Tuesday, June 5, 2012

ጅቡም ይበላል (ክፍል ሁለት)


    በተነሣንበት ርእሰ ጉዳይ ላይ ያላችሁን አስተያየትና የግል አመለካከታችሁን እንድታካፍሉን በጠየቅነው መሠረት ከተላኩልን መካከል መርጠን ከዚህ በታች እናስነብባለን፡፡ ሁሉንም ማካተት ባለመቻላችን ቅር እንደማትሰኙ በመተማመን ይህንን ማድረግ ባለመቻላችን ይቅርታ እንጠይቃለን፡፡

1. በመጀመሪያ ለውይይት የጋበዛችሁበትን ርእሰ ጉዳይ እንደወደድኩት መግለጽ እፈልጋለሁ፡፡ እኔ ርዕሱን ከቤተክርስቲያን (ኢ.ኦ.ተ.ቤ/ን) ነባራዊ ሁኔታ አንጻር ቃኝቼ ለመመልከት ሞክሬያለሁ፡፡ በቤተ እምነታችን ውስጥ ስር የሰደደና እድሜ ጠገብ ችግር እንዳለ የማይካድ መሆኑ እንዳለ ሆኖ ነገር ግን ችግሩን ለመቅረፍ እውነተኛ ትጋትና ልብ የሚደርስ መፍትሔ አለመታየቱ ከምናወራው ችግር በላይ አሳሳቢ እንደሆነ ይሰማኛል፡፡ የትኛውም ቦታ ችግር፣ አለመግባባት፣ መንገድ መሳት መኖሩ እሙን ነው፡፡ ግን ችግሩን ወደነው ደግሞም ተስማምተን መዝለቅ ከቻል ይህ ድንዛዜና አዚም ነው፡፡

        በመንፈስ ቅዱስ እንደተሸሙ በሚነግሩን ዳሩ ግን የመንፈስ ቅዱስ ፍሬ በማናይባቸው አባቶች ዘንድ እንዲመጣ የምንመኘው አስተዳደራዊ ለውጥ የአሁኑ ይባስ ወደሚያሰኝ ደረጃ መጥቶአል፡፡ ለዚህም ደግሞ እንደ ማባባሻ ሆኖ የታየኝ ሕጉን (ቃለ ዐዋዲ) የራሳቸው ጥቅም ማስከበሪያ፣ እውነት ገፍቶ ሲመጣ ደግሞ ማሸሻ አጥር አድርገው መጠቀማቸው እንደሆነ ይሰማኛል፡፡ ማንኛውም ሕግ የሚወጣው ለራስ አሳብ የሁል ጊዜ ይሁንታ ማግኛ ለመሆን ሳይሆን ሰዎች መብትና ግዴታቸውን ጠንቅቀው በማወቅ ተግባራቸውን ፍትሐዊ በሆነ መንገድ መከወን እንዲችሉ ለማስቻል ነው፡፡ ከዚህ ውጪ ከሆነ ግን ሕጉን (መተዳደሪያ) ያለ አግባብ ተርጉመውታል አልያም ፍየል ወዲያ ቅዝምዝም ወዲህ አይነት ሆኖአል ማለት ነው፡፡ ይህ ደግሞ በሕሊናም በፈጣሪም ፊት በወንጀለኝነት የሚያቆም ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን እያየን ያለነውም ከዚህ ቢብስ እንጂ የተሻለ አይደለም፡፡  

