Tuesday, May 29, 2012

ይታገሉታል እንጂ አይታደሉትም



 
         ዓይናችሁ በተነሣንበት ርእስ ላይ እንዳረፈ አንድ ነገር ለማስተካከል እንደምትሞክሩ እገምታለሁ፡፡ ነገር ግን ዛሬ ለማየት የምንሞክረው ስለምንታገለው እንጂ ስለምንታደለው ነገር ስላልሆነ “ይታደሉታል እንጂ አይታገሉትም” የሚለውን የተለመደ ብሒል ከላይ በአነበብነው መልኩ ተክተነዋል፡፡

         ሰዎችን ለሕይወት እንዳላቸው አመለካከት በዕድል አልያም በሥራ የሚያምኑ ብለን ልንከፍላቸው እንችላለን፡፡ ስኬትን የእድል ተጽእኖ ውጤት አድርገው የሚመለከቱ ወገኖች ሁሉንም ነገር ከዐርባና ከሰማንያ ቀን ዕጣ ፈንታ ጋር አያይዘው የሚመለከቱ ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ ስኬታማነትን የታታሪነት ውጤት አድርገው የሚመለከቱ ሰዎች መመሪያቸው “ጥረህ ግረህ ብላ” የሚለው ቅዱስ ትእዛዝ ነው፡፡ እድልና ጥረት አብዛኛውን ጊዜ አከራካሪ እንዲሁም ለተለያዩ አሳቦች መንሸራሸር ምክንያቶች እንደመሆናቸው ብዙ ምንጮችን ባጣቀሰና አሳበ ሰፊ በሆነ ሁኔታ ልናብራራቸው አሳማኝ ምክንያት አይፈቅድልንም፡፡

         ቆም ብለን ለማገናዘብ ፋታ ካገኘን ለምንድ ነው ሰዎች “ይታደሉታል እንጂ አይታገሉትም” የሚለውን አባባል የሚጠቀሙት? ደግሞ ሌላ ጥያቄ እናክልና ለዚህ አባባል በሰዎች ልቡና ውስጥ ያለው መነሻና መድረሻስ ምን ሊሆን ይችላል? እናንተ የቻላችሁትን ያህል ለመጠየቅ ሞክሩ፡፡ እኔ ግን ለጊዜው የታየኝን ልግለጽ “ምሬትና ተስፋ መቁረጥ” እንደ መነሻ፤ እድል የሚያመጣውን መጠበቅና በስንፍና መርካት ደግሞ እንደ መድረሻ (የመነሻው ውጤት) ሆነው አግኝቼአቸዋለሁ፡፡ ብዙ ሞክረን አልሳካ ሲለን፣ ያዝነው ያልነው ነፋስን የመከተል ያህል ሲሆንብን አወይ እድሌ! እንላለን፡፡ ታዲያ ይህ ወደ በለጠ ትጋት ሳይሆን ወደባሰ ውሳኔ የምንደርስበት ሆኖ ይስተዋላል፡፡ ጊዜው ለእኔ ጥሩ አይደለም፤ እድሌም ጠማማ ነው በማለት ለስንፍና እንዳረጋለን፡፡  

         የመታደል እንጂ ያለመታገል አመለካከት ለብዙዎች እምነታቸውም ጭምር ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ የተበላሸው እንዲስተካከል፣ የጠመመው እንዲቀና፣ የሳተው እንዲመለስ፣ የዛለው እንዲበረታ ከመሥራት ይልቅ “ስላልታደልኩ ነው እንጂ ይህና ያ አይሆንብኝም ነበር” በማለት አለመታደላቸውን የሚነግሩን ብዙ ናቸው፡፡ ይህ አባባል እኔ አልችልም ጌታ ግን ይችላል፣ እኔ አልዋጋም እርሱ ግን ይታገልልኛል፣ ጌታ በአሸነፈው ውጊያ ድሉ ለእኔ ይቆጠርልኛል (መታደል)፣ የሚሰማኝ ይሰማዋል በሚል እምነት የምንናገረው ከሆነ ጠንካራ ጎኑ ያይላል፡፡ ነገር ግን ይህንን ማለት መቻል በራሱ ሌላ ትግል ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ብዙ ሰው ማመንን እንደ ቀላል፣ መሥራትን ግን እንደ ተራራ ሲመለከት ነው የኖረው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ማወቅ (መጽሐፍትን መመርመር) እንደ ክህደት አለማስተዋል ደግሞ እንደ እምነት እየተቆጠረ የኖርንበት ዘመን የትየለሌ ነው፡፡ የታመነው ምስክር ግን  “የሰናፍጭ ቅንጣት የምታህል እምነት ተራራን ማንፏቀቅ፣ ግንድንም ወደ ባህር ልብ ማስጠም ትችላለች” ብሎናል፡፡ አቅሙ ስላለን እንሠራ ይሆናል አቅም ስላለን ግን አናምንም፡፡ ብዙ የሚረዱ አሕዛብ እንዳሉ እናውቃለን፡፡ ይህ ግን ወደ እውነት አላደረሳቸውም፡፡

                          ይታደለዋል እንጂ ከጌታ ደጅ ጠንቶ፤

                          አሁን ምን ያደርጋል አንዱ በአንዱ ቀንቶ፡፡

         ክርስትና ሩጫውን (መልካሙን ገድል) ለመጨረስ የምንተጋበት ሜዳ እንደመሆኑ በእምነት ሆኖ መታገል ግድ ይላል፡፡ (2 ጢሞ. 4÷7) ክርስቲያን ወታደር እንደመሆኑ በጦሩ ሜዳ ላይ ድልን ለመቀዳጀት ጸጋውን ትምክህት በማድረግ መታገሉ አማራጭ የሌለው መንገድ ነው፡፡ ነገር ግን በመንፈሳዊው አኗኗር ረገድ የእግዚአብሔርን ዕቃ ጦር ከመልበስና በመንፈስ ሠይፍ ክፉውን ከመቃወም፣ የጠላትን አሠራር ከመታገል ይልቅ የእግዚአብሔርን መንጋ እረኛ ለሚመስሉ የግብር ተኩላዎች፣ አሳቢ ለሚመስሉ የጥቅም ባሪያዎች፣ እኔ የጎደለኝ ምንድነው? ከማለት ይልቅ ወንድሜ ለምን ተቀባይነት አገኘ ለሚሉ ቃየሎች፣ እውነትን በተራበ ሕዝብ ላይ ተረት ለሚያጋሱ ባልቴቶች አለመታደላችንን እየለፈፍን እጅና እግራችንን አጣጥፈን ብንቀመጥ ባለ ዕዳ ከመሆን አናመልጥም፡፡

        እግዚአብሔር የልቡን አሳብ ያካፈላቸው፣ የቃሉ ደጅ የተከፈተላቸው፣ የሰማዩን በማስተዋል የተባረኩ ብዙ አዋቂዎች እንዳልተረዳ ፈርተው ኖረው ፈርተው ሞተዋል፡፡ እውነትን እስከ መጋደል ባንመሰክር የማወቃችን ትርፉ ምንድነው? ያወቅነውን ለሌሎች ለማካፈል ከመታገል ይልቅ በአልታደልኩም መደለያ ለራሳችን እየሞቅን ብቻ መኖር ደስታው ምን ጋር ነው?

        እውነት ሰማይና ምድር የጸኑበት ነው፡፡ ነቢያትና ሐዋርያት ሸንጎ ለሸንጎ የተንከራተቱለት፣ በአደባባይ እስከ ደም መፍሰስ የመሰከሩለት ነው፡፡ መጥምቁ ዮሐንስ የንስሐን አዋጅ የሰበከው የእግዚአብሔርን በግ ያስተዋወቀው አንበጣ እየበላ የግመል ጠጉር እየለበሰ ነበር፡፡ ከአመጸኛው ዓለም የተለየውም ላመነበት እውነት በመሞት ነው፡፡ እኛ የላመ የጣመ እየበላን፣ ያማረ የተዋበ እየለበስን ለእውነት ባንመሰክር ደግሞም ለዚህ ባንታገል ምንኛ ምስኪኖች ነን፡፡ አንድ ጉባኤ ላይ መምህሩ አስተምሮ ከጨረሰ በኋላ አንድ አባት ቀረብ ብለው “በጌታ የተነገረውን የሰሙትም ለእኛ ያጸኑትን እግዚአብሔርም እንደ ራሱ ፈቃድ በምልክትና በድንቅ ነገር በልዩ ልዩ ተአምራትም መንፈስ ቅዱስንም በማከፋፈል አብሮ የመሰከረለትን እውነት ትተህ አንድ ሰዓት ሙሉ በአሳብህ ልክ የሰፋኸውን ውሸት የጋትከን ማን አስጨንቆህ ነው” ያሉትን አስታውሳለሁ፡፡

        የእግዚአብሔር ቃል የሚያዘን ከትግልም ከፍ ያለ ነገር ነው፡፡ ይህም ለቅዱሳን አንድ ጊዜ ፈጽሞ ስለተሰጠ ሃይማኖት እንድንጋደል የሚመክር ነው፡፡ (ይሁዳ 3) ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ የእግዚአብሔርን ምሥጢር እርሱንም ክርስቶስን እንዲያውቁ እጋደላለሁ የተሰወረ የጥበብና የእውቀት መዝገብ ሁሉ በእርሱ ነውና ይለናል፡፡ (ቆላ. 2÷1) በዚህ መሠረት የምንታገልለት ብቻ ሳይሆን የምንጋደልለት ሃይማኖት ክርስቶስ ነው፡፡

