Tuesday, December 25, 2012

ሥራህን ሥራ!




                                         ማክሰኞ ታህሳስ 16/2005 የምሕረት ዓመት

           ጌታ ለእያንዳንዱ ሰው ሥራ ሰጥቶታል ያንን መሥራት የእርሱ ፈንታ ነው፡፡ ቢቻለው እሱን ማገድ የዲያቢሎስ ሥራ ነው፡፡ በእርግጥ ሥራውን እግዚአብሔር እንደሰጠህ ያህል ሰይጣን ሊያግድህ ይሞክራል ሌላ ነገር በበለጠ ደስ የሚያሰኝ ሊያቀርብልህ ይጥራል፡፡ በዓለማዊ ተስፋዎች ያባብልሃል የሃሜት ጎርፍ ያስወርድብሃል በሐሰተኛ ክስ ያሰቃይሃል ለክብርህ እንድትከላከል ያደርግሃል ደራሲያን እንዲጠይቁህ እጅግ ስመ ጥር ሰዎች በክፉ እንዲናገሩህ ይጠቀምባቸዋል፡፡
           ጲላጦስ፣ ሄሮድስ፣ አናንያ፣ ቀያፋ በአንተ ላይ ያድማሉ ይሁዳም በአጠገብህ ቆሞ በሰላሳ ብር ሊሸጥህ ይከጅላል፡፡ አንተም “ይኸ ሁሉ የመጣብኝ ለምንድን ነው?” በማለት ይደንቅሃል ይኸ ሁሉ የመጣብህ ሰይጣን በዘዴ ከሥራህ ሊስብህና እግዚአብሔርን ከመታዘዝ ሊያሰናክልህ መሆኑን ልትገነዘብ አትችልምን?
           ሥራህን ሥራ አንበሳው ቢያጓራ ፍንክች አትበል፣ የሰይጣንን ውሾች ለመውገር አትቁም፣ ጥንቸሎቹንም  በማባረር ጊዜህን አታጥፋ፣ ሥራህን ሥራ ዋሾቹ ይዋሹ ጠበኞቹ ይጣሉ ማኅበረኞቹ ይወስኑ፣ ደራሲዎቹ ይድረሱ፣ ሰይጣንም የፈለገውን ያድርግ አንተ ግን ምንም ነገር እግዚአብሔር የሰጠህን ሥራ ከመፈፀም እንዳያግድህ ተጠንቀቅ፡፡
           ገንዘብ እንድታተርፍ አልተላክም፣ እንድትበለፅግም አላዘዘህም፣ ሰይጣንና አገልጋዮቹ የሚነዙትን የሐሰት ወሬ እንድታስተባብል አልተጠየክም እነዚህን ሁሉ ነገሮች ብታደርግ ሌላ ሥራ ልትሠራ አትችልም፤ ይህም ብቻ ሳይሆን ለራስህ እንጂ ለጌታ አልሠራህም፡፡
           ሥራህን ሥራ ዓላማህ እንደ ኮከብ የፀና ይሁን፣ ተወው ዓለም እንደፈለገው ይነታረክ ይጨቃጨቅም፡፡ ጥቃት ይደርስብህ፣ ትበደል፣ ትሰደብ፣ ትታማ፣ ትቆስል፣ ትናቅ ይሆናል፡፡ ኃይለኛ ያጎሳቅልህ፣ ወዳጆችህ ይተዉህ፣ ሰዎች ይንቁህ ይሆናል፡፡ አንተ ግን የፀና ውሳኔ በማያወላውል ቅናት በመጨረሻ ላደርገው የሰጠኸኝን ሥራ ፈፀምኩ ለማለት እስክትችል ድረስ የሕይወትህን ዓላማና የተፈጠርክበትን ግብ ተከተል፡፡

Tuesday, December 11, 2012

ሰው አያክፋችሁ (ካለፈው የቀጠለ)



                                               
                                            ማክሰኞ ታህሳስ 2/2005 የምሕረት ዓመት

           ባለፈው ክፍል የአንዳችን እንቅስቃሴ በሌላው ሕይወት ላይ በበጎም ሆነ በክፉ ያለውን ከፍ ያለ ተጽእኖ ለመዳሰስ ሞክረናል፡፡ ሁላችንም ብንሆን በሰው ላይ የምንፈርድበት ብቻ ሳይሆን በእኛም ውስጥ የሚፈረድበት ኑሮ አለን፡፡ ብዙዎች ለራሳቸው እንኳ ደግመው ሊያስቡት ከሚያንገሸግሻቸው ነገር ጋር ይኖራሉ፡፡ እንዲህ ካለው ጠባይና አኗኗር ጋር ተፈጥረው ግን አይደለም፡፡ አብዛኛው ሰው ያከፋው ነው፡፡ ጥላቻን የሚያግቱ፣ ተንኮል የሚያስቀጽሉ፣ ዓመጽ የሚያሰለጥኑ እንደ ምድር አሸዋ በዙሪያችን ናቸው፡፡
           ባል ያከፋቸው ሚስቶች ጥሩ እናት መሆን ሲያቅታቸው፣ አሳዳጊ ያከፋቸው ልጆች ጥሩ ባልንጀራ መሆን ሲሳናቸው፣ ጓደኛ ያከፋቸው ወጣቶች መልካም አባት መሆን ሲቸገሩ፣ ኅብረተሰቡ ያከፋቸው ሰዎች በቅን መምራት ሲተናነቃቸው አስተውለናል፡፡ ክፉ የምንለው ያከፋነውን ነው፡፡ ርኩስ የምንለው ያረከስነውን ነው፡፡ ጠፋ የምንለው ያባረርነውን ነው፡፡ ከሀዲ የምንለው ያስካድነውን ነው፡፡ ጌታ ሆይ ይቅር በለን!
           የሮም ንጉሥ የነበረውን ኔሮን ቄሳር ክርስቲያኖችን እንደ ጧፍ ለኩሶ እንደ ሻማ በማቅለጥ፤ ከአንበሳና ከነብር ጋር በማታገል ይዝናና የነበረ ክፉ መሪ እንደነበር ታሪክ ያስታውሰናል፡፡ ኔሮን ወደ ሥልጣን የመጣበትን መንገድ ስንመለከት፤ እናቱ አግሪፒና በ12 ዓመቷ የ15 ዓመት ዕድሜ በነበረው በኋላም ንጉሥ በሆነው ወንድሟ ካሊጉላ ትደፈራለች፡፡ በ13 ዓመቷ ትዳር መስርታ የልጇ የኔሮን ጥብቅ ወዳጅ ሆናለች፡፡ አግሪፒን አጎቷ የነበረውን ንጉሥ ክላውዴዎስ (ቀዳማዊ) ከማግባቷ በፊት ሁለተኛ ባሏን በመድኃኒት ገድላለች፡፡ ከዚያም ክላውዴዎስን በመርዝ በመግደል ኔሮ ዙፋኑን ወርሶ ወደ ንግሥና እንዲመጣ አድርጋለች፡፡ ጨካኙን ኔሮን ስናስብ እንዴት ባለ ሁኔታ ውስጥ እንዳደገ ልብ ማለት ትምህርት ያተርፍልናል፡፡
