Tuesday, October 30, 2012

መልከኞቹ (ማጠቃለያ)



               ማክሰኞ ጥቅምት 20/2005 የምሕረት ዓመት

6. የማያመሰግኑ፡ - እግዚአብሔርን አለማማረር ብቻ ሳይሆን ማመስገን አለመቻልም ኃጢአት ነው፡፡ በደሙ ዋጋ የገዛንን ጌታ ተመስገን ማለት ዋጋው ብዙ ነው፡፡ ሌሎች የሰጡን ቁሳዊ እርሱ ግን የሰጠን መንፈሳዊ በረከት ነው፡፡ ሰዎች ስለ እኛ ገንዘባቸውን፣ ጊዜያቸውን፣ አሳባቸውን ሰጥተው ይሆናል፡፡ እርሱ ግን ነፍሱን ስለ እኛ አኑሯል (ዮሐ. 15÷13)፡፡ በሰዎች ዘንድ ስለተደረገልን ነገር የምንሰጠው የምስጋና ምላሽ “ኪስ አይገባም” በሚል ማራከሻ ይጣጣል ይሆናል፡፡ እግዚአብሔር ግን ምስጋናችንን የመሥዋዕት ያህል በፊቱ ልክ እንደተወደደ መዓዛ ይቀበለዋል (ዕብ. 13÷15)፡፡  
         በአስተሳሰብ ብስለት ውስጥ ባሉ ሰዎች መካከል ምስጋና የመልካም ሰብእና አንዱ መለኪያ ነው፡፡ ተቀብሎ ያላመሰገነ እንደ ቀማኛ ይቆጠራል፡፡ ምስጋና ሰጭውን ለበለጠ ልግስና ሲጋብዝ አመስጋኙን ደግሞ ከቁራሽ ላይ የሚቆርስ አዛኝ ያደርገዋል፡፡ በመንፈሳዊ ሕይወትም አመስጋኝነት ከእግዚአብሔር ጋር ያለንን ግንኙነት የሚያሳይ ልኬት ነው፡፡ እንደውም የምትቀበለው በአመሰገንከው ልክ ነው የሚባል አባባል አለ፡፡ በእርግጥም ምስጋና ሰብእናችንን የምናስውብበት ጥሩ መዋቢያ ነው፡፡
        ዙሪያችንን ስንቃኘው ሰዎች ከምስጋና ቃል ይልቅ በብዙ የምሬት ንግግር የተሞሉ ናቸው፡፡ በቤት በአደባባይ፣ በጉዞ በመንደር የምንሰማው ሁሉ ከመዓት ቀጥሎ ያለ ሌላ መዓት ነው፡፡ አንዳንዴ በአፋችን እንደተናገርነው እንደዚያው እየተደረገብን እንደሆነ አስባለሁ፡፡ በየዕለቱ ለእግዚአብሔር ከምናቀርበው ውዳሴ በላይ ወቀሳችን የበዛ ነው፡፡ ኢዮብ ሁሉን አጥቶ “ይባረክ” (ኢዮ. 1÷21) ያለውን እግዚአብሔር እኛ ባናመሰግነው ያ ሁኔታ ምን ያህል ይወቅሰናል?
         ተወዳጆች ሆይ ምስጋና ጥቂቱን ብዙ የሚያደርግ ኃይል ነው፡፡ በሆነው ብቻ ሳይሆን ባልሆነውም፣ በተቀበላችሁት ብቻ ሳይሆን ምላሽ በዘገየባችሁ ነገር፣ አለኝ በምትሉት ብቻ ሳይሆን ነበረኝ በሆነባችሁም ነገር ሁሉ ጌታን አመስግኑ፡፡
7. ዕርቅን የማይሰሙ፡ - እንደዚህ ዘመን ሰው ከራሱ ጋር የተጣላበት ጊዜ ያለ አይመስልም፡፡ ሁሉም ራሱን እያስታመመ፣ እያባበለ፣ ለማስተራረቅ እየሞከረ ነው፡፡ ነገር ግን ከራሳችን ፀብ ጋር ለመታረቅ እንኳ የእግዚአብሔር መሐል መግባት ያስፈልገናል፡፡ ሁሉ ቢጣላ ኖሮ ማን ያስታርቅ ነበር? ብላችሁ አስባችሁ ታውቃላችሁ? የእግዚአብሔር ቃል “የሚያስተራርቁ ብፁዓን ናቸው የእግዚአብሔር ልጆች ይባላሉና” (ማቴ. 5÷9) ይላል፡፡
