Friday, May 18, 2012

ማን ይናገር?


 “አንድ ስለሰማሁት የቤተ መቅደስ ታሪክ ላውጋችሁ፡፡ ሰባኪው በእጅጉ ተቸግሮአል፡፡ መንስኤው በእድሜና በሀብት አንጋፋ የሆኑት ምእመን በስብከት ወቅት ማንቀላፋት ብቻ ሳይሆን ክፉኛ ማንኮራፋታቸው ነው፡፡ አዛውንቱ ከመድረኩ የመጀመሪያው መስመር ላይ ከፊት ለፊት ስለሚቀመጡ ሰባኪው በሁኔታው እጅግ ታውኳል፡፡ በመጨረሻ ግን ሰባኪው አንድ ብልሃት ውል አለው፡፡ አዛውንቱ ሁሌም ከልጃቸው ልጅ ጋር ወደ ቤተ መቅደሱ ይመጡ ነበር፡፡ ስለዚህ ሰባኪው ያንን ብላቴና ጠራና ወደ አንድ ጥግ ወስዶ “አንድ ነገር ታደርግልኛለህ? በየሳምንቱ እሁድ ሃምሳ ሳንቲም እሰጥሃለሁ” አለው፡፡

“ተስማምቻለሁ፡፡ ፍላጎትዎ ምንድነው?” አለ ልጁ - በችኮላ፡፡
“ከባድ ነገር አይደለም፡፡ አያትህ ማንኳረፍ ሲጀምሩ ቆንጠጥ ታደርጋቸውና ታነቃቸዋለህ፡፡ የአዛውንቱ እንቅልፍ አይደልም እኔን የረበሸኝ፡፡ ችግሩ ሰውየው ሲያንኳርፉ በአዳራሹ የተሰበሰበውን ምእመን በሙሉ ከእንቅልፍ ያነቁብኛል፡፡ የእኔ ደግሞ ብዙ የስብከት ርዕስ የለኝም፡፡ እናም ሕዝቡ ከእንቅልፉ እንዲነቃ አልፈልግም፡፡ አለበለዚያ ምእመናኑ በስብከቴ ሊሰላቹ ይችላሉ”
“ሂሳቡን ይመድቡ!” አለ ልጁ - እጁን እየዘረጋ፡፡
“በቅድሚያ? አታምነኝም እንዴ?” አለ ሰባኪው በድንጋጤ፡፡
“ሥራ - ሥራ ነው (ቢዝነስ ኢዝ ቢዝነስ)፡፡ ይህ የእምነት ጉዳይ አይደለም፡፡ ሃይማኖትም አይደለም፡፡ ሃምሳውን ሳንቲም ያስረክቡኝና ግዳጄን ልፈጽም” ልጁ ኮስተር በማለት መለሰ፡፡ በዚያች እለት ልጁ ተግባሩን ቀጠለ፡፡ አዛውንቱን እየጎሰመ እንቅልፍ ነሳቸው፡፡ አዛውንቱ ልጁን እየተመለከቱ “ምን ነካህ?” ቢሉትም ምላሽ መስጠት ቀርቶ ፊታቸውን እንኳን ማየቱንም አቆመ፡፡ ጆሮውንም ወደ ሰባኪው ቀሰረ፡፡
ከስብከቱ በኋላ አዛውንቱ “አንተ ተንኮለኛ! ምን አግብቶህ ትቀሰቅሰኛለህ? በእርጅና ሳቢያ በምሽት መተኛት አልችልም፡፡ ከሳምንቱ ቀናት አንዲት እሁድን ተመቻችቼ በምተኛበት ወቅት ለምን ገዳፋ ትሆነኛለህ? ምን ነካህ? ምን ተፈጠረ? ደግሞ ለስብከቱ ያለህ ትኩረት . . . አንዲት ቃል ተረድተህ ቢሆን እንኳ ጥሩ . . . ” አሉት፡፡
“አባቴ . . . ይህ የሃይማኖት ጉዳይ አይደለም” አለ ልጁ “ለአድራጎቴ በቅድሚያ ሃምሳ ሳንቲም ይከፈለኛል፡፡ በሚቀጥለው እሁድም ሥራዬን እቀጥላለሁ”
“ቆይ! እኔ አንድ ብር እሰጥሃለሁ፡፡ አትረብሸኝ!”
“ጥሩ! ሂሳብ በቅድሚያ” ልጁ ፈነጠዘ፡፡
በተከታዩ እሁድ ሰባኪው ግራ ተጋባ፡፡ አዛውንቱ ያንኳርፋሉ፡፡ ልጁ ደግሞ ወደ ሰባኪው አልመለከት አለ፡፡ “ልጁ ምን ነካው? ዛሬ ሂሳቡን በቅድሚያ ስላልከፈልኩት ይሆን?” በማለት ሰባኪው አሳብ ገባው፡፡
ከስብከቱ ፍጻሜ በኋላ ልጁና ሰባኪው ተገናኙ፡፡ “ምን ነካህ? ለሃምሳ ሳንቲም አታምነኝም? ይኸውልህ!” አለ ሰባኪው፡፡
“ጥያቄው የዱቤ ጉዳይ አይደለም፡፡ አያቴ እንዳልረብሻቸው አንድ ብር መድበውልኛል፡፡ ስለዚህ እርስዎን እንዳገለግል ከፈለጉ . . . እንግዲህ ምርጫው የእርስዎ ነው” አለ ልጁ ፀጉሩን እያከከ፡፡
“እኔ እኮ ምስኪን ሰባኪ ነኝ፡፡ በዚህ አይነት ከሀብታሙ አያትህ ጋር መፎካከር አልችልም
“ሥራ - ሥራ ነው፡፡ ሂሳቤን ከፍ ካላደረጉ አያቴ ብቻ ሳይሆኑ እኔም ማንኮራፋት እጀምራለሁ፡፡ ከዚያም አዳራሹ ይታወካል፡፡ የአያቴን ብቻ ሳይሆን የእኔንም ሂሳብ ሊኖርብኝ ነው፡፡ ለጊዜው በሳምንት ሁለት ብር ሂሳብ እንስማማ፡፡ ከዚያ የገበያው ሁኔታ እየታየ እንደራደራለን” አለ ልጁ - በድፍረት፡፡”

