Tuesday, October 23, 2012

መልከኞቹ (ካለፈው የቀጠለ)

                                                    ማክሰኞ ጥቅምት 13/2005 የምሕረት ዓመት 

“እግዚአብሔርን እንዲያውቁ በግልጥ ይናገራሉ፡፡ ዳሩ ግን የሚያስጸይፉና የማይታዘዙ ለበጎ ሥራም ሁሉ የማይበቁ ስለ ሆኑ በሥራቸው ይክዱታል” (ቲቶ. 1÷17)፡፡
          ባለፈው ንባብ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የእምነት ልጁ ለሚሆን ጢሞቴዎስ የአምልኮት መልክ ካላቸው ነገር ግን ኃይሉን ከካዱት ሰዎች እንዲርቅ የመከረበትን ክፍል መነሻ አድርገን መንፈስ ቅዱስ ለልባችን ያለውን የልቡን ምክር ለማየት ሞክረናል፡፡ እንደ ተናገሩ አለመኖርና ያመኑበትን በተግባር ምስክርነት አለማጽናት የክርስትናው ፈተና ብቻ አይደለም፡፡ አላመኑም ብለን በምንፈርጃቸው ከክርስትናው ጥሪ ተካፋይ ባልሆኑ ወገኖች ዘንድም ብርቱ ችግር ነው፡፡ ማኅበራዊ ኑሮአችን ላይም መራርነት የሚሞጅርበት እንዲህ ያለው ነገር ነው፡፡ በንግግራቸው ውስጥ መስማማት ያስተዋልንባቸው ሰዎች በተግባር ግን ሲጣሉ ተመልክተናል፡፡ ምክንያቱም በተግባር መገለጥ በቃል ከማብራራት በብዙ ከፍ ያለ ስለ ሆነ ነው፡፡
          ከእግዚአብሔር ጋር ባለን ግንኙነት ቀርቶ ሰው ከሰው በሚኖረው አብሮነት ውስጥ እንኳን መልከኛ እንጂ ኃይለኛ (የተግባር ሰው) አለመሆን ጉዳቱ የከፋ ነው፡፡ ብዙ ቤተሰባዊነት፣ ጓደኝነት፣ ወዳጅነት፣ ትዳርና ማኅበራዊነት በመልከኝነት በሽታ የተጠቁ ናቸው፡፡ ለዚህ ምክንያቱ ደግሞ ልክ በጢሞቴዎስ ዙሪያ እንደነበረው ሁሉ የሐሰተኞች ትምህርት መበራከት ነው፡፡ ሐዋርያው ይህንን መልእክት እንዲልክ ግድ ያለው በጊዜው የነበሩ የስህተት አስተማሪዎች ምእመናኑ ክርስትናን በኃይሉ (በትንሣኤው) ከመኖር ይልቅ በመልኩ (ማስመሰል) ወደ መኖር ዝቅታ እንዲመለሱ ተጽእኖ ያደርጉ ስለነበር ነው፡፡
          እንደ እውነተኛ የእግዚአብሔር አገልጋይ ሐዋርያው ያሳይ የነበረው ትጋት በእጅጉ የተገባ ነበር፡፡ በእውነት ላይ ከፍ ከፍ የሚል የትኛውንም የስህተት ትምህርትና የሥጋ ትምክህት በእግዚአብሔር አሳብ መቃወም ቅዱስ ተጋድሎ ነው፡፡ በመጨረሻው ቀን የሚያስጨንቅ ዘመን እንዲመጣ ይህንን እወቅ የሚለው አሳብ የእግዚአብሔር ሰዎች እያንዳንዱን ዘመን መዋጀት እንዳለባቸው የሚያነቃቃ ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ የአምልኮት መልክ እንዳላቸው ነገር ግን ኃይሉን እንደካዱ የሚነግረን ሃይማኖተኞች ጠባይ በጥቂቱ ሲቃኝ፡ -  
1. ራስ ወዳድነት፡ - መወደድና መውደድ በሰው ታሪክ ውስጥ ቋሚ ተግባር ነው፡፡ የማኅበራዊነት ማጣፈጫው ቅመምም ይህ በፍቅር ላይ የተመሰረተ ግንኙነት ነው፡፡ አብዛኛውን ጊዜ ራስ ወዳድነት አሉታዊ ጎኑ ብቻ ሲጠቀስ እናስተውላለን፡፡ ነገር ግን ራስን መውደድ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተነቀፈው ባልንጀራችንን በዚያው ልክ ካልወደድን ነው (ማር. 12÷31)፡፡ ከዚህም ባለፈ ሰው ራሱን ካልወደደ ከክፉ እንዴት መራቅ ይችላል?
