Wednesday, May 23, 2012

እውነት ማለት የኔ ልጅ



ሰስተው እንደቁዋጠሩት ጥሪት፣ ከአባት ከእናት አትወርሺው፤
እንደቁዋንቁዋ ሃይማኖትሽ፣ በአደባባይ አታነግሺው፤
እውነት የነፍስሽ ነው ልጄ፣ የማንነትሽ ክታብ፤
የድብቅ ገመናሽ ንባብ፡፡
የእኔ ልጅ፣
ከየአደባባዩ ቡዋልት፣ ከየሸንጎው እንቶ-ፈንቶ፣
                                 እውነት ፍለጋ ስትባዝኚ፤
ማስተዋልሽን አታባክኚ፡፡
ፈጣሪ በራሱ አምሳል፣ ኑሮ ብሎ እንደፈጠረው፤
እያንዳንዱ ምስለ-ፍጡር፣ በእለት-ተእለት ማህደሩ፤
እውነት የራስ ነው ልጄ፣
የነፍስሽ ሳቅና ለቅሶ፤
የሕሊናሽ ሙግት ቅኝት፤
የራስሽ ለራስሽ ግኝት፡፡
የሕሊናሽ ነው ልጅ፣ ነቅተሽ እርሱን አድምጪ፤
ሲስቅ ዳንኪራ እርገጪ፤
ሲያለቅስ መርዶ ተቀመጪ፡፡
እንጂማ ልጄ፣
ሳቅ ጥርስ እንዳይመስልሽ፣ ያነባስ መች አልቅሶ፤
በሕይወት ስንክሳር ቅኝት፣ ደስታ ሀዘኑ ተመሳቅሎ፤
የክት እውነቱን በብብቱ፣ ያደባባዩን በገጹ አዝሎ፤
ነው ልጄ የሰው ውሎ፡፡
እና ልጄ፣
ብልጭ ካለ ጥርስ ላይ፣ ከሚፈሰው እንባ፣ እውነት ፍለጋ ስትባዝኚ፤
ማስተዋልሽን አታባክኚ፡፡
       (ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ፣ የግጥም ስብስብ፣ 2004 ዓ.ም)

1 comment:

  1. Be ewinet lib yemineka hasab new. Tsega yibzalachu!

    ReplyDelete