        ከላይ ያነበብነውን ወግ ያወጋን ኦሾ የተባለው ጸሐፊ ነው፡፡(ትርጉም፡- ዳዲሞስ፣ ርዕስ፡- የልብ ቋንቋ፣ ዓመተ ምሕረት፡- 1998፣ ገጽ 61-64) ከላይ የተነሣንበትን ርዕስ ዋና ጭብጥ ለማብራራት በእጅጉ ስለሚረዳ ለመንደርደር ተጠቅመንበታል (ከእባብ እንኳ ልባምነትን እንድንማር ታዘን የለምን?)፡፡ በዚህ ወግ ውስጥ በዋናነት ሁለት ነገሮችን እንመለከታለን፡፡

1. የሕዝቡን መንቃት የማይሻ አገልጋይ

          የተኛ መንቃት እንዳለበት፣ ክርስቶስ ደግሞ ለንቃት የሚሆን አብርሆት እንደሆነ መጽሐፍ ይመሰክራል፡፡ (ኤፌ. 5÷14) መፍዘዝንና አለማወቅን ልክ እንደ ትክክለኛ የእምነት አንዱ ክፍል አድርገን የምናይ ከሆነ ምስኪኖች ነን፡፡ ሰው የሚጠፋው ከእውቀት ማነስ ስለሆነ ልማት የሚኖረው እግዚአብሔርንና የእግዚአብሔርን በማወቅ ነው፡፡ (ሆሴ. 4÷6) ተቀመጥ በወንበሬ፣ ተናገር በከንፈሬ እንደሚባል አፈ ንጉሥ የእግዚአብሔር አገልጋይ ሕዝቡን የጥበብና የማስተዋል ሁሉ መዝገብ ወደሆነው ጌታ የማድረስ ኃላፊነት አለበት፡፡ (ቆላ. 2÷1) ከላይ ያየነው ሰባኪ ግን ቃሉ በሙላት ስለሌለው ከሕዝቡ መንቃት ይልቅ ማንቀላፋታቸውን ናፋቂ ነበር፡፡

