Tuesday, July 17, 2012

በመልካም መበደል (ካለፈው የቀጠለ)


        
ባለፈው ጽሑፋችን በመልካምነት ስለመበደል በመጠኑ ለመነጋገር የሞከርን ሲሆን በዚህ ክፍልም ያነሣነውን ርእስ በተሻለ በማብራራትና የሚረባንን አሳብ በማንሸራሸር መጣጥፋችንን እናጠናቅቃለን፡፡
       አንድ አባት “በዚህ ዘመን መልካምነት መልክ ሆኖአል” በማለት የተናገሩትን አስታውሰዋለሁ፡፡ ምን ማለት ፈልገው ይሆን? ብዬ ስጠይቅ በቀጥታ አእምሮዬ ውስጥ የመጣው የእግዚአብሔር ቃል ነው፡፡ እርሱም “የአምልኮት መልክ አላቸው ኃይሉን ግን ክደዋል (2 ጢሞ. 3÷5)” የሚል ነው፡፡ ይህ የተፃፈው በጊዜው ለቅዱስ ጳውሎስ የመንፈስ ልጁ ለሚሆን ለጢሞቴዎስ ነው፡፡ ነገር ግን ከመንፈስ ቅዱስ የመጣ መመሪያ እንደመሆኑ እኛም ራሳችንን እንፈትሽበት ደግሞም ተግባራዊ እናደርገው ዘንድ የተገባ ቃል ነው፡፡
       የአምልኮት መልክ አላቸው የሚለው አገላለጽ ላላመኑት የተነገረ አይደለም፡፡ ይልቁንም በቂ እምነት አለን ብለው ለሚመፃደቁት፣ ክርስቶስ እንዳላቸው ለሚለፍፉት፣ በእግዚአብሔር ስም በእናመልካለን ምክንያት ለሚሰበሰቡት ነው፡፡ ይህንን ማሰብ ምንኛ ልብን የሚያዝል ነገር ነው? ብዙ ጊዜ የክርስትናውን ማኅበረሰብ ስንመለከት አብዛኛው ክርስቲያን ስለመሆኑ የሚጨነቅ ሳይሆን በመባሉ የረካ ብቻ ነው፡፡
       ጌታ በአንድ ስፍራ ላይ ለደቀ መዛሙርቱ ሲናገር ጽድቃችሁ (መልካምነት) ከፈሪሳውያን ጽድቅ ካልበለጠ መንግስተ ሰማያት መግባት አትችሉም (ማቴ. 5÷20) ብሏል፡፡ ፈሪሳውያን ትልቁ ትምክህታቸው የአብርሃም ልጅ መሆናቸው ነበር፡፡ የአብርሃም ልጅ መሆን መልካም ነገር ነው፡፡ ዳሩ ግን የአብርሃም ልጅነታቸውን የአብርሃምን ተግባር ለመፈፀም ሳይሆን ለማፍረስ ተጠቀሙበት፡፡ በመልካሙ በደሉበት! ጌታ ግን ያለተግባር መመሳሰል የዘር ፉከራው ፋይዳ እንደሌለው በተግሣጽ ተናገራቸው፡፡ በእርግጥም በዓመጽ እየኖሩ በሰው ጽድቅ ተንጠላጥሎ ለመጽደቅ መሞከር የከፋ አመጽ ነው፡፡ ለዚህ ነው ከላይ አባባላቸውን የተዋስነው አባት ስለ መልከኛው መልካምነት የነገሩን፡፡
       በክርስትናው ውስጥ እየታየ ያለው ውድቀት ኃይሉን መካድ ነው፡፡ ክፉው መልካምን ለብሶ ከተንቀሳቀሰ በቀጥታ መልካምነት ኃይሉ ተክዶአል ማለት ነው፡፡ ስሙ አለ ግን ሞቶአል! ባለፈው ክፍል ላይ የመጀመሪያውን በመልካም የመበደል ትርጉም አይተናል፡፡ በዚህ ክፍል ደግሞ ሁለተኛውን አይነት ማለትም ከትዕቢት የመነጨውን በመልካም የመበደል ሁኔታ እንመለከታለን፡፡
       በወንጌላዊው ሉቃስ መጽሐፍ ውስጥ መንፈስ ቅዱስ ከሚያስነብበን አስደናቂ ድርጊት መካከል ፈሪሳዊውና ቀራጩ በእግዚአብሔር ፊት ያቀረቡት ጸሎት ልንነጋገርበት ላሰብነው ለዚህ ርእሰ ጉዳይ ግልጥ የሆነ ትስስር ያለው ነው፡፡ (ሉቃ. 18÷9-14) ኢየሱስ ክርስቶስ ሊያገለግል ነፍሱንም ለብዙዎች ቤዛ አድርጎ ሊሰጥ የመጣበትን ዓላማ ለማሰናከል ሰይጣን አብዝቶ ከተጠቀመባቸው መካከል ፈሪሳውያን በዋናነት ይጠቀሳሉ፡፡ ጌታም አለማመናቸውንና ራሳቸውን ማጽደቃቸውን በብርቱ ሲቃወመው እንመለከታለን፡፡        
       ለሁላችንም ግልጽ እንደሚሆነው ፈሪሳውያን ጌታን ከጠሉበት ጥልቅ ምክንያት አንዱ ለዘመናት ተሸፍኖ በኖረው ኃጢአታቸው መካከል ፍጹም ንፁሕ የሆነው ጌታ ሲገኝ ከበሬታን በሚሰጣቸው ሕዝብ መካከል ነውራቸው መጋለጡ ነው፡፡ ፀሐይ እንዳረፈችበት ቆሻሻ ብርሃን የሆነው ክርስቶስ ጽድቃችን ብለው በሚመኩበት ተግባራቸው ፊት ሲቆም የተመኩበት መልካምነት እንደ መርገም ጨርቅ ሆኖ ታየ፡፡ ስለዚህም ካፈርኩ አይመልሰኝ አይነት ዘመቻ በጌታ ላይ ዘመቱ፡፡