             ክርስትና በክርስቶስ ወንድማማቾች የሆኑ ልዩ ልዩ ወገኖች ሕብረት ነው፡፡ በዚህ ውስጥ ደግሞ የተወሰደብን መብት አለ፡፡ ያውም እውነተኛ ክርስቲያን የሆነ አንድ ሰውን “ወንድሜ አይደለህም” ማለት አለመቻል ነው፡፡ በሥጋ ከአባችን የተወለደ ወንድማችንን ወንድሜ አይደለህም ማለት በሕግም በሕሊናም አግባብ እንደማይሆነው ማለት ነው፡፡ ራስ ወዳድነት እኛን በምንወድድበት ልክ ሌላውን መውደድ አለመቻል፣ እኛን የሚያስፈልገን ነገር ሌላውንም እንደሚያስፈልገው አለማሰብ ነው፡፡
2. ገንዘብን ወዳድነት፡ - በእግዚአብሔር ቃል ውስጥ የክፋት ሁሉ ስር የሚለውን ስፍራ የያዘው ገንዘብን መውደድ ነው (1 ጢሞ. 6÷10)፡፡ ጌታ በትምህርቱ አንድ ሰው ለሁለት ጌቶች መገዛት እንደማይችልና ወይ አንዱን መውደድና ሌላውን መጥላት አልያም አንዱን ንቆ ሌላውን መጠጋት እንዳለበት አስረድቶአል (ማቴ. 6÷24)፡፡ ስለዚህም ለእግዚአብሔርና ለገንዘብ መገዛት አትችሉም! በማለት ይደመድማል፡፡ ብዙዎቻችን ከእግዚአብሔር ሌላ የዚህ ዓለም ገዥ የሆነውን ዲያብሎስ ብቻ ነው የምናውቀው፡፡ ዳሩ ግን ቃሉ ገንዘብንም እንደ ሌላ ጌታ ያቀርብልናል፡፡ ጌታ የምንገዛለት አካል ነው፡፡ ገዢ ደግሞ በሙሉ ነገራችን ላይ አዛዥ ነው፡፡
            ለአንድ ክርስቲያን ገንዘብ በአግባቡ ጥቅም ላይ የሚያውለው ምድራዊ ነገር ነው፡፡ የሚያስተዳድረው እንጂ የሚተዳደርለት፣ የሚገዛው እንጂ የሚገዛለት ሊሆን ግን አይገባም፡፡ ገንዘባቸው የሚመራቸውን ሰዎች ማሰብ የምድሪቱን መከራ የማሰብ ያህል ነው፡፡ በምድራችን ላይ ከሚሠራው ከየትኛውም አመጽ ጀርባ ያለው ደጀን ገንዘብ ስለሆነ፡፡ (መልካሙን ለማድረግ የሚተጉ እንዳሉ ሆነው) ገንዘብን መውደድ የሚለው አሳብ ገንዘብን ወደ መጥላት መፍትሔ ባያደርሰንም የክፋት ስር የሚሆንበትን ሁኔታ በማስተዋል የሕይወታችንን ጌታ በገንዘባችንም ላይ ጌታ እንድናደርገው ያስገነዝበናል፡፡  
3. ትምክህትና ትዕቢት፡ - ባላቸው ነገር የሚመኩ ሰዎች እንደ አገልጋይ ያሳዝኑናል፡፡ ምክንያቱም ዓለምና ሞላዋ የእነርሱ ብትሆን እንኳ አንድ ቀን (በእግዚአብሔር የትግበራ ጊዜ) እንደ መጎናፀፊያ ልትጠቀለል የተፈረደባት በመሆኑ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ቃል እንኳን ኃጢአት የሆነውን የዚህ ዓለም ነገር ቀርቶ ጽድቃችን የምንለውን የእኛን ትምክህት የዘጋው የመርገም ጨርቅ ብሎ ነው፡፡ ሰው ይመካ ዘንድ ለሰው የተተወ አንዳች ነገር በእግዚአብሔር ዘንድ የለም፡፡ እግዚአብሔር የማንም ባለ ዕዳ ስላይደለ የሚመካ ቢኖር በእግዚአብሔር ይመካ!
            በየዘመናቱ የእግዚአብሔር ቅጣት ፍጥነትና ኃይል ከተገለጠባቸው ነገሮች አንዱ ትዕቢት ነው፡፡ አብዛኛውን ጊዜ ትምክህትና ትዕቢት ልክ እንደ ጨው ይዋዋሳሉ፡፡ የብዙ ጎበዞች ውድቀት መጀመሪያው ትዕቢት ነው፡፡ ትዕቢት ሌላውን አሳንሶ ራስን ኮፍሶ መኖር ነው፡፡ ታዲያ የእግዚአብሔር ክንድ በየጊዜው እንዲህ ያለውን ክምር ሲንድ ነው የኖረው፡፡ ትዕቢት ራስን ላለመግዛት ትልቅ አርነት ነው፡፡ በክርስቶስ ኢየሱስ የነበረውን አሳብ ልብ ካልነው “ትህትና” የሚል ነው (ፊል. 2÷5)፡፡ ትዕቢት የእግዚአብሔር ልጅ ራሱን ባዶ ባደረገበት በዚህ አሳብ ፊት እንዴት የሚብስ ቅጣት ይቀበል ዘንድ ይገባዋል?   
