላል ሲሆን ይቅርታን መጠየቅ ግን ከባድ ነገር ነው፡፡ ሕጎችን ማውጣት ቀላል ሲሆን እነርሱን መከተሉ ደግሞ ከባድ ነገር ነው፡፡ ቀላሉ በእያንዳንዱ ምሽት ማለሙ ሲሆን ከባዱ ደግሞ ለስኬታማነቱ መዋጋት ነው፡፡
     ሙሉ ጨረቃን ማድነቁ ቀላል ሲሆን ሌላኛውን ጎን ማየቱ ግን ከባድ ነገር ነው፡፡ ቀላል የሆነው ለአንድ ሰው የሆነ ቃል ኪዳን መግባቱ ሲሆን የሚከብደው ደግሞ ያንን ቃል መፈጸሙ ላይ ነው፡፡ እወዳችኋለሁ ማለት ቀላል ሲሆን ከባዱ ደግሞ ያንን በሕይወት ማሳየቱ ነው፡፡ ሌሎችን መተቸት ቀላል ሲሆን ራስን ማሻሻል ደግሞ ከባድ ነው፡፡ ስህተትን መሥራት ቀላል ሲሆን ከዚያ መማሩ ደግሞ ብርታትን ይጠይቃል፡፡ ስላጣነው ፍቅር ማንባቱ ቀላል ሲሆን ላለማጣት መንከባከቡ ግን ይከብደናል፡፡ መቀበል እጅግ ቀላል ሲሆን መስጠት ደግሞ ልባዊ ርኅራኄን ይጠይቃል፡፡ ስለ መሻሻል ማሰብ ቀላል ሲሆን ከባዱ ግን ወደ ተግባር መቀየሩ ላይ ነው፡፡ ወዳጅነትን በቃላት መጠበቁ ቀላል ሲሆን ትርጉማቸውን መጠበቁ ግን ከባድ ነገር ነው፡፡
     ልጅ እያለን ከሰማናቸው ነገሮች መካከል አንዱ በአካባቢያችን ውሻ ሲያላዝን (የተለየ ድምጽ ሲያሰማ) "ሰው ሊሞት ነው' የሚለው አባባል ነው፡፡ እጅግ በሚገርም ሁኔታ ግን "እኔ ልሞት ነው' የሚል ያለመኖሩ ጉዳይ ነው፡፡ በተለይ አልጋ የያዙ ካሉ የሰዉ ሁሉ ትኩረት መጠቋቆሚያ የመሆናቸው ጉዳይ አጠያያቂ አይሆንም፡፡ ግን የቱ ይሻላል? ሰውን ማስተካከል ወይስ ራስን ማስተካከል፣ እነርሱ ልክ አይደሉም ማለት ወይስ እኔ ልክ አይደለሁም ማለት፣ የሌሎችን ስህተት መዳኘት ወይስ የራስን ድካም መታገል የቱ ይሻላል? ተወዳጆች ሆይ ለሚከብደውና ለሚበልጠው እንትጋ!

ሁለት ባልዲዎች


       ጀምበር አዘቅዝቃ ወደ መኝታዋ ስታዘግም የተሰማ የባልዲ ቁም ነገር ነው፡፡ ሁለት ባልዲዎች(የውሃ መቅጃ) በሁለቱ ጫፍ በገመድ የተወጠሩለት አንድ አነስተኛ መዘውር ነበር፡፡ አንደኛው ባዶ ሆኖ ወደ ጉድጓድ ሲወርድ በሌላኛው ጫፍ የተንጠለጠለው ባልዲ ደግሞ በውሃ ተሞልቶ ወደ ላይ ይወጣል፡፡ አንደኛው መቅጃ ዓለም የምታቀርበው በጣም ጥቂት ነገር ብቻ ነው እያለ የማይቋረጥ ማማረሩን ቀጥሏልወደ ጉድጓዱ አፍ ሙሉ ሆኜ ወጥቼ ወደ ታች ስመለስ ግን ሁል ጊዜም ባዶ ነኝእያለ ይጨነቃል፡፡
      ሌላኛው ባልዲ በበኩሉ በደስታ ተሞልቶ እንዲህ ሲል ይመልሳልምንም ያህል ባዶ ሆኜ ወደታች ብወርድም እንኳን ሁልጊዜም ሙሉ ሆኜ ከፍ እላለሁ፡፡ብዙው ነገር የሚወሰነው እኛ በውስጣችን እንዳስቀመጥነው ነው፡፡ ንፋስ በረሃማ ቦታ ላይ ሲነፍስ የሚያፍን የአቧራ ክምር ይፈጥራል፡፡ ዳሩ ግን ያው ነፋስ በአትክልት ቦታ ውስጥ ቢያልፍ የማራኪ አበቦችን ጣፋጭ መዓዛ ይረጫል፡፡
