Friday, May 25, 2012

መልክአ እናት



ሰላም ለኪ እናታችን
ባለሽበት እንዳለሽ
አንቺ የተባረክሽ ነሽ
ሰላም ለዓይኖችሽ
ከጭስ ጋራ ለሚማጎቱ
ከእንቅልፍ ጋር ለተፋቱ
ተቅበዝባዥ ፍጡር ሆኜ ኑሮዬን ከምገፋ
ምነው እንባሽን በሆንኩ
ከዓይኖችሽ ስር እንዳልጠፋ፡፡
ሰላም ለከንፈሮችሽ ትላንት ለማውቃቸው
ዛሬ ለምናፍቃቸው
ውዳሴ ክብር ምርቃት
ጭብጨባ ሙገሳ ሽልማት በተረፈበት ቀዬ
ምነው ያ'ንቺን እርግማን - ይናፍቃል ጆሮዬ
ከሌሎች ውዳሴና ክብር እልፍ ጊዜ የተሻለ
ለካ በ'ርግማንሽ ውስጥ እናትነትሽ አለ፡፡
ሰላም ለጣቶችሽ
ለሰዎች የቀረቡ፣ከራስሽ ግን የራቁ
መስጠት መለገስ እንጂ መቀበልን ለማያውቁ
ሰላም ለኪ!
ባለሽበት እንዳለሽ፡፡
(በዕውቀቱ ስዩም፣ የግጥም ስብስብ፣ 2001 ዓ.ም)

1 comment: