Sunday, January 1, 2012

የተወደደ መስዋዕት (ካለፈው የቀጠለ)


     ምስጋና ጣፋጭ ከሆነ መዓዛ፣ ቅን ከሆነ አስተሳሰብ በቀር ምንም ከማያውቅ የሰው ነፍስና መንፈስ የወጣ ውብ አበባ ነው። ልክ አዲስ የተወለደ ሕጻን በፈገግታው ሙሉ ቤቱን ደስ የሚልና አስደሳች እንደሚያደርገው ሁሉ አመስጋኝ ልብ ያለውም ሰው ሙሉ ዓለምን ደስተኛ ያደርጋታል፡፡ የምስጋና ቃል ጥቂት ቢመዝንም ትርጉሙ ብዙ ነው። ለሰጪው የነፍስ ደስታን ሲሰጥ እንዲሁ ተቀባዩ ከእኛ ጋር የሚኖረውን ወዳጅነትም ማለዳ ማለዳ አዲስ ያደርገዋል፡፡ ስለዚህም የምንወደው  ጠባያችን ምስጋና እንዲሆን ፈቅደን መምረጥ ይኖርብናል፡፡ ልብ በሉ! አመስጋኝ ሰው በእሾህ መሐል እንዳለች ውብ ጽጌረዳ ዘመኑን ሁሉ ማራኪ እንደሆነ ይጨርሳል፡፡
     ማንም ሰው ለደስታና ለፍጹምነት ያለውን አጭሩንና እርግጠኛውን መንገድ ሊነግረን ከወደደ ስለሆነልንና ስለሆነብን ማንኛውም ነገር ጌታ እግዚአብሔርን የምናመሰግንበትን መርህ እንድናዘጋጅ ሊነግረን ይገባል፡፡ የትኛውም የከፋ ነገር ቢከሰት እንኳን አመስጋኝነት ወደ በረከት ሊለውጠው አቅም አለው፡፡ ለራሳችንም ልንሠራ ከምንችለው በላይ ተአምር ሲሠራ ማየት እንችላለን፡፡ አመሰግናለሁ ለማለት ምንአልባትም በጊዜው አስቸጋሪ ይሆናል፡፡ ነገር ግን ፍሬው ጣፋጭ መከሩም ብዙ ነው፡፡ በዓለም ላይ ትልቁ ምላሽ አመሰግናለሁ የሚለው ነውና!
     ስለ ማመስገን ስናስብ ሁለት ነገሮችን እናስታውሳለን፡፡ የመጀመሪያው ስለተቀበልነው ነገር የሚሰማን ዓይነት ምስጋና ሲሆን ይህም ድንገተኛ ነው፡፡ ሌላኛው ደግሞ ስለሰጠነው ነገር የሚሰማን ምስጋና ሲሆን ይህም ትልቁ ነው፡፡ ለአብዛኞቻችን የመጀመሪያው የለመድነው ዓይነት ሲሆን ከስጦታ ጋር በተያያዘ የሚሰማን ደስታና የጋለ ስሜት ነው፡፡ እንግዳ የሚሆነውና ጥንካሬን የሚጠይቀው የምስጋና ዓይነት ግን ሁለተኛው ነው፡፡ ሁላችንም ልንስማማበት እንደምንችለው ይህ ይበልጥ አስደናቂ ነው። በሌሎች ሕይወት ጨለማ ላይ ጥቂት ብርሃን የማብራት ድካማቸውን የመጋራት ከዕንባቸው ጋር የማንባት አጋጣሚውን ስናገኝ ምን ያህል ሰላም ይሰማናል? ምን ያህልስ እንደሰታለን? እንደ እውነቱ ከሆነ መልካም ፈቃዳችንን እና የልግስና ስሜታችንን ለመግለጥ እድሉ ስለገጠመን ጥቂት የሆነ ግን ደግሞ ታላቅ እርካታ ይሰማናል፡፡
    ስለዚህ ምስጋናችንን የተቸርነውን ጥቂት ካላቸው ጋር ፈቅዶ በመጋራት ልናሳይ ያስፈልገናል፡፡ ትክክለኛ ምስጋና የእውነተኛ ወዳጅነት ልዩ ምልክት ነው፡፡ ይበልጥ ማመስገን ደግሞ ይበልጥ ባለጸጋ መሆን ነው፡፡ ነገሮች ጥሩ ባልሆነ መልኩ እየሄዱብን ሳለ የምናሳየው የምስጋና ጠባይ ሁኔታዎች ከዝንባሌያችን ጋር በተስማሙበት ጊዜ ከምናቀርበው ምስጋና ይልቅ ዋጋው እጅግ ከፍ ያለ ነው፡፡ ብዙ በተደረገልን ቅጽበት ትንሽ ማመስገን ቀላል ሲሆን ምንም ባልተደረገልን ሰዓት ጥቂት ማመስገን ግን ይከብደናል፡፡ ለጥቂቱ ካላመሰገንን ለብዙውም አናመሰግንምና በማመስገን ደካማ ከሆን ደግሞ በሁሉም ጠባያችን ደካማ እንሆናለንና በሁሉ ማመስገንን አሁኑኑ እንጀምር!
     ሰውን ካፈቀርክ ፍቅርህ ሊታይ ይገባል፡፡ ስለ ሰው ሀዘን ከተሰማህ ርኅራሄህ ሊገለጥ ይገባል፡፡ ጥቂት ውለታን ብትፈልግ ትህትናህ ሊብራራ ይገባል፡፡ በነገር ሁሉ አስተዋይ ከሆንክ ደግሞ ምስጋናህ ሊታይ ይገባል፡፡
    ተወዳጆች ሆይ! አመስጋኝነታችን እየደመቀ በመጣ ቁጥር ይበልጥ ለመቀበል ዋጋ ያለን እንሆናለን፡፡ ከሁሉም የሚበልጠው ውብ ጠባያችንም ባለን የምስጋና መጠንና ብርታት ታይቶ የሚፈተን ነው፡፡ ስለዚህ ለሚቀጥፉት እንኳን መዓዛን እንደሚሰጠው ግሩም ሐረግ አመስጋኝ ሁን!

3 comments:

  1. ሰውን ካፈቀርክ ፍቅርህ ሊታይ ይገባል፡፡ ስለ ሰው ሀዘን ከተሰማህ ርኅራሄህ ሊገለጥ ይገባል፡፡ ጥቂት ውለታን ብትፈልግ ትህትናህ ሊብራራ ይገባል፡፡ በነገር ሁሉ አስተዋይ ከሆንክ ደግሞ ምስጋናህ ሊታይ ይገባል፡፡ Tebarek!

    ReplyDelete
  2. It is good expresion. Thank u.

    ReplyDelete
  3. wow speecheless.

    ReplyDelete