        እግዚአብሔር ለእኛ ላለው ፈቃድ ልኬቱ የራሱ የእግዚአብሔር አሳብ ነው፡፡ የእግዚአብሔርን ፍላጎትና ምሪት ከቃሉ ውጪ በሰው አሳብና ምክር ልንመዝነው አንችልም፡፡ በእግዚአብሔር ቃል ውስጥ ንቃት የዝግጅት ከፍተኛው አካል እንደሆነ ተገልፆልናል፡፡ (ማቴ. 24÷42) ያልነቃ ሰው በቀላሉ ለጠላት ኢላማ ይሆናል፡፡ ከእውነትም ከውሸትም የቀላቀለ መሐል ሰፋሪ ነው፡፡ ሊመጣ ያለውን ሳያውቅና ሳይገምት በድንገት ይደርስበታል፡፡ እንቅስቃሴው ሁሉ ወደነፈሰው ነው፡፡ ከወንጌል ጠባይ አንዱ በሥጋ አሳብ የዛሉትን በመንፈስ ማንቃት፣ በዚህ ዓለም ነገር ያንቀላፉትን በእውነት ቃል መቀስቀስ ነው፡፡ ይህ እንዲሆን ደግሞ የእግዚአብሔርን አሳብ የሚያገለግሉ ሁሉ ቃሉን ያለ መጨመርና ያለመቀነስ በሕዝቡ ልብና ጆሮ ማድረስ ይገባቸዋል፡፡ ነገር ግን የምናስተውለው ከዚህ የተለየ ነው፡፡

        ከላይ ባነበብነው የሰባኪው ንግግር ውስጥ በዋናነት የምናስተውለው የሕዝቡን መንቃት እንደማይሻና ለዚህም ምክንያቱ ብዙ የስብከት ርዕስ (በእግዚአብሔር ቃል ላይ የጠለቀ መረዳት) አለማወቁ እንደሆነ ነው፡፡ ከዚህ የሚከፋም ደግሞ አለ፡፡ እውነቱን እያወቁና እግዚአብሔር ለሕዝቡ ያለውን መልእክት እየተረዱ ሐቁን በኃይል ማፈን! በዚያም በዚህም ውስጥ ያለው ስውር ዓላማ ግን ሰው እንዲነቃ አለመፈለግ ነው፡፡ ለዚህስ ምክንያቱ ምን ሊሆን ይችላል?

ሀ. መብትና ኃላፊነትን ማወቅ፡- የእግዚአብሔር ቃል በእግዚአብሔር መንግስት ያለንን ስፍራና መወጣት ያለብንን ተግባር በግልጥ የሚያሳይ ነው፡፡ በእርሱ መንግስት ያለንን መብት በአግባቡ ስንረዳ ከአጉል ወቀሳ፣ ግብዝነት ከተጠናወተው ኑሮ፣ ግምታዊ ከሆነ እንቅስቃሴ፣ አፍአዊ ከሆነ ማስመሰል እንላቀቃለን፡፡ መቼ መናገር፣ የት መናገር፣ ለምን መናገር እንዳለብን ጠንቅቀን እናውቃለን፡፡ ሰው መብትና ኃላፊነቱን በትክክልና በአግባቡ ሲረዳ የሚቆጣጠረው እውነት፣ የሚገዛውም ሐቅ ይሆናል፡፡ ሰው ምን ይላል ከሚል መመሪያ እግዚአብሔር ምን ይላል ወደሚል መገዛት ይሸጋገራል፡፡ ነገር ግን የሰዉ መንቃት እንደልብ ስለማያገላብጥ አይፈለግም፡፡ ከዚህ የተነሣ ላለማንቃት ይሠራል፡፡

ለ. ምክንያታዊ መሆን፡- እግዚአብሔርን ለመረዳት እምነት እንጂ ምክንያት አያሻንም፡፡ የተረዳነውን እግዚአብሔር ለመውደድ፣ ለመከተል፣ ለማምለክ ግን ከበቂ በላይ ምክንያት አለን፡፡ ይህም ስለ እርሱ ያወቅነው የእውቀት መጠን ነው፡፡ ከቃሉ ጋር ያለን ተዛምዶ እያሽቆለቆለ በመጣ ቁጥር እምነት ከመስማት መስማት ደግሞ የእግዚአብሔርን ቃል ስለሆነ ለምናደርገው ነገር ሁሉ ምክንያት እያጣን በዘፈቀደ የምንወጣና የምንገባ አይነት ሰዎች እንሆናለን፡፡ ሰው ለሚያደርገው ማንኛውም ነገር ሕያው የሆነውን ቃል ምክንያቱ በዚያም ውስጥ የተገለጠውን መመሪያ መሰረቱ ሲያደርግ ለሥጋና ደም (ለሰው አሳብ) መታዘዝን ያቆማል፡፡ ይህ ደግሞ እንደ ልብ ለመዝረፍና በሰው ኪስ ለማዘዝ አይመችም፡፡ ሰው ወዶ በፍቅርና በመረዳት ከሚያደርገው ፈርቶና ደንቁሮ ቢያደርገው ስለሚመረጥ የሰው መንቃት አይፈለግም፡፡ ፍንጭ ለመስጠት ያህል ስለሆነ ለጊዜው እነዚህ ይበቁናል፡፡