        በዓለማችን ላይ ከተነሡ አያሌ ዓመፀኞች ጀርባ ያለው ነገር በኔሮን ቄሳር ካየነው ብዙም የሸሸ አይደለም፡፡ በወላጅ፣ በጓደኛ፣ በወዳጅ፣ በፍቅረኛ ዓላማቸውን የሳቱ፣ ከሕሊናቸው የተጣሉ፣ የሕይወት ታሪካቸው ጥላሸት የተለቀለቀ፣ ራሳቸውን እየፈሩ የሚኖሩ፣ የማንነት መቃወስ የገጠማቸው ከእነርሱ ስህተት በላይ ሰው አክፍቷቸው ነው፡፡
         በአገራችን የገጠሩ ክፍል ዛሬም ድረስ ሙሉ ለሙሉ ጠርቶአል በማይባልበት ሁኔታ ደም የመቃባት ክፉ ውርስ አለ፡፡ ለዚህ መባባስ እንደ አንድ ምክንያት ተደርጎ የሚቀርበው ደግሞ ወገኑ ሞቶበት ደም ያልመለሰ ወንድ እንደ ነውረኛ መቆጠሩና ሚስት ለማግባት እሺታን መነፈጉ ነው፡፡ እንዲህ ባለ ሁኔታ ውስጥ ሰው ሸሽቶ ካልሆነ በቀር አብሮ ሆኖ ሕሊናውን መጠቀም አይችልም፡፡ ባይወድም ይከፋል፡፡ አቅም ባይኖረውም ይሸፍታል፡፡ ታዲያ እድሜ ሰጥቷችሁ ከዓመታት በኋላ ብትገናኙ ያ መልካምነት ሞቶ ተቀብሮአል፡፡ ያ ትህትና አፈር ትቢያ ሆኖአል፡፡ ያ ርኅራሄ ላይመለስ እርቆ ሄዶአል፡፡ ለልቡ ተጠግታችሁ “ምነው? ምን ገጠመህ?” ብትሉት ልክ እንደ ሙሾ አውራጅ እየተንሰቀሰቀ “ሰው አከፋኝ” ይላችኋል፡፡ ሰው አያክፋችሁ!
         ሕይወት ቅብብሎሽ ናት፡፡ አንዱ ትውልድ ሲሄድ ያን ተከትሎ ሌላው ይመጣል፡፡ ታዲያ ይህኛው ሲከፋ ለመጪው ውርስ ሆኖ ይቀራል፡፡ ከዚያም ክፉና ደግ ምርጫ ሳይሆን የውርስ ቅብብሎሽ ይሆናል፡፡ በእርግጥም እውነታው እንዲሁ ነው፡፡ ከማይጠፋው ዘር የተወለዱ ሁሉ የማይጠፋ ነገር ሲቀባበሉ ይኖራሉ፡፡ ያለ ምርጫቸው በሰው ምርጫ፣ ያለ ፍላጎታቸው በሰው ፍላጎት፣ ያለ ውዴታቸው በሰው ግዴታ የኑሮ አቅጣጫቸው የተወሰነ ያላለቀ ነገር (unfinished business) አላቸውና ዛሬም ከብርቱ ፈተና ጋር ናቸው፡፡

