Tuesday, May 1, 2012

በእጁ ፊት



“ቃልህ ተገኝቶአል እኔም በልቼዋለሁ አቤቱ÷ የሠራዊት አምላክ ሆይ÷ በስምህ ተጠርቻለሁና ቃልህ ሐሴትና የልብ ደስታ ሆነኝ፡፡ በዋዘኞችና በደስተኞች ጉባኤ አልተቀመጥሁም ቁጣን ሞልተህብኛልና በእጅህ ፊት ለብቻዬ ተቀመጥሁ” (ትን. ኤር. 15÷16)፡፡

        በብሉይ ኪዳን እግዚአብሔር ከተጠቀመባቸው ታላላቅ ነቢያት አንዱ ኤርሚያስ ነው፡፡ እንደ ስሙ ትርጓሜ እግዚአብሔር በእስራኤል ላይ ከፍ ከፍ ያደረገው ሰው ነው፡፡ በትንቢቱም ላይ ያለው ጥቅል መልእክት እግዚአብሔር ታላቅና ቅዱስ ነውና ሕዝቡ ከተሳሳተ መንገዳቸው ተመልሰው በእውነት ልብ እንጂ በሐሰት እንዳያመልኩት ማስረዳት ነው፡፡ በፍፁም ልብ እግዚአብሔርን የሚፈልጉ እንደማያጡትም ይናገራል፡፡ ነቢዩ በዘመኑ የእግዚአብሔርን አሳብ ያገለገለው በብዙ ሠልፍና ተግዳሮት መሐል ነበር፡፡

        የሕዝቡ መቅበዝበዝ ደግሞም ወደ መድኃኒታቸው ዘወር ለማለት ፈቃደኝነት አለማሳየታቸው አልፎም ተርፎ በነቢዩ ሕይወት ላይ መነሣሣታቸው አገልግሎቱን የእንባ አድርጎበት ነበር፡፡ ታዲያ በአደባባይ በሕዝቡ ሁሉ ጆሮ የእግዚአብሔርን ቃል ሲናገር ደስ አያሰኛቸውም ደግሞም ለስድብ ሆኖባቸው ነበር፡፡ ባል ከሚስቱ ሽማግሌውም ከጎበዙ ጋር እጅ ለእጅ ተያይዘው በአንድነት እግዚአብሔርን ተቃውመዋል፡፡ ነቢዩንም የሰላሙ ሰዎች እንኳን ሳይቀሩ እንክሰሰው እናስፈርድበት ይሉ ነበር፡፡ እግዚአብሔር ከይቅርታ እስኪደክም፣ ኤርምያስም እግዚአብሔርን አታለልኸኝ ብሎ ድፍረትን እስኪናገር፣ ኢየሩሳሌም የሚራራላትን ስለ ደኅንነቷም ይጠየቅ ዘንድ ፈቀቅ የሚለውን እስከማታውቅ ድረስ የቆንጆነቷን ጌጥ የሙሽርነቷን ዝርግፍ ጌጥ ረሳች፡፡ (ኤር. 2÷32) እለት እለት በነቢዩ ወደ እነርሱ ለሚመጣው የእውነት ቃል እንቢተኝነታቸውን ገለጹ፡፡ ነቢዩ ቀኑን ሁሉ ግፍና ጥፋት እያለ ይጮኻል ነገር ግን ቃሉ ስድብና ዋዛ ሆኖበት፣  ሕዝቡም ተሳልቆና አላግጦበት በተመለሰ ጊዜ በእጁ ፊት ለብቻው ቁጭ ብሎ የተገኘውን ቃል በላ፡፡ ከላይ የተነሣንበት ክፍል የተጻፈው በዚህ ሁኔታ ነው፡፡

       በእውነት ሐሴት የማያደርግ ደግሞም ዋዛ ያሳረፈው ሕዝብ ምንኛ ምስኪን ነው? ከእግዚአብሔር ጥበብ ይልቅ የሰውና ምድራዊ ብልሐት የገዛው ወገን እንዴት ተላላ ነው፡፡ ነቢዩ በእጁ ፊት ለብቻው ቁጭ ብሎ ያደረገውን ከአዲስ ኪዳን አሳብ ጋር በማዛመድ በዝርዝር ለማየት እንሞክራለን፡፡  

1. ቃልህ ተገኝቶአል

       ሰማይና ምድር የጸኑበት ደግሞም የሚያልፉበት የበረታ ቃል የእግዚአብሔር ቃል ነው፡፡ የተገኘ ነገር የማይገኝበትም ጊዜ እንዳለ እንረዳለን፡፡  “የእግዚአብሔርን ቃል ለመሻት ይርዋርዋጣሉ አያገኙትምም” (አሞ. 8÷12) የሚለው የነቢዩ ቃል ይህንን ያረጋግጥልናል፡፡ ለተገለጠው የእግዚአብሔር አሳብ ፈቃደኝነታችንን ካላሳየን በተከደነ ሰዓት መንከራተታችን ግልጥ ነው፡፡ ነቢዩ ኤርምያስ ውድቀት በበረከተበት ሰው ሁሉ እንደገዛ ፈቃዱ በሚሄድበት ዘመን የእግዚአብሔር ቃል እንደተገኘ ይነግረናል፡፡ ሕዝቡ በተሳሳተ መንገድ እየሄደ ትክክለኛው ቃል አለመቅረቱ ሕዝቡ ለእግዚአብሔር ጀርባውን ሰጥቶ ሳለ ቃሉ መገኘቱ የእግዚአብሔር ጸጋ ምን ያህል ቻይ እንደሆነ ያሳያል፡፡ ሕዝቡ ግን በእግዚአብሔር ጸጋ ለተገለጠው ቃል የነበራቸው ምላሽ የሚያሳዝን ነበር፡፡

