Friday, February 21, 2014

ምክር፡

                               
                           አርብ የካቲት 14 ቀን 2006 የምሕረት ዓመት

          ልጄ ሆይ፤ ዋዘኛና ቀልደኛ አትሁን፡፡ በመከራ ለሚኖሩ ሰዎች ሁሉ የምታዝንና የምትራራ ሁን፤ በድኃ ላይ አትጨክን፤ ርስቱንና ቤቱንም በምክንያት አትውሰድበት፤ ለመጨረስም የማትችለውን ነገር አትጀምር፡፡ እሳትና የሞላ ውኃ አትድፈር፡፡ በማናቸውም ነገር ከሚበልጥህ ሰው ጋር ባልንጀርነት አትያዝ፡፡ ከዳኛ ጋር ወዳጅ ሁን፡፡ በፊቱ በቆምህ ጊዜ እውነቱን እንዲፈርድልህ፡፡ ከሀኪምም ጋር ወዳጅ ሁን፡፡ በታመምህ ጊዜ ፈጥኖ እንዲመጣልህ፡፡

          ልጄ ሆይ፤ በልተህ ስትጠግብ ረኃብን፤ ስትበለጥግ ድኅነትን፤ ስትሾም ሽረትን፤ ሌላውንም ይህን የመሰለውን ሁሉ አትርሳ፡፡

         ልጄ ሆይ፤ ለሞተው ወዳጅህ ከማልቀስ ይልቅ በሕይወቱ ሳለ የክፋት ሥራ ለሚሠራ ወዳጅህ አልቅስለት፡፡

         ልጄ ሆይ፤ ባለ ጠጋ ሲወድቅ ሰው ሁሉ ይደግፈዋል፤ ድኃ ሲወድቅ ግን ሰው ሁሉ ወዲያው ይገፋዋል፡፡ ባለ ጠጋ ሲከሰስ በሸንጎ የተቀመጠው ሁሉ ይሟገትለታል፤ ድሀ ሲከሰስ ግን በሸንጎ የተቀመጠው ሁሉ ይፈርድበታል፡፡ መልካም ዳኛ በመካከላቸው የተቀመጠ እንደ ሆነ ግን ፍርዱ እንደ ፀሐይ ያበራለታል፡፡ ስለዚህ በምትኖርበት ሀገር መልካም ዳኛ አያጥፋብህ፡፡

Tuesday, February 18, 2014

ምክር፡

                                    Please Read in PDF: Miker 4

                                       
                    ማክሰኞ የካቲት 11 ቀን 2006 የምሕረት ዓመት

        ልጄ ሆይ፤ ክፉ ሕልም አለምሁ ብለህ አትደንግጥ፡፡ ደግ ሕልምም አየሁ ብለህ ደስ አይበልህ፡፡ ሕልም ማለት የሰው አሳብ እንደ ሆነ እወቅ፡፡ እንኳን ሌሊት በሕልም ቀንም ባይን የታየ ነገር ሳይደረግ ይቀራል፡፡ ደግሞ ሌሊት በሕልም፤ ቀንም ባይን ያልታየ ነገር እንዲያው በድንገት ይደረጋል፡፡ እግዚአብሔር ይሁን ያለው ነገር ጊዜውን ይጠብቃል እንጂ ምንም ቢሆን ሳይሆን አይቀርም፡፡