       ጌታ የይሁዳ አንበሳ ነውና በዙሪያችን የሚውጠውን ፈልጎ እንደ አንበሳ የሚያደባ የጨለማ ኃይል ሁሉ አያስፈራንም፡፡ እርሱ የሕይወት ውኃ ምንጭ ነውና ሰባት እጥፍ የሚነደው እሳታቸው ላቆሙት ስህተት አያንበረክከንም፡፡ ሁሉን ያያልና በምናየው አናማርርም፡፡ ሁሉን ይሰማልና በምንሰማው አንሸበርም፡፡ ሁሉን ያውቃልና ባልደረስንበት ነገር ተስፋ አንቆርጥም፡፡ ሰው እንዲህ ካለው የጥበብና የእውቀት መዝገብ ካልቀዳ የአረም መጫወቻ መሆኑ እሙን ነው፡፡

       የመጀመሪያዎቹ ክርስቲያኖች በድቅድቅ ጨለማ ላሉት የሚደነቀውን የወንጌል ብርሃን  ያደረሱት በብዙ ትግልና መጋደል ነው፡፡ እዚህ አልታገልኩም እንጂ አልታደልኩም የሚል ምክንያት የለም፡፡ በዚህ ዓለም ባለው ኑሮአችንም እንዲሁ ነው፡፡ ዛሬ ላለንበት የኑሮ ደረጃ (ድህነት) ያበቃን አለመታደል ነው ወይስ አለመታገል? የትዳራችሁ መፈታት፣ የጎጆአችሁ መፍረስ አለመታደል ነው ወይስ አለመታገል? የልጆች ስነ ምግባር መጉደል፣ የወላጆች መወስለት አለመታገል ወይስ አለመታደል? በመስሪያ ቤት፣ በቤተ እምነት ያለው የከፋና የተበላሸ አስተዳደር አብሮን ያለው ስላልታገል ወይስ ስላልታደልን? ጊዜያችንን ሰውተን ብዙ ተግባራችንን ትተን መጥተን በየመድረኩ የሥጋና የደም አሳብ፣ ጸብና ክርክር፣ በብልሃት የተፈጠረ ተረትና መጨረሻ የሌለው የትውልዶች ታሪክ የምንሰማው ስላልታደልን ነው ወይንስ ስላልታገልን? ፈተና የወደቅነው፣ ሰው የደረሰበት ያልደረስነው ስላልታደልን ወይንስ ስላልታገልን?

       ተወዳጆች ሆይ መኖር ብርቱ ሠልፍ ነውና ይታገሉታል እንጂ አይታደሉትም፡፡ ሕይወት በአልታደልኩም ፍልስፍና ሳይሆን በመንፈሳዊ ሕቡአዊነት ትግል የምትፈታ እንቆቅልሽ ናት፡፡ መንፈሳዊ ዓለም ሩጫውን ጨርሻለሁ ለማለት በፊታችን ያለውን ጉዞ በድል ለማጠናቀቅ የምንጋደልበት ነውና እንታገላለን እንጂ አንታደለውም፡፡ ለወዳጅነታችሁ መጽናት፣ ለትዳራችሁ መዝለቅ፣ ለፍቅራችሁ ማበብ፣ ለሥራችሁ ስኬት፣ እንዲመጣ ለምትሹት ለውጥ በሚያስፈልጋችሁ ሁሉ ወደ ጸጋው ዙፋን በእምነት በመቅረብ በሙሉ አቅማችሁ ታገሉ፡፡ ምክንያቱም ድልን ትግል ይቀድመዋል፡፡ በእርግጥም ኑሮን ይታገሉታል እንጂ አይታደሉትም!!

8 comments:

  1. Great. Jesus Bless You

    ReplyDelete
  2. Great. Jesus Bless you.

    ReplyDelete
  3. Egziabher amlak ewinetegna yehonew ersun yelakewinm Eyesus kirstosin enawik zend bezemen fitsame be anid liju tenagironal. Le eyandandachin beteseten tsega metagel degmo kegna yemitebek new....Tsegaw yagizen!

    ReplyDelete
  4. Rly it's very interesting view...God bless u!

    ReplyDelete
  5. Kiristian erif yizo wede huala ayarisim....metagelachin le bereket yihun!

    ReplyDelete
  6. Sinfinachinin be edil lay kemalakek yisewiren...lalew yichemeriletal lelelew gin....

    ReplyDelete
  7. Egziabher yebereket amilak new! Yeminbarekew gin yalechinin tikitim bithon befitu yizen sinkerib new...bebado gin bereket yelem!

    ReplyDelete
  8. geta yebarkeh yachi ande dinar teftobat metregiawan yeza esketagegnat deres endefelegechat egnam yemnfelgewn eskenagegn deres tegten mefeleg alebn.

    ReplyDelete