       ጌታ ፈሪሳውያንን ለእግዚአብሔር ዕዳቸውን ለመክፈል እንዳልቻሉ ድሆች (ሉቃ. 7÷40)፣ የተሻለ መቀመጫ ለማግኘት እንደሚጣሉ እንግዶች (ሉቃ. 14÷7) በታዛዥነታቸው እየተመኩ ለሌሎች ጉድለት ግድ እንደሌላቸው ልጆች (ሉቃ. 15÷25) አድርጎ ገልጾአቸዋል፡፡ ፈሪሳዊው በሳምንት ሁለት ጊዜ እንደሚፆም ደግሞም አስራት እንደሚያወጣ ከዚህ ሁሉ በላይ እንደ ቀራጩ ባለመሆኑ እንደሚያመሰግነው አይኖቹን አንስቶ ለእግዚአብሔር አስረዳ፡፡ (ማቴ. 23÷23) ቀራጩ ግን ድካሙን በበቂ ሁኔታ የተረዳ ስለነበር ደረቱን እየደቃ የእግዚአብሔርን ምሕረት ይጠይቅ ነበር፡፡
       ጌታ ቀራጮችን ቤተ ክርስቲያንን እንዳልሰማ አረመኔ ገልጾአቸዋል፡፡ (ማቴ. 18÷17) በሌላ ስፍራ ግን በኋላ ማቴዎስ የተባለውን ሌዊ ከቀራጭነት ተነሥቶ እንዲከተለው እንደጠየቀው ተጠቅሷል (ሉቃ. 5÷27)፡፡ በጸሎት ጌታ ፊት የቆመው ቀራጭ መልካሙን ጸሎት በመልካም ሲጠቀምበት፤ ፈሪሳዊው ግን እንዲህ ባለው በጎ ነገር ይበድልበት ነበር፡፡ ቀራጩ ስለ ራሱ ኃጢአት ግዝፈት ሲያስተውል ፈሪሳዊው ግን ስለ ራሱ ልብ በቂ ዕውቀት አልነበረውም፡፡ ብዙ ሰዎች ስለ ሰዎች መውጣትና መግባት በቂ መረጃ ሲኖራቸው ስለ ራሳቸው ብርታትና ድካም ግን አያውቁም፡፡ ካስተዋልን ሰውን ለመክሰስና ለመውቀስ ፈሪሳዊው በጸሎት ስፍራ ላይ ምን ይሠራል? ምክንያቱም ስፍራውን ያለ አላማው እየተጠቀመበት ነው፡፡ ዛሬም እየተመለከትን ያለነው ይህንኑ ነው፡፡
       ቤተ ክርስቲያን የእርቅ ቦታ ሆና ሳለ የእግዚአብሔር አደባባዮች መሰዳደቢያ ሲከፋም ድንጋይ መወራወሪያ ሆነዋል፡፡ ሲጀመር ድንጋይ ለመወርወር፣ ለመሳደብ፣ ለመደባደብ መፆምና መጸለይ አያስፈልግም፡፡ የሚያስፈልገው ጥሩ ዱርዬ መሆን ነው፡፡ ለባልንጀራ ጉድጓድ ለመቆፈርም አስቀዳሽ አወዳሽ መሆን አይጠይቅም፡፡ ይህንን ጡንቻ ለማፈርጠም የሚጠይቀው የክፋትን ብረት መግፋት ብቻ ነው፡፡ ሰዎች የእግዚአብሔርን ቃል ያህል በልባቸው አሳብ ሲመሩ ማየት ምንኛ አሳፋሪ ነው፡፡ እኛ መንፈሳዊ ስድብ፣ አድማ፣ ድብድብ፣ አመጽ አለን፡፡ ነገር ግን ይህንን ከየት አመጣነው? ከማንስ ተማርነው? በመልካሙ መበደል ይሏችኋል ይህ ነው፡፡ እንዲህ ያለው ደግሞ ሳናውቅ በስህተት አይነት የሚሠራ አይደለም፡፡ ሆን ተብሎ እውነትን ረግጦ በእግዚአብሔር አሳብ ላይ የሚፈጸም አመጽ ነው፡፡
       ፈሪሳዊው በትእቢቱ ሲኮነን ቀራጩ ግን በእምነቱ ሊድን ችሏል፡፡ የፈሪሳዊው ጸሎት ስለ ቀራጩ ለእግዚአብሔር መረጃ እንደማቀበልም ነበር፡፡ ራሳችንን እንደ መንፈሳዊ ፓፓራዚ የምናስብ፣ ለእግዚአብሔር የመረጃ ምንጭ እንደሆን የሚሰማን ካለን በደላችን ጌታን አውቅልሃለው የማለት ያህል ነውና ፈጥነን ንስሐ እንግባ፡፡ በመልካሙ ፆም፣ በመልካሙ ጸሎት፣ በጎ በሆነው መንፈሳዊ ተግባር የምንበድልበት ከሆነ እንግዲህ የእኛ ብልጫ ምኑ ላይ ነው?    

3 comments:

  1. Egziabher yibarkachu betam astemari hasab new.

    ReplyDelete
  2. Melkaminet leyismula yemininorew hiwot sayhon yemaninetachin megelecha lihon yigebal. Mikinyatum bemasimesel yemininorew hiwot wist ereft yelemina!

    ReplyDelete
  3. ye-geta stegawi yibizalachihu ei-nidihi bale masitewali yemitasitelalifuti melieikiti yezelalemi hiyiweti newi

    ReplyDelete