         ልጄ ሆይ፤ አካልህና ልብስህ ዘወትር ንጹሕ ይሁን፡፡ እጅህን ለሥራ፤ ዓይንህን ለማየት፤ ጆሮህን ለመስማት ፈጣኖች አድርግ፡፡ አፍህን ግን በጠንካራ ልጓም ለጉመህ ያዝ፡፡ አረጋገጥህ በዝግታ፤ አነጋገርህ በለዘብታ ይሁን፡፡ ያልነገሩህን አትስማ፤ ያልሰጡህን አትቀበል፡፡ ያልጠየቁህን አትመልስ፡፡ ሽቅርቅር አትሁን፤ ንብረትህ ጠቅላላ ይሁን፤ ምግብህና መጠጥህ በልክ ሆኖ ያው የጠዳና የጣፈጠ ይሁን፡፡ ምግብህና መጠጥህም የሚቀርብበት ዕቃ ሁሉ ንጹሕ ይሁን፡፡ የምትተኛበት አልጋና የምትቀመጥበት ስፍራ ከእድፍና ከጉድፍ ንጹሕ ይሁን፡፡ በእውነትና በሚገባ ነገር ሁሉ ይሉኝታ አትፍራ፡፡ የምትሠራው ሥራ ሁሉ የመንግሥት ሥራ ካልሆነ በቀር ፖለቲከኛ አትሁን፡፡

Tuesday, February 11, 2014

ምክር፡



                         ማክሰኞ የካቲት 4 ቀን 2006 የምሕረት ዓመት

       ልጄ ሆይ፤ በነገርህ ሁሉ የታመንህ ሁሉ፡፡ በአነጋገርህም ደማም ሁን፡፡ ሰውን የሚያስፈራና የሚያሳዝን ነገር ለመናገር አትድፈር፡፡ በልዝብ ምላስ ሰውን አታታል፡፡ ሰውንም ከሚያሙ ሰዎች ጋር አትደባለቅ፡፡ ልጄ ሆይ፤ ንብረትህ በልክ ይሁን፡፡ ቤተ ሰዎችም አታብዛ የቀንድ ከብትና የጋማ ከብትም በብዙ አታርባ፡፡ ላንተ የማይገባውን ነገር ከማንም ቢሆን አትቀበል፡፡ አንተም ለማንም ቢሆን የማይገባውን ነገር አትስጥ፡፡ የማታገኘውንም ነገር አትመኝ፡፡ በዓይንህ ካላየህና እርግጥ መሆኑን ካልተረዳኸው በቀር በማንም ሰው ላይ የሚወራውን ወሬ እውነት ነው ብለህ አትቀበል፡፡ ለሰውነትህ የሚያስፈልገውን ነገር ለማግኘት አስብ እንጂ ሰው የሚጠፋበትን ሰው የሚጨነቅበትን ነገር አታስብ፡፡

       ልጄ ሆይ፤ ሮጠህ ለማታመልጠው ነገር አትሽሽ፡፡ እርሱም ሞት ነው፡፡ ደጋ ብትወጣ፤ ቆላ ብትወርድ፤ ወንዝ ተሻግረህ ብትሔድ፤ በዋሻ ብትደበቅ፤ ጠመንጃና መድፍ ይዘህ ብትሰለፍ ምንም ቢሆን ከሞት ለማምለጥ አትችልም፡፡ እግዚአብሔርንም ፍራ በሥጋና በነፍስ ላይ ሥልጣን አለውና፡፡ ንጉሥንም አክብር እግዚአብሔር ሠይፍን አስታጥቆታልና፡፡ በአንተም ላይ የሹመት ሥልጣን ያላቸውን አገረ ገዢዎችን ሁሉ አክብራቸው፤ ታዘዝላቸው፡፡ አባትና እናትህን፤ የእግዚአብሔርን ቃል የሚያስተምሩህን መምህሮችህን፤ የሀገር ሽማግሌዎችንና ባልቴቶችን ሁሉ በሚቻልህ ነገር እርዳቸው፡፡

       ልጄ ሆይ፤ ካረጀህ በኋላ እንደ ገና ተመልሼ ምነው ልጅ በሆንኩ ብለህ አትመኝ፡፡ ምንም ቢሆን አታገኘውምና፡፡ ወደፊትም ምነው በሞትኩ ብለህ አትመኝ፤ ምንም ቢሆን አይቀርልህምና፡፡
        ልጄ ሆይ፤ እገሌ ቸር ነው ይበሉኝ ብለህ ገንዘብህን ለማንም አትስጥ፡፡ ለወዳጅ ከመስጠት ለዘመድ መስጠት ይሻላል፡፡ ለጠላት ከመስጠት ለወዳጅ መስጠት ይሻላል፡፡ ከሁሉ ይልቅ ለተቸገሩ ድሆች መስጠት ይበልጣል፡፡ ለድሆች የሰጠ ሰው ብድሩን በሰማይ ያገኛል፡፡