4. ሐሜትና ስድብ፡ - “ለቀብር የሄዱ ሰዎች አስከሬን ቀርቶባቸው “በሕይወትም እያለ አርፋጅ ነበር፡፡ ዛሬ እንኳ ምናለ በሰዓቱ ቢገኝ?” እየተባባሉ ያሙታል፡፡ ታዲያ ገና ሳይጨርሱ በለቀስኛ ታጅቦ ይደርሳል፡፡ እነዚያው ያሙት ሰዎች “ውይ እድሜው ረጅም ነው፡፡ ስናነሳው መጣ” ተባብለው በውሸት እንባ እውነተኞቹን ተቀላቀሉ፡፡” የሚል ታሪክ ባልንጀራዬ አጫውቶኛል፡፡ የሞተን ሰው እድሜው ረጅም ነው! ያሰኛቸው የሐሜት አመል ነው፡፡ ለብዙዎች ሐሜትና ስድብ ፈቃድ ያላቸው ኃጢአቶች እንደሆኑ ይሰማቸዋል፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር በዚህ ላይ ምንም አይነት ቅራኔ እንደሌለው ስለሚያስቡ ነው፡፡
            አሉ አሉ! የብዙ ሰዎችን ኑሮና ትዳር አናግቷል፡፡ ቡና አፍልተው ማማትም ማሳማትም የማለዳ ተግባራቸው የሆነ ሰዎችንም እናውቃለን፡፡ እድሜው ይጠር እያሉ ተብዬው ሲደርስ እድሜህ ረጅም ነው የሚሉ ሸንጋዮች ብዙ ናቸው፡፡ ስድብንም ስናይ ከሰዎች ክፉ ንግግር ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ሁለቱም በአፍ መበደል ናቸው፡፡ የእግዚአብሔር ቃል ስለ ስድብ ብርቱ ትምህርትን ይሰጠናል፡፡ “የመላእክት አለቃ ሚካኤል ግን ከዲያቢሎስ ጋር በተከራከረ ጊዜ ስለ ሙሴ ሥጋ ሲከራከር፡- ጌታ ይገሥጽህ አለው እንጂ የስድብን ፍርድ ሊናገረው አልደፈረም” (ይሁዳ 9) ተብሎ ተጽፏል፡፡ እውነተኛ አማኝ ለአፉ ጠባቂ አለው፡፡     
5. አለመታዘዝ፡ - መታዘዝ ከመሥዋዕት እግዚአብሐርን ማዳመጥም የአውራ በግ ስብ ከማቅረብ ይበልጣል (1 ሳሙ. 15÷22)፡፡  ቅዱስ ጳውሎስ መታዘዝን እዚህ ቦታ ላይ ያቀረበው ከወላጆች ጋር በማያያዝ ነው፡፡ ቃሉ እግዚአብሔር የሕፃንነታችን ወዳጅ እንደሆነ ቢናገርም ተግባራዊ በሆነ ሁኔታ እኛ ከእግዚአብሔር ጋር ሕብረት ከማድረጋችን በፊት ከወላጆቻችን ጋር ያለን ግንኙነት ይቀድማል፡፡ መንፈሳዊውን ልደት (ዳግም መወለድ) የሥጋ ልደት ይቀድመዋልና፡፡ ለወላጆች መታዘዝ አምላካዊ መመሪያ ያለው ትዕዛዝ ነው፡፡ የምናያቸውን የሥጋ ወላጆች መታዘዝን ካልተማርን የማናየውን የመንፈስ ወላጅ እግዚአብሔርን እንዴት እንታዘዘው ዘንድ ይቻለናል?
         ልጆች እውነትን መሰረት ባደረገ መልኩ ወላጆቻቸውን መታዘዝ ይኖርባቸዋል፡፡ ነገር ግን የእግዚአብሔርን ቃል በሚቃወምና መመሪያውን በሚጥስ መልኩ ልጆች ወላጆቻቸውን እንዲታዘዙ አግባብ አይደለም፡፡ ምክንያቱም ስለ ስሜ ቤቶችን ወይም ወንድሞችን ወይም እኅቶችን ወይም አባትን ወይም እናትን ወይም ሚስትን ወይም ልጆችን ወይም እርሻን የተወ ሁሉ መቶ እጥፍ ይቀበላል የዘላለምንም ሕይወት ይወርሳል (ማቴ. 19÷29) የሚለው የጌታ ቃል የታመነ ነው፡፡ (በዚህ ብሎግ “እሺታ ያለ ቦታው” የሚለውን ርዕስ እንድታነቡት እንጋብዛለን)!
                                                                - ይቀጥላል - 

No comments:

Post a Comment