Tuesday, May 22, 2012

ማን ይናገር? (ካለፈው የቀጠለ)



        የክርስቶስን ትንሣኤ ለማፈን ገንዘብ ጥቅም ላይ ውሎ እንደነበር መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል፡፡ (ማቴ. 28÷15) ወንጌል እንዳይሰበክ የእግዚአብሔር ክብር እንዳይገለጥ ሕዝቡ ወደ ማስተዋል እንዳይመጣ ዛሬ ድረስ ገንዘብ ትልቅ ድርሻ ያበረክታል፡፡ ነገር ግን ቃሉ አይታሠርምና የሰው አቅም ሊያቆመው አይችልም፡፡ የሰውም ማንኮራፋት ሊያውከው ከቶ አይችልም፡፡

       አገልጋዩ ማን ይናገር? ተገልጋዩ ደግሞ ማን ይናገረኝ? ማለት ይኖርበታል፡፡ ከእኛ የምንናገር ከሆነ እውነትን ወደ ጎን እየተውን ለራሳችን ነገር እየተሸነፍን እንሄዳለን፡፡ በእግዚአብሔር ፊት ሀብታችን ክብራችን ጉልበታችን በአጠቃላይ የሥጋ አቅም ሊወድቅ እንዲሁም በመንፈስ ድሆች በልባችን ንጹሆች በመሆን ጽድቅን በሚራብ ማንነት መቅረብ ይኖርብናል፡፡ የእርሱ ባለ ጠግነት ተዘንግቶ በእኛ ባለ ጠግነት የምንመካ ከሆነ መፈለግንም ማድረግንም በእኛ የሚሠራ ጌታ ተትቶ እኔነታችን የሚተጋ ከሆነ መንፈስ ለእኛ ለሚናገረው ጆሮ የለንም ማለት ነው፡፡

        ተወዳጆች ሆይ ማን ይናገር? ሰው ወይስ እግዚአብሔር፣ ሐብት ወይስ ጸጋ፣ ሥጋ ወይስ መንፈስ? ምድራችን የምትናጠው ሁሉም የራሱን የሚናገርባት የአምላካችን አሳብ ወደ ጎን የተተወባት በመሆኗ ነው፡፡ እግዚአብሔር ለልባችን፣ ለኑሮአችን፣ ለሙሉ ሕይወታችን እንዲናገር ስንፈቅድለት፡-

ሀ. ምሪት እናገኛለን፡- አብዛኞቹ ተንቀሳቃሽ ነገሮች መሪ አላቸው፡፡ መሪ ወደምንፈልግበት ቦታ በአግባቡ እንድንደርስ የሚያስችለን ነገር ነው፡፡ ይህም ብቻ ሳይሆን መሪ ሌሎቹን ክፍሎች የሚመራ ነው፡፡ እግዚአብሔር የምንፈልገውን እንደ ፈቃዱ እየመዘነ ወደሚፈልገው የሚመራን አምላክ ነው፡፡ ሰው ምሪት ከሌለው መረን እንደሚሆን ሁሉ የእግዚአብሔር ምሪት ከሌለን ቃልም ተግባርም ብልሹ ይሆናል፡፡ አብዛኞቻችን የሁኔታን፣ የሰውን፣ የዓለምን ምሪት በአግባቡ ተለማምደናል፡፡ ዳሩ ግን የቸገረን የእግዚአብሔርን ምሪት ተግባራዊ ማድረግ ነው፡፡ ጌታ ያስችላል! እርሱ እንዲናገረን ስንፈቅድ ደግሞ ምሪቱና ትእዛዙን የምንፈጽምበት ኃይል አብሮ ወደ ኑሮአችን ይመጣል፡፡

ለ. ሰላማችን ይበዛል፡- ይህንን ጽሑፍ በመጻፍ ላይ እያለሁ አንድ ሰው የተናገረኝ ንግግር ደጋግሞ ወደ አእምሮዬ ይመጣ ነበር፡፡ ይህም “ቃልህ የሰበረውን በመረቅ አትጠግነውም” የሚለውን አባባል አስታወሰኝ፡፡ ሰው ከራሱ የሚነግረን ምርጡ እንኳን ችግር አለበት፡፡ ይህም ዓለም እንደሚሰጥ ያለ ሰላም ያስገኝልን ይሆናል፡፡ ዳሩ ግን ነፍሳችን የምትናፍቀው መንፈሳችን የሚጠማው ሰላም ያለው እግዚአብሔር በሚናገረው ውስጥ ነው፡፡ እንዲህ ያለውን እውነት መረዳታችን በራሱ በሰው ነገር እንዳንደነቅ ከእግዚአብሔር የሆነውንም ነገር ወደ መጠባበቅ እንድናዘነብል ያስችለናል፡፡ በእርግጥስ ሰላማችን የሚበዛው እግዚአብሔር በሚናገረን ውስጥ አይደለምን? “ዋላ ወደ ውኃ ምንጭ እንደሚናፍቅ፤ አቤቱ እንዲሁ ነፍሴ ወደ አንተ ትናፍቃለች” (መዝ. 41÷1)፡፡

2 comments:

  1. Egziabher lelibachin yinageren-mastewal yibzalin!

    ReplyDelete
  2. Sewin sayhon ye haymanotachinin ras ena like kahin yehonewin geta endinmeleket Egziabher yirdan!

    ReplyDelete