Tuesday, July 24, 2012

የቃየል መንገድ


                 
       ከውድቀት በኋላ የሰው ልጅ ከእግዚአብሔር ጋር ያለው ግንኙነት በመሥዋዕት ላይ የተመሰረተ እንደሆነ በቅዱሳት መጽሐፍት ውስጥ እናስተውላለን፡፡ ሰው በእግዚበብሔር መልክነት እንደምሳሌው የኖረባቸው ጊዜያት እጅግ የተወደዱና የመለኮትን አሳብ መታዘዝ የታየባቸው ቢሆኑም ሰው እንዲህ ያለውን ቅዱስ ሕብረት ጠብቆ የዘለቀው ለአጭር ጊዜ ነው፡፡
       እግዚአብሔር ለሰው የሚያስፈልገውን ሁሉ አስቀድሞ በመፍጠር ሰውን በተጠናቀቀና በተዋበ ዓለም በማስቀመጥ ምን ያህል አሳቢና አፍቃሪ መሆኑን አሳይቶናል፡፡ ዳሩ ግን ሰው ከነበጀቱ እንደ ዔደን ገነት ባለው ያማረ ስፍራ መቀመጡ ደግሞም ሊጠቀም የሚችልበት ብዙ አማራጭ መሐል መመላለሱ ፈጣሪውን ላለመበደል አቅም አልሆነውም፡፡ ስለዚህ ባለመታዘዝ ጠንቅ ኃጢአት በአንድ ሰው አዳም ምክንያት ወደ ዓለም ገባ፡፡ ከዚህ የተነሣ ሰው እግዚአብሔር ፊት የሚቆምበት መንፈሳዊ ድፍረትና ተቀባይነት አጣ፡፡
       አዳም ከበደለ በኋላ በመልኩ እንደ ምሳሌው ልጅ በመውለዱ ኃጢአተኝነት ለሰው ሁሉ ደረሰ (ዘፍ. 5÷1)፡፡ ይህ ክፍል እኔ ባልበደልኩትና በስፋራው ላይ ተገኝቼ ባልበላሁት ከአዳም ኃጢአት ጋር ስለ ምን እደመራለሁ? ለሚለው የአንዳንድ ሰዎች ሙግት ከበቂ በላይ ምላሽ የሚሆን ይመስለኛል፡፡ እግዚአብሔር አዳምን በመልኩ (ጽድቅ፣ ቅድስናና እውቀት) እንደ ምሳሌው (ምድርን መግዛት) እንደፈጠረው ከተረዳን (ዘፍ. 1÷26) ከውድቀት በኋላ ኃጢአተኛው አዳም በመልኩ (ኃጢአተኝነት) እንደ ምሳሌው (ፍርሃት) ልጅ በመውለዱ ኃጢአት በዘር የሚደርስ (orginal sin) ሆኖአል፡፡ 
        አቤልና ቃየልን የምናገኛቸው በዘፍጥረት ምዕራፍ አራት ላይ ሲሆን ርእሳችን የሚገኘው ደግሞ በይሁዳ መልእክት ውስጥ ነው፡፡ በዘፍጥረት መጽሐፍና በይሁዳ መልእክት መካከል የብዙ ዘመናት ልዩነት አለ፡፡ ዳሩ ግን በሁለቱም ዘመናት ውስጥ አንድ መንገድ እንመለከታለን፡፡ ይህም የቃየል መንገድ ነው (ይሁዳ 11)፡፡ የቃየል መንገድ በአዲስ ኪዳኗ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በስህተት አስተማሪዎች ምክንያት ጠላት በስንዴው መካከል ከዘራቸው እንክርዳድ ትምህርቶች አንዱ ነው፡፡ እንደነዚህ ላሉቱ እግዚአብሔር ያለውን መልእክት ሐዋርያው ሲናገር “ወዮላቸው” በማለት ነው፡፡ ይህም የመንገዱን አስከፊነት እንዲሁም የቅጣቱን ክብደት የምንረዳበት እጅግ ግልጥ የሆነ ማሳያ ነው፡፡