     አንድ ሕፃን ለመራመድ ሲፍጨረጨር ብናስተውል ማብቂያ የሌላቸውን ውድቀቶች እናያለን፡፡ ስኬቶቹ ግን በጣም ጥቂት ናቸው፡፡ ነገር ግን በተደጋጋሚ ውድቀቶቹ እንዳሉ ሆነው የማይቻል የሚመስለውን ነገር ማድረግ የቻለው ሕጻን በኃይለኛ ደስታ ውስጥ ይዋጣል፡፡ በጊዜው አቋሙን ስለ መጠበቁ እንጂ ስለ ወደቀባቸው ጊዜያት ያን ያህል ሳይጨነቅ ከደስታ ወደ ደስታ ይሸጋገራል፡፡
     አንተም አታማር፣ ጊዜም አታጥፋ፡፡ ተስፋ በማድረግና ጠንክረህ በመሥራት ሕይወትህን በደስታ ሞልተሃት ኑር፡፡ እርግጥ ነው ብዙ ነገሮች አስቸጋሪ ይሆኑብናል፡፡ ነገር ግን ሁልጊዜም ቢሆን ሕይወትህን ስኬታማ የምታደርግበት፣ ራስህን በውብ ወጣትነት የምትቀርጽበትና በውስጣዊ ሕይወትህ ያለህን ብልጽግና የምትጨምርበት እልፍ መንገድ አለ፡፡
     ስለዚህ ሙሉ ዓለም ቢታሰስ ለአንተ የተሻለ ቦታና ሁኔታ ሊኖር እንደማይችል ማሰብህን አቁም፡፡ ስኬት የምታመራው ፈጽሞ ተስፋ ወደማይቆርጡና አዎንታዊ በሆኑ ነገሮች ላይ ለማተኮር ወደወሰኑ ሰዎች ነው፡፡ ምንም እንኳን ያልተሳኩ ነገሮቻችን፣ የውደቀት መጠናችንና የስህተታችን ብዛት ቢያይልም ከዚህም የተነሣ ምንም ያህል ባዶ ሆነን ወደታች ብንወርድም እንኳን ሁልጊዜም ሙሉ ሆነን ከፍ እንላለን፡፡ የትንሣኤ ምስጢር ያለውም እዚህ ውስጥ ነው። እንደ ምድረ በዳ ያሉ የሕይወት ውጣውረዶች እንደ ተራራ ወደአለ ከፍታ፣ እንደ መቃብር ያሉ የኑሮ ዝቅታዎች እንደ ትንሣኤ ወደአለ ልዕልና የሚያሻግሩን ናቸው።
     አሁን አንተን አንድ ጥያቄ እጠይቅህ ዘንድ እወዳለሁ። ከመዘውሩ በአንደኛው ጫፍ ላይ እንዳለህ አስብና አንተ ብትሆን ልትል የምትችለውን አእምሮህ ሰሌዳ ላይ ጻፍ። እርሱንም ከእውነታውና መሆን ካለበት ከትክክለኛው ነገር ጋር አነጻጽር። ልክ እንዳልሆንክ አንዳች የተሳሳተ ነገር እያደረክ እንደሆነ ከተሰማህ ችግሩ የሚጠይቀውን መፍትሔ ከማድረግ ወደኋላ አትበል። ያለ ዕለት ከዕለት ግጥሚያዎቻችን እና ፈተናዎቻችን ሕይወት ባዶና አንድ ዓይነት ትሆናለች፡፡ ችግሮች አብዛኛውን ጊዜ ልንማራቸው ግድ የሚሉን እውቀቶች ናቸው፡፡
    ስለዚህ ሁሉንም የሕይወት ተሞክሮዎች ደስተኝነት ከሰፈነበት አቀባበልና ከእምነት ጋር ተግባባቸው፡፡ በሚያጋጥምህ በእያንዳንዱ ችግር ውስጥ የተደበቁትን ስጦታዎች በማስተዋል ሆነህ መርምር፡፡ ሰው መሆን እንደ እንግዳ ቤት ነው፡፡ እያንዳንዱ ማለዳ አዲስ አዳራሽ ነው፡፡ ደስታ፣ ሐዘን፣ ሕመም እና ጊዜያዊ ግንዛቤዎች እንደአልተጠበቀ ጎብኚ ሆነው ይመጣሉ፡፡ ሁሉንም በጸጋ ተቀበላቸውና ተደሰትባቸው ለሕይወትህም ፍስሐ ይሆኑ ዘንድ ፍቀድላቸው፡፡