Saturday, December 17, 2011

የወዳጅ ሰንሰለት


እጅግ የሚያስፈልገን ነገር መረጃ ቢሆን ኖሮ እግዚአብሔር የግንኙነት ባለሙያ በላከልን ነበር፡፡
እጅግ የሚያስፈልገን ነገር ሙያዊ ሥልጣኔ ቢሆን ኖሮ እግዚአብሔር ሳይንቲስት በላከልን ነበር፡፡
እጅግ የሚያስፈልገን ነገር ፌሽታ ቢሆን ኖሮ እግዚአብሔር አዝናኝ በላከልን ነበር፡፡
እጅግ የሚያስፈልገን ነገር ገንዘብ ቢሆን ኖሮ እግዚአብሔር የምጣኔ ሀብት ሊቅ በላከልን ነበር፡፡
ነገር ግን እጅግ የሚያስፈልገን ነገር ይቅርታ ነበር ጌታ እግዚአብሔር አዳኙን ላከልን፡፡ አሜን!
ሰፊ በሆነው የሰው ልጆች ግንኙነት ውስጥ የቆሰለው ቁስሉ የሚሽርበት ያደፈው የሚነጻበት፣ የወደቀው የሚነሳበት፣ የተሰበረው የሚጠገንበት ቀዳሚ ተግባር ይቅርታ ነው፡፡ ስለ ይቅርታ ጥርት ያለ አስተሳሰብ ሊኖረን ይገባል፡፡ በእርግጥም ከስሜት ነፃ መሆን የማይቻል ቢሆንም እንኳን ይቅርታ ምርጫ መሆኑን ግን ልብ ማለት ያስፈልጋል፡፡ ምንም እንኳን አሁንም ጉዳቱ በውስጥህ ቢሆንም ይቅር ልትል ግን ትችላለህ፡፡
ይቅር ለማለት ለመደሰትና የመጀመሪያውን ደረጃ ለመሄድ አንተ የመጀመሪያው ሁን፡፡ በሰብአዊ ወንድምህ ወይም እህትህ ፊት ደስታ ሲፈካ ታያለህ፡፡ በዚህም የሕይወት አስዋቢ፤  የደስታ ምንጭ፤ ተአምር አድራጊ መሆን ይቻላል፡፡ ሁል ጊዜም ሰዎች ወደ እኛ እንዲመጡ ሳንጠብቅ ቀዳሚ መሆናችን የደስታ እጅግ ማራኪ ገጽታ ውስጥ እንድንቆይ ያደርገናል፡፡
ባልንጀሮቻችንን መውደድ ከቻልን በዚያኑ ልክ ደግሞ የወቀሳ መዓት ልናወርድባቸው፤ ተስፋን በእነርሱ ላይ የቆረጠ ፊት ልናሳያቸው አይቻለንም፡፡ ሁሉም ሰው ያው ሰው ነውና፡፡ ብዙ ጊዜ ራሳቸውን ፍፁም አድርገው የሚመለከቱ ሰዎች አይወደዱም፡፡ ራስን ማጽደቅ በእርግጥም አያስኬድም፡፡ ስህተት እንዳለብን ማመን አለመቻል ደግሞ በራሱ ስህተት ነው፡፡ ለጥፋቱ ይቅርታ ለማድረግ ፍላጎት አለማሳየት  ደግሞ ትልቅ ስህተት ነው፡፡
ሰዎችን ለመዳኘት የሚፈጥኑ ሰዎች የአእምሯቸውን ሚዛን ያወሳስቡታል፡፡ በሌላው ሰው ላይ በደንብ አድርገው ለመፍረድ ጥሩ ምክንያት ይኖራቸው ይሆናል፡፡ ነገር ግን እንዲህ በማድረጋቸው ራሳቸውን ለጥላቻ መንፈስ ክፍት ያደርጋሉ፡፡ ይቅር መባባልና መወዳጀት በእርጋታና በትጋት ከተደረጉ የሰውን ልጅ ልቡና የሚጠርቡና የሚቀርፁ የፍቅር መዳፎች ናቸው፡፡ ምንም እንኳን ጥረትን ቢጠይቅም ይቅር ማለት እንዳለብን ልንወስን ግን ይገባል፡፡ ስለዚህ የቱንም ያህል ከባድ ቢሆንም  እንኳን አድረገው፡፡ በዚያም ጊዜ የተሰማህ ቅሬታ ጥሎህ ሲሄድ ይታወቅሃል በምትኩም የነፍስህን አደባባይ ሰላም ሲከባት ይሰማሃል፡፡
ይቅር ባይነት ስሜትህን ሳይሆን ውሳኔህን ይጠይቃል፡፡ የፈቃደኝነትም ተግባር ነው፡፡ ስለዚህ ምክንያት አትጠብቅ፡፡ አንዴ ይቅር ለማለት ከቆረጥክ እንዲህ ቢሆን ኖሮእና ነገር ግንየሚሉትን ቃላት አታንሣቸው፡፡ ስለ ተቃረነህ ሰውም ስትናገር ትህትናን በተላበሰ መንገድ ይሁን፡፡ ነገር ግን ሁሉን ለመልካም አድርገው!      “አውቄ በድፍረት፤ ያለ ዕውቀት ስቼ በስህተት የበደልኳችሁ ከልቤ ይቅርታ”
(ይቀጥላል)

1 comment:

  1. ከዚህም በላይ ቢጻፍ መልካም ነው፡፡ ያትጋልን፡፡

    ReplyDelete