Monday, February 6, 2012

እሺታ ያለ ቦታው


  
    ሕይወት የእያንዳንዱ እለት ውሳኔዎቻችን ድምር ውጤት እንደመሆኗ በየቀኑ ፈቃደኝነታችንን የምናሳይባቸውና በእንቢታ የምናልፋቸው ነገሮች መኖራቸው ግድ ነው፡፡ ከዚህም በመነሣት ኑሮ እሺ ብቻ ሳይሆን እንቢም እንደሆነ እንገነዘባለን፡፡ በእርግጥም በማስተዋል ሆነን ካየነው የሚጥም እንዳለ ሁሉ የሚመር፣ የሚወራ እንዳለ ሁሉ የማይነገር፣ የሚገለጡበት እንዳለ ሁሉ የሚሸሸጉት፣ እሺታ እንዳለ ሁሉ በእንቢታ የሚለዩት መኖሩ ኑሮ ሚዛናዊነትን እንደሚጠይቅ ያስረዳናል፡፡ ለብዙዎቻችን በቦታውና በሰዓቱ እንቢ ማለት አለመቻል ብርቱ ፈተናችን ነው፡፡ ለጥቅማችን እንቢ ከምንል በእሺታችን ብንጎዳ እንመርጣለን፡፡ ነገር ግን መልካሙን በሙሉ ፈቃድ መታዘዝ እንጂ ሁሉንም እሺ ማለት ትክክል ሊሆን አይችልም፡፡ ምንም እንኳን የምንኖረው ሁሉ በተፈቀደልን ዓለም ላይ ቢሆንም በዚያው ልክ ደግሞ ሁሉም አይጠቅመንም፡፡
     በብሉይ ኪዳን እግዚአብሔርን እሺ ማለት የምድርን በረከት እንደሚያበላ ስናነብ በአዲስ ኪዳን ደግሞ ሰይጣንን እንቢ (መቃወም) ማለት ከራሱ ከእግዚአብሔር ጋር እንደሚያጣብቅ ያስረዳናል፡፡ በቦታው ካልሆነ እሺታ፤ በጊዜው የሆነ እንቢታ የተሻለ ነው፡፡ እሺታችንን እውነተኛ የሚያደርገው እሺ የምንልበት አሳማኝ ምክንያት እንደመሆኑ፤ እንቢታችንም በዚህ ጎዳና ካለፈና እውነት ካለው አግባብነቱ አጠያያቂ ሊሆን አይችልም፡፡ ስለዚህም ከከንቱ እሺታ በእውነትና በመንፈስ የሆነ እንቢታችን ዋጋው ትልቅ ነው፡፡ አንዳንድ ሰዎች እንቢ ማለት አለመቻላቸውን እንደ ጽድቅ ሲቆጥሩት እንታዘባለን፡፡ እንዲህ ያሉ ሰዎች ኃጢያትን  እየሠሩ እንቢ ባለማለታቸው ብቻ መልካም ያደረጉ የሚመስላቸው ናቸው፡፡ ጥቂት ጊዜ ወስዳችሁ እንቢ ማለት ባለመቻላችሁ አልያም እንቢ ለማለት ፈቃደኛ ባለመሆናችሁ በሕይወታችሁ ውስጥ ስለገጠማችሁ ኪሳራ አስቡ፡፡ ፈቃዳችሁም ከሆነ በአስተያየት መስጫው ላይ አካፍሉን፡፡
    እውነተኛ በሆነ መንገድ እንቢ ማለት ያልተቻላቸው ሰዎች ከሁሉም ዓይነት እያነሱ ሁሉንም ለማስደሰት ነፍሳቸውን እያስጨነቁ ከእንቢና ከእሺ ሌላ እየፈለጉ የሚኖሩ ሆነዋል፡፡ በዚህም መንገድ የሚከፍሉት ዋጋ የሚያገኛቸው ኪሳራ ሁለንተናዊ ነው፡፡ በአግባቡ እንቢ ማለት አለመቻል የኑሮን ሌላ ጎን ለማወቅ ፈቃደኛ አለመሆንም ነው፡፡ ሙሴ የፈርዖን የልጅ ልጅ መባልን በእምነት እንቢ ብሎ ከእግዚአብሔር ሕዝብ ጋር መከራን ለመቀበል ባይመርጥ፣ ዮሴፍ ከጲጥፋራ ሚስት የኃጢአት ገበታ ራሱን ባይሰበስብ የዝሙት ግብዣዋን ንቆ ባይሸሽ (እንቢ ባይል) ዛሬ ስለ እነርሱ የምናነበው ምን ሊሆን ይችል ነበር? ይህንን ባላደርግ እመርጣለሁ፣ ይህንን መሥራት እፈልጋለሁ፣ ይህንን ወድጄዋለሁ ይህን ደግሞ ጠልቼዋለሁ ማለትን መፍራት የለብንም፡፡ እውነተኛ እንቢታ የወዲያው ቢሆንም ውጤቱ ግን የእድሜ ልክ ነው፡፡ ሰዎች የማንፈጽመውን ተስፋ ከምንሰጣቸው ላንተገብረው እሺ ከምንላቸው ይልቅ በወቅቱ ለምንመልስላቸው እንቢታ ዋጋ ይሰጣሉ፡፡   
     ተወዳጆች ሆይ እንቢ ማለት ባለመቻላችሁ እንደ ሞኝ ተቆጥራችሁ፣ ከደካሞች ተደምራችሁ፣ ከሰው ትኩረት ተነፍጋችሁ፣ በመከራ ወጀብና አውሎ እያለፋችሁ፣ ኃጢአትን በውድም በግድም ተለማምዳችሁ፣ በአንደበት በድላችሁ ይሆን? ባላመንበት ነገር እሺ ብለን፣ ለቤተሰብ ደስታ ብቻ ስንል ካላረፍንበት ሰው ጋር ተሞሽረን፣ ከማንወደው ተግባርና የኑሮ ዘይቤ ጋር እየተሟገትን ይሆን? የምላችሁ ይህንን ነው “የእንቢታም ትክክል አለው” አልያ ግን “እንቢ አያውቁ” የብዕር ስማችን መሆኑ አይቀሬ ነው፡፡ ልብ በሉ! እስከ ሞት እሺ የማንለው፣ እስከ ስኬት የምናዘገየው፣ በይደር የማናቆየው ጉዳይ ሊኖረን ያስፈልጋል፡፡ “እሺ እሺ አብዝታ ቀረች ተንከራታ” እንደተባለው እንዳይሆንብን ከዓመፃ ጋር አለመተባበር ክፉውንም በእንቢታችን መኮነን ክርስትና ነውና ለዚህ መትጋት ይኖርብናል፡፡
                  ክፉውን እንቢ ብትሉ ለሐሰትም ባትታዘዙ የሰማይን በረከት ትበላላችሁ!   

2 comments:

  1. እጅግ በጣምየሚባርክ መልእክት ነው። ጌታ ጸጋውን ያብዛላችሁ እንዲህ ትውልዱን በሚያንጽ ቃል ትበረቱ ዘንድ የእውነቱ ቃል ባለቤት ክርስቶስ ኢየሱስ አብሮአችሁ ይስራ። (www.michael yemane.blogspot.com)

    ReplyDelete