        የያዕቆብ ወንድም የይሁዳ መልእክት አንድ ምእራፍ ያለው ቢሆንም በውስጡ የያዘው ትምህርት ግን በጣም ሰፊ ነው፡፡ ሾልከው ስለ ገቡ የስህተት ትምህርቶች፣ የአምላካችንን ጸጋ በሴሰኝነት ስለሚለውጡ ሴሰኛች፣ ንጉሣችንንና ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን ስለሚክዱ ዓመፀኛች፣ ሥጋቸውን ስለሚያረክሱ ግድየለሾች፣ ጌትነትን ስለሚጥሉ ትዕቢተኞች፣ ሥልጣን ያላቸውን ስለሚሳደቡ ሰነፎች እንዲሁም ውኃ ስለሌለባቸው ደመናዎች (የስህተት አስተማሪዎች) በመልእክቱ ውስጥ ከተጠቀሱት አሳቦች መካከል ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ መልእክቱን በማስተዋል ሆነን በመንፈስ ቅዱስ አጋዥነት ብናጠናው ልባችንን  የሚሞላና ለነፍሳችን የሚረባ ብዙ ትምህርት እንዳለው አምናለሁ፡፡
        “ከብዙ ቀን በኋላም ቃየል ከምድር ፍሬ ለእግዚአብሔር መሥዋዕትን አቀረበ፡፡ አቤልም ደግሞ ከበጎቹ በኩራትና ከስቡ አቀረበ፡፡ እግዚአብሔርም ወደ አቤልና ወደ መሥዋዕቱ ተመለከተ ወደ ቃየልና ወደ መሥዋዕቱ ግን አልተመለከተም (ዘፍ. 4÷4)” የመጀመሪያዎቹ ቤተሰቦቻችን የመጀመሪያ ልጆች ታሪክ ነው፡፡ ዛሬ የምናያቸው ብዙ ብልሽቶች ጽንሰትና ውልደት የሚጀምረው ከላይ ባለበብነው ክፍል ላይ ነው፡፡ በእድሜያችን የምንሠራው በጎም ሆነ ክፉ ተግባር በወደፊቱ ትውልድ ላይ የሚኖረው መልካምም ሆነ መጥፎ ተጽእኖ ግልጽና ብዙ ነው፡፡
        ወንድማማቾቹ በመሠዊያው ፊት መሥዋዕታቸውን ይዘው ሲቀርቡ እነርሱ ብቻ አይደሉም የተለያዩት ከእነርሱ በኋላ የተነሣውም ትውልድ መሠዊያው ፊት ሲደርስ እየተለያየ ነው የኖረው፡፡ ስለመለያየት ስናወራ እነሆ የዓለምን ሁሉ ኃጢአት የሚያስተሰርይ የእግዚአብሔር በግ ቀራንዮ መስቀል ላይ በተሰቀለ ጊዜ በቀኝና በግራ የተሰቀሉትን ሁለት ወንበዴዎች እናስታውሳቸዋለን፡፡ በመስረቅ ብቻ ሳይሆን በመግደልም ሕብረት አድርገው የኖሩ፤ ፍቅራቸው በክፉ ባልንጀርነት ላይ የተመሰረተ ዓመፀኞች ነበሩ፡፡ ዳሩ ግን ራሱን የዘላለም መሥዋዕት አድርጎ ባቀረበው፣ ስለ ሁሉ በሞተው በአንዱ በክርስቶስ ደግሞም ለዘላለም ሞታችን ማርከሻ የዘላለም ሕይወት በሆነው ጌታ መስማማት አልቻሉም፡፡ አንዱ በእግዚአብሔር ልጅ ላይ ያለውን ጠንካራ እምነት ሲመሰክር ሌላው ደግሞ እኔነቱንና ትምክህቱን አሳየ፡፡ ይህም ለሁለቱ ባልንጀሮች የአንድና የሁለት ቀን ሳይሆን የዘላለም ልዩነት ሆነ፡፡
      ከላይ ባነሣነው ርእስ ዙሪያ ማለትም ስለ ቃየልና አቤል አብዛኞቻችን ደጋግመን ስለሰማነው በቂ እይታ እንዳለን የምናስብ እንደመሆኑ አንባቢዎች ይህ ታሪክ በይሁዳ መልእክት ላይ ከተጠቀሰበት ምክንያት አንፃር ያላችሁን አስተያየት ብትሰጡበት የተሻለ በመሆኑ በትህትና እንጋብዛለን፡፡
                                                
                                                        - ይቀጥላል -
        

No comments:

Post a Comment