         የእግዚአብሔር ልጅ በመሆን ውስጥ ካሉት ትልልቅ ደስታዎች አንዱ ማስታረቅ ነው፡፡ ዛሬ መለያየትን ወደ አንድነት ለማምጣት፣ ጠላትነትን ወደ ወዳጅነት ለመቀየር የሚጠይቀው ድካም ቀላል የሚባል አይደለም፡፡ እስከ ዛሬ ድረስ ለስንት ዓመታት የሚሸመገሉ ሰዎች አሉ፡፡ እንዲህ ያለው ውኃ ቅዳ ውኃ መልስ የሃይማኖት ሰዎች የሚባሉትን ሳይቀር ይጠቀልላል፡፡ አንዳንዴ ምን አለ የጊዜውን ርዝማኔ እንኳ አክብረው ቢታረቁ ያሰኛል፡፡ እግዚአብሔር እንደ መፍትሔ አስቀምጦን እንደ ችግር ኖሮ ከማለፍ ይጠብቀን፡፡
          አንዳንዶች ለበቀል የእኔ የሚሉትን አንድ ቀን በመጠባበቅ ላይ ናቸው፡፡ ሌሎች ደግሞ ቀኑን በሙሉ በደፈጣ ያሳልፋሉ፡፡ ብዙ ሊታረቅልን የሚገባ ነገር ያለን ሰዎች ነን፡፡ እንግዲህ እርቅን አለመስማት በፀብ እንደጸኑ መቀጠል ነውና ጌታ ከሚያስተራርቁት ወገን ያድርገን፡፡
8. መልካሙን የማይወዱ፡ - መልካም አለማድረግ ምርጫ ነው፡፡ መልካሙን መቃወም ግን ከዚህ ይከፋል፡፡ በመልካምነት ላይ ውጊያ የተጀመረው ምድር ላይ አይደለም፡፡ ገና ከስነ ፍጥረት ጅማሬ አንሥቶ በሰማይ የፈነዳ አብዮት ነው፡፡ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ መልካምነትና መልካሞች ሲሰደዱ ኖረዋል እየኖሩም ነው፡፡ በዚህም ዓለም እየሆነ ያለው ይኼው ነው፡፡ መልካም የምንሆነው ጠላት ላለማፍራት አይደለም፡፡ ምርጫችን ስለ ሆነ ግን መልካም እንሆናለን፡፡ ሰው በምርጫው ደጉን ብቻ ሳይሆን ክፉውንም ያስተናግዳል፡፡ እናም ጽኑ!
         መልከኛው ክርስትና ከተገለጠባቸው ጠባያት ትልቁ ይህ ይመስለኛል፡፡ የመልካም ጥግ እግዚአብሔር ነው፡፡ ሰው የቱንም ያህል መልካም ቢሆን እግዚአብሔርን አልፎ መልካም አይሆንም፡፡ ታዲያ እንዲህ ያለውን ጌታ በመልካምነት ኃይል ሳይሆን በመልካምነት መልክ (በውስጠ ምስጢር ክፉ) ለማክበር መሞከር ምን ያህል ድፍረት ነው፡፡ ሰዎች አህዛብ ጋር ያገኙትን መልካምነት እኛ ጋር መጥተው ካጡት “ታዲያ ምን ብልጫ ታደርጋላችሁ” (ማቴ. 5÷46) የተባለው ለዚህም አይደል?
9. ከእግዚአብሔር ይልቅ ተድላን መውደድ፡ - እግዚአብሔርን የምንወድበት መንገድ የሥጋ ወላጆቻችንን እንኳ ከምንወድበት ፍቅር  ይለያል፡፡ እነርሱን በሥጋ ልደት ይህንን ዓለም እንድንቀላቀል መንገድ ስለሆኑን እንወዳቸዋለን፡፡ እርሱን ደግሞ በመልኩ እንደ ምሳሌው ስለ ፈጠረን በሰውም መካከል ሰው ሆነን እንድንገኝ ስለ ፈቀደ እንወደዋለን፡፡ ከዚህ ሁሉ በላይ በውድ ልጁ ከዘላለም ሞት ስላዳነን እንወደዋለን፡፡ በዚህም ዓለም በሚኖረን የእግረ መንገድ ቆይታ በእያንዳንዱ የሕይወት ክፍላችን ውስጥ የምናገኛቸውን ሰዎች (ትዳርንም ጨምሮ) እንወዳቸዋለን፡፡ ዳሩ ግን የእግዚአብሔርን የመወደድ ስፍራ ማንም ሊይዘው አይገባም፡፡  
        በዚህ ክፍል ላይ ሐዋርያው የሚወቅሳቸው ሰዎች እግዚአብሔርን በዚህ ዓለም ተድላ የለወጡ ናቸው፡፡ ዴማስ የአሁኑን ዓለም ተድላና ደስታ ወዶ ከእውነት እንዴት ፈቀቅ እንዳለ እናውቃለን (2ጢሞ. 4÷10)፡፡ በዘመናችንም ሰዎች ተድላንና እንደ ዓለም የሆነውን ደስታ ዋጋ ከፍለው እየወደዱ ነው፡፡ የእግዚአብሔርንም ነገር እንዲህ ባለው መንገድ ለመሸፈን እየተሞከረ ነው፡፡ ያንን የቀራንዮ ደስታ ግን የትኛውም የዚህ ዓለም ከንቱ ነገር ሊጋርደው አይችልም፡፡ ጌታን የጋረደብን ማንኛውም ተድላና ደስታ ቢኖር ግን በስሙ ሥልጣን እንዲወገድም መጸለይ ይኖርብናል፡፡   
         እግዚአብሔር ከየትኛውም ነገራችን በላይ እንድንወደው ይጠይቀናል (ዮሐ. 21÷15)፡፡ እርሱ በእኩል ፍቅር ከሌሎች ጋር የምንወደውና የምናመልከው አምላክ አይደለም፡፡ ነፍስን እስከ መስጠት ደግሞም እስከ መስቀል ሞት ታዝዞ የወደደንን ጌታ በሚበልጥ ፍቅር እንድንወደው ጸጋ ይብዛልን፡፡
መፍትሔ፡ - በአብዛኛው የአምልኮት መልክ አላቸው ኃይሉን ግን ክደዋል ተብሎ ስለ ተነገረባቸው የአፍ አማኞች ጠባይ ለመዘርዘር ሞክረናል፡፡ አሁን ደግሞ ቅዱስ ጳውሎስ ለእውነተኛ ምዕመናን ያስቀመጠውን መፍትሔ እናያለን፡፡
ሀ. ቃሉ፡ - የእግዚአብሔር ቃል ጥሩ መንሽ ነው፡፡ እውነቱን ከሐሰት፣ ቅዱሱን ከርኩሰት፣ ጽድቁን ከኃጢአት አጥርተን እንድንለይ ይረዳናል፡፡ አብዛኛውን ጊዜ መደናገርና ለስሕተት አሠራር መመቸት የሚመጣው ቃሉን በሙላት ባለመረዳት ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ መፍትሔው ቃሉን ዕለት ዕለት መመርመር ነው (ሐዋ. 17÷10)፡፡ ይህ ከሆነ ኃይለኛ እንጂ መልከኛ በሆነ አምልኮ ውስጥ አንወድቅም፡፡
ለ. እውነቱን መከተል፡ - ሰዎች እውነትን መረዳት ብቻ ሳይሆን የተረዱትንም እውነት መከተል ይቸግራቸዋል፡፡ ጌታ የሚወደኝ ቢኖር ይከተለኝ ሲል በእውነተኛነቴ የተስማማ ቢኖር ይከተለኝ ማለቱ ነው፡፡ ለተረዳነው የእግዚአብሔር ቃል ምላሽ የምንሰጠው እውነቱን በመከተልና በቃል ብቻ ሳይሆን በሥራ ላይም በማዋል ነው፡፡
ሐ. መራቅ፡ - መራቅን በትንሹ በሁለት መንገድ ልናየው እንችላለን፡፡ የልብና የአካል በሚል! ሁለቱም ችግሩ በሚጠይቀው መጠን አስፈላጊ ናቸው፡፡ “የጌታን ስም የሚጠራ ሁሉ ከዓመፅ ይራቅ” (2ጢሞ. 2÷19) የሚለው ማኅተም ያለበት የተደላደለ የእግዚአብሔር መሠረት እስካለ ድረስ ክርስትናን በእውነተኛ ኑሮ መግለጥ ለሚፈልጉ ሁሉ ጠንካራ ትዕዛዝ ነው፡፡ ክፉ ባልንጀርነት መልካሙን የክርስትና ኑሮአችንን የሚያጠፋው ከሆነ ጊዜ መስጠት ለቀብር መሰናዳት ነው፡፡ ማስተዋል ይብዛላችሁ!
            

No comments:

Post a Comment