መፍትሔ

         እኔ ከሞትኩ . . . አይነት ኑሮ ለምድሪቱ ጭንቅ ነው፡፡ የሆነ ቦታ የሚጨክን ሰው ያስፈልጋል፡፡ ከአያት ከቅድመ አያት የመጣ ነገር ሁሉ ለልጅ ልጅ አይተላለፍም፡፡ እኛ የተጫነንን ሌሎች ላይ መጫን የለብንም፡፡ እኛ የመረረን ሌሎችንም እንዲመራቸው ቸልተኛነት ልናሳይም አይገባም፡፡ የከፉብንን በመክፋት፣ የጠሉንን በመጥላት፣ ያንገላቱንንም በማንገላታት ምድሪቱን በጨለማ ልንለውሳት አይገባም፡፡ እናም እንደ ብርሃን ልጆች በመመላለስ ክፉውን እንዋጋ፡፡ ጸጋ ይብዛላችሁ!  

Tuesday, December 4, 2012

ሰው አያክፋችሁ



                                        ማክሰኞ ሕዳር 25/2005 የምሕረት ዓመት

        በሰው ልጅ ታሪክ ውስጥ ከመልካምነት ይልቅ ክፋት ዓለምን እንደገዛ እናስተውላለን፡፡ አለመታዘዝ ያመጣውን ውድቀት ተከትሎ የሰው ዝንባሌ “የማልወደውን ክፉን ነገር አደርጋለሁና ዳሩ ግን የምወደውን በጎውን ነገር አላደርገውም” (ሮሜ. 7÷19) ወደሚል ሙግት ገብቶአል፡፡ ከመምረጥ ጀምሮ እስከ ድርጊት ድረስ ሰዎች በብርቱ ይፈተናሉ፡፡ አንዳንድ ጊዜም ከነ አካቴው ሁሉን እርግፍ አድርጎ የመተው ውሳኔ ላይ ይደርሳሉ፡፡ ማለትም በጎም መጥፎም ያለመሆንና ያለማድረግ! ሰው ግን ከሁለት አንዱን ነው፡፡ ከእነዚህ ራሱን የሚያገልበት ሌላ ሦስተኛ ክልል የለም፡፡ ልክ እንደ አንድ ቀን ሁለት ገጽታ ብርሃንና ጨለማ ነው፡፡ በብርሃን እንመላለሳለን ወይም በጨለማ እንመላለሳለን፡፡ ክርስትና ግን እንደ ብርሃን ልጆች መመላለስ ነው፡፡ ከክፉ መራቅ ሰላማችንን የሚጸናበት ዋስትና ነው (ኢሳ. 48÷22)፡፡  
         በታሪክ ከተነሡ እጅግ ክፉና አምባገነን መሪዎች መካከል አንዱ ሂትለር ነው፡፡ በየዘመናቱ ብዙ አስጨናቂዎችን ሰዎች ርደውና ተንቀጥቅጠው አስተናግደዋል፡፡ ብዙዎች ሞተው፤ አንዳንዶች ደግሞ አጉል ነዋሪ ሆነው በዚያ አረመኔያዊ ሥርዓት ውስጥ አልፈዋል፡፡ አንዳንዴ ባለፈው የአገራችን ሥርዓት ውስጥ ጨካኝ የነበሩና የገዛ ጎረቤታቸውን በቁም የቀበሩ ሰዎች በዚህኛው ሥርዓት ውስጥ ሲሽቆጠቆጡ ስናያቸው የሥርዓቱ ለውጥ ጭካኔያቸውን እንዳዳፈነው እንጂ እንዳጠፋው አይሰማንም፡፡ የዚያ አምባገነናዊነት ግርሻት ያየለበባቸው ደግሞ ለዚህኛው ሥርዓት ተቆርቋሪ መስለው በዚያኛው አመጽ ይገለጣሉ፡፡ እናም ራሳቸውን ያረካሉ፤ ክፋት ያስገብራልና ዘመን ቢቀያየርም ክፉውን አያስረጀውም፡፡ እግዚአብሔር ግን ይለውጣል!
         ለዚህ ጽሑፍ ርዕስ ያደረኩትን ቃል ያገኘሁት ለልቤ እጅግ ቅርብ ከሆነ አባት (ከአንዱ እግዚአብሔር) ምክር መካከል ነው፡፡ ዘመኑ መካሪም ተመካሪም የሰለቸበት ነው፡፡ ከዚህ ይልቅ ሰው ሁሉ ወደ ልቡ አሳብ ተጠምዷል፡፡ ምን አልባት “ደግሞ በዚህ ዘመን ምን በጎ መካሪ አለ?” ልትሉ ትችላላችሁ፡፡ ነገር ግን ሰው አያስተውልም እንጂ እግዚአብሔር በአንድ በሌላም መንገድ ይመክራል፡፡ አንዳንዴ ሳት ብሏቸው እንኳ ጥሩ እንደማይናገሩ ከምናስባቸው ሰዎች ሕይወት ያለባቸው ቃላት ሲወጡ እናስተውላለን፡፡