2. ስለ ሐብቱ የሚያንኮራፋ ተገልጋይ

      የምንሰበሰበው በስሙ፣ የምናመልከው ስለ ክብሩ፣ የተከተልነው ስለ ፍቅሩ፣ የምንታገሰው ስለ ተስፋ ቃሉ ከሆነ በእግዚአብሔር ነገር ላይ የሥጋ አቅማችንን ለማሳየት ዓለማዊ መፍትሔ ለመፈለግ የምናደርገው ምንም ዓይነት ጥረት አይኖርም፡፡ ስለ እግዚአብሔር የሰማነውን የአንዲት ደቂቃ አሳብ ሰማይና ምድር እንኳን አይተኩትም፡፡ እግዚአብሔር በአንድ ልጁ በኩል ያደረገውን የተቀበልነው በጸጋ (የማይገባ ስጦታ) ነው፡፡ (ኤፌ. 2÷ 4-8) በሚያስፈልገንም ሁሉ የሚረዳንን ኃይል የምንቀበለው ከጸጋው ዙፋን ነው፡፡ (ዕብ. 4÷16) የሕይወት ራስና የእግዚአብሔር ሙላት ወደሆነው ክርስቶስ የምናድገውም በዚሁ ጸጋ ነው፡፡ (2ጴጥ. 3÷18)

          የእግዚአብሔር ቤት ያለንን የምናሳይበት ሳይሆን ባለ ጠጋ የሆነውን ጌታ የምናወድስበት፣ ያደረግነውን የምንዘረዝርበት ሳይሆን ያደረገልንን ዘወትር እየዘከርን ልባችንን ከእጃችን ጋር በማንሣት የምናመሰግንበት ነው፡፡ ሐብትና ንዋይ የሚናገርበት ሳይሆን መንፈስ ቅዱስ የሚያዝበት የእውነት ዓምድና መሠረት ነው፡፡ በእግዚአብሔር ፊት የምንቆመው ጸጋው በሰጠን እድል ፈንታ እንጂ እኛ ለእግዚአብሔር እንደሰጠነው በሚሰማን ነገር አይደለም፡፡ ምክንያቱም ሰው በራሱ ነገር እንዳይመካ እግዚአብሔር ትንሹንም ትልቁንም ሐብታሙንም ደሀውንም የሚቀበልበት መንገድ አንድ ሆኖአል፡፡
                                                                       ይቀጥላል

3 comments:

  1. ለጠቢብ አንድ ቃል ...ስለጊዚያዊ ደስታ የሚሰብክ ለፍላፊ/ሰባኪ አላልኩም/ስለ ኑሮው መሰበክ የሚወድ ምእምን በበዛበት ዘመን ይህ አያስደንቅም የጥቅስ ጋጋታ በዝቶ ከሚቸገሩ ከቤተክርስትያን ቀርተውም ሀጢያት ከሚያስቡ መተኛታቸው መልካም ነው ።

    ከዘመኑ ብልጥ ተናጋሪ/በህይወቱ የማይለወጥ ምእመን ሲበዛ ከሚደሰት ጥሩ ተናጋሪ/ ከስብከት ሲመለስ ከሚሰስን ተሰባኪ ይሰውረን

    ReplyDelete
  2. Ergit new hulachinm gar dikmet ale. Kidus menfesu yabertan! Kale hiwot yasemalin.

    ReplyDelete
  3. Be ewinet gizewin yetebeke eries new. Egziabher le hulachinm mastewalin yadlen!

    ReplyDelete