         ቃል ሁለት አይነት አተረጓጎም አለው፡፡ የመጀመሪያው ሬማ የሚለው ሲሆን የእግዚአብሔር መንፈስ ፈቃዱን ለመግለጽ ወደ ሕዝቡ የሚያደርሰውን ድምጽና መልእክት የሚያስረዳ ነው፡፡ ይህም ነቢዩ ኤርምያስ ተገኝቶአል ያለውን ቃል ያስገነዝበናል፡፡ ሁለተኛው ሎጎስ የሚለው ሲሆን ይህም አካላዊ ቃል ክርስቶስን የሚገልጥ ነው፡፡ (ዮሐ. 1÷1) ቃል ሥጋ እንደሆነ በሥጋና በደም እንደተካፈለ በምስሉም እንደ ሰው እንደተገኘ የምንረዳበትም ነው፡፡ ስለዚህ አካላዊ ቃል ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡

2. እኔም በልቼዋለሁ

       ነቢዩ ለተገኘው የእግዚአብሔር ቃል የሰጠውን ፈጣንና ቀጥተኛ ምላሽ የሚገልጽ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ቃል ከተብራራባቸው ነገሮች አንዱ ምግብ (እንጀራ) የሚለው ነው፡፡ (ማቴ. 4÷4) ሰው ሥጋው ያለ መብል እንደማይጸና ሁሉ ያለ እግዚአብሔር ቃል እንጀራነትም የሰው መንፈስ ሕያው ሊሆን አይችል፡፡ የሥጋ መብል ሥጋዊ እንደሚያደርግ የመንፈስ እንጀራም መንፈሳዊ ያደርጋል፡፡ በልቼዋለሁ የሚለው አገላለጽ ቃሉን ማጣጣምንና ከራስ ጋራ ማዋሀድን ይገልጣል፡፡

        ኤርምያስ ከእግዚአብሔር አፍ የመጣውን የተገኘውን ቃል በላ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ራሱ እኔ እያለ ከተናገራቸው ሰባት መገለጫዎች አንዱ “የሕይወት እንጀራ እኔ ነኝ ወደ እኔ የሚመጣ ከቶ አይራብም በእኔ የሚያምንም ሁል ጊዜ ከቶ አይጠማም፡፡ ነገር ግን አይታችሁኝ እንዳላመናችሁ አልኋሁ” (ዮሐ. 6÷35) የሚለው ነው፡፡ በሰው መካከል ተገኝቶ በሥጋና በደም የተካፈለ አካላዊ ቃል ክርስቶስ ኢየሱስ ነው፡፡ እናምንበትና እናመልከው ዘንድ ኃጢአተኛ እንደሆን ደግሞም መድኃኒት እንደሚያስፈልገን ለምናምን ሁሉ የእግዚአህሔር ልጅ የእንዲሁ ስጦታ ሆና ተገልጧል፡፡ (ዮሐ. 3÷16) ተወዳጆች ሆይ ቃሉ ተገኝቶአል፡፡ እኛ ግን በልተነዋል ወይ?

        በእርሱ የሚያምን የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር የሚወደውን ልጁን አሳልፎ ለሞት ሰጥቶአል፡፡ ወልደ እግዚአብሔር ኢየሱስ ጠላቶቹ ሳለን ለወዳጅ ከመስጠት በሚበልጥ ፍቅር እስከ መስቀል ሞት ታዝዋል፡፡ መንፈስ ቅዱስም የመዳናችንን የምስራች በአመነው ልብ ውጥ በዘላለም ዋስትና አትሞአል፡፡ ነቢዩ ቃልህ ተገኝቶአል እኔም በልቼዋለሁ እንዳለ በእኛም ዘንድ እንዲሁ እንዲሆን ጌታ ይርዳን፡፡
- ይቀጥላል -



3 comments:

  1. Amen ye Egziabher tsega yagzen! Egziabher yibarkachu.

    ReplyDelete
  2. Be eju fit be eminet yeminkerbibetin tsega yadlen! Awon tiyakewochachin bicha sayhonu hiwotachinm be eju fit metayet alebet! Kibir hulu ladanen geta yihun!

    ReplyDelete
  3. "Ye lijum ye Eyesus kirstos dem ke hatiyat hulu yanetsal!".Egziabher mastewalin yabzalin!

    ReplyDelete