Friday, June 22, 2012

ማን ያግባሽ? (ክፍል ሁለት)



          በመጀመሪያው ክፍለ ንባባችን አንባቢዎች አሳባችሁን እንድትገልጹ በመጋበዝ በይቀጥላል ቀጠሮ እንዳጠናቀቅን የሚታወስ ነው፡፡ በዚህ መሰረት ከተላኩልን አሳቦች መካከል መርጠን ከዚህ በታች እናስነብባለን፡፡

1. ስለ እውነት ለመናገር ርዕሱን ስመለከት ጥያቄው ለእኔ ብቻ የቀረበ ያህል ተሰምቶኛል፡፡ ቤተ ፍቅር በዚህ ርእሰ ጉዳይ የምንወያይበትን አሳብ ስላቀረባችሁ በግል ደስ ብሎኛል፡፡ ለዚህ ምክንያቴ ደግሞ በጋብቻ ላይ ያለው ፈርጀ ብዙ ችግር ነው፡፡ ወደ ትዳር የገቡትን ስናይ “ላም . . . ወልዳ እንዳትልሰው እሳት እንዳትተወው ልጅ ሆነባት” አይነት ነው፡፡ መጋባት ለመረዳዳት መሆኑ ቀርቶ ለመጎዳዳት ሆኗል፡፡ ብዙዎችም እናርፋለን ብለው እሳት ላይ ተጥደዋል፡፡ ታዲያ የቤተሰብና የሕብረተሰብ ምንጭ ስለሆነው ትዳር መወያየት፣ ትውልድ ስለሚቀረጽበት ተቋም መነጋገር አገብጋቢ ጉዳይ ይመስለኛል፡፡
       ቀጥታ ወደ አሳቤ ስገባ እንደ እኔ አመለካከት ብር ያለውን አልያም አፍ ያለውን ማግባት የትዳርን ዝልቀትና ጣዕም አይወስነውም፡፡ ለመኖር እጅግ አስፈላጊው ነገር ያለው ባለን ላይ ሳይሆን በሆነው ላይ ነው፡፡ ጥሩ ስብእና ኖሮት ሀብት ካለው በያዘው ላይ በጥበብ የሚያዝ እንጂ የሀብቱ ሎሌ አይሆንም፡፡ እንደዚሁ መደመጥ በቃል ብዛት የሚመስለውም አፈኛ ትልቁ ቋንቋ አሳብ እንደሆነ ያስተዋለ ስብእና ካለው የትዳሩ ምሰሶ በዚያኛው ሀብት በዚህኛው አፍ መሆኑ ቀርቶ እውነተኛ ልብ ይሆናል፡፡ ይህ ድምዳሜዬ በመነሻ ካስነበባችሁን የጥበበኛው አባት መደምደሚያ ጋር በአብላጫው ይመሳሰላል፡፡
        በዙ ጊዜ ሃይማኖተኛ በሆኑ ሰዎች ዘንድ የሚስተዋለው አንድ አቅጣጫ ብቻ ነው፡፡ ልጁ አልያም ልጅቷ መንፈሳዊ የሆነ አልያም የሚመስል ነገር በእነርሱ ዘንድ ማየታችን ብቻ! ሕይወት ከብዙ አቅጣጫ መመልከትን ትጠይቃለች፡፡ ለዚህ አጋርነት የምንመርጠው ሰው አስተዳደግ፣ ለትዳር ያለው ምልከታ፣ ለደስታና ለሀዘን፣ ለማግኘትና ለማጣት ያለው አተያየት፣ ለወላጆቹ ያለው ፍቅር ወዘተ መስተዋል ይገባቸዋል፡፡ እንዲህ ማድረግ መጠራጠር አይመስለኝም፡፡ እኔ እንዲህ ያለውን ሒደት መጠበብ ነው የምለው ወይም በኋላ መማቀቅ እንዳይመጣ ቀድሞ መጠንቀቅ፡፡ እኔን ማን ያግባሽ ካላችሁኝ “ሀብቱም አፉም ልቡ የሆነ” የሚል ምላሽ አለኝ፡፡ ቤታችሁ የፍቅር ይሁን!!
                                                                            ትህትና ለገሰ

2. ሙሽራው ክርስቶስ ለእጮኛው ያቀረበው ጥያቄ አድርገን ብንመለከተው በነፍሳችን ብዙ የምናተርፍ ይመስለኛል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “በእግዚአብሔር ቅንዓት እቀናላችኋለሁና እንደ ንጽሕት ድንግል እናንተን ለክርስቶስ ላቀርብ ለአንድ ወንድ አጭቻችኋለሁና . . .” (2ቆሮ. 11÷2) በማለት የታሰብንለትን ክብር ያስተዋውቀናል፡፡ ትዳር ባለበት በየትኛውም ዘመን እንዲህ ያለው የመተጫጨት ሂደት መኖሩ ሲታሰብ ልብን ፈገግ የሚያደርግና ለመደነቅ የሚያበቃ የበዛ ምክንያት ባይሰጥም ከሁሉ ለሚበልጥ ጌታ እጮኛ የመሆን ነገር ግን ከመታሰብ የሚያልፍ ተግባራዊ ደስታ አለው፡፡ አንድ ታላቅ ንጉሥ ሎሌውን ወደ ትንሽ መንደርና የድንኳን ቤት ልኮ በዚያ ውስጥ የምትኖርን ጎስቋላና ምስኪን ሴት ለልጁ ሚስትነት ቢያጫት ምንኛ ድንቅ ነው?
        በማግባትና በመጋባት መካከል ልዩነት መኖሩ ለሚያስተውሉ ሁሉ ግልጽ ይመስለኛል፡፡ ማግባት የአንደኛውን ወገን የማሳመን ኃይል የሚያጎላ ሲሆን መጋባት ግን በሁለት ሰዎች መሐል ያለን የጋራ መግባባት (መስማማት) የሚያሳይ ነው፡፡ ይህ ሐቅ በተግባራዊው ኑሮ ላይም በድምቀት ይስተዋላል፡፡ በአንድ ሰው የፍቅርም ሆነ የኃይል ተጽእኖ ስር የወደቁ ትዳሮች በገቡ እንጂ ባላገቡ አጋሮች የዘወትር ልሰናበት ጥያቄ የተወጠሩ ናቸው፡፡ መጋባትን በአግባቡ የፈጸሙ ሰዎች ትዳር ውስጥ ልዩነትን ወደ አንድነት፣ መራራቅን ወደ ቅርበት ሲያመጡት እንመለከታለን፡፡ ምክንያቱም አንዱ በሌላው ውስጥ ብቻ ሳይሆን ሌላውም በአንዱ ውስጥ ስፍራን አግኝቶአል፡፡    
                                                                
                                                                ይቀጥላል

2 comments:

  1. Ewinet new bemegibat ena bemegabat mekakel tilik liyunet ena. Megibat be akal mekerareb sihon megabat gin be lib anid mehonin yichemiral!...ye Egziabher tsega yibizalachu!

    ReplyDelete
  2. Hiwot bebizu akitacha memelketin tishalech bemilew hasab esimamalew. Minim enquan menfesawi sew negerochin befikir ena betigist yemimeleket bihonim ye gar amelekaket bemiteyku gudayoch lay gin temesasay akuam kelele alemegibabat menoru aykerim.

    ReplyDelete