       ልጄ ሆይ፤ ማናቸውንም ነገር ቢሆን ለመስማት እንጂ ለመናገር አትቸኩል፡፡ ከወዳጅህም ጋር በተጣላህ ጊዜ ቀድሞ በወዳጅነታችሁ ጊዜ የነገረህን ምስጢር አታውጣበት፡፡ ከወዳጅህም ጋራ አንድ ጊዜ ጠብ ከጀመርክ በኋላ፤ ምንም ብትታረቅ ሁለተኛ ምስጢርህን ለእርሱ ለመናገር አትድፈር፡፡ ቂምህንም አትርሳ፡፡ ቂምህን አትርሳ ማለቴ ከታረቅህ በኋላ ክፉ አድርግበት ማለቴ አይደለም፡፡ ነገር ግን እርሱ ሞትንና ኩነኔን የማያስብ ክፉ ሰው የሆነ እንደ ሆነ እርቅ አፍርሶ እንዳያጠፋህ ሳትዘናጋ ተጠንቅቀህ ተቀመጥ ማለቴ ነው፡፡

Sunday, February 9, 2014

ምክር፡

                                   Please Read in PDF: Miker 2                                 
                                 
                           እሁድ የካቲት 2 ቀን 2006 የምሕረት ዓመት


       ልጄ ሆይ፤ ይህ ዓለም ቀድሞ ከወዴት መጣ ኋላስ ወዴት ይሄዳል ብለህ ለመመርመር አትጨነቅ፡፡ እንኳን የዓለምን ነገር የራስህንም ነገር መርምረህ ለማወቅ አትችልም፡፡ አሳብህም ሁሉ ለዛሬ ብቻ ይሁን እንጂ ላለፈው ቀን ለትናቱ፤ ወይም ለሚመጣው ቀን ለነገ አታስብ፡፡

      ልጄ ሆይ፤ ወዳጅ ማለት ሰው አይምሰልህ፡፡ ነገር ግን ወዳጅ ማለት ጊዜ ነውና በጊዜህ ሁሉ ይወድሃል፤ አለጊዜህ ግን ወዳጅህ እንኳ ይጠላሃል፡፡ ጊዜ ማለትም ቀንና ሌሊት አይምሰልህ፡፡ ነገር ግን ጊዜ ማለት የእግዚአብሔር አሳብ የሚፈጸምበት ነው፡፡ ስለዚህ በሆነውም በሚሆነውም ነገር ሁሉ የእግዚአብሔር ፈቃድ ይሁን እያልህ ተቀመጥ፡፡

      ልጄ ሆይ፤ ብዙ ተድላና ደስታ ለማድረግ አትጨነቅ፤ ይህንን ለማድረግ የፈለግህ እንደ ሆነ ግን ለሰው መራራትና ደግነትን አታገኛቸውም፡፡ ስለዚህ ተድላና ደስታህ በልክ ይሁን፤ እድሜህንም ያለ ሀዘንና ያለ መከራ በደስታ ብቻ ለመጨረስ አይሆንልህም፡፡ ነገር ግን ሀዘንና ደስታ ከባሕርይህ ጋር ባንድነት ተዋህደው የሚኖሩ ናቸውና በእድሜህ ሙሉ ሁለቱንም በየተራ ታገኛቸዋለህ፤ ካልሞትህም በቀር ከኀዘንና ኃጢአት ከመሥራት አትድንም፡፡

      ልጄ ሆይ፤ መቅሰፍት ይመጣብኛል ብለህ አትጨነቅ፡፡ ትልቅ መቅሠፍት ማለት አሳብ ማብዛት ነው፡፡ ልጄ ሆይ፤ የሰውን ነገር ችሎ ለማይኖርና አሳብ ለሚያበዛ ከኃጢአቱም ለማይመለስ ሰው ቶሎ መሞት ይሻለዋል፡፡

      ልጄ ሆይ፤ ደጉን ሰው ለማጥፋት አታስብ፤ ደጉን ሰው ለማጥፋት ብታስብ ግን ራስህን ጨምረህ ታጠፋለህ፡፡ ለሌላ ሰውም የክፋትን መንገድ አታስተምር፡፡ ፈጣሪህም እግዚአብሔር እንደ ሆነ እመን፡፡ ነገር ግን የእርሱን መጀመሪያና መጨረሻ መርምሬ አገኘዋለሁ ብለህ አትጨነቅ፡፡

Friday, February 7, 2014

ምክር፡

                         አርብ ጥር 30 ቀን 2006 የምሕረት ዓመት

       ‹‹የተወደድህ ልጄ ሆይ፤ ሰው ሁሉ በዚህ ዓለም የሚኖርበት ዘመኑ እጅግ አጭር ነው፡፡ ከዚያም የሚበዛው በመከራና በሀዘን ይፈጸማል፡፡ ይህንንም መከራና ሀዘን አንዳንድ ሰዎች በገዛ እጃቸው ፈልገው ያመጡታል፡፡ አንዳንድ ሰዎች ግን ሳያስቡት በድንገት ይመጣባቸዋል፡፡ መከራና ሀዘን በገዛ እጃቸው ፈልገው የሚያመጡ እንዴት ያሉ ሰዎች ናቸው ትለኝ እንደ ሆነ ስማኝ ልንገርህ፡፡

       አንዳንድ ሰዎች የሰው ገንዘብ ሊሰርቁ ሄደው እዚያው ይሞታሉ ወይም ተይዘው ይቀጣሉ፡፡ አንዳንድ ሰዎች የሰው ሚስት ለመቀማት ሄደው እዚያው ላይ ይሞታሉ ወይም ይቆስላሉ፡፡ አንዳንድ ሰዎች ሰውን ለማጥፋት የሐሰት ነገር ይዘው ይነሡና ባወጡት ዳኛ በቆጠሩት ምስክር ተረተው ይቀጣሉ፡፡ አንዳንድ ሰዎች የሰው ማኅተም አስመስለው ቀርጸው አትመው በውስጡም የሐሰት ቃል ጽፈው ይገኙና ይቀጣሉ፡፡ አንዳንድ ሰዎች አይታወቅብንም አይሰማብንም ብለው ንጉሥ ለመግደል  መንግሥት ለማጥፋት ሲመክሩ ይገኛሉና ብርቱ ቅጣት ይቀጣሉ፡፡ አንዳንድ ሰዎች ለኩራትና ለትእቢት ብለው አንበሳና ዝሆን ለመግደል በረሃ ይወርዱና በበረሃ በሽታ ይሞታሉ ወይም ያው ለመግደል የፈለጉት አውሬ ይገድላቸዋል፡፡

       እነዚህን የመሰሉ በገዛ እጃቸው መከራንና ኀዘንን በራሳቸው የሚያመጡ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ ደግሞ ሳያስቡት በድንገት መከራና ኀዘን የሚመጣባቸው እንዴት ያሉ ሰዎች ናቸው ትለኝ እንደ ሆነ ስማኝ ልንገርህ፡፡

Wednesday, February 5, 2014

ከዛፉ ውረዱ (ካለፈው የቀጠለ)


                                 Please Read in PDF: Kezafu Weredu 2
                                                                     
                           እሮብ ጥር 28 ቀን 2006 የምሕረት ዓመት

            ሱሰኛ መሆን ማለት፡

1. በአንድ ነገር ተጽእኖ (ባሪያ) ስር ማደር ነው፡ ሰዉ በቤተሰቡ አልያም ራሱን በራሱ የሚያስተዳድር ብቻ አይደለም፡፡ የተለያዩ አሳዳሪዎችም አሉት፡፡ ከአንዳንዶቹ ለመፈታት ጥቂት አቅም የሚጠይቅ ሲሆን ሌሎቹ ግን በአብዛኛው ያታግላሉ፡፡ ሱስ ባሪያ ላደረገን ነገር መኖር ነው፡፡ በማያቋርጥ ድግምግሞሽ ከተሸነፍንለት ሱስ ጋር መታየት ነው፡፡ አንድ ሰው ያለ ተጨማሪ ነገር ሊከውን የሚችለውን ያለ ሱሳችን ማድረግ አለመቻልም ነው፡፡ ተጽእኖው ያየለ እንደ መሆኑ ሕይወትን እስከ መክሰር ወዳሉ ውሳኔዎች ያደርሳል፡፡ ለአመጽ ያስጨክናል፣ ለጭብጥ እፍኝ  የማይሞላውን ያደፋፍራል፡፡ ከእውነታው ጋር ሳይሆን ከምናባችን ጋር ነዋሪ ያደርገናል፡፡ ማኅበረሰቡ ትልቅ ግምት ለሚሰጣቸው ነገሮች ትኩረት ነፋጊ መሆንን ያስከትላል፡፡ በጋራ እንድንኖርባት በተሰጠችን ዓለም የራሳችንን ሌላ ዓለም እንድንፈጥርና ራሳችንን እንድናገልል እንሆናለን፡፡ ‹‹አላስችልህ አለኝ›› የምንልበት ጎጂ ነገር ካለ በእርግጥም ሱሰኛ ሆነናል ማለት ነው፡፡

        አብዛኛውን ጊዜ ሱስን ከጫት፣ ከሲጋራ፣ ከሀሺሽ፣ ከአልኮል . . ጋር ብቻ ማያያዝ የተለመደ ነው፡፡ በእርግጥ እንደነዚህ ያሉ ነገሮች በግልጥ የምናስተውላቸውና ማኅበረሰቡ ችግሩ መሐል ሆኖ ሲቃወማቸው የቆዩ ጎጂ ልምምዶች ናቸው፡፡ ነገር ግን ጠንከር ያለና ቁርጥ ተቃውሞ ታይቷል ለማለት አያስደፍርም፡፡ እኔ እንደማስበው ለዚህ ምክንያቱ ማኅበረሰቡ ከፍተኛ ግምት የሚሰጣቸው ሰዎች ራሳቸው ሱሰኛ መሆናቸው ይመስለኛል፡፡

       በሱሰኝነት ላይ የተደረጉ ጥናቶችን በተወሰነ መልኩ ለማየት ሞክሬያለሁ፡፡ ዳሩ ግን ተግባራዊ ለመሆንና ለውጥ ለማምጣት አልታደሉም፡፡ ምናልባትም ጥናቶቹ ራሳቸው በሱሰኞች የተሠሩ ይመስሉኛል፡፡ ያልተለወጠ አይለውጥምና ቤተ መፃሕፍት ከማሞቅ ያለፈ ወደ ሞት እሳት እየተማገደ ያለውን ትውልድ ሊታደጉት አልቻሉም፡፡ ሱሰኝነት ከተለያዩ አመሎች ጋር ይዛመዳል፡፡ ጫት ማላመጥ ብቻ ሳይሆን ክፋት ማመንዠግም ሱስ ሆኖ ይታያል፡፡ ሲጋራ ማጨስ ብቻ ሳይሆን ሰው ማጨስም ከባድና ጎጂ ሱስ ነው፡፡ ‹‹አመሏ ነው›› እንደ ልባቸው እንዲኖሩ ፈቃድ የሆናቸው ብዙ ሱሰኞች አሉ፡፡ የተላመድነው ክፉ ጠባይ ካላስገበረ ያስፋሽካል፡፡