Friday, June 1, 2012

ጅቡም ይበላል


            
         በአገራችን የገጠሩ ክፍል በጅብ የተነከሰ የቤት እንስሳ እንደ ርኩስ ስለሚቆጠር አይበላም፡፡ ታዲያ አንድ የቆሎ ተማሪ ጅብ የነከሰው በግ በልቶ ስለነበር ወደ መምህሩ ዘንድ በመሄድ “የኔታ ጅብ የነከሰው በግ ይበላል ወይስ አይበላም?” በማለት ጠየቃቸው፡፡ መምህሩም የአይን ጥቅሻ ያህል አሰብ አድርገው “አካባቢው ላይ ሌላ የምግብ አማራጭ አለ ወይስ የለም?” በማለት ለጥያቄው ጥያቄ መለሱለት፡፡ ተሜም “በፍጹም አማራጭ አልነበረም” ሲል መለሰላቸው፡፡ አስተዋዩ መምህር “እንግዲያማ እንኳን በጉ ጅቡም ይበላል” አሉት፡፡
         ድህነት አማራጭ ማጣት ነው፡፡ የከፋ ቅጣት ትኩረት መነፈግ ነው፡፡ ትልቁ ሞት ተስፋ መቁረጥ ነው፡፡ የሠራችሁትን የሚበላ፣ የወለዳችሁትን የሚስም፣ ጣፋጭ ቃላችሁን የሚሰማ፣ ቀርባችሁ የሚሸሽ፣ ፈልጋችሁ የሚሸሸግ፣ ምራችሁ የሚበቀል፣ ወዳችሁ የሚገፋ ሲበረክት ውሳኔያችሁ የጨነቀው እርጉዝ ያገባል ስትወልድበት ግራ ይጋባል አይነት መሆኑ በኑሮአችን ውስጥ የሚስተዋል ሐቅ ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ልጆቻቸውን ቀቅለው ስለ በሉ እናቶች፣ ለአገልጋዮች ብቻ የተፈቀደውን መሥዋዕት ስለበላ ነቢይ ዳዊት እናነባለን፡፡
         አማራጭ ማጣት የጠሉትን ያስቀላውጣል፣ የተጸየፉትን ያስታቅፋል፣ ሰው መሐል ብቸኛ ያደርጋል፣ ሕሊናን ተጋፍቶ ድንበር ያስጥሳል፡፡ በየሆስፒታሉ ሐኪሙን እባክህ አድነኝ! ትምህርቴን ልጨርስ፣ እናትና አባቴን ልጡር፣ እንደ ሰው ወግ ማዕረግ ልይ፣ ልጆቼን ላሳድግ እያሉ የሚሞቱ ወገኖቻችን ያለ መሞት አማራጭ ቢኖራቸው ኖሮ ሞትን ፊት ለፊት ባልጨለጡት ነበር፡፡ ዳሩ ግን ምን ያደርጋል? ሐኪሙ አይኑ ፈጦ ሟች በድን ይሆናል፡፡ ቀጣዩ ቀብር ብቻ ነው!!
         አንዳንድ ጊዜ በኪሳችሁ ብዙ ብር ይዛችሁ ምን እንደምትበሉ፣ ምን እንደምትገዙ ግራ ገብቶአችሁ አያውቅም? ለካ የምንፈልገውን ለማግኘት የመግዛት አቅማችን ብቻውን በቂ አይደለም? ደጃችን ድረስ የምንፈልገው ነገር ሲመጣ ይህንን ለሚያደርጉ ሰዎችስ አክብሮታችን ምን ያህል ነው? በእርግጥ አንድ እውነት አለ፡፡ ሰው ላልደከመበትና ዋጋ ላላስከፈለው ነገር ያለው ምልከታ የወረደ ነው፡፡ ይህ ሊሆን ግን አግባብ አይደለም!
        በሰው ላይ ከመፍረዳችን በፊት ልክ ከላይ እንደተመለከትነው የተግባር መምህር አውጥተን አውርደን፣ ዙሪያ ገባውን ፈትሸን ነገሩን ለመመርመር የምንጥር ስንቶቻችን ነን? ወይንስ አይናችሁ እንዳየች፤ ጆሮአችሁ እንደሰማች ትፈርዳላችሁ?               
         ውድ አንባቢዎች በዚህ ርዕስና አሳብ ዙሪያ በሰፊው ብንወያይበት እንዲሁም ለእናንተ የታያችሁን ብታካፍሉን መልካም ነውና በፍቅር እንጋብዛችሁአለን፡፡ በአድራሻችን betefikir@gmail.com ብላችሁ ላኩልን፡፡
ይቀጥላል
                              

4 comments:

  1. Amarach yata sew enkuan liyadergew liyasibewim yemaywedewin neger liyaderg yichilal. Gin ye Egziabher lij Eyesus kirstos amarach yelelew mirchachin new. Bemanignawim yenuro hunet wist binhon ke ersu wichi nuro mot new...Libachin be Egziabher yitsina!

    ReplyDelete