      ጅቡም ይበላል የሚለው አሳብ የሚነሣው እዚህ ላይ ነው፡፡ የምናየውና የምንሰማው ብልሽት እንዲስተካከል የተገኘውን ሁሉ አማራጭ ተጠቅመናል ብዬ በግል አምናለሁ፡፡ ብዙ ሰዎች ለዚህ ብርቱ ዋጋ ከፍለዋል፡፡ ዛሬም ግን ቤ/ን የአሕዛብ መዘባበቻ፣ የጠቃዋሚዎች መሳለቂያ ከመሆን አልወጣችም፡፡ ታዲያ ይህን ጊዜ ጅቡም ይበላል እንዳላችሁት እኛ አንነካ እንጂ ሌላው ድፍት ይበል ብለው በእግዚአብሔር መንጋ ላይ የሚያንኮራፉትን ልንቃወም የተገለጠና ማስረጃ ጠገብ የሆነ ጉዳይ ያለባቸውን ደግሞ እንዲሻሩ መታገል ይኖርብናል እላለሁ፡፡ እረኛ ጉበኛ ነው! ሕዝቡ ሲተኛ ነቅቶ የሚፀልይ፣ ሊመጣ ያለውንም በመንፈስ ቀድሞ የሚያስተውል ነው፡፡ ዛሬ ግን እኛ ስንጸልይ እነርሱ እያንኮራፉ ነው፡፡ እንኳን ሊሆን ያለውን ሊነግሩን ቀርቶ የሆነውን ያለፉ አባቶች እውነተኛ የኑሮ ፍሬ በተግባር እየካዱት ነው፡፡ ክብራቸው እንደተነካ ሲሰማቸው ግን እንደ ሳማ ቅጠል የሚለበልቡ ናቸው፡፡ እናማ ምእመናን ለመፍትሐየ የሚቀርበውን አማራጭ ሁሉ ከዘጉት ጅቡም ይበላል ማለት ያለብን አይመስላችሁም? እግዚአብሔር ያስበን፡፡                                     
                                                                      ሐብተ ማርያም ክፍሌ

2. ከዚህም በላይ በትጋት መፃፍ እንዳለባችሁ ይሰማኛል፡፡ አስተያየት ለመስጠት ያህል ያነሣችሁት ርእሰ ጉዳይ ሰፊና በብዙ ሊያነጋግር የሚችል ሆኖ ሳለ ሃይማኖታዊ ነገር ላይ ሚዛኑ ያጋደል ነው፡፡ ይህ ደግሞ አንባቢዎች በተለያየ እድሜና የእውቀት ደረጃ ላይ ያሉ እንደመሆናቸው አሳባቸውን ከፈለጉት አንግልና በፈለጉት መልኩ እንዳይገልጹ ጫና የሚያሳድር ይመስለኛል፡፡ ስለዚህ ጽሑፉ ቦይ ባይቀድና የራሱን መስመር ባያበጅ እንዲሁም ሰዎችን ከራሳቸው እይታ አንፃር እንዲመለከቱ አርነት ቢሰጥ መልካም ነው እላለሁ፡፡
                                                                            አቤ

3. ርእሱን ከኢኮኖሚና ከፖለቲካ አንፃር ብንመለከተው ልባችንን የሚኮረኩርና ጩኽታችንን የሚጮኽልን እንደሆነ አምናለሁ፡፡ ብሎጋችሁን ሳነብ የመጀመሪያዬ እንደመሆኑ አመለካከቴን ለመግለጽ የሚጋብዝ ርእስ በማግኘቴ ተደስቻለሁ፡፡ ልጅ ሳለሁ “የሚበላው ያጣ ሕዝብ አንድ ቀን መሪውን መብላቱ አይቀርም” የሚል አባባል ሰምቻለሁ፡፡ እውነታውን እየተረዳሁት የመጣሁት ግን ርሀብ ምን እንደሆነ በደንብ ስማር ነው፡፡ ስለ ምግብ ብቻ እያወራሁአችሁ እንዳልሆነ እንደምትረዱልኝ ተማምኜባችሁአለሁ፡፡ ፍትሕ፣ ነፃነት፣ ሰላም፣ እኩልነት እነዚህ ሁሉ በምንም የማንደልላቸው ርሀቦች ናቸው፡፡ የእነዚህን መጓደል እንጀራ አይተካውም፡፡
ይቀጥላል


No comments:

Post a Comment