         እግዚአብሔር የእስራኤልን ሕዝብ ይረግምለት ዘንድ ባላቅ የከፈለበትን የበልዓም አንደበት መርቆበታል (ዘኁ. 22)፡፡ በእርግጥ ተደላድለን ውሸት ከምንናገር እግዚአብሔር ጠምዝዞን ለእውነት ብንመሰክር ይበልጣል፡፡ በየአደባባዩ የሚጠፋውን መብል እያሰቡ፣ ሕሊናቸውን አራቁተው ሆዳቸውን እየሞሉ በዚህ ዓለም ከንቱ መለፍለፍ የተጠመዱ ሁሉ ከበለዓም ስሕተት (ይሁዳ 11) ሊማሩ ያስፈልጋቸዋል፡፡   
        የስነ ልቦና ባለሙያዎች እንደሚያስረዱት ልጆች እያለን ከቤተሰቦቻችና ከማኅበረሰቡ ጋር የነበረን ግንኙነት (Attachment) ወደ ማወቅ ደረጃ ከመጣን በኋላ በቀጣይ ኑሮአችን ላይ ከፍተኛ ተጽእኖ (በጥሩም በመጥፎም) ያሳድራል፡፡ የአንድ ሰው ክፋት የብቻው ክፋት፣ የአንድ ሰው መልካምነት የብቻው መልካምነት አይደለም የሚል መከራከሪያ የሚቀርበውም ለዚህ ነው፡፡ አብዛኛውን ጊዜ የምንመለከተው ወንጀል ተባባሪና አሰልጣኝ ያለው ነው፡፡ በጣም ጨዋ እንደነበሩ የምናውቃቸውን አልባሌ ቦታ ስናገኛቸው አድራሻ ለመለወጥ ያበቃቸው ክፉ ባልንጀርነት እንደሆነ እናያለን፡፡  
        ሰውና ሁኔታ ያከፋው ካልሆነ በስተቀር ማንም ክፉ ሆኖ የተፈጠረ የለም፡፡ ወድጄ መሰለህ እንዲህ ያለ ጠባይ የያዝኩት፣ አመል ያወጣሁት በማለት የሚናገሩ ወገኖች ብዙ ናቸው፡፡ ማንም በጥረት የተበላሸ የለም፡፡ አንዳንዱ እንጀራ በልቶ ለማደር፣ ሌላው ከሰው ተመሳስሎ ለመኖር፣ አንዳንዱ የእጁን ላለማጣት ብቻ ሁሉም ለከፋበት ምክንያት ያቀርባል (ምንም እንኳ ምክንያት ባይታደግም ግን እኮ ከፀሐይ በታች ባለው ኑሮ ምክንያተኝነት ስልጣኔ ነው እንጃ እንግዲህ አንዱን ምረጡ)፡፡    
      በጭካኔውና በአረመኔነቱ ከምናውቀው ሂትለር ጀርባ ያለውን ታሪክ በአጭሩ ለመመልከት ብንሞክር፤ እናቱ ክላራ ከእርሷ በ23 ዓመት እድሜ ለሚበልጣት ለአጎቷ የልጅ ልጅ ሦስተኛ ሚስት የነበረች ስትሆን በትዳር በቆየችባቸው ጊዜያት ሁሉ ባለቤትዋን ትጠራው የነበረው “አጎቴ” እያለች ነበር፡፡ ግንኙነታቸው የተጀመረውም በአጎቷ ቤት በቤት ሠራተኛነት ታገለግል በነበረበት ጊዜ ነው፡፡ ታዲያ ሂትለር ልጅ እያለ እናቱ ክላራ ብቸኛ ጓደኛው ነበረች፡፡
         አስራ ስምንት ዓመት ሲሞላው እናቱ በካንሰር ሞተችበት፡፡ በዚህም ምክንያት ለከፍተኛ የልብ ስብራትና ለበለጠ ብቸኝነት ተጋለጠ፡፡ አንዳንድ የታሪክ ምሁራን እንደሚያስረዱት ሂትለር በሴሜቲኮች በተለይም በአይሁዶች ላይ ጥላቻና የበቀል ስሜት ያደረበት የሚወዳት እናቱ አይሁዳዊ በሆነ ዶክተር የተደረገላት ሕክምና ውጤት አልባ በመሆኑ ነው፡፡ እንግዲህ በግፍና በሰው ሰቆቃ ራሱን ያረካ የነበረው አዶልፍ ሂትለር ወደዚህ የክፋት ጣሪያ የደረሰው በዚህ መንገድ ነው፡፡ እናንተስ እንዴት ታዩታላችሁ?
                መልካም የምንሆነው ለራሳችን ብቻ ብለን አይደለም፡፡ ሌሎችንም ከእሳት ነጥቆ ለማውጣት እውነተኛ መንገድ ስለሆነ ጭምር ነው፡፡ በጎ ነገር ዘር ነው፡፡ ዘር ደግሞ ከተዘራ በኋላ እንደ ዘራነው ልክ አይሆንም፡፡ ስለዚህ በጎነታችንም ሆነ ክፋታችን መሐን ሊሆን አይችልም፡፡ በጎ የዘራችሁ ደስ ይበላችሁ!
                                                